Wednesday, April 25, 2012

ቴዲ አፍሮ ምን ዘፈነ ? እንዴት አቀነቀነ ?


እነሆ አገሬው የቴዲ አፍሮን ‹‹ ጥቁር ሰው ›› ከፋሲካ ጀምሮ እስካሁን እያጣጣመ ይገኛል፡፡ አድማጩ ሙዚቃው የፈጠረበትን ስሜትም በተለያዩ መንገዶች እየገለጸ ነው፡፡ እንደጠበኩት አላገኘሁትም…ከማውቀው ደረጃ ወርዶብኛል… ጥሩ ነው… በጣም አርክቶኛል… የሚሉ ናቸው አስተያየቶቹ፡፡ በርግጥ የአብዛኛው ሰው ፍላጎት ወደየትኛው ይወድቃል የሚለውን መልስ ለማግኘት እንደ አውሮፓ መገናኛ ብዙሃን አስተያት አሰባስቦ ደምሮና ቀንሶ የሚነግረን አካል የለንም፡፡ ስለዚህ አስተያየታችን የግምት ትራስ ላይ የተደገፈ መሆኑን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡
በደምሳሳው ከሚገለጹ ሃሳቦች በተጨማሪ የተወሰኑ ዘፈኖች ላይ ከረር ያሉና ምናልባትም ታሪካዊ ማስረጃዋችን የተደገፉ ክርክሮችና ውይይቶችም በማህበራዊ ገጾች አንብበናል፡፡ በዚህ ረገድ የካሴቱ መጠሪያ የሆነው ‹‹ ጥቁር ሰው ›› የታሪክና የስም መዛባት ችግር እንዳለበት ተጠቁሟል፡፡ የቴዲ አብዛኛው ዘፈኖች ርዕሰ ጉዳይ ‹‹ ፍቅር ›› ላይ መውደቃቸውም እየተነገረ ነው፡፡ የግጥሞቹም ጥንካሬና ብስለት የእሱ አልመስልህ እያለን ነው የሚሉ ወገኖችም ጥቂት አይደሉም፡፡ እነዚህና ሌሉች ደቃቅ አስተያቶች  መኖራቸው እውነት ነው፡፡
በርግጥ ቴዲ አፍሮ ምን ዘፈነ  ? እንዴትስ አቀነቀነ ? በአዲሱ አልበሙ ምንስ ነገረን  ? የሚለው አጀንዳ ብዙ የሚያከራክርና የሚያጽፍ በመሆኑ እኔም ስሜቴን ላካፍል ፈለግኩ፡፡ የሙዚቃ ንጥረ ነገር ስለሆኑት ፒች፣ ስኬል፣ ሀርመኒ፣ ሪትምና ሜሎዲ በዝርዝር የምለው ነገር ግን አይኖርም፡፡
                            አጠቃላይ ምልከታ
የቴዲን ሙዚቃዋች ከአቅጣጫ አንጻር እንመድባቸው ብንል ፍቅር፣ ታሪክ፣ ተስፋና ፓለቲካ ላይ ይወድቃሉ፡፡ እነዚህን አንጓዋች እንዴት ሰነጣጠቃቸው ስንል ደግሞ ስልቱን እናገኛለን፡፡ የዘይቤ አጠቃቀሙ በዋናነት ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡ እንደሚታወቀው ዘይቤ ግጥም ብሩህ ሆኖ ለአይነ ህሊና እንዲታይ፣ ለእዝነ ህሊና ኮለል ብሎ እንዲሰማ በአጠቃላይ ጣዕምና ለዛው እንዲታወቅ የማድረግ ኃይል አለው፡፡
የቴዲ ሙዚቃዋች በሙሉ በዘይቤ የበለጸጉ ናቸው ማለት ባያስደፍርም ንጽጽር፣ ደጋጋሚ፣ ተምሳሌት በተለይም ደግሞ አሊጎሪ የተሰኙት ዘይቤዋች በስራዋቹ ውስጥ ይታያሉ፡፡ ለአብነት ስለፍቅር፣ ባሻው፣ ኃይል እና ፊዮሪናን አሊጎሪ ውስጥ መመደብ ይቻላል፡፡ አሊጎሪ ማለት አንድ ትርጉም ያለው የሚመስለን ነገር ግን ውስጡ ሲመረመር የማይታይ ትርጉም ያለው ሀሳብ ነው፡፡
የጥቁር ሰው አልበም ሌላኛው የጎላ ስልት ዜማዋቹ እንዲወደዱ የአጃቢዋቹ ሚና እንዲጎላ መደረጉ ነው፡፡ ከ 11 ዱ ዘፈኖች ውስጥ ከአጃቢ ሚና  የጸዱት ‹ ህልም አይደገምም › እና ‹ ጨዋታሽ › ብቻ ናቸው፡፡ ሌሎቹ በመደበኛ አጃቢዋች ፣ በሆታ፣ በቀረርቶ፣ በጸናጽል፣ በሌሎች ቋንቋዋችና በጸጋዬ ግጥም የታቀፉ ናቸው፡፡
 ‹‹ ቴዲ እንደዚህ ዓይነት ነገር ያበዛል- ለምንድነው  ?›› ስል አንድ ጓደኛዬን ጠይቄው ነበር
 ‹‹ ብቻውን መብላት ስለማይፈልግ ! ›› አለኝ እየሳቀ
መልሱ ቀልድ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ እውነታው ግን የሙዚቃውን ቅርጽ ለማሳመር፣ ዘፈኑን ለማድመቅና በአድማጩ እዝነ ህሊና ውስጥ ሰምጦ እንዲቀር ለማድረግ ነው፡፡ ጥቂት እውነት ከፈለጋችሁ ፊዬሪና፣ ስለፍቅር፣ ጸባዬ ሰናይና ኃይል የሚባሉት ሙዚቃዋች ውስጥ አጃቢዋችን ደጋግማችሁ ስሙ፡፡ በማግስቱ ብቻችሁን እነዚያን ቃላት ትደጋግማላችሁ፡፡ ምናልባትም የጥንቱን ኮረስ / chorus / ለየት ባለ ስልት እየተጠቀመበት ይመስለኛል፡፡ በ5ኛውና በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን በግሪክ ታዋቂ ቲያትሮች ውስጥ ለድምቀት የሚጠቀሙበት ኮረስ ወደ ሙዚቃው የተሸጋገረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በርግጥ ኮረስ በአንድ ሙዚቃ ላይ ሁለትና ከዚያ በላይ የሆኑ ሰዋች ሲያቀነቅኑት ነው፡፡ ቴዲ በስልቱ የአንበሳውን ድርሻ ይዞ በጥቂት ቦታ ነገር ግን በአስፈላጊው ምዕራፍ ላይ አጃቢዋች ጎልተው እንዲወጡ አድርጓል፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን እጀባን ከመጠን በላይ በመጠቀሙ ጩኀት የበዛ አስመስሎታል፡፡
ዝርዝር እይታዋች
ሀ . ታሪክ ቀመስ ሙዚቃዋች
‹ ጥቁር ሰው › እና ‹ ስለ ፍቅር › የብዙዋች መነጋገሪያ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ካነሱት  ጭብጥ አንጻር ትልቅ ትኩረት የሚደረግባቸው ይመስለኛል፡፡ በርግጥ ስለፍቅር ከላይ እንደገለጽኩት ከመልዕክት አንጻር አሊጎራዊ ይዘት ያለው ነው፡፡ በጥቁር ሰው ሙዚቃ ውስጥ ባልቻ፣ ፊታውራሪ ኃ/ጊዮርጊስ፣ አሉላ፣ መንገሻ፣ ገበየሁና ጣይቱ ተጠቅሰዋል፡፡ ታሪኩ የሚጀምረው የአጼ ሚኒልክን የክተት ጥሪ በማቅረብ ነው፡፡ ወዲያው የእያንዳንዱ ገድል ይቀርባል፡፡ ቴዲ
            ‹ ባልቻ አባቱ ነፍሶ
             መድፉን ጣለው ተኩሶ ›  ባለው አቀራረብ ላይ መድፉን የጣለው አባተ ቧ ያለው መሆኑና ባልቻ መድፍ ተኳሽ እንዳልነበር የቀረቡ ክርክሮች ነበሩ፡፡ በርግጥ አባተ ይህን መሰሉ ገድል ነበረው
            ‹‹ በሰራው ወጨፎ ባመጣው እርሳስ
              ተፈጠመ ጣሊያን አበሻ እንዳይደርስ
              አባተ በመድፉ አምሳውን ሲጥል
              ባልቻ በመትረየስ ነጥሎ ሲጥል… ››  በሚለው ግጥም ውስጥ የስራ ድርሻው የተጠቆመ ይመስላል፡፡ ይሁን እንጂ በጦርነቱ ጠዋት ላይ ገበየሁ ሲሞት የተተካው ባልቻም ሌላ ተግባር እንደነበረው የሚጠቁም ሀሳብ አለ፡፡
            ‹‹ ገበየሁ ቢሞት ተተካ ባልቻ
              መድፍ አገላባጭ ብቻ ለብቻ ››  ቴዲ በግጥሙ ላይ ሰፋ ያለ ድርሻ የሰጠውን ባልቻ ከዚህ አንጻር ማጉላት ፈልጎ ሊሆን ይችላል ብለን ለማሰብ መንገዱ ዝግ አይደለም፡፡ እንደ ባልቻ ሁሉ የፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ የአድዋ ሚና ትልቅ አልነበረም የሚሉ መከራከሪያዋችም ነበሩ፡፡ በነገራችን ላይ ሀብተጊዮርጊስ በጦርነቱ ዋዜማ ላይ በሰጡት ምክር፣ ኋላም ባሳዩት የጦር ስልት የጦሩ መሪ እስከመሆን ደርሰዋል፡፡ እኚህ ሰው ቀደም ባለው የወላሞና የእምባቦ ጦርነት ላይ
            ‹‹ የሀብቴ ጦረኛ አጋም መቁረጥ ያውቃል
             የሚኒልክን ጠላት ልመንጥረው ይላል ›› ተብሎ ተዘፍኖላቸዋል፡፡ በጦር ስልት ብቻ ሳይሆን በዲፕሎማሲና በፍርድ አሰጣጥ የነበራቸው ችሎታም  ከሌሎቹ የላቀ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ሁለት እንግሊዞች ያለፍቃድ በኬንያ በኩል ወደ ግዛታቸው ሲገቡ ተገደሉ፡፡ ቆንሲሉ ‹‹ ኡ ኡ  ›› አለ፡፡ ሚኒልክ ጉዳዩን መክረን መልስ እንሰጣለን በማለት አባ መላን ያስጠራሉ፡፡ አባ መላ አልተጨነቁም፡፡ ሰውየውን ወደኔ ላከውና አነጋግረዋለሁ አሏቸው፡፡ ቆንሲሉ አባ መላ ፊት እንደቀረበ
 ‹‹ ዜጎቼ ደማቸው ስለፈሰሰ መሬቱ ይሰጠኝ ›› አለ፡፡
 ‹‹ በሀገራችሁ ይህን መሳይ ደንብ አለ ? ›› ጠየቁ
 ‹‹ አዋ ! ›› መለሰ ቆንሲሉ
 ‹‹ እንግዲያውስ የቴዋድሮስ ልጅ አለማየሁ በሀገራችሁ ስለሞተ ለእኛ ለንደንን ስጡን፡፡ እናንተም ይህን ውሰዱ ›› ብለው ወረቀት ላይ ጽፈው ከፈረሙ በኋላ ‹‹ በል ፊርማህን አኑር ! ›› ይሉታል፡፡ ቆንስሉ አልፈርምም ብሎ ወጣ፡፡ ሚኒሊክና ጣይቱ ከደስታቸው ብዛት አንገታቸውን አቅፈው ሳሟቸው፡፡ በመሆኑም ያለው ታሪክ ከቴዲ ግጥም ጋር የሚፋለስ አይደለም፡፡ በርግጥ በአድዋ ዘመቻ ወቅት  ትልቅ ጦር ይዘው የዘመቱት ራስ መኮንን፣ ራስ ሚካኤል፣ ራስ ወሌ፣ ራስ ወ/ጊዮርጊስ፣ አዛዥ ወ/ጻዲቅና ደጃች ተሰማ ናደው በግጥሙ ውስጥ ቦታ አልተሰጣቸውም፡፡ በአንድ ዘፈን ይህን ሁሉ ነገር ማካተት ይከብዳል፡፡ በሌላ በኩል በስነ ጽሁፍ ‹‹ የገጣሚው መብት ›› የሚባል ሀሳብ አለ፡፡ ቴዲ በዚህ መብቱ ተጠቅሞ ለስራው የሚያመቹትን ብቻ ለቅሞ ያስገባ ይመስለኛል፡፡
ከዚህ ይልቅ ስለ ሚኒሊክ እንደ መዝፈኑ ላይቀር የሳቸውን ስራ ለምን አጉልቶ አላቀረበውም ? የሚለው ሀሳብ መነሳት ያለበት ይመስለኛል፡፡ ለአድዋ ድል ትልቅ መሰረት በጣለው የአምባላጌ ድል ላይ ሚኒሊክና የጦር አዛዦቹ ምርጥ ታሪክ ነበራቸው፡፡ በድል ውስጥ ጀግኖች መፈጠራቸው አይቀሬ  የመሆኑን ያህል ድሉ ሲነሳ ውጤቱ ገዝፎ የሚታየው ከሚኒሊክ አመራር፣ አስተሳሰብና አስተዳደር አንጻር ነው፡፡ ቴዲ ሚኒሊክ ጥሪ ብቻ እንዲያቀርቡ አድርጎ የግጥሙን ደምና ስጋ የሞላው በሌሎች ብዙ ቅርንጫፎች ነው፡፡ ይህም ሚናቸው እንዲደበዝዝ አድርጎታል፡፡ ግጥሙን ዝም ብሎ ያየ ሰው የተጻፈው ለባልቻ ነው - ለሚኒልክ ? ብሎ ሊጠይቅ ይቸላል፡፡
በተረፈ ግን ጥቂትም ቢሆን የሚኒሊክ የክተት ጥሪና የተሰጠው ምላሽ መልዕክቱ ከፍ እንዲል አድርጎታል፡፡
                                    ‹‹ አድዋ ሲሄድ ምኒሊክ ኑ ካለ
                                      አይቀርም በማርያም ስለማለ
                                      ታደያ ልጁስ ሲጠራው ምን አለ ?
                                      ወይ
                                      ወይ ሳልለው ብቀር ያኔ
                                      እኔ አልሆንም ነበር እኔ ››
ጥሪው ብቻ ሳይሆን ህዝቡ የተጠራበት ስልት የሚኒሊክን የአመራር ጥበብ ያሳያል፡፡  ህዝቡ ሚኒሊክንም ሆነ ማርያምን ሳይፈራ/ ሳያከብር ቢቀር ኖር ውጤቱ ምን ይሆን ነበር  ? በቀላሉ ኢትዮጽያ የነጻነት ተምሳሌት፣ የአፍሪካም ሆነ የዓለም ጭቁን ህዝቦች ሞዴል አትሆንም ነበር፡፡
‹‹ ስለ ፍቅር ›› በንጽጽራዊ ዘይቤ ጎልብቶ አሊጎራዊ ውጤት ላይ የሚያርፍ ስራ ነው ፡፡
 ‹‹ እግር ይዞ እንዴት አይሄድም
               ሰው ወደፊት አይራመድም
             አፈር ይዞ ውስጡ አረንጓዴ
   ለምን ይሆን የራበው ሆዴ ››
 የቴዲ ዋና ጥያቄ ያለው እነዚህ ስንኞች ውስጥ ነው፡፡ እግር የርምጃና የዕድገት ምልክት ነው ፡፡ በርግጥ እግር ይሄድ ዘንድ የተመዛዘነ ፍቃድ ከአእምሮ ይፈልጋል፡፡ አእምሮአችን በዕውቀትም ሆነ በቅንነት ደምና ነርቮች ስላልተሞላ እያለን ተርበናል፤ እያለምን ከድህነት ወለል ፈቅ አላልንም፡፡ ይሁን እንጂ ‹‹ ፍቅር ›› ካለ በጋራ ማቀድ፣ መስራትና ዕውቀትን መጨበጥ እንደሚቻልም ይጠቁመናል፡፡ ጥቁምታው ወደ 17ኛው ክ / ዘመን የሚያሻግር ነው፡፡ ቴዲ የጥበብ መሰረት እንደነበር ሊያሳየን የሞከረው በንጉስ ፋሲለደስ አማካኝነት ነው፡፡
  እንደሚታወቀው ፋሲለደስ በ 1636 ዓ.ም አስደናቂዋቹን ግንቦች ገንብቷል፡፡ ከዚያ በፊት በድንጋይ መስራት የተለመደ አልነበረም፡፡ ጎንደር እንደ አውሮፓ እውነተኛ የከተማ ቅርጽ ለመያዝ የበቃቸው ከፋሲለደስ በኃላ የመጡ መሪዋቸ እዛው መክተም መቻላቸውና የባህል፣ የንግድና አስተዳደር ማዕከል በመሆኗ ነው፡፡ በፋሲለደስ ዘመነ መንግስት የሸዋው ስብስብ የሆኑት ‹‹ ተዋህዶ›› እና የጎጃምና ትግሬው ስብስቦች የነበሩት ‹‹ ቅባቶች ›› በፈጠሩት ውዝግብ የሀገሪቱ ፓለቲካ ተመሰቃቅሎ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ቴዲ አፍሮ የሃይማኖት እውቀት የነበረውንና ጎበዝ ጸሀፊ የሆነውን ‹‹ ዘርያቆብ ›› ወይም ዓለም አንቱ ያለውን ‹‹ ላሊበላ ›› ለጥበብ ምሳሌነት ለምን አልመረጠም ብሎ መከራከር አይቻልም ፤ ይህም ‹‹ የገጣሚ መብት ›› ነውና፡፡
የጥበብ መሰረት ነበርን ፣ ይህን ሀብት መነሻ በማድረግ ዛሬ የሀገር ጅራት የሆነቸውን ሀገር ማሳደግ እንችላለን ነው የሚለው፡፡
‹‹ የት ጋር እንደሆን ይታይ የኛ ጥበብ መሰረቱ
  የኋላው ከሌለ የለም የፊቱ
  ሳይራመድ በታሪክ ምንጣፍ
  ሰው አይደርስም ከዛሬ ደጃፍ ›› በማለት ነው፡፡ ይህ የፓለቲካ ሰዋችን አስተሳሰብ የሚሞግት ሀሳብ ነው፡፡ አካሄዳችን ደርግ ዘውዱን አበሻቅጦ ፣ ኢህአዴግ ደርግን ረግሞና አስረግሞ መሆኑ ይታወቃል፡፡ የኃለኞቹን ለዛሬው ድክመት መሸፈኛ ማድረግ የተለመደ ነው፡፡ እድገትና ንጽጽር ከራስ ጋር ሳይሆን ካለፈውና ከወደቀው ስርኣት ጋር ነው፡፡ ቴዲ ሁልግዜም ከኃለኛው ራሱን የቻለ ምርጥ ተሞክሮ ስላለ እናክብረው፣ መነሻ እናድርገው የሚል ይመስላል፡፡
የዚህ ዘፈን ንጽጽር ከፓለቲካው ዓለም አልፎም መንፈሳዊውን እውነት ያሳያል፡፡
‹‹ አንተ አብርሃም የኦሪት ስባት
  የነ እስማኤል የይሳቅ አባት
  ልክ እንደ አክሱም ራስ ቀርጸሃት ራሴን
  በፍቅር ጧፍ ለኩሳት ነፍሴን ››
ቴዲ አብርሃምን ለምን ተጠቀመ ብለን ስንጠይቅ የነበረውን ከፍተኛ ፍቅርና በፍቅርም ያገኘውን የድል አክሊል እንመለከታለን፡፡ አብርሃም በ 86 ዓመቱ እስማኤልን የወለደው ከሚስቱ ሳራ ሳይሆን ከሰራተኛይቱ ነበር፡፡ ‹‹ ካረጀሁ በኃላ እንዴት ፍትወት ይሆንልኛል ? ›› የሚል አስጨናቂ ጥያቄ ራሱን በሚጠይቅበት ግዜ ደግሞ ከሳራ ይስሀቅን መውለድ ችሏል፡፡ ለእግዚአብሄር ፍቅር ሲል ደግሞ በስንት መከራ የተወለደውን ይስሀቅን ለመስዋትነት እንደ በግ ሊያርድ በሞርያ ተራራ ተገኘ፡፡ ልጄ ለምን ተመታ ብሎ ጦርነት የሚያውጅ እንጂ የሚወደውን ልጅ ለመሰዋትነት የሚያቀርብ ቤተሰብ ይኖር ይሆን ? እውነተኛ ፍቅር በመኖሩ ግን አብርሃም ራሱም ሆነ ልጁ ተባረኩ፡፡ የሚፈልገውን አግኝቶም 175 ዓመታት ኖሯል፡፡
ቴዲ ከታሪክም ሆነ ከመንፈሳዊ አንጻር የሚነግረን እንግዲህ ፍቅርን ነው፡፡ ርስ በርስ እንዲሁም ወደ ኋላ እየሄዱ ከመወነጃጀል ፍቅርን አጀንዳ በማድረግ ችግሮቻችንን እንፍታ ነው የሚለው፡፡ ይህን አለማድረግ ደግሞ ያሉብንን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ይባስ የሚያወሳስብና የምናልመውን እድገት የማያመጣ ነው፡፡ ይህን ለመስራት ‹ ግዜው አይደለም፣ ያለፈበት ነው፣ አሰልቺ ነው › በማለት በሮች መዘጋት እንደማይገባቸውም ተከታዩን ስንኞች እንካችሁ ብሎናል፡፡
‹‹ ሰው ለመውደድ ካልኩኝ ደከመኝ
  ያኔ ገና ውስጤን አመመኝ ››
በ‹‹ ስለፍቅር ›› ም ሆነ በ ‹‹ ጥቁር ሰው ›› ሙዚቃዋች ውስጥ ደጋሚ ድምጽ / Alliteration / የተሰኘው ዘይቤ ጎልቶ መታየቱ መጠቀስ ይኖርበታል፡፡ ባልቻ ሆሆ፣ ሳልል ዋይ፣ አመመኝ የሚሉ ቃላቶች ተደጋግመው ይሰማሉ፡፡ ድግግሞሹ ያለ ምክንያት ቢገባ ኖሮ የግጥሙን ውበትና መልዕክት ያፈዘው ነበር፡፡ ነገር ግን ቀረርቶው የውጊያው ማቀጣጠያ ፣ ሳልል ዋይ የዘመቻው ምላሽ፣ አመመኝ ህዝቡም ሆነ ሀገሪቱ አሁን ያሉበት ሁኔታ ምናልባትም ነገም ፍቅር ከጠፋ ከህመሙ ማገገም ያለመቻልን የሚጠቁም ቁልፍ ቃላቶች ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡
ለ . ፍቅር ቀመስ ሙዚቃዋች
 ደስ የሚል ስቃይ፣ ስቴድ፣ ህልም አይደገምም እና ጸባየ ሰናይን በገራገር አይን ካየናቸው የፍቅር ይዘታቸው ከፍ ያለ ይመስላል፡፡ ምልከታችን ጠለቅ የሚል ከሆነ ግን ሌላ ምላሽ ልናገኝ እንችላለን፡፡ ለምሳሌ ‹‹ ደስ የሚል ስቃይ ›› በተባለው ዘፈን ውስጥ ስለሰው የሚያነሳው ስንኝ አንድ ቦታ ብቻ ነው የሚገኘው፡፡
‹‹ ምን ይዞ ነው ለመንገዱ
  እንዲህ አርቆ ሰው መውደዱ ››  በዚህም ምክንያት የዘፈኑ ጭብጥ ፍቅር ነው ይባል ይሆናል ፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ዘፈን የእናት ወይም የሀገር ፍቅርን የማይወክልበት ምክንያት አይኖርም፡፡ ‹‹ ሰው ›› በሰውኛ ዘይቤ ተወክሎም ሀገርን ሊወክል ይችላልና፡፡ዞሮ ዞሮ የፍቅሩ ግለት ከፍተኛ መሆኑን እንመለከታለን፡፡ ገጣሚው የፍቅሩን ግለት ለመለካት የሚያስችል ቃላት እንደሌለው፣ ፍቅር እንደ ኩፍኝ ወጥቶ የማያልቅ መሆኑም ተመልክቷል፡፡ ሙዚቃው የያዘው ሀሳብ በጥልቅ ስንኞች የጠነከረ ነው፡፡
“‹‹ ከሚገባሽ በታች ከምችለው በላይ
   እስኪወድሽ ልቤ ደስ በሚል ስቃይ ››  ይህን ሃሳብ ለማፍታታት ሰፊ ተመስጦ ወይም ቁዘማ ሳያስፈልግ አይቀርም ፡፡
‹‹ ህልም አይደገምም ›› የሚለው ሙዚቃ ፍቅርን በዕውኑ ዓለም ደፍረው ለማሸነፍ ለሚቸገሩ አፍቃሪያን የተሰጠ ገጸ በረከት ይመስላል፡፡ በርግጥ ፍቅርን በሙሉ ዓይን ለማየት የማይደፍሩ ብዙ ምስኪኖች ጋሻ የሚያደርጉት ደብዳቤን፣ ህልምንና አማላጆችን ነው፡፡ የቴዲ ‹ ህልም አይደገምም › ከሄለን በርሄ ‹ የህልሜ ጓደኛ ትመጣለህ ዛሬ በግዜ ልተኛ › ከተሰኘው ሙዚቃ ብዙም የማይራራቅ ሆኖ ነው ያገኘሁት፡፡
‹‹ ጸባዬ ሰናይ ›› ምርጥ ውበት ብቻ ሳይሆን የሚደነቅ ጸባይ የተላበሰች ሴት የተገለጸበት ሙዚቃ ነው፡፡ ቴዲ ምርጥ ውበትና ጸባይን እንድንቀበል ያደረገው የግጥሞቹ ሀሳብ በንጽጽርና ተምሳሌት ዘይቤ ጎልተው እንዲወጡ በማድረግ ነው፡፡ ውበቷ ከገሊላ ቁንጅና ጋር ተወዳድሯል፡፡ ንጉስ ሰለሞንን ያንበረከከችው ንግስት ሳባና ጁሊየስ ቄሳርንና ማርክ አንቶኒን ያብረከረከቸው የግብጽዋ ንግስት ክሊዋፓትራ ቴዲ ለሳላት ቆንጆ ምን ያህል ግዙፍ የተጽዕኖ ጥላ እንደፈጠሩም መመልከት ይቻላል፡፡
‹‹ አየን ጀምበር ወዳለም አጎንብሳ
  ያይንሸን ብሌን ዉሃ ለብሳ
  ገጥሞሽ የሳባ ሞገስ የክልዮፓትራ
  አምረሽ ትታይ ጀመር በራስሽ ተራ ››
መ . ተስፋ ጠሪ ሙዚቃዋች
‹ ባሻው ›  እና  ‹ ኃይል › ለዚህ ምድብ የሚስማሙ ይመስላል ፡፡ ‹‹ ባሻው ›› በኑሮ ውድነት ተስፋ ለቆረጡ፣ በስራ ማጣት ተስፋ ላጡ፣ በመልካም አስተዳደር እጦት ለተንገላቱ፣ በስራ አለመርካት ለሚጨነቁ፣ በሀገር ናፍቆትና ፍቅር ለሚብሰለሰሉ ሁሉ መድህን መስሎ ታይቶኛል ፡፡
‹‹ ቢከፋም ቢለማም ያለም ኑሮህ ምን ባይቀና
  ሁን አንተ ጤና
  ቸር አስብበት በሰጠህ እድሜ
  አይዞህ ወንድሜ ››
በርግጥም በባህላችን ትልቁ ምርቃት ዕድሜና ጤና ይስጥህ የሚለው ነው ፡፡ ሁለቱ ካሉ ወልዶ መሳም ዘርቶ መቃም ይቻላል፡፡ ወጣቱ ቴዲ እንደ ሽማግሌ ጭራና ከዘራ ይዞ አይዟችሁ ብሎ ሲያጽናና ደምቆ ይታያል፡፡ ነገ የፈለጉበት ቦታ ለመድረስ ለዛሬ መስጠት የሚገባውን ክብር የሚገልጽበት ሀሳብ የረቀቀ ነው ፡፡
‹‹ ዓመት ያህላል ቀን እየዞረ
 ዛሬም ራሱ ነገ ነበረ
 የግዜ ሚዛን አይላወስም
 ዛሬን የሌለ ለነገ አይደርስም ››
‹ ዛሬም ራሱ ነገ ነበረ › የሚለው ትንቢት አመልካች ሀሳብ ብዙዋቻችን ከምናውቀው ብሂል 360 ድግሪ ተጠማዞ ቁጭ ያለ ነው፡፡ ምክንያቱም ትናንት ነበር ብለን ነው የምናስበው፡፡ ግን የቀንን ኡደትንና መልክን በጥሞና ስናስብ አባባሉ ባይባል እንጂ ልክ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ እናም በአንድ በኩል እያጽናና በሌላ በኩል ነገን ሳይሆን ዛሬን ጠንክረን እንድንሰራበት፣ አሰፈላጊ ከሆነ ጠንክረን መብቶቻችንን እንድናስከብርበት ያሳስበናል፡፡
‹‹ ኃይል ›› ከመልእክት አንጻር የባሻው ቀጣይ ክፍል ነው የሚመስለው፡፡ አስቸጋሪ ሁኔታዋች ቢኖሩም ‹ አይዞን ቀላል ይሆናል › እያለ ነው የሚያጽናናን፡፡ ሆኖም የአገላለጹ ዘዴ የተለያየ ነው፡፡ ቴዲ ፈጣሪ ለሰው ልጆች ፍቅር ሲል የደረሰበትን ጥቃት ገና በመክፈቻው በምሳሌነት ማሳየት የፈለገ ይመስላል፡፡
 ‹‹ ዳገት ላይ አትዛል ጉልበቴ
   የተራራው ጫፍ ፍቅር ናት ርስቴ
  ቀላል ይሆናል ቀና አርገኝ ጽናቴ ››
እነዚህ ስንኞች ፈጣሪ መስቀሉን ተሸክሞ ወደ ቀራንዮ ተራራ ያደረገውን ከባድና ፈታኝ ጉዞ የሚወክሉ ናቸው፡፡ የተራራው ጫፍ ከሸክም ያረፈበት ብቻ ሳይሆን ለፍቅር ሲል ነፍሱን ያጣበት ቦታ ነው፡፡ በጎኑ የተሰቀሉት ሁለት ሌቦች በሳዩት ምግባር አንዱ ለገነት ሌላው ለውድቀት ተዳርገዋል፡፡ ገነት የገባው ሰው ጽናት ላላቸው ሁሉ ፍሬያማ ውጤት ማሳይ ሆኖ የተወከለ ነው፡፡ ከፈጣሪ እልፈት በኃላ ሰማይና ምድር በአስደንጋጭ ትዕይንት ተመሰቃቅለው ነበር፡፡ በዚህም  ኃጢያተኞች ሳይቀሩ ዓለም ያከተመላት መስሏቸው ነበር፡፡
‹‹ ደመና ሲያይ መስሎት የጨለመ
  አለ ቂል ሰው ሁሉም አከተመ ›› ይለዋል ቴዲ ይህን ሀሳብ ለማጠናከር፡፡ ሆኖም ፈጣሪ መሃሪ ነውና ሌላ አዲስ ቀን፣ ሌላ አዲስ ኪዳን አስተዋውቋል፡፡ እናም በፓለቲከኞች ፍላጎት ሳይሆን ፈጣሪ ያለ ዕለት ሁሉም ነገር ቀላል እንደሚሆን አብራርቷል፡፡ ይህ ግጥም በዚህ መልኩ ተፍታቶ ተገለጸ እንጂ ከሚገባው በላይ በማጠሩ ሀሳቡን በአግባቡ የገለጸ አይደለም፡፡ ነገሮች ቀላል የሚሆኑበት አመላካች ማብራሪያዋች አልገቡበትም፡፡ የጸጋዬ ገ/ መድህን ግጥም ጉልበት ይሆነው ዘንድ ተፈልጎ ነው መሰለኝ በድምጽ ቢገባም በዘፈኑ ሀሳብና በግጥሙ መልእክት መካከል ሊነገር የሚያሰቸግር ክፍተት ይታያል፡፡ ይህን ክፍተት በቴዲ ሀሳብ ግለጽ ብባል ደስ የሚል ስቃይ በሚለው ዘፈን ውስጥ የመጀመሪያውን አንቀጾች በአስረጅነት እጠቅሳለሁ፡፡ ‹ ከሚገባሽ በታች ከምችለው በላይ › የሚለውን ቃል፡፡ እኔ ይህ ቃል መሃሉ እንደ ሸንበቆ ክፍት ነው የሚመስለኝ፡፡
ሰ . ፓለቲካ ቀመስ ሙዚቃዋች
ፊዮሪና በዜማም ሆነ በግጥም ውበት የደመቀ ሙዚቃ ነው፡፡ ፊዮሪና በዋናው ፍቅርን፣ ፊዮሪና በተሳቢው አሰመራን ለመጫኑ ግልጽ ነው፡፡ ቴዲ ለኤርትራ ያለው ፍቅር የጠነከረ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ‹ ዳህላክ › በሚለው ስራው የሁለቱ ወንድማማቾች ሀገሮች መለያየትና ይህም ያስከተለውን ስነ ልቦናዊ ቀውስ በተሳካ መልኩ መግለጹ ይታወቃል፡፡
በዚህም ስራው የሁለቱ ሀገራት መለያየት ውስጡ ያለውን የፍቅር እሳተ ጎመራ ለግዜው አዳፈነው እንጂ ፈንድቶ ከመውጣት የማያግደው መሆኑን አብራርቷል፡፡
‹‹ ጋራው ቢከልለን ያ ተራራ
   አትወጪም ከሃሳቤ ጓል አስመራ ›› በማለት
እንደ ሌሎቹ ስራዋቹ ሁሉ እዚህም ውስጥ ፍቅርና ተስፋ የሃሳቡ ምርኩዝ ሆነው ይታያሉ፡፡ ብሩህ ቀን መጥቶ ፊዮሪናንም ሆነ አስመራን እንደሚመለከት ተስፋ ያደርጋል፡፡
‹‹ ዘመን አልፎ ዘመን እስኪታደስ
  ቀን ቢመስልም የማይደርስ
  በፍቅር ሲቃና መሰረቱ
  ደሞ እንዳዲስ አንድ ይሆናል ቤቱ ››
በርግጥም የጀርመን፣ ጣሊያን፣ ቻይና፣ ቬትናም፣ የመን፣ የወዘተ ሀገሮች የውህደት ታሪኮች መነሻ ሆነውት ይሆናል - ቴዲ አፍሮን፡፡ በአጠቃላይ ስቴድ፣ ኦ አፍሪካ፣ ጨዋታሽና ህልም አይደገምም የሚሉት ስራዋቹ ከሌሎቹ አንጻር ሲታዩ ያልታሹ ይመስላሉ፡፡ በአንዳንድ ሙዚቃዋቹ ውስጥ የሀሳብ መመሳሰል ይታያል ፡፡ በድምሩ ሲታይ ግን የቴዲ ስራዋች ባነሱት ሀሳብ፣ በቴክኒክ፣ በጆሮ ገብነታቸው ዛሬም ልዩነት የፈጠሩ ናቸው ፡፡  በዚህ አልበሙ ስለፍቅር፣ ታሪክ፣ ተስፋ፣ ማንነትና ውህደት ዘፍኗል፡፡ ያቀነቀነውም ጥሩ ዜማን ከሚስብ የዘይቤ ቀለም ጋር በማዋሃድ ነው፡፡ የነገረን ደግሞ ፍቅር እንዲኖረን፣ ተስፋ እንዳንቆርጥ፣ ስለ አንድነት እንድናስብና በእጃችን የሚገኘውን ዛሬን በአግባቡ እንድንጠቀምበት ነው ፡፡


Friday, April 20, 2012

‎ያልተደራጁ ውሾች‎



በደ/ዘይት እየተወራለት የመጣውን  የኩሪፍቱ ሪሶርት ለመመልከት አንድ ከሰዓት ከአንድ ቡድን ጋር አቅንቼ ነበር፡፡ ወደ መዝናኛው ያመራሁት በሳምንት አንድ ቀን ለ30 ደቂቃ በነጻ መጎብኘት ይቻላል በሚባልበት ቀን ነበር፡፡ ከዚህ ቀን ውጪ  ለመግቢያ የሚጠየቀው ወጪ / በርግጥ ምሳ ይጨምራል / የሀገሬን ድሃ ማዕከል ያደረገ አይደለም፡፡

ወደዚህ መዝናኛ ሳመራ በርካታ ውሾች አራትና አምስት ሆነው በትናንሽ ዛፎች ጥላ ስር ተለሽልሸዋል፡፡ በዱር እንስሳት ባህሪያዊ እሳቤ ቢሆን የቡድን ምስረታው በራሱ መልእክት ነበረው፡፡ የጎረምሳ ቡድን…ብዙ ሚስቶችን የሚያስገብር የአባወራ ቡድን…አንድ ቤተሰብን ያቀፈ ቡድን… ወዘተ በማለት ፡፡ እነዚህ ግን የቤት እንስሳት ናቸው፡፡ በወንድማቸው ቀበሮና በአጎታቸው ተኩላ አይን ለአፍታም ቢሆን ካየናቸው ዱር ተኮር ትንተና አናጣም ፡፡ አዲስ ውሻ ወደ ጥላው መንደር ሲመጣ የራሱን መሬት በራሱ ግዜ ከተመራ በኋላ በተቻለ መጠን ድንጋዩንና አሸዋውን በእግሮቹ ይጠራርጋል፡፡ ስራው የሚያበቃው ርጥብ መሬት ከታየ በኋለ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው የዛፎቹ ጥላ ብቻ በራሱ በቂ አለመሆኑን ነው ፡፡

ሙቀቱ ድብን ስላደረጋቸው ነው መሰለኝ የርስ በርስ ግጭቶች አይታይባቸውም፡፡ ውሾች በሙቀት ወቅት ያሳዝናሉ፡፡ ሁመራና ጎዴ ያየኋቸው ውሻዋች ትዝ አሉኝ ፡፡ በስህተት ቢረገጡ እንኳን ቀልጥፈው በመነሳት ‹‹ ው…ው… ›› የሚባለውን ውሻዊ ወግ ለማሰማት አቅም ያንሳቸዋል፡፡ ጎበዝ ከሆኑ እንደምንም የአንድ አይናቸውን ቆብ ከፈት አድርገው ብዥ ያለን ምልከታ ይጠቀሙ ይሆናል፡፡

አወዳደቃቸውና ፍርግጥግጥ ማለታቸው ከጎዳና ተዳዳሪዋች ጋር ቅርበት ያላቸው ያስመስላል፡፡ድንገት ደግሞ የአሜሪካው ኬኒል ክለብ ፍረጃ ወይም ጥናት ትዝ አለኝ ፡፡ ይህ ቡድን የአለማችን ውሾች በሙሉ ዝርያቸው 150 ያህል ነው ብሎ ይነሳል ፡፡ እነዚህን ዝርያዋች ደግሞ በሰባት መሰረታዊ ቡድን ከፍሏቸዋል ፡፡ የስራ፣ የስፓርት፣ የአደን፣ የከብት ጠባቂ፣ የጌጥ /አሻንጉሊገቶች/ እና ስፓርታዊ ያልሆኑ  በሚል፡፡

ውሻ በዚህ መልኩ ይፈረጅ እንጂ ከሰው ልጆች ጋር ብዙ ታሪክ ስርቷል፡፡ በነገራችን ላይ ከኛ ጋር ሲኖር 25ሺ አመታትን አስቆጥሯል ፡፡ ትስስራችንም ‹‹ የፍቅር እስከ መቃብር ›› ያህል መሆኑን የሚያመላክቱ መረጃዋች ሞልተዋል ፡፡ ለአብነት ያህል በዴንማርክ፣ አየርላንድ፣ ጀርመንና ቻይና የተቆፈሩ የጥንት መቃብር ቦታዋች ውሻና ሰዋች አንድ ላይ ተቀብረው ተገኝተዋል ፡፡ ‹‹ እኔ ስሞት ከተከበረው ውሻዬ አጠገብ ቅበሩኝ ›› የሚል ኑዛዜ ነበር ማለት ነው!

ውሻ ቀደም ባሉት ጦርነቶች መልእክት አቀባይ ሆኖ ስርቷል፡፡ ዛሬ ደግሞ በወንጀል ምርመራ፣ መስማት ለተሳናቸው ጆሮ እና እጅ ሆኖ፣ ማየት ለተሳናቸው ዓይንና እግር ሆኖ አጋርነቱን አጠናክሯል፡፡ ከሌላው አለም ሱፍን አስበልጣ ወደ ውጭ የምትልከው አውስትራሊያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ በጎችን አደራ ሰጥታ ወደ መስክ የምታሰማራው ለውሾች ነው፡፡ ውሻ ዳርና ዳር ሆኖ ምናልባትም ጥርሱን እየፋቀ ‹‹ ና ተመለስ ብዬሃለሁ ! …›› ይለዋል በጸባይ ፡፡ 

‹‹ ይሄ ነጫጭባ ዛሬ ምን ቀምሷል ?!.... መስመሩን ይዞ አይጓዝም እንዴ ?! ›› ይለዋል አብሻቂ በግ ሲያጋጥመው ደግሞ ::
ታዲያ ይህን መሰሉ ውሻ ያለው ክብር፣ ፍቅርና እንክብካቤ ቀላል እንዳይመስላቸሁ፡፡ ቢያጠፉ እንኳን ‹ ጥፋ ከዚህ! ልክስክስ ! › ተብሎ አይዋረድም፡፡ ወይም ድንገት ሳያስብ ጀርባው በወፍራም ዘነዘና አይወቀጥም ፡፡ መጀመሪያ ልክ እንደ በኩር ልጅ ምቾት የሚሰጥ እቅፍ ውስጥ ይገባል ፡፡ ከዚያም ጀርባው፣ አንገቱና ጆሮው ላይ ለስላሳ ጣቶች ስልት ባለው መልኩ እንዲደንሱ ይደረጋል፡፡ ከዚያ ነው የሚከተለው ንግግር የሚደመጠው  ‹‹ ምነው ቦቢ?! What’s wrong with you ? are you alright any way? Ohhh! My hero! I hope you will not repeat such a silly mistake! ›› በመጨረሻም ምርቃት ጣል ይደረግለታል - ማለትም የሆነ ቦታ ይሳማል፡፡

መቼም የጓደኛችንን ውሻ ተግባር እንዘርዝረው ብንል ስፍር ቁጥር የለውም፡፡ ታዲያ ምነው የደ/ዘይት ውሾች ያለስራ ተቀመጡ?!       ‹ አደገኛ ቦዘኔዋች ›  ብለን ለመጥራት የሚቀረን አላፊ አግዳሚውን ባለመተናኮላቸው ብቻ ነው ፡፡ በየቦታው እንደ ችቦ ተሰባስበዋል፡፡ ግን አልተደራጁም፡፡ ሳይንሳዊ መስመር እንከተል ካልን  ከሰባቱ ዝርያዋች የት ውስጥ እንደሚወድቁ ማጥናት ያስፈልጋል፡፡ የመደራጀት ጥያቄ አቅርበው ‹ ፍትሃዊ  አይደለም › የሚል ምላሽ አግኝተው ከሆነስ ? ደግሞ ለውሻ እንዲሉ….. 

ግራም ነፈሰ ቀኝ የአካባቢው ነዋሪዋች፣ ባለሀብቶችም ሆነ ባለስልጣናት ውሻን የልማት ምንጭ አድርገው ማየት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በመደራጀት ለመጠቀም ሲሉ ግን ውሾች ራሳቸው መራራውን ሃላፊነት ቀድመው መውሰድ አለባቸው፡፡
እነሆ የደ/ዘይት አርሶአደሮች በባህላዊ መንገድ ቢሆንም አጭር ስልጠና እንዲያዘጋጁ ጥያቄ ማቅረብ አለባቸው፡፡ ይህ ስልጠና መሬት ላይ የሚያስቸግራቸውን አይጥና አይጠ መጎጥ በመቀነስ ረገድ ዓይነተኛ ሚና ይኖረዋል፡፡ ካስፈለገ የባሌን ወይም የሰሜን ቀበሮን የአደን ስልት በተሞክሮ መውሰድ ይቻላል፡፡  ተሞክሮው ይቀመራል፣ የተቀመረው ይስፋፋል ፡፡ የሀገራችን ውሻ ጥርሱን እየፋቀ ባይሆንም ኮቴ እየነከሰ ከብት መጠበቅ ይችላል፡፡ በቀንድ ከብት ብዛት ከአፍሪካ መሪ ለሆነቸው ሀገር ጠንከር ያለ ተሞክሮ አስፈላጊ በመሆኑ ለልምድ ልውውጥ አሜሪካ ወይም አውስትራሊያ መጓዝም የግድ ነው፡፡ ርግጥ ነው ባሁኑ ግዜ አፋጣኝ ምላሽ ሊያገኝ የሚችለው የቻይና ጉዞ ነው፡፡ ቻይናዋች ግን ውሻዋቻችንን በሰላም ይመልሳሉ ማለት ዘበት በመሆኑ ልዩ ጥንቃቄ ያስፈልጋል፡፡

የደ/ዘይት ውሾች ቀጣዩ ጥያቄዋቻቸው ባለሀብቶችን ይመለከታል፡፡ ባለሀይቋ ከተማ የሚዝናናባትን እያረካች ያለቸው በዋናነት በራሱ በሀይቁ ተፈጥሮ ሲሆን አልፎ አልፎ ጥቂት ጀልባዋች ዊን ዊን እንዲሉ ታደርጋለች፡፡ እነዚህ ውሾች ጥቂት ስልጠና ቢያገኙ ሀይቁ ባፍዛዥ የሰርከስ ትርዒት ሊደምቅ ይችላል፡፡ የውሾች የዋና ውድድር ቢካሄድስ? ለአብነት ባለሀብት የተረዳቸው 14ሺህ የሚደርሱ የአሜሪካ ውሾች በየአመቱ የውሻ ትዕይንት ያቀርባሉ፡፡ በእንግሊዝ፣ ሜክሲኮና ስፔን የውሻ የሩጫ ውድድር የተለመደ ነው፡፡

ማን ቀረ ? መንግስት ? … መንግስት ያው በተፈጥሮው በኮምፕሌይን ማሸን complex ውሳኔዋችን አዋጪ በሆነ መንገድ የሚያመርት ተቋም ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ጥያቄው ህገመንግስታዊ መብት መሆኑን ተናግሮ ወቅታዊ አለመሆኑን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ጥያቄው አንገብጋቢ መሆኑን ጠቅሶ ለምላሹ ዘርፈ ብዙ ምርምር እንደሚያከናውን ቆምጫጫ መልስ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ጥያቄው አንድ ቀን እንደሚነሳ እንደሚያውቅ ገልጾ ነገር ግን የበጀት አመቱ ዝርዝር ጉዳዩን address እንደማያደርገው ሊያሰምርበት ይችላል፡፡

መቼ እንደሚያደርገው ባይታወቅም አንዳንዴ ደግሞ እንደ ግሩም አጭር ልቦለድ ነገሩን ባልተጠበቀ መልኩ ሊጨርሰው ይችላል፡፡ ‹ የውሾችን ችግር መፍታት › በማለት ባለ አራት ነጥብ የአቋም መግለጫ ሊያወጣ ይችላል፡፡ የውሾች ችግርን መፍታት…..

. በኮንዶሚንየም ሰፈሮች የሚታየውን ዘረፋ ለመቀነስ
. በሞተው ስፓርት ላይ ቅመም ለመጨመር
. የቀበሮን እብሪት ለማስተንፈስ
. መርሃ ግብሩን ለማሳካት ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል፡፡



Tuesday, April 17, 2012

‎የፌስ ቡክ ወግ‎








ፌስ ቡክ ከነችግሩና ከነሱሱም ቢሆን ብዙ ሚዛን የሚደፉ ጠቀሜታዋች እንዳሉት መከራከር የዋህነት ነው፡፡ የቁምነገረኝነቱን ጎን መመርመር ለእናንተ ትቼ ከፌዛዊ መልኩ/ ጥቅሙ ጥቂቶቹን ልወርውር፡፡

ፌስ ቡክ በደበረዋትና ብቸኛ በሆኑ ግዜ የተረት አባት ሚናን ተክቶ ሊያስቆት ይችላል፡፡ መቼም የአጫጭር ጥቅሶች ባህር በመሆኑ ጥቅስ አፍቃሪ ብቻ ሳይሆኑ በንግግርዋ መሃል ‹‹ እጠቅሳለሁ ›› የሚል ማዋዣ እንዲጠቀሙ መንገድ ይመራል፡፡ በየመንገዱ ጥቅሶች ካጋጠመዋት ‹‹ ግዛ-ግዛ ›› የሚል ሞጋች መንፈስ እንደበቀለብዋት ይገነዘባሉ፡፡ የፌስ ቡክ ጣሪያና ግድግዳ ፎቶ በፎቶ በመሆኑ በየቤቱ ለእንግድነት ሲሄዱ ‹‹ እስኪ ያቺን አልበም ወዲህ በላት ?›› የሚል ጥያቄ ያመነጫሉ፡፡ አልፎ አልፎ  የስዕል ኤግዚቢሽኖች መከፈታቸውን ሲሰሙ ‹‹ መግዛት ባንችል እንኳን ሄደን ማበረታታት አለብን !! ›› የሚል ደመቅ ያለ ንግግር ወደ ሌሎች ጆሮ እንዲደርስ ሳያደርጉ አይቀርም፡፡ መቼም ግጥም ወይም መጣጥፍ ለሚዲያ ቢልኩ ውበቱ፣ መልዕክቱ፣ ሚዛናዊነቱ፣ ደጋፊነቱ ወዘተ የተባሉ ህጋዊና ህገወጥ ሳንሱሮችን ማለፍ አለበት፡፡ ፌስ ቡክ ገጽ ላይ ታዲያ ሲፈልጉ ሰክረው፣ ወይም በእንቅልፍ ልብዋ አይንዋን  እያጨናበሱ ሁሉ ያለ ከልካይ ይጽፋሉ፡፡ የዚህ እኩያ የሆነ ነጻነት አሜሪካ ወይም ህንድ ያገኛሉ ? በፍጹም !!! 
 
ፌስ ቡክ ብቻ ሳይሆን የፌስ ቡክ ኦንላይን ተጠቃሚዋችም ነገረ ስራ ከተመረመረ በጣም ነው የሚያስቀው፡፡ በጣም ነው የሚያሳዝነው፡፡ ብዙ በጣሞች፡፡ ታዲያ ለወሬ እንዲመቸን ለተጠቃሚዋች ባህሪ ስያሜ እየሰጠን ነው የምናወራው ያው ለመዝናናት ያህል የቀረበ መሆኑንም አስምሩልኝ - በተለይ ለወግ አጥባቂዋች

1 . አድፋጭ ፤  ይህ ቡድን ዘወትር በአውሮፓ በረዶና ጉም የተሸፈነ ነው የሚመስለው፡፡ ብዙ ግዜ ኦንላይን ላይ አይጠፋም ፤ ግን አይታይም፡፡ አልፎ አልፎ ወይ ጥቅሱን ወይ ፎቶውን ወይ ዜናውን ዋናው ሰሌዳ ላይ በተን ያደርጋል፡፡ ጠፋ እንዳትሉት ደግሞ ሰሌዳው ላይ በተለጠፉት መረጃዋች ላይ ወይ ፍቅሩን አሊያም ተቃራኒ ሀሳቡን ሲገልጽ ያዩታል፡፡ ማህበራዊ ተሳትፎውን በጓጉንቸር ቁልፍ የከረቸመ ይመስላል፡፡ አድፍጦ ይሰራል ወይም አድፍጦ ጓደኞቹን ይከታተላል ለማለት ያስቸግራል፡፡ መስኮትና በሩ በተዘጋ ቤት ውስጥ ስንት ቀን ? ስንት ወር ? መቀመጥ ይቻላል፡፡ ‹‹ አይወብቃቸውም ? ›› እላለሁ አንዳንዴ  ‹‹ አይጨንቃቸውም ? ››

2. ጠባቂ ፤  ይህ ቡድን መብራቱን አያጠፋም፡፡ ሰውየው የቅርብም ሆነ የሩቅ ጓደኛዋ ሊሆን ይችላል፡፡ ከተለያያችሁም ረጅም ግዜ አስቆጥራችሁ ይሆናል፡፡ የፈለገ ቢሆን ግን ቅድሚያውን ወስዶ ሰላምታ አያቀርብልዋትም፡፡ የግድ ከእርስዋ የሚለኮሰውን ክብሪት ይጠብቃል፡፡ ዛሬ ቅድሚያውን መውሰድዋን ግምት ውስጥ አስገብቶ እንኳ በሚቀጥለው ግዜ የማያልቀውን ሰላምታ ለማስቀደም ፍላጎት የለውም፡፡ ደግነቱ ሁሌም ቅድሚያውን የሚወስዱ ከሆነ ፈታ ብለው የሚያወሩ ናቸው፡፡ የኩራት ጉዳይ ወይስ የክብር ፍለጋ ?        ‹‹ ወንድ ወደሽ ጺሙን ፈርተሸ ›› እንዴት ይሆናል ነው ነገሩ ???

3. ስልታዊ አፈግፋጊ ፤ ይህ ቡድን መስመር ላይ መኖሩ በመብራቱ ይታወቃል፡፡ አገር ሰላም ነው ብለው ወሬ ሲጀምሩ በጥንቃቄም ቢሆን መልስ ይሰጣል፡፡ ወሬው የፓለቲካ፣ የኑሮ ውድነት፣ የወቅታዊ ሁኔታዋች ላይ ሲያነጣጥር ደህና እደር እንኳን ሳይልዋት መብራቱን ድርግም አድርጎ ያጠፋል፡፡ የርዕዮተ ዓለምና የሌላ አመለካከት ካላችሁ ደግሞ እርሶ ኦን ላይን እንደገቡ የርሱ መስኮት ጨለማ ይውጠዋል፡፡ ወይም ደግሞ ደቃቅ ሰላምታ ያቀርብልዋትና ምላሽዋን ሳይጠብቅ ቤቱን ክርችም ያደርጋል፡፡ ይሄ እንግዲህ አገም - ጠቀም መሆኑ ነው፡፡ ሰላምታ ሲልኩለት ባላየ ማለፍም ስልቱ ነው፡፡ ከዛ የእርሶ መስኮት ሲዘጋ ‹ በጣም ይቅርታ አላየሁትም ነበር › የሚል መልዕክት በጣም ዘግይታ ትደርሶታለች፡፡ እዚህ ቡድን ውስጥ ያሉ ሰዋች በጥርጣሬና በፍርሃት የተዋጡ ነጻነት የራቃቸው ስለሚመስሉኝ ያሳዝኑኛል፡፡ ሁሌም በአንድ ጥቅስ የሚጽናኑም ይመስለኛል     ‹‹ በጎመን በጤና !!! ››

4. ተቸካይ  ፤ ብዙም ባይሆኑ እዚህ ቡድን ውስጥ የሚገኙ ተጠቃሚዋችም አሉ፡፡ ለጓደኝነት ጠይቀዋታል፣ ወይም ጓደኝነትዋን ተቀብለዋል፡፡ በኦን ላይን ሜዳ ላይ ለሚልኳቸው መልዕክትም ሆነ ሰላምታ ግን ምላሽ አይሰጡም ፡፡ ምን ማለት ነው ? ምን እያሰቡ ነው  ? የሆነ ነገር ሰሌዳው ላይ በመወርወር ይሳተፋሉ ነገር ግን የጓደኞቻቸውን ተሳትፎ በማድነቅም ሆነ በመተቸት አስተያየት አይሰጡም ፡፡ ወይ ጉድ የሆነ ፓርቲ አላያቸውም እንጂ ‹‹ መሃል ሰፋሪ! የያዘውን የማይለቅ ! የድሮን የበግ ዋጋ በመጥራት ግዜውን የሚያሳልፍ ! ›› ወዘተ ወዘተ እያለ ያሸክማቸው ነበር ፡፡

5 . ሰጥቶ ተቀባይ ፤ ይህ ቡድን መልከ ብዙና ነገረ ዓለሙ የገባው ይመስለኛል፡፡ እንደ ነጋዴ ሳየው ወዲህ የሚልከውንም ሆነ ከዚያ የሚመጣለትን መረጃ በአግባቡ ያውቃል፡፡ በዲፕሎማት ጎን ከታየ ለያዘው ነገር በመከራከር ከዛኛው ወገን የሚገኙ ተሞክሮዋችን አንድ ባንድ ይለቅማል፡፡ ውይይት ለመክፈትም ሆነ የውይይት ግብዣ ሲቀርብለት ለመታደም አይቸገርም፡፡ በር ዘግቶ ሲሰራ መልዕክት ብትልኩለት ምላሹ ፈጣን ነው፡፡

6. የሌሊት ወፎች ፤ ፌስ ቡክ ላይ ቀን ዳናቸውን አጥፍተው ሌሊት ደምቀው የሚታዩ ሰዋች አጋጥመውኛል፡፡የለሊት ወፍ ቀን በየዛፉና በየዋሻው ቁልቁል ተዘቅዝቃ ነው የምታሳልፈው፡፡ ለሊት ቀን የጠፋውን ግዜ ለማካካስ በሚመስል መልኩ እንደ ጀት ስትካለብ ትውላለች ፡፡ ማታ ማታ መስኮታቸውን የሚከፍቱ ፌስ ቡከሮች እንደ ለሊት ወፍ ተኝተው ሳይሆን በስራ ወዲህና ወዲያ ሲካለቡ የሚውሉ ይመስለኛል፡፡ በርግጥ እንደ ለሊት ወፍ ወይም እንደ ‹ አርጋው በዳሶ › በጭንቅላታቸው ቆመው አይደለም የሚሰሩት፡፡ የእንቅልፍ ሰዓታቸውን ስለሚሻሙ ብቻ ሳይሆን ባልነበሩበት ሰዓት ምን እንደተከናወነ ለማወቅ ከአንዱ ሳይት ወደሌላው በፍጥነት የሚሮጡ ይመስለኛል፡፡ ስታዋሯቸው ሁኔታዋችን በአጭሩ ለመቋጨት የሚሞክሩትም ከዚህ አንጻር ሊሆን ይችላል፡፡ ውጪ ያሉትስ ይሁን እዚሁ እያሉ ካለ ለሊት አንታይም የሚሉት ምንድነው ሀሳባቸው ? ፌስ ቡክ ውስጥ የምታማልል ጨረቃ አለች እንዴ  ? በተምስጦ እያነበቡ ቅኔ ለመቀኝትም ሊሆን ያችላል ? የአይን ቆብ ላይ ያረገዘ እንቅልፍን ለመገላገል ያመችም ይሆናል፡፡

7 . የመብራት ሃይል ባልደረባ ፤ በሀገራችን እምነት ካጡ መ/ ቤቶች አንዱ መብራት ሃይል ነው፡፡ የማይታመነው ባልተጠቀሙበት ታሪፍ ላይ ያሰኘውን እጥፍ ጨምሮ ማስከፈሉ አይደለም፡፡ ብርሀን ሆነልኝ ሲሉ ወዲያው በጨካኝ እጁ ወደ ጨለማ ይወረውሮታል፡፡ በቃ ጠፋ! ብለው ተስፋ ሲቆርጡ ብልጭ ብሎ ሊያስደስትዋት ይችላል፡፡ ወዲያው ደግሞ ምስጋናዋትን አስጨርሶ ድራሹ ይጠፋል ‹‹ እረ እልም ያድርግህ እቴ !! ›› የማይደርስ ርግማን ከኋላው ይከተለዋል፡፡ እና አንዴ ይበራል፣ አንዴ ይጠፋል፡፡ ፌስ ቡክም ላይ መስኮታቸውን በኦን ላይን መብራት ብልጭ አድርገው በሆነ ነገር እንደ ደነገጡ ሁሉ ድርግም አድርገው የሚዘጉ ሰዋች አሉ፡፡፡ አንዳንዴ እንደውም ይህ ነገር በር ቢሆን አቤት ጩኀቱ !! ስል አስባለሁ ፡፡ አሁንም አዘናግተው ብቅ ይሉና ወዲያው ጨለማው ውስጥ ይሰወራሉ፡፡ ይህን ጨዋታ ለማራዘም ከፈለጉ የርስዋን መብራት ድርግም አድርገው ቆይተው ድንገት ሲያበሩት ያ የመብራት ሃይል ባልደረባ በብርሃን ተርታ ተሰልፎ ያገኙታል፡፡ ወዲያው ግን ጨለማ ይውጠዋል፡፡ አሁን ለብርሃን ሳይሆን ለጨለማ ይስቃሉ፡፡ ምንድነው እንደዚህ ማብሪያ - ማጥፊያ ማንገጫገጭ !!!  ‹‹ እረ አንፓሉ ያቃጠላል ?? !! ››

ስለደከመኝ ምድቡን እዚህ ጋር አቁሜዋለሁ ፡፡ እርስዋን የት ቅርጫት ውስጥ አገኙት ?? ያልታየ ምድብ ካለም ልምድዋን ይወርውሩ፡፡ 12 ከደረስን በሁለት ተከፍለን አንድ የፌስ ቡክ ፕሪምየር ሊግ እንመሰርታለን ፡፡



Monday, April 16, 2012

‎ መለስ ዜናዊና የህወሃት የትግል ጉዞ‎



‹‹ መለስ ዜናዊና የህወሃት የትግል ጉዞ ›› በኮ/ል ኢያሱ መንገሻ የተጻፈ መጽሀፍ ነው፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም ‹‹ ሰርዶ ›› እና ‹‹ ካብ ማህደር ፈንቅል ›› የተሰኙ ስራዋችን ለንባብ አብቅተዋል፡፡  ለደራሲው ምስጋና ይድረሰውና አንዳንድ ጠቃሚ መረጃዋችን ላካፍላችሁ፡፡……..
 
የአቶ ዜናዊ ልጆች 
 
 አቶ ዜናዊ በአጠቃላይ 13 ልጆች አሏቸው፡፡ ሰሰን ዜናዊ በአድዋ ከተማ ጠላ ጠምቃ እየሸጠች የምትተዳደር ነች፡፡ ገርግስ ዜናዊ እንግሊዝ አገር የምትገኝ ስትሆን፣ ቢንያም ዜናዊም በተመሳሳይ እንግሊዝ ሀገር ይገኛል፡፡ በመምህርነት ስራ በአድዋ ከተማ የሚገኝው ፍሰሃ ዜናዊ የመለስ ታላቅ ወንድም ሲሆን፣ ጸጋዬ ዜናዊ ደግሞ ራማ በተባለች አነስተኛና አድዋ አጠገብ በምትገኝ ትንሽ ከተማ ቡቁልት እየሸጠ ኑሮውን ይመራል፡፡
 
   ማሚት ዜናዊ ቀደም ብሎ ታጋይ የነበረች ሥትሆን አሁን ባለትዳርና አስተማሪ ሆና ባድዋ ከተማ ትገኛለች፡፡ ካሁሱ ዜናዊ ታጋይና አሁን በሽሬ ከተማ በመንግስት ስራ ላይ ተሰማርታ እየሰራች ያለች ስትሆን፣ ግዛቸው ዜናዊ ደግሞ በስደተኞች ጉዳይ መ/ቤት እየሰራ ይገኛል፡፡ ሀይሌ ዜናዊ በአዲስ አበባ ቤተክህነት ውስጥ፣ ዘውዲ ዜናዊ በት/ሚኒስትር ውስጥ በጸሃፊነት፣ ኒቆዲሞስ ዜናዊ ደግሞ በባንክ ሰራተኝነት እየሰሩ ይገኛሉ፡፡
 
መለስ በልጅነት
 በህጻንነት እድሜው ጠብና ድብድብ የመሳሰሉት ባህርይዋች የማይታይበት ሰላማዊና ትእግስተኛ ነበር፡፡ በአብዛኛው በልጅነት ዕድሜው በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የተለያዩ ጥፋቶችን መፈጸም ያለና የተለመደ ክስተት ቢሆንም፣ መለስ ግን ከፍ ሲል ከተገለጸው  ባህሪው የተነሳ ቤተስብ ልጆቻቸው እንዲፈጽሟቸው የማይፈልጉ ተግባራትን አይፈጽምም ነበር፡፡ ጥሩ ስነምግባርም ነበረው፡፡
 
የአቶ ዜናዊ ምስክርነት
 
መለስ አንድ ቀንም አጥፍቶ አያውቅም ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳም ገስጨው አላውቅም፡፡

ሰይጣን ፍለጋ
 
በአድዋ በሚገኝ አንድ የመዋኛ ኩሬ ሰይጣን ይዋኝበታል የሚል አመለከከት ነበር፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ መለስና ጓደኞቹ ይመክሩና እውነታውን ለማረጋገጥ አንድ ለሊት ወደቦታው ያመራሉ፡፡ ደፈጣ ይዘው ሰይጣኑን ሲዋኝ እናየዋለን በማለት ጠበቁ፡፡ ጸጥታ ብቻ ሆነ፡፡ጥበቃው ያሰለቸው መለስ ካደፈጠበት ይነሳና ለምን ገብተን አናረጋግጥም ? በማለት ጓደኞቹን ይጠይቃቸዋል፡፡ አዋንታዊ ምላሽ ያገኛል፡፡ ፈጥኖና ቀድሞ ልብሱን በማውለቅ ወደ ቀዝቃዛው ኩሬ ዘሎ በመግባት በጨለማ ውስጥ ዋና ቀጠለ፡፡ ጓደኞቹም ተከተሉት፡፡ ሰይጣን ፍለጋውንም ተያያዙት፡፡ ተፈላጊው ሰይጣን ግን አልተገኝም፡፡

መለስና ትምህርት

በየዓመቱ ከፍተኛ ውጤትን እያስመዘገበ የ2ኛ ደረጃ ትምህርቱን ከማጠናቀቁ በተጨማሪ በ64 ዓም የ12ኛ ከፍል መልቀቂያ ብሄራዊ ፈተናን በከፍተኛ ውጤት ማለፍ ችሏል፡፡ በወቅቱ ከተጠቀሰው ት/ቤት ተፈታኝ ከነበሩት ተማሪዋችና በአጠቃላይ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ውጤት ማምጣታቸው ተረጋግጦ ለቀዳማዊ ሀይለስላሴ ሽልማት ከበቁ አስር ወጣት ተማሪዋች መካከል አንዱ ነበር፡፡

የዶ/ር ዳንኤል ፈቀደ ምስክርነት
ዶ/ር ዳንኤል የመለስ የት/ቤት ጓደኛና አብሮ ተሸላሚ ከነበሩት ተማሪዋች አንዱ ነበሩ፡፡ አሁን በአ/አበባ ዩኒቨርስቲ የህክምና ፋከልቲ መምህር ናቸው፡፡ ‹‹ መለስ ትጉህ ጥንቁቅና ጎበዝ ተማሪ ነበር፡… በትርፍ ሰዓት የቅርጫት ኳስንና የጠረጼዛ ቴኒስ ጨዋታ መጫወትን ይወድ ነበር፡፡መለስ ጥቃትን አይወድም ነበር፡፡ በዕድሜ ሆነ በጉልበት ተለቅ ብለውና በልጠው ይታዩ የነበሩ ተማሪዋች በእሱ ላይ የሚፈጽሙትን ማናቸውም የማስፈራራትና ተጽዕኖ የመፍጠር ሁኔታን አጥብቆ የመቃወምና ያለመቀበል ባህሪና ሁኔታ ይታይበት ነበር፡፡ … ለዩኒቨርስቲው ተማሪዋች ህብረት አመራርነት ተወዳድሮም የሳይንስ ፋኩልቲ ተማሪዋች ህብረትን እንዲወክል ተመርጦም ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ነበር የነበረውን ዕምቅ የአመራር ችሎታ ባህሪያትንና በተስብሳቢ ፊት በመድረክ ላይ አሳማኝ ማራኪ ንግግርን የማድረግ ተሰጥኦውንና ብቃቱን ማሳየት የጀመረው፡፡›› ብለዋል፡፡

ማገብት
 
የትግራይ ህዝብ የትጥቅ ትግል ከ11 ባልበለጡ ታጋይች የካቲት 11/1967 ዓም ደደቢት በተባለ ቦታ እንደተጀመረ ይፋ ከመደረጉ በፊት ለህዝባዊ ትጥቅ ትግሉ መጀመርና ለህወሃት መመስረት መሰረትና ጥንስስ የነበረ አንድ አደረጃጀት ነበር- እሱም ማህበር ገስገስቲ ብሄረ ትግራይ ነበር፡፡
 
የማገብት መስራቾች

ማገብት ዩኒቨርስቲ በነበሩ ተማሪዋች የትግራይ ተወላጆች ተመሰረተ፡፡ መስራቾቹ አግአዚ ገሰሰ፣ ስዩም መስፍን፣ አባይ ጸሀዬ፣ በሪሁ በርሀ/ አረጋዊ/ ፣ አይሉ መንገሻ/ ነጠበ/፣ ግደይ ዘርአጽዮን፣ አስፍሃ ሐጎስ/ ሙሉጌታ/ ነበሩ፡፡ በሂደት ስበሰሃት ነጋ፣ ሙሴ ተህለና ገሰሰው አየለ በምስረታው ተቀላቅለዋል፡፡
 
መለስ ተሕለና መለሰ ዜናዊ
 
መለስ ተሕለ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተማሪዋች ንቅናቄ ታሪክም ሆነ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የትግራይ ተወላጆች ተማሪዋች ማህበር ንቅናቄ ውስጥ ስማቸው ጎልቶ ከሚጠሩ ታዋቂ ታጋይ ተማሪዋች አንዱ ነበር፡፡ በዋቢሸበሌ ሆቴል ላይ ተፈጸመ በተባለ የቦንብ ፍንዳታ እጁ አለበት በሚል የሐሰት ውንጀላ በመጋቢት 67 ዓም በደርግ መንግስት በግፍ የተገደለ ወጣት ተማሪና ታጋይም ነበር፡፡ ይህን ታጋይ ለመዘከር ለገሰ ስሙን በመታሰቢያነት ምርጫውና መጠሪያው አደረገው፡፡

ደደቢት

የካቲት 11/1967 የትጥቅ ትግል የተጀመረበት ቦታ ነው፡፡ ደደቢት የእጣን ዛፍ ጨምሮ የተለያዩ የበርሃ ዛፎች የተሞላበት በርሃ ነው፡፡ የመሬቱ ገጽታ ሰበርባራ መሬት የበዛበትና ለአይን የሚገባ ትልቅ ተራራ የማይታይበት ቆላ መሬት ነው፡፡ ከየካቲት እስከ ሰኔ ያሉት ወራቶች የእሳትን ያህል የሚፋጅ የሀሩር ንዳድ ከሰማይ የሚዘንብባቸው ጊዚያቶች ናቸው፡፡መንደር የሚባል እምብዛም አይታይበትም፡፡ ዛፎችን እንደ መኖሪያ ጎጆ፣ አለቶችን ደግሞ እንደ መኝታ መደብ አድርገው የሚገለገሉበት ቦታ ነበር፡፡

ተሓህት
ተሓህት የተመሰረተውና ህልውና ያገኝው በሰኔ 1967 ዓም ሕርሚ ላይ በተካሄደው አጠቃላይ ስብሰባ ነው፡፡

የወይን መፈጠር
በስዩም መስፍን የሚመራ ስምንት አባላት የነበሩበት ሃይል ወደ አዲግራት ከተማ በመግባት በከተማው ውስጥ በሚገኝው አግአዚ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ላይ ኦፕሬሽን በማካሄድ የሚፈለጉ ቁሳቁሶችን እንዲያመጣ ተሰማራ፡፡ ግዳጁም የተሳካ ነበር፡፡ በዚህ ሁኔታም ይፈለጉ የነበሩት ቁሳቁሶች ማለትም ወረቀትን ጨምሮ ቀለም፣ ታይፕራይተሮችና ማባዣዋች ተገኙ፡፡ ይህን በመጠቀምም የተሓት የመጀመሪያው ልሳን ወይን ቁ. 1 በጥር 1968 ዓም ተጽፎ ወጣ፡፡/ ይዘቱም ማስተባበያ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ተህሃትና ግንባር ገድሊ ሃርነት ትግራይ ለመዋሃድ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተው ግንባሩ ኢ-ዴሞክራሲያዊ ተግባር በመፈጸሙ በተህሃት ተመቶ ነበር፡፡ እናም ‹‹ ይድረስ ስህተት እየፈጸሙ ላሉ ወገኖቻችን›› በሚል ርዕስ ለትግራይ ህዝብ እውነታውን የማሳወቅ ስራ ነበር/

ሬሽን
 
ሕወሓት ከጨቅላነቱ ጀምሮ ተግባራዊ እያደረገው የነበረና፣ በዚህ የተነሳም የተወሰኑ አባላቱን ያስለመዳቸው አንድ ነገር ነበር፡፡ እሱም የሲጋራ ሬሽን ነበር፡፡ ሲጃራ ለሚያጨሱና ሱስ ለነበራቸው አባላቱ በድርጅቱ አሰራር መሰረት በየቀኑ አምስት ፍሬ ሲጃራ በሬሽን መልክ ይታደላቸው ነበር፡፡ 5   ‹‹ ግስላ ›› እየተባለ ይታወቅ የነበረ ሲጃራ በዚያን ሰዓት ለድርጅቱ የሲጃራ ሬሽን ዕደላና ለአጫሾቹ ብቸኛ አማራጭ ነበር፡፡ በወቅቱም ምርት ሲጃራው ተወዳጅም ነበር፡፡

የአህዴን አመሰራረት
 
በህወሃትና በኢህዴን መካከል ተከራረዋ በተባለ ቦታ 142 ቀናትን ያስቆጠረ ውይይት ተካሂዷል፡፡ … በተካሄደው አብይ ስብሰባ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ለመመስረትና ትግሉን ለመቀጠል የወሰኑ 51 አባላት የተሳተፉበት ነበር፡፡መጀመሪያ አብረዋቸው የመጡ 64 የሚሆኑት የተቃውሞ ንቅናቄ አባላት የነበሩት ግን ትግል መቀጠል አይቻልም በማለት ቀደም ብለው ራሳቸውን በማግለላቸው እንዲሸኙ ተደርገዋል፡፡… ኢህዴን እንደተመሰረተ ይፋ የተደረገበት ጉባኤ የተጠናቀቀው ታምራት ላይኔ፣ አዲሱ ለገሰ፣ ጌታቸው ጀቤሳ፣ ተፈራ ዋልዋ፣ በረከት ስምኦን፣ ሃይሌ ጥላሁን፣. ታደሰ ካሳ፣ ህላዌ ዮሴፍ እና ዘለቀን የድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት አድርጎ በመምረጥ ነበር፡፡ ሚያዚያ 11/1973 ዓም ኢህዴን ረጅሙን የትጥቅ ትግል መጀመሩን በይፋ አወጀ፡፡

ዝነኛው ሳህል
እግዜር አለምን ሲፈጥር ተናዶ በክርን እየደቆሰ የተማታበት መሬት ይመስላል፡፡ ንዴቱ ከመሬቱ ገጽታ ላይ ተጽፏል፡፡ ተደራርበው የተቀመጡ ያገጠጡት ድንጋዮች ተፈጥሮ በዘመናት የቆለላቸው አይመስሉም፡፡ አንድ ሃይል ለምጽአት ቀን በጥበብ ጠርቦ ያስቀመጣቸው የመቃብር ድንጋዮች እንጂ፡፡ ተራሮቹ መረማመጃ ቀርቶ ለእግር መቆናጠጫ የሚሆን ቦታ የላቸውም፡፡ ለሰው ቀርቶ ለዝንጀሮዋችም ቢሆን አይመቹም፡፡ አንዳንዶቹ ተራሮች እስከ ትከሻቸው ድረስ ጉም ለብሰው ሲታዩ ዓለምን በመናቅ የአመጽ ጋቢ ተከናንቦ በእብሪት ተወጥሮ የቆመን ወንበዴን ይመስላሉ፡፡/ ጸሀፊው የበዓሉ ግርማን አባባል ሲጠቀም/

‎ዘራ ያዕቆብ

ዘራ ያዕቆብ፣

ሀዲስና ብሉይ ኪዳናትን ፣የቤተክርስቲያን አባቶችን ታሪክና ቀኖናዊ ህግጋትን ጠንቅቆ የሚያውቀው ንጉስ ዘራ ያዕቆብ ‹‹ መጽሀፈ ልደት ›› እና  ‹‹ መጽሀፈ ብርሃን ›› የተሰኙ መጽሀፍትን ጨምሮ የስርዓተ ቅዳሴ ደንብና መመሪያዋችን የተመለከቱ ሰራዋችን ማበርከቱ ይታወቃል፡፡ የቤተመንግስቱን መቀመጫ ያደረገው ደብረ ብርሃን ውስጥ ሲሆን ህንጻውን እንዲሰሩ ያደረገውም በቤተመንግስቱ ታላላቅ መኳንንቶች ነው፡፡ ስራውን ሳያጠናቅቁም የማዕረግ ልብሳቸውን እንዳያደርጉ ተከልክለው ነበር፡፡ ፍጹም ጀግና እንደነበረና በርካታ አስተዳደራዊ መሻሻል እንዳደረገ የሚነገርለት ዘርያቆብ በርኩስ መናፍስት ፍርሀት ዘወትር ይሸበር ነበር፡፡

መላ ሀገሪቱን ዳር እስከ ዳር ሰጥ ለጥ አድርጎ የመግዛት ችሎታ የነበረው ይህ ሰው፣ ህዝብ በፍርሃትና በስጋት እንዲኖር ያደርግ የነበረ፣ ማንም እንደሚቀበለው ከኤዛና እና ከላሊበላ ቀጥሎ ታላቁ የክርስትና እምነት ሊቅ የሆነው ይህ መሪ፣ በቆራጥነት ሲዋጋቸው የኖሩት የምድራዊና የርኩስ መንፈስ ኅይላት ጉዳት እንዳያደርስቡት  በፍርሃት ተውጦ ይኖር እንደነበር ለማመን በርግጥ ይከብዳል፡፡

ጠጉራቸው ከጠንቋዮች እጅ ገብቶ በዚህ ፈሪሀ እግዚሀብሄር ባደረበት መሪና በቤተ መንግስቱ ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ከሚል ፍርሃት የተነሳ፣ የልፍኝ አሽከሮቹ ራሳቸውን እንዳይላጩ ክልክል ነበር፡፡ መነኮሳት በግቢው ውስጥ እየዞሩ ርኩሳን መናፍስትን ለመከላከል ሌትና ቀን ከጠዋት እስከ ማታ ፣ ከምሽት እስከ ንጋት ያለማሰለስ መዝሙረ ዳዊትንና ሌሎች መዝሙሮችን፣ በተለይም ራሱ የቀመረውን ‹‹ አምላክ ገዥ ነው ›› የተሰኝውን መዝሙር እያዜሙ የንጉሱን መኖሪያ ቤት ጸበል ሲረጩ ያድራሉ ይውላሉ፡፡

አስማትን በመፍራት ከቅጥር ግቢው ውስጥ አንድ ትልቅ ጉድጓድ አስቆፍሮ፣ የግቢው ነዋሪ ሁሉ ባለማቋረጥ ጸበል እያመጣ እንዲሞላው ያደርግ ነበር፡፡ ይህ ውሃ ከአስማት ይጠብቃል፣ ከደዌ ይፈውሳል ተብሎ የሚታመን ሲሆን ስርዓተ ጥምቀቱም ይፈጸምበታል፡፡

የኢትዮጽያ ታሪክ  / ትርጉም ዓለማየሁ አበበ /

Sunday, April 15, 2012

‎የቆሰለ ስሜት‎

ሰሞኑን ፌስ ቡክ ላይ ያነበብኩት የደመወዝ ጭማሪ ቀልድ ብብቴን በሃይል በመኮርኮሩ ‹‹ ስቄያለሁ ›› ማለት ብቻ አይገልጸውም፡፡ የዚህ ቃል ሱፐርላቲቭ ዲግሪ ምን ይሆን ? አዋ ‹‹ በእጅጉ ተንፈቅፍቄያለሁ! ››

 ‹‹ ጤፍ 1780 ብር በደረሰበት በአሁኑ ወቅት መንግስት እንዴት 73 ብር ብቻ ይጨምራል ? ›› ይለዋል አንዱ ጨጎራው የቆሰለ
 ‹‹ መንግስት ደመወዝ የጨመረው ለጤፍ መግዣ እኮ አይደለም ›› ሌላኛው ቁስለኛ በማሾፍ መልክ ይመልሳል
 ‹‹ እናስ ለምንድነው የጨመረው ? ››
 ‹‹ ለጤፍ መግዣ ሳይሆን ለጤፍ ማስፈጫ ነው ››

መራር ቀልድ ቢሆንም ህይወትን ለማጣፈጥ መሳቅ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ቀልድ በመምህራን ቆዳና ጅማት የተሰራ ይምሰል እንጂ የሁላችንንም አዳርና ውሎ ይመለከታል፡፡ እንደውም እንደዚህ አይነት ጉዳዮች በማይታይ ቁጥርና ማህተም ከመዝገብ ቤት የሚወጡት ‹‹ ለሚመለከተው ሁሉ ! ›› በሚል ርዕስ ይመስለኛል፡፡

ነገሩ ወደው አይስቁ አይነት ነውና እንስቃለን፡፡ ግን ደግሞ ከአፍታ በኋላ እንቆዝማለን፡፡ የተወራውና የሆነውን እያነጻጸርን እንበሽቃለን፡፡ ውሃ በገመድ እንደሚወጣበት ግድጓድ ርቀን ከቆምንበት ሸለቆ ውስጥ፤ ኑሮ ተንደላቆ ወደተኛበት የዳሽን ተራራ አንጋጠን ለማየት እንሞክራለን፡፡ ጨረሩ፣ የሸረሪት ድሩም ሆነ የህይወት ዳመናው ርቀቱን ሲጋርደን ደግሞ ነገር አለሙ ይጨልምብናል፡፡ ያኔ በታችኛው ከንፈር ፈጣሪን በላይኛው ከንፈር መንግስትን እንራገማለን፡፡

የነበረን ተስፋ ካሉብን መቶ ያህል የችግር ቀዳዳዋች ውስጥ አስር ያህሉን እንኳን መድፈን ካልቻለ ስሜታችንን፣ ቁጣችንና ትዕግስታችንን እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ? እናም ተድላን ሳይሆን ያለመራብ ሚዛንን የእምነት ያህል በአስተማማኝ መልኩ አንገታችን ላይ ማንጠልጠል ካልቻልን እንዴት አንሰጋም ? ለምን አያመንም ?

የሰሞኑን የመምህራን ስሜት በዚሁ አግባብ ማየት ያለብን ይመስለኛል፡፡ ሙያው የሚገባውን ሳይሆን ኑሮ ውድነትን ለማሸነፍ ይቻል ዘንድ ጭማሪ ጠየቁ፡፡ ጭማሪው ተፈቀደ፣ መጠኑና ወደፊት የሚራመዱበት መሰላል ጭምር ተገለጸ፡፡ የስኬል ማሻሻያውን ለግዜው ትተን የደመወዝ ጭማሪው ግን ግልጽ ነበር፡፡ አንድ አዲስ ነገር ብቅ ባለ ቁጥር ከበሮን በጣም የሚደልቁ ቡድኖች ሁሌም አሉ፡፡ ከበሮው ‹‹ የመምህራን ህይወት ተሻሻለ፣ መምህር አለፈለት! ›› የሚሉ ድምጾችን አስተጋባ፡፡ ከበሮ ሲያዩት ያምር ሲይዙት ያደናግር ነውና በትክክለኛው ሰው መዳፍና ጣቶች ባለመዳበሱ ቅኝቱን ጠብቆ መጓዝ አልቻለም፡፡ እናም ምቾት ነሳ፣ ቁጣን አስነሳ፡፡

ጭማሪው ‹‹ እንደ ጤፍ ማስፈጫ ማነሱ ሳይቀር በስማችን ተነገደበት አሉ፡፡ አንዳንዶቹም ተደፍረናል! ክብራችንና ለሰው ልጆች የምንሰጠው አገልግሎት ተንኳሷል ›› ነበር ያሉት፡፡ የከበሮው ድምጽ ግን ይገርማል፡፡ በዲያቆንና በቄሶች እጅ ሲመታ እንዴት ነበር ከፈጣሪ ጋር የሚቀራረበው ? በማርሽ ባንዶች ነፍስ ያላወቀች ብትር ሲኮረኮር እንዴት ነበር ስሜትን የሚፈነቅለው ? በኦርኬስትራ ቡድን ውስጥ ‹ ክሽ ክሽ › ከሚል ድምጽ ጋር ተዋህዶ ሲሰማ እንዴት ነበር ህብረ- ዜማውን የሚያራምደው ? ለካስ የከበሮ ድምጽ አንዳንዴ ያስጠላል ? ለካስ ከበሮ ሙያና እውነትን ካልያዘ ከሚንከባለል በርሜል አይሻልም ? ለካስ የከበሮ ድምጽ እንደ መብረቅ ያሸብራል ? ለካስ ከበሮ ጡሩንባና ቱሪናፋ! ከሚባሉ ስድቦች ጋርም የዝምድና ሀረግ አለው፡፡
አዋ! ለአነስተኛው ጭማሪ የደስታ መግለጫም ሆነ ማጣፈጫ አንድ ሆኖ ወፍራም ድምጽ የሚያወጣውን ከበሮ ከመምረጥ ይልቅ ፤ ብዙ ሆነው ስስ ድምጽን ሊያመርቱ የሚችሉ መሳሪያዋችን መጠቀም ይሻል እንደነበር ይሰማኛል፡፡ ይህን ድምጽ ‹ ክላሲካል › ወይም ለስላሳ ሙዚቃ ማለት እንችላለን፡፡ ያለ ምንም ጩኅት ረጋ ብሎ መልእክትን ያስተላልፋል፡፡ በርግጥ መልእክቱ አሳዛኝም ሆነ አስደሳች ሊሆን ይችላል፡፡

ግን በጥሞና ሰምቶ የተናደደ ሰው እንኳ መፍትሄውንም በጥሞና እንዲያስብ ሊያደርግ ይችላል፡፡ የክላሲካል ተምሳሌነቱ ብዙ ነው፡፡ መንግስት የጭማሪውን ዜና በፓስታ አሽጎ ከሆነ አጽናኝ ጽሁፍ ጋር ለመምህራኑ በየአድራሻቸው ቢሰጥ በመጀመሪያ ጨዋነቱንና አክብሮቱን ሊያንጸባርቅ ይችላል፡፡ ሰዋች በተፈጥሮአቸው ክብርና ሞገስ ስለሚፈልጉ የብሩ ማነስ ሳይሆን የመንግስት ትህትና አሸንፏቸው ለሁለመናቸው ልጓም ያዘጋጃሉ፡፡ ነገሮች ሁሉ የጉዟቸውን ሃዲድ የሚይዙት ከግራና ቀኝ፣ ከፊትና ኋላ ምልከታና ውሳኔ በኋላ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ ሰላምና መረጋጋት ብሎም መልካም አስተዳደርን ለማሳደግ የማይናቅ ሚና ይጫወታል፡፡ ርግጥ ፓለቲካው ይህን ለማድረግ አቅም ወይም የተዘረጋ ስርዓት አለው ወይ ? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ቀላል አይደለም፡፡

የክላሲካሉ ሙዚቃ ሌላ ጥቅም ዛሬ በርካታ መምህራን ያሰጋቸውን ፍርሃት መቀነሱ ነው፡፡ ዛሬ ‹ ደመወዝ ተጨመረ! › የሚለውን ወሬ የሰማ ነጋዴ ወይም ቤት አከራይ በማግስቱ ከበሮውን የሚደልቀው ሰቅጣጭ በሆነ መልኩ መሆኑን ከልምድ እናውቃለን፡፡ ቢያንስ ጤፍ ላይ 400፣ የቤት ኪራይ ላይ 100 ብር ቢጨመር ውጤቱ ምን ይሆናል ? አሁን በተጨመረው ገንዘብ ላይ ሌላ ፐርሰንት ጨምሮ መስጠት ፡፡ ላለው ይጨመራል - ይላል መጽሀፉ ፤ የሌለው ከነገም ህይወቱ ተበድሮም ቢሆን ይከፍላል - መጽሀፉ ባይልም ግዴታው ይኅው ነው ፡፡ እንግዲህ ‹‹ ግፍ ›› በህግ ሌላ ትርጉም ካልተሰጠው በስተቀር ከዚህ የተሻለ ትርጉም ሊመጣለት አይችልም፡፡ መንግስት እነዚህን ግፎች መከላከል ያለበት ሰዶ- በማሳደድ ሳይሆን አስቀድሞ ብልጥ በመሆን ነው፡፡ ለድሃ አጋር የሆኑ ስልቶችን በመንደፍ ፡፡

በጥንታዊ ግሪክ፣ ቻይናና ህንድ ትምህርት የሚካሄደው በቄሶችና በአዋቂዋች ነበር፡፡ በጥንት ግሪክ የኪነጥበብ፣ ፓለቲካና ፍልስፍና ጉዳዬች ከፍተኛ ቦታ ስለነበራቸው ለልጆች ለማስተላለፍ ልዩ ጥረት ተደርጓል፡፡ በጥልቅ ፍልስፍናቸው የምናውቃቸው እነ ቴልስ፣ አናክስማንደር፣ ፓይታጎረስ፣ ሶቅራጥስ፣ ፕሌቶ፣ አሪስቶትል አንቱ የተባሉት በሚያነሱት ሀሳቦችና በሚፈጥሩአቸው አዳዲስ ነገሮች ብቻ ሳይሆን ከሊቅ እሰከ ደቂቅ በማስተማራቸው ነበር፡፡

በአሁኑ ወቅትም በቻይና፣ ታይዋን፣ ዴንማርክ፣ ጀርመን፣ ጃፓን፣ ኔዘርላንድ፣ ስዊዘርላንድ፣ ኮሪያ፣ አሜሪካ፣ ደ/አፍሪካ በመሳሰሉ ሀገሮች መምህራን ምርጥ ተከፋይ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህል በጃፓን የተራ መምህራን እርከን 36 ደረጃ አለው፡፡ ሁለተኛው እርከን ላይ የሚገኝ መምህር በወር 156 ሺህ 500 የን የሚያገኝ ሲሆን የመጨረሻው እርከን 455 ሺህ 900 ይደርሳል፡፡ ለመሪ መምህር 26 ለዳይሬክተር ደግሞ 15 እርከን የተፈቀደ ሲሆን እንደቅደም ተከተላቸው 488 ሺህ 400 እና 516 ሺህ 200 የን ያገኛሉ፡፡ በአውስትራሊያ አራት ዓመት የሰለጠነ መምህር በአመት 41 ሺህ 109 ዶላር ሲያገኝ የመጨረሻው ደረጃ ላይ ሲደርስ 58 ሺህ 692 ዶላር ያገኛል፡፡ ዳይሬክተሩ እስከ 95 ሺህ 106 ዶላር ይከፈለዋል፡፡

በደቡብ አፍሪካ አምስት ዓመት ልምድ ያለው መምህር 115 ሺህ 276 ራንድ ሲያገኝ ከ5 – 9 ዓመት ልምድ ካለው 146 ሺህ 087 ይደርሳል፡፡ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የሚገኝ አንድ የአሜሪካ መምህር 43 ሺህ 695 ዶላር ነው በዓመት የሚያገኝው፡፡ ይህን ሂሳብ ወደ እኛ ብንቀይረው በወር 61 ሺህ 901 ብር አካባቢ ይመጣል፡፡ የአፍሪካ ሀገሮች አሀዝ ከዚህ ይነስ እንጂ የሚያበረታታ ነው፡፡ ይህም መንግስት የሰጠውን ቦታ የሚያመላክት ሲሆን በኢኮኖሚ የደረጀ መምህር በራሱ የሚተማመንና ምርታማ ዜጋ እንዲሆን የሚያስችል ነው፡፡ በእኛ እውነታ የእድገታችን ነገር ላይፈቅደው ይችላል….
የሀገራችን መምህራን ግን እንደስራቸው ተመጣጣኝ ተከፋይ አይደሉም፡፡ የኢኮኖሚ አቅማቸው ለንቋሳ በመሆኑ ደግሞ ለብዙ ችግሮች ተጋላጭ ናቸው፡፡ በሀገራችን በጋዜጠኝነትና በህዝብ ግንኙነት ሙያ ላይ የተሰማሩ ሰዋችን የኋላ ታሪክ ስናጠና የምናውቀው አብዛኛው መምህራን የነበሩ መሆናቸውን ነው፡፡ ለምን ሙያውን ቀየሩ ? ለሚለው ጥያቄ ቀድሞ የሚመጣው ምላሽ በህብረተሰቡም ሆነ በተማሪው ተፈላጊውን አክብሮት ባለመግኝታቸው ነው፡፡

አንዳንድ ተማሪ አስፈራርቶ ዘርቶ ያላጨደውን ማርክ ይቀበላቸዋል፡፡ ወር የማያደርሳቸውን ደመወዝ በማስላት ፍላጎቱን ይገዛቸዋል፡፡ ጎጃምና ሌሎች ከተሞች ብትሄዱ ተማሪና አስተማሪ እኩል እየተሳፈጡ ጠላ ይጠጣሉ፡፡ በብዙ ከተሞች ተማሪዋች አሰተማሪያቸውን ድራፍትም ሆነ ጫት ይጋብዛሉ፡፡

በአ/አበባና ትላልቅ ከተሞች ተማሪው ከመምህሩ የተሻለ ሞባይል፣ የተሻለ ላፕቶፕ፣ የተሻለ አልባሳት አለው፡፡ ሞባይላቸውን ክፍል ውስጥ እንዲዘጉ ለተማሪዋች የተናገሩ መምህራን ‹‹ እናንተ ስለሌላችሁ ነው! ›› ተብለው ተስቆባቸዋል፡፡ ጭንቅላቱን ሳይሆን ኪሱ በፈጠረበት የአቅም ችግር ሊሰደብ፣ ተገቢ ያልሆነ አግቦ ሊደርስበት ይችላል፡፡ ይህም በራስ መተማመኑ እንዲሸረሸር ያደርገዋል ፤ ይሸማቀቃል፡፡ ሌላ ምሳሌ ልጨምር፡፡ አንድ ጎረምሳ አንዲት ወጣት ሰሌዳውን ካጠፋች በኋላ ከንፈሯን ይስማል፡፡ አስተማሪ ከሆናችሁ

‹‹ ምን እያደረክ ነው አንተ?! ›› ማለታችሁ በጣም የግድ ነው
‹‹ ቾኩን እየጠረኩላት ! ›› ጎረምሳው ሳይጨነቅ ይመልሳል
‹‹ በእጅህ አትጠርግም እንዴ ታዲያ ?! ›› ንዴቶት ጨምሯል
‹‹ አይ ቲቸር እጅ እጅ እንዳይል ብዬ ነው! ››

ይህ ምላሽ ያስቅዋታል ወይስ ያበሽቅዋታል፡፡ አሁንም ወደው አይስቁ ማለታችን አይቀርም፡፡ ክፍለግዜው የቲያትር ቢሆን ይህ ምላሽ ባልገረመ ነበር፡፡ ግን መምህር ፊት በድፍረት ብዙ ነገር ይደረጋል፡፡ መምህር የሚያስተምረው ቀለምን ብቻ ሳይሆን ስነ ምግባርን ነው፡፡ በጉዳዩም ይጨቃጨቃል፤ ይሰደባል፤ ይመታል፡፡ እናም ሁልግዜ ስራውን ሳይሆን ከኋላ የሚሰለፉ አላስፈላጊ ጉዳዬች ላይ እንዲያተኩር ያደርገዋል፡፡ ደረጃ በደረጃም ሙያውንና ራሱን መጥላትና ሃላፊነቱን በአግባቡ አለመወጣት ይከተላል፡፡

ታዲያ የትምህርት ጥራት እንዴት ይፈጠራል ? የነገ ሀገር ተረካቢው ትውልድ ምግባርና ብቃት እንዴት ይረጋገጣል ? እናም የመምህራንን ክብርና አቅም አንድም ለተገቢነቱ በጣም ቢያንስ ግን ለልጆቻችንና ለነገው ዜጋ ስንል እናሰድግ፤ እናለምልም፡፡

‎‹‹ ምግብ ለስራ ››‎



የሌለኝን የ IT ግንዛቤ ወደ አንድ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እነሆ ደብረዘይት ከከተምኩ አስር ቀናት ሆኑኝ፡፡ ጓደኞቼ ሲደውሉልኝ ስራ አመራር ኢንስቲትዩት እንዳለሁ እገልጽ ነበር፡፡

‹‹ እህ ምግብ ለስራ ነሃ! ›› ነበር ቀጣይ ምላሻቸው
ይህን ስያሜ እንዴት ሳልሰማሁ ቀረሁ በሚል ተገረምኩ፡፡ ‹‹ ምግብ ለስራ ›› እና ‹‹ ስራ ለምግብ ›› የሚባሉ ቋንቋዋችን የማውቅበት መልኩ ሌላ ነበር፡፡

መቼም ለምቾት ሩብ ጉዳይ የቀረውን ይህን ግቢ ይህን ስያሜ ማሸከም ጡር ሳይሆን አይቀርም፡፡ ግቢው በሚያምሩ ዘንባባዋች፣ የተለያዩ የደን እጽዋትና ለአይን ማራኪ በሆኑ አበባዋች የተሞላ ነው፡፡ እነዚህ ደኖች ላይ በልጅነቴ ሳድን የነበርኳቸው ፒተር፣ ዋሽንት፣ ፍላይ ካውቸር፣ ግንደ ቆርቁር፣ ቀሳሚና ቢጮሌ የምንላቸው ወፎች ጣእመ ዜማቸውን እስከምሽቱ ድረስ ይለግሳሉ፡፡ ርግጠኛ ነኝ እንደ እኔ ስራዬ ብሎ የሚያጣጥማቸው ሰው የለም፡፡ ዘወትር ውሃ የሚረጩት ጎማዋች የሳሩ ገላ ትንቡኬ እንዲሆን አድርገውታል፡፡ ምናለፋችሁ ግቢው እንደ ህጻን ገላ የለሰለሰ፣ ሌላው ቀርቶ ልክ እንደ ህጻን ልጅ ዘወትር ሲስቅ የሚሰማ ነው፡፡

77 ደብልና 67 ሲንግል አልጋ የያዙ የሚያምሩ ቤቶችን ይዟል፡፡ በርካታ መማሪያ ክፍሎች፣ መሰብሰቢያ አዳራሾችና መወያያ ክፍሎች አሉት፡፡ ኮምፒውተርና አያሌ መጻህፍትን ያቀፈ ቤተ መጻህፍት፣ ሽንጠ ረጃጅም የምግብና የመዝናኛ አዳራሾች ከህንጻው ቁጥር ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡

የመዝናኛ ነገር ከተነሳ የቅርጫት ኳስ፣ የእጅ ኳሰና የቴኒስ መጫወቻ ሜዳዋች በሚያምሩ ጽዶችና ሳሮች ታጅበው ይቀበልዋታል፡፡ የኮኔክሽን ጉዳይ ገባ - ወጣ የማለት ችግር ቢኖርበትም ቤተመጻኅፍት ቁጭ ብለው ከኢንተርኔት ጋር ያወጋሉ፡፡ላፕቶፕ ከያዙ ደግሞ የተወሰነው የግቢ ክፍል ጋር ተሰይመው በገመድ አልባው ግንኙነት ሩቅ የሚገኝውን ሰርቨር መረጃ አንጣ በማለት ይኮረኩሩታል፡፡

ታዲያ የግቢው እድሜ ቀላል እንዳይመስሎት!! በተመድ የልማት ድርጅት ድጋፍ በ1949 አም ነው የተቋቋመው፡፡ በወቅቱ የተሰጠው ስም ፐብሊክ አድሚንስትሬሽን ኢንስቲትዬት የሚል ነበር፡፡ ‹‹ ስምን መልአክ ያወጣዋል ›› የሚል አባባል ነበር የማውቀው፡፡ ይህን ግቢ ሰይጣን ተተናኩሎት ነው መሰለኝ ከሃትሪክ በላይ አራት ግዜ ስሙን ፐዋውዞታል፡፡

በ1961 - የስራ አስኪያጆች ማሰልጠኛ ማእከል ተባለ
በ1962- የመርሀ ሙያ ማሻሻያና መመዘኛ ማእከል እንደሚገባው ተነገረው
በ1968- የስራ አመራር ማሰልጠኛ መካነ ጥናት እንደሚሻለው ተገለጸለት
ከ1977 በኋላ ደግሞ- የኢትዬጽያ ስራ አመራር ኢንስቲትዩት ተብሏል፡፡ በነዚህ ጊዜያት ሁሉ ተጠሪነቱና አላማው ለየቅል ነበር፡፡ አሁን ግን በአጭሩ ምርምር፣ ምክርና ስልጠናን በስፋት እየሰራበት ነው፡፡ የመ/ቤትዋን በጀት ይጭነቀው እንጂ ከሚሰጡት 51 አይነት አጫጭር ስልጠናዋች የፈለጉትን መውሰድ ይችላሉ፡፡

እና እላችኋለሁ ለምሳ 84፣ ለእራት 84፣ ለቁርስ 50፣ በቀን ሁለት ጊዜ ቡናና ሻይ 65 ፣ ለአልጋ 100 ብር ከተመደበ ሲበሉ መዋል ነው፡፡ ለካስ ምድረ ቀጭንና ወፍራም ባስስልጣን እንደ ቀስት እየተወረወረ ይህን ግቢ የሚወረው ለዚህ ነው - ወይ አለማወቅ ደጉ፡፡ መቼም የቡፌ አቀራረባቸው የሚታማ አይደለም፡፡ በሻይ ሰዓት የሚቀርቡ ኩኪሶች ራሱ ራሳቸውን የቻሉ ምሳና ራት መሆን የሚችሉ ናቸው፡፡ እዚህ ግቢ ከመጣው ጀምሮ የኑሮም ሆነ የኢኮኖሚ ኢንፍሌሽንና ዲፍሌሽን ትዝ ብለውኝ አያውቁም ፡፡ ‹‹  ሆድ ፕላስቲኩ! ከአምስት ቀናት በኋላ ደግሞ እንደ አሪፍ ፓለቲከኛ ሽብልል ብለህ ወደ ቀድሞህ ይዞታህ መመለስን ትችልበታለህ ›› ስል ወቀሳ ቢጤ አቀረብኩለት፡፡

 የመንግስት ሰራተኛው ይህን ምርጥ ግቢ ‹‹ ምግብ ለስራ ›› ሲል የሰየመው እንድም ወቅታዊ የምግብ ጥያቄን ስለሚያስረሳ በሌላ በኩል ደግሞ ወደዚህ ስልጠና የተላከ ሰራተኛ የኪስ አበል ስለማያገኝ ነው ፡፡ የሞላውን ሆድ በቢራ ለመሸርሸር አይቻልም ማለት ነው፡፡

ኢንፍሌሽን በየት ዞሮ መጣ !!! እንደ ቀስት ተወርውሬ አመልጠው ይሆን ??

‎‹‹ አንደኛው ዝሆን ››‎





ሰሞኑን ጎን ለጎን ሳነባቸው ከነበሩት መጽሀፍት መካካል ሁለቱን አጠናቀቅኩ፡፡ የአቶ ስዬ አብርሃ እና የዶ/ር ያእቆብ ሃይለማርያምን፡፡ የአቶ ስዬ መጽሀፍ ‹‹ ነጻነት እና ዳኝነት በኢትዮጽያ ›› ይሰኛል ርእሱ፡፡ ባለ 440 ገጽ ሲሆን ዋጋው 70 ብር ነው፡፡

አቶ ስዬ ከፍተኛ የመንግስት አመራር ከመሆናቸው ውጪ የተዘረዘረ ስብዕናቸውን / የአንድ ወገን መረጃ ቢሆንም / በከፊል እንዳውቅ ያደረጉኝ የተስፋዬ ገ/አብ መጽሀፍት ናቸው፡፡ በተለይም በደራሲው ማስታወሻ ላይ ‹‹ ሁለቱ ዝሆኖች ›› በሚል ርዕስ በቀረበው ጽሁፍ፡፡

በጽሁፉ ላይ አቶ ስዬ ወይም ‹‹ አንደኛው ዝሆን ›› ለስልጣን የሚተጉ፣ ጠብ አፍቃሪ፣ የህክምናን ሙያን በከፊል ያጠኑ፣ ዲፕሎማሲ የማያውቁ፣ ተቆጪ፣ ሰውን የሚንቁ፣ ወታደራዊ ብቃት ያላቸው፣ ለይቅርታ የራቁ፣ በምንወደው የቶም ኤንድ ጄሪ ፊልም ላይ እንደ ቶም የተወከሉ መሆናቸውን እናነባለን፡፡

ይህ መነሻ የሚሰጠው አንድ ደራሲ ምናልባት ጥቂት ለየት ያሉ ነገሮችን ጨማምሮበት በአንድ መጽሀፍ ወይም ቴአትር ውስጥ አሪፍ ገጸባህሪ መሳል ይችላል፡፡ እንግዲህ እኔም ይህን ቀመር እያስታወስኩ ነበር ከላይ የተጠቀሰውን መጽሀፍ ማንበብ የጀመርኩት፡፡

በኮሌጅ ቆይታ ወቅት የመጽሀፉን አጠቃላይ ጭብጥ በአንድ ወይም ሁለት መስመር አስረዳ ? የምትል ጥያቄ እንጠየቅ ነበር፡፡ ይህን ጥያቄ አሁን ተውሼ የአቶ ስዬን መጽሀፍ ባስረዳ ‹‹ እኔ የታሰርኩት በሙስና ሳይሆን ከጠ/ሚ/ር መለስ ጋር በነበረኝ የፓለቲካ መስመር ልዬነት ነው፡፡ ፍ/ቤቱም ሙሰኛ መሆኔን በበቂ ሁኔታ ሊያሳይ አይችልም ›› የሚል መልእክት እናገኛለን፡፡
በርግጥ ይህ ቱባ መልእክት የተገኘው በየምዕራፉ ሀሳቡን ለማዳበር በተጠነጠኑ ቀጫጭን ድውሮች ድምርነት ነው፡፡ አቶ  ስዬ በየምእራፉ ሰለማስረጃ፣ መቃወሚያ መግለጫ፣ የመከላከያ ማስረጃ፣ የሰነድ ማስረጃ፣ የሰዋች ምስክርነትና የቅጣት ውሳኔ አካሄድ ደረጃ በደረጃ ለማሳየት ሞክረዋል፡፡

ወታደራዊ ስብዕናው ጎልቶ ከሚነገርለት አንድ ሰው ይህ መጽሀፍ መመረቱ ያስገርማል፡፡ የሚገርመው አንድም ያልተጠበቀ በመሆኑ ሲሆን በዋናነት ግን መጽሀፉን ጅማት ሆነው ሊያቆሙት የቻሉት እውነታዋች ናቸው፡፡ እነዚህ እውነታዋች የአቶ ስዬ የማስታወስ ብቃት፣ ማስታወሻ የመያዝና መረጃዋችን ስብስቦ እንዳግባቡ የመስፋት፣ ለህግ ያላቸው ግንዛቤ የማይናቅ መሆኑና ብዙም ሊታማ የማይችለው የትረካ አቀራረባቸው በግልጽ መታየታቸው ናቸው፡፡

ዝሆን እጅግ አደገኛ በሆኑት አንበሳና አዞ ፊት እንኳ የተለየ ድፍረት የሚያሳይ እንሰሳ ነው፡፡ የራበው አዞም ሆነ አንበሳ ግን አዘናግቶና ልዬ ስልት ተጠቅሞ ገቢ ሊያደርገው ይችላል፡፡ አቶ ስዬ የሚያስቡትን ሁሉ ያለ ፍርሃት ይናገራሉ፡፡ በፍ/ቤት ከዋናው ርዕስ በመውጣት የፓለቲካ ጉዳዬች ሲናገሩ በዳኞች በተደጋጋሚ እየተገሰጹ ያስቆሟቸው እንደነበር እናነባለን - በርግጥም እኔም በአንድ የግል ጋዜጣ ውስጥ ስሰራና ጉዳዩን ለመዘገብ ስከታተል ይህን አይቻለሁ፡፡

ከድፍረቱ በተጨማሪ እንደ ቶም ሳይሆን እንደ ጄሪ ብልጠት የተላበሰ የአዳኝ - ታዳኝ ስልት ይከተሉ ነበር፡፡ ለአብነት ያህል በፍ/ቤት ባገኙት የመናገር አጋጣሚ  ክሱ የፓለቲካ መሆኑን ሳይጠቁሙ አያልፉም፡፡ ጎን ለጎን ግን የሚቀርብባቸውን የተለያዬ ክሶች ሁሉ  በሰውና በጽሁፍ ማስረጃዋች ለመከላከል ከፍተኛ ትግል ሲያካሄዱ ይታያል፡፡ ጉዳዩ የፓለቲካ ከሆነ ያለቀለት በመሆኑ መልፋት ላይስፈልግ ይችላልና፡፡

አቶ ስዬ በመጽሀፋቸው ደጋግመው ሲያደንቁት የተሰማ ተቋምም አለ፡፡ እንደውም ‹‹ መተኪያ የሌላቸው ተቋማት ›› በማለት ነው የግሉን ፕሬስ ሚና የገለጹት፡፡ ምናልባትም ቀድሞ ከነበራቸው አመለካከት አንጻር የሚፈተሸ ከሆነ ወደ ‹ ይቅርባይነት › ወይም ‹ አድናቂነት › ተሸጋግረዋል ማለት ነው፡፡ በርግጥ ወደዚህ አቅጣጫ ለማምራት የሚያስችሉ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ተጽእኖዋች መኖራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡

ከዋና ጉዳያቸው ጎን ለጎን ስለዳኝነትና ፓሊስ አሰራር፣ ስለፍትህ መጎደል፣ ስለምርጫ ቦርድ ነገር፣ ስለእስረኞች አያያዝ፣ ስለ ምርጫ 97 አንድምታዋች፣ ህወሃትን ጨምሮ ስለ ፓለቲካ ድርጅቶች ድክመትና ጥንካሬ ቀደም ብሎ በተገለጸው ‹‹ ዝሆናዊ ›› መንገድ እምነታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጥቅሉ ወንድ ልጅ ሀዘናዊ ስሜትን ደብቆ መያዝ ይችላል ይባላል፡፡ በተናጥል ስናይ ደግሞ ፓለቲከኞችና ወታደሮች ልበ ደንዳኖች እንደሆኑ ይታመናል፡፡ ለሞትና ለሌሎች ውጣ ውረዶች ቅርብ በመሆናቸውና ጉዳዩን በመለማመዳቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ሀሳብ ግን ሁልግዜ ትክክል አይደለም፡፡ ለምሳሌ አቶ ታምራት ላይኔ ከእስር ከተፈቱ በኋላ በአንድ የእምነት አዳራሽ ተገኝተው ስለ ፈጣሪ ቃል ያስተምሩ ነበር፡፡ ቪዲዮውን የተመለከትኩ ግዜ እጅግ ብዙ ነገሮች አስገርመውኝ ነበር፡፡ የገረመኝ ሰሜን ዋልታ ይገኝ የነበረ አንድ አለማዊ ፓለቲከኛ በምንም ወደ ማይዋሰነው ሃይማኖታዊ የደቡብ ጫፍ የመምጣቱ ገዳይ አልነበረም፡፡ የገረመኝ የአቶ ታምራት ምላስና እንባ ጣፋጭ መሆናቸው ነበር፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል የሚሰብከው አንደበታቸውና በተወሰነ ርቀት ከአይናቸው የሚወርደው መጠነ ሰፊ እንባ በእጅጉ የተናበቡ ነበር የሚመስሉት፡፡ ንግግራቸው የትምክህትን ኮፍያ ያወለቀ ነበር፡፡ አንደበታቸው  ይቅርታን ወደ ነፍሳቸው ለማስገባት የሚካድም ነበር፡፡ አንደበታቸው ታላቅ ‹ ፈጣሪ › መሆኑን፣ በምድር ላይም የሰው ታላቅ ካለ  በ ‹ግዜ › ድጋፍ የቆመ ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ነበር፡፡ እናም ይህን አንደበታቸውን ሲያስፈልግ በጥያቄ ምልክት፣ ሲያስፈልግ በቃለ አጋኖ፣ ሲያስፈልግ በትምህርተ ጥቅስ፣ ሲያስፈልግ እንደ አራት ነጥብ ሆኖ ሲያስረዳ የነበረው እንባቸው ነበር፡፡ በቃ ! ስሜት የሚንጥ ንግግር ሰፈልቅ….የሌሎችን ስሜት የሚያሸብር እንባ ይከተላል ፤ እስከማስታውሰው ድረስ ፍሰቱ እንዲህ ነበር፡፡ አቤት እንዴት ነበር የሚወርደው ? የወንድ ልጅ ለዚያውም የፓለቲከኛ፣ ለዚያውም የወታደር…

በአቶ ስዬ መጽሀፍ ውስጥ ግልጽ እንባ ባይታይም ለቤተሰባቸው ያለቸውን ጥልቅ ፍቅርና ስስ ነፍስ እንመለከታለን፡፡ እሳቸው እስር ቤት ገብተው ሲጨነቁ የሚታዩት ለወንድሞቻቸውና ለእህታቸው ነበር፡፡ምን ሆነው ይሆን ? በማለት ብዙ ይቆዝማሉ፡፡ ለእናታቸው የነበራቸው ስስትና ፍቅር ደግሞ የተለየ ይመስላል፡፡ በልጆቹ የእስር ምክንያት ህይወታቸው አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ስጋታቸውን፣ ፍርሃታቸውን፣ የውስጥ ጩኅታቸውን ሳይቀር በእንባ ሳይሆን በቃላት በመግለጽ ለአንባቢ ሲያጋቡት ይታያል፡፡
በአቶ ስዬ መጽሀፍ ውስጥ ያልታየ ጉዳይ አለ ከተባለ አውቀውም ሆነ በስራ ስህተት ምክንያት ያጠፉትን ወይም ካነሱት ትልቅ ርእስ አንጻር የእሳቸውን  አሉታዊ አስተዋጽኦ አለመጠቆማቸው ነው፡፡

በማጠቃለያ ምዕራፍ ያቀረቧቸው ሀሳቦች የተነሱበትን የዳኝነት ነጻነት /ነጻነትና ዳኝነት የሚለው የእሳቸው ርዕስ በተለይም ነጻነት ሰፊ ሃሳብ በመሆኑ ለኔ አልተመቸኝም / መርሆዋች እውን ለማድረግ የምሶሶ ያህል የሚጠቅሙ ናቸው፡፡ ችግሩ እነዚህን ጸጋዋች እንዴትና በነማን እናግኝ የሚለው ነው፡፡በቅድሚያ እነማን መስዋእትነት ይክፈሉ ነው፡፡ ቢፒአር የተማሩ ትናንሽና ትላልቅ መሪዋችም በሙሉ የሚከተለውን የሃሪ ትሩማን ጥቅስ ሰምተውታል  << A leader is a person who knows the road, who can keep a head, and who can pull others after him. >>

በርግጥ ይህን መሰረታዊ መመሪያ ለማስፈጸም ብዙ፣ ምናበ ሰፊና ሰላማዊ ዝሆኖች ያስፈልጉናል፡፡




‎ዳንዲ የነጋሶ መንገድ‎



‹ዳንዲ የነጋሶ መንገድ›› በዳንኤል ተፈራ የተዘጋጀ ፣በዶክተር ነጋሶ ህይወት ዙሪያ የሚያጠነጥን ፓለቲካ ቀመስ መጽሀፍ ነው፡፡ በመጽሀፉ ትረካ መሰረት የምናስብ ከሆነ ዶክተሩ ምስኪን ወይም ታማኝ ፓለቲከኛ መስለው ይታዩናል፡፡ በርግጥ ታማኝነት እንዴትና ለማን የሚሉ መሰረታዊ ጥቄዋችን መመለስ ይኖርብናል፡፡ ዶክተሩ በፍጹም ብልጣብልጥ አይደሉም፣ ዲፕሎማት አይደሉም፣ ብዙ ግዜ ፓለቲካ የሚጠይቀውን አስመሳይነት፣ ፈጣጣነት፣ ዋሾነትና ጨካኝነት ዕውን የሚያደርግ ነፍስ የላቸውም፡፡ ታዲያ እንዴት ፓለቲከኛ ሆኑ? ይህን ስራ እንደማይተውም ይናገራሉ- እንዴት ይዘልቁት ይሆን? ለግዜው ቅርብ የሆነው መልስ እንጃ በመሆኑ እንጃ ብያለሁ እኔም፡፡ ለማንኛውም አንዳንድ ሀሳባቸውን እነሆ…….የነጋሶ መንገድ…..

ሲጋራ እንዴት እንደጀመሩ

በእደ ማርያም አዳሪ ትምህርት ቤት ተደራራቢ አልጋ ላይ ተኝተን አለማየሁ ከታች ሆኖ ቫይስሮይውን ሲያቦነው እኔ ከላይ ሆኜ አሸታለሁ፡፡ በኋላ ‹‹ እንካ እስኪ ሞክረው›› ብሎ ይሰጠኝና ስሞክረው ጣመኝ፡፡ በዚያው አጫሽ ሆንኩ፡፡ ‹‹ እንካ አጭስ›› ሲለኝ የነበረው በኋላ ‹‹ እኔ አልሰጥህም እራስህ ግዛና አጭስ›› ማለት ጀመረ፡፡ በኋላ ኒያላ መጣ፡፡ ኒያላ መመረት ከጀመረ አንስቶ ነው ደንበኛ አጫሽ የሆንኩት፡፡ ባለቤቴም ከኒያላ ሌላ አጢሳ አትውቅም

የብሔር ጭቆና አጀማመር

አጼ ምኒሊክ ይከተሉት የነበረው ስርዓት ባላባታዊ ነው፡፡ ይህ ገዥ መደብ የመጣው አማርኛ ተናጋሪ ከሆኑ ህዝቦች ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት የበላይነትን እንዲያገኝ ክርስትያን ያልሆኑትን ሁሉ በግድ ያጠምቁ ነበር፡፡የአስተዳደሩ ቋንቋ አማርኛ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ሌሎች ሃይማኖታቸውን፣ባህላቸውንና ቋንቋቸውን እንዲተው የተደረገበት ሁኔታ ነበር፡፡ በኢትዮጽያ የብሄር ጭቆና የተጀመረው ያን ጊዜ ይመስለኛል፡፡

የተቃውሞ ሰልፍ እንዴት ይበተን ነበር?

ያኔ ተቃውሞን ለመከላከል በጣም ከበዛባቸው አንዳንድ ተማሪዋችን ያስራሉ፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን ከኛ ጋር ግብግብ በመግጠም ወይ በጭስ ነበር የሚበትኑት፡፡ አሁን ግን ተቃዋሚ ሰልፈኞች በጥይት ተቆልተዉ የሚበተኑበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ያውም በዚህ ዘመን…

መንግስት ህዝብን ይፈራ/ያከብር ነበር?!

ዙምባቤ ነጻ ትውጣ በማለት እንግሊዝ ኤምባሲ ፊት ለፊት ተሰለፍን፡፡ ያኔም ከፓሊስ ጋር ተጋጭተናል፡፡ እነዋለልኝን አስረዋቸው ነበር፡፡ እኛ ደግሞ እነዋለልኝ ይፈቱ ብለን ሰልፍ ወጣን፡፡ አፍሰው ወደ ሰንሳፋ ሲወስዱን ኮተቤ ላይ ስንደርስ አንድ ልጅ ከመኪና ላይ ወድቆ ይሞታል፡፡ ወሪው በአዲስ አበባ ይዛመትና ከተማዋ ቀውጢ ሆነች፡፡ ፈርተው በማግስቱ ፈቱን፡፡

ሚሲዮኖች በወለጋ እንዴት በዙ?

ሚሲዮኖች ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሸዋ መጥተው ለመንቀሳቀስ አጼ ሚኒሊክን ፈቃድ እንዲሰጧቸው ሲጠይቋቸው እሳቸውም ‹‹ ሸዋ፣አርሲ፣ሀረርና ጅማ ክርስቲያኖችና እስላሞች ስለሆኑ የሚሲዮን ትምህርት አያስፈልጋቸውም እናንተ መሄድ ያለባችሁ ገና ወዳልሰለጠነውና አሁንም አረመኔ ወደሆነው ጠረፍ አካባቢ ነው አሏቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ወለጋ ሄደው አስተማሩ

የመጀመሪያው የኦሮሞ የትግል እንቅስቃሴ

የኦሮሞን ህዝብ እግዚሀብሄር ከሰማይ መጥቶ አይታደገውም ስለዚህ ራሱ ተደራጅቶ ለመብቱ መታገል አለበት…. የሚል አቋም ይዘን መቀስቀስ አለብን፡፡ ለዚህ ደግሞ ጽሁፎችን ማዘጋጀት ይኖርብናል ብለን ርዕሰ ጉዳይ ተከፋፍለን መጽሔት ለማዘጋጀት በቃን፡፡ መጽሔቱ ‹‹ oromo voice against tyranny›› የሚል ነበር፡፡ በኋላ በአማርኛና በኦሮምኛ ተተርጉማ  ቀርባለች፡፡ የሚያሳዝነው በመጽሔቷ የተነሳ ብዙዋች ለእስር ተዳርገው ነበር፡፡

የመጀመሪያ ፍቅር

በ13 ዓመቴ ከሚዛን ወደ ደምቢዶሎ የተባረርኩት በፍቅር ምክንያት ነው፡፡ ከበቡሽ ሀብት ይመር የምትባል የመንደራችን ልጅ እና እኔ በጣም እንወደድ ነበር፡፡ የ18 ዓመት ልጅ ነበረች፡፡ አቶ ከበደ ጨብራሻ አገባት፡፡ ስታገባ ድንግል አልነበረችም፡፡ ለካ የአካባቢው ሰው ድንግልናዋን የወሰደው ነጋሶ ነው ብለው ያሙኝ ኖሯል፡፡ እኔና አቶ ከበደ ኳስ ሜዳ የተጣላን ጊዜ በዚህ ምክንያት ነው ብለው ሰዋች ለአባቴ ሲነግሯቸው ‹‹ ይሄንን አድርጎ ከሆነ እቀጣዋለሁ›› ብለው ወደ ደምቢዶሎ መለሱኝ፡፡

የመጀመሪያው ትዳር

በ1964 ዓም ክረምት ላይ ደሲቱን አገባሁ፡፡ በዓመቱ በ1965 ኢብሳ ተወለደ፡፡ ኢብሳ ያልንበት ምክንያት ለሁለት ሳምንት ተቋርጦ የነበረው መብራት ልክ እሱ በተወለደ ማታ ስለበራ ነው፡፡ ኢብሳ ማለት ደግሞ የሚያበራ ማለት ነው፡፡ ሁለተኛዋ ልጃችን ጃለሌ ናት…
የኦነግ መቋቋም

እዚህ በነበርኩ ጊዜ አዲሱ፣ ጸጋዬ፣ዮሀንስ፣ለታና ዮሀንስ ኖጎ የሚባሉ የድሮ ጓደኞቼን አግኝቻቸው አወራን፡፡ ማታ ማታ ይጠፋሉ፡፡ ‹‹ ማታ የት ሄዳችሁ?›› ስላቸው ‹‹ ስበሰባ ነበረን›› ይሉኛል፡፡ ለካ ኦነግን እያቋቋሙ ነበር፡፡ እኔን ግን ስብሰባቸው ላይ አይጠሩኝም፡፡ በህብዑ ነበር የሚሰሩት፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ እነ ባሮ ቱምሳ ፣ጄኔራል ታደሰ ብሩ፣ ዲማ ነጋዋ፣ ዮሀንስ ለታ ዮሀንስ ኖጎ እና አዲሱ ቶሎሳ አዲስ ፕሮግራም በማዘጋጀት ስራ ላይ ተጠምደው ነበር፡፡

ታሪክ ሰሪው ሌንጮ

በ1967 ዓም መጀመሪያ ንጉሱ ከተወገዱ በኋላ ሰላማዊ ሰልፍ በተደረገ በሳምንቱ ወደ ጀርመን ሄድኩ፡፡ ሌንጮ/ዮሀንስ ለታ ወደ ጀርመን እሄዳለሁ ብዮው ሲሸኘኝ፣
‹‹ ምን ለመማር ነው የምትሄደው?›› አለኝ
‹‹ ታሪክ››
‹‹ አንተ ሄደህ ታሪክ ተማር፣ እኛ እዚህ ታሪክ እንሰራለን!›› ብሎ አሾፈብኝ

ለዶክትሬትዲግሪ ያቀረቡት የመመረቂያ ጽሁፍ

<<The history of seyyoo oromo of south western wallaga, Ethiopia from 1730 to 1986>>
ዲግሪውን ያገኙት በ1977 ዓም ነው፡፡

የአልማዝ መኮ/የፓለቲከኞች/ ሁለት መልክ

አልማዝ ኦሮሞ ስለሆነች የኦህዴድ አባል እንድትሆን ለማግባባት ሞክሬ ነበር፡፡ እምቢ አለች፡፡ ቆይቶ የኦሮሚያ አስተዳደር ስራ አስፈጻሚዋች፣ የኦሮሚያ ሴቶች ቢሮ ሃላፊ ሆና አየኋት፡፡ ሰኔ 15 ቀን 1993 ዓም እኔ ከኢህአዴግ ስብሰባ በለቀቅኩ ዕለት ታዲያ ለኢህአዴግ ተቆርቋሪ ሆና ‹‹ ነጋሶ ሂሳቡን ሳያወራርድ እንዴት ይወጣል?›› ብላ ትችት ሰነዘረች፡፡ የሚገርመው ይህን ባለች በሳምንቱ ለስብሰባ ወደ ብራዚል ተልካ፣ በኒውዬርክ ስታልፍ እዛው ጥገኝነት ጠይቃ መቅረቷን ሰማን፡፡ ብዙም ሳትቆይ የኦነግ አባል መሆኗ ተወራ፡፡

የደስታ እንባ?

ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረ ጊዜ መለስ ለንደን ሆኖ ምን እንደተሰማው የነገረኝን አስታውሳለሁ፡፡ ‹‹ አሜሪካኖች ‹ኢህአዴግ አዲስ አበባን ተቆጣጠረ› ሲሉን ከደስታዬ ብዛት አለቀስኩ!›› ነበር ያለኝ

ማስተከከያ

በኤርትራ ሪፈረንደሙ በሚካሄድ
በት ጊዜ ድምጽ መስጫው ‹‹ ባርነት ወይስ ነጻነት›› የሚል ነው ተብሎ የተወራው ትክክል አይደለም፡፡ የድምጽ መስጫው ‹‹ ነጻነት ትፈልጋለህ ወይስ አትፈልግም;› ›› የሚል ምርጫ ነበር፡፡

ሽርሽር በነጠላ ጫማ

የነጻነትቸው ቀን ሲከበር መለስ ኤርትራ ሄዶ በትግርኛ ንግግር ሲያደርግ  እኔም ነበርኩ፡፡ እኔ፣ መለስና ኢሳያስ / ስሊፐር ጫማ አድርጎ/ ከተማ ውስጥ ዞረናል፡፡ በእውነት ትልቅ ነጻነት ነበር የተሰማኝ፡፡ ሱቅ እየገባን፣ ማታ ማታ እየዞርን አንድ ሁለት ቦታ መጠጥ እየተጎነጨን ተዝናንተናል፡፡ ያረፍነው በራሰው ካሳ ቤት ውስጥ ነበር፡፡

የመምሪያ ሃላፊዋቹ እንዴት ተባረሩ?

ኢህአዴግ በ1983 ዓም ሀገሪቱን ሲቆጣጠር ከማስታወቂያ ሚኒስትሩ ዲማ ነጋዋ በቀር የመምሪያ ሃላፊዋች በሙሉ  የኢህአዴግ ታጋዬች ነበሩ፡፡ የፕሬስ መምሪያ ተስፋዬ ገብረአብ፣ የቴሌቪዥን አማረ አረጋዊ፣ የኢዚአ መዝሙር ፋንቴ፣ የኦሮምኛ ፕሮግራም ሃላፊ ደግፌ ቡላ እና የኦሮምኛ ራዲዬ ፕሮግራም ሱሌይማን ደደፎ ነበሩ፡፡…. ታዲያ ባደረግናቸው ግምገማዋች አንዳንዶቹ የአቅም ፣ ሌሎቹ የሙያ ፣ ቀሪዋቹ ደግሞ የስነምግባር ችግር ነበረባቸው፡፡ ለምሳሌ ሙስናን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለዜና ስራ አበልና መኪና ተመድቦላቸው እነሱ ማስታወቂያ ይሰራሉ፡፡ በሰራተኛው ላይ አምባገነን የመሆንና ሌሎች ችግሮችንም ይፈጥራሉ፡፡ ሴቶችን ያመናጭቃሉ፣ በዘመድ ይሰራሉ፡፡ የአመለከከትም ችግር ነበረባቸው፡፡ ለስሙ የኢህአዴግን ነገር ያስቀድማሉ፣ የብሄሮችን መብት በተመለከተ ግን ትምክህተኝነትና ጠባብነት የሚያራምዱ ነበሩ፡፡ በነዚህ ምክንያቶች ሁሉንም እንዲለቁ አድርገናል፡፡ በዙዋችን ወደ ኢህአዴግ ተቋማት -ፋና፣ ዋልታ፣ ሲዛወሩ ተስፋዬ ገብረአብ ወደ እፎይታ መጽሄት ተልኳል፡፡ ከነአካቴው እንዳይባረሩ ደግሞ ሁሉም ታጋዬች ናቸው፡፡

ዝነኛው አንቀጽ 39

እኔና ዳዊት አንቀጽ 39 መኖር አለበት፣ መሬትም መሸጥ መለወጥ የለበትም የሚል አቋም ይዘን ተከራክረናል፡፡ የብሄር ጥያቄን በተመለከተ የኦሮሞ ህዝብ የራሱን እድል በራሱ የመወሰን መብቱ እስከመገንጠል መከበር አለበት የሚል ነበር አቋሜ፡፡ እዚህ ጋ መገንጠል አለበት ማለትና የመገንጠል መብቱ ይከበርለት ማለት ልዩነት እንዳለው ልብ ማለት ያሻል፡፡ አሁንም የህዝቡ የራሱን ዕድል በራስ የመወሰን መብቱ መከበር ትክክለኛ ነው፣ ዴሞክራሲያዊም ነው እላለሁ፡፡

የፕሬዝዳንቱ ቤት

ይገርምሃል ! ሌላ ሀገር አንድ ርዕሰ- ብሄርን እንዲህ አድርገው ይይዛሉ? አላውቅም፡፡ እነዛ አሮጌ ቤቶች በራቸው ሲዘጋ ከስር አይጦች ያስገባ ነበር፡፡

እጅ መንሻ

ባለስልጣኖች ጉብኝት በሚያደርጉበት ጊዜ የአካባቢው ትናንሽ ባለስጣናት ከአካባቢው ነዋሪዋች ላይ ቅቤ፣ በግ፣ ከብት እና ሌላም ሌላ ነገር እየሰበሰቡ ሲሰጧቸው ታዝቤያለሁ፡፡ በእኔ ስም ይዘው እንዳይመጡ በጥበቅ አስጠነቅቃቸው ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ግን ከባሌ አገልግል ጭነው ይዘውልኝ እንደመጡ አስታውሳለሁ፡፡ አሁን እነ አባዱላና እነ መለስ በየአካባቢው አንዴ ጋቢ፣ሌላ ጊዜ በሬ ተበረከተላቸው የሚባለውን ስሰማ ‹‹ ወዴት እየሄድን ነው? ›› እላለሁ፡፡ እንደኔ እንደኔ ትክክል አይደለም፡፡

የግም-ገማ ጣጣ

የፋይናንስ ቢሮን  ይመራ የነበረውን አቶ አለማየሁ ደሳለኝን ስንገመግም ቆይተን ሳንጨርስ ለምሳ ወጣን፡፡ ከምሳ ስንመለስ አለማየሁ ቤተመንግስት  ግቢ ውስጥ  ራሱን በሽጉጥ ገደለ፡፡ የሚያሳዝነው አለማየሁ በግምገማው ምንም አልተገኘበትም፣ ንጽህነቱን ልንነግረው ነበር፡፡ ግምገማው እጅግ ከባድ ስለሆነ የሚያለቅሱና እንደ እብድ  የሚያደርጋቸው ነበሩ፡፡

በሰው ልክ የሚሰፉ አዋጆች

አቶ ስዬ አብርሃ ተከስሶ ፍርድ ቤት በቀረበ ጊዜ ፣ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ የነበረችው ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ በዋስ ልትለቀው እንደሆነ ታወቀ፡፡ ይሔኔ ‹‹ አቶ ስዬ በዋስ እንዳይለቀቅ ቶሎ አዋጅ መውጣት አለበት›› ተባለና የወቅቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተፈራ ዋልዋ ደወለልኝና ‹‹ እባክህ በፓርላማ በኩል ጸድቆ የመጣውን አዋጅ ቶሎ ፈርምልን›› አለኝ

የአልጀርሱ ስምምነት

የአልጀርሱን ስምምነት ለመፈረም በተስማማንበት ወቅት አዲሱ ለገሰ መናደዱ ትዝ ይለኛል፡፡ ‹‹ ከዚህ በኋላ በሻዕቢያና በህውኀት መካከል ችግር ተፈጥሮ ወደ ጦርነት የምንገባ ከሆነ የኛን ህዝብ ሂዱና ተዋጉ ብዬ አልቀሰቅስም!›› አለ፡፡ የሆኖ ሆኖ የአልጀርሱ ስምምነት በፓርላማ ጸድቀ፡፡ እኔም በስነስርዓቱ መሰረት ፈርሜያለሁ፡፡ ‹‹ ያለ ቅድመ ሁኔታ የአልጀርሱን ስምምነት እንቀበላለን›› ብለን ለመፈረም መወሰናችን ትልቅ ስህተት ነበር፡፡

የነስዩም ስህተት

ስዬም መስፍንና አሊ አብዶ ህዝቡን አስወጥተው ‹‹ ባድሜ ለኛ ተፈረደ›› ብለው ሲያውጁና ሲያስጨፍሩ እኔ ወለጋ ነበርኩ፡፡ እነሱ ያደረጉት ትክክል አልነበረም፡፡….. እኛን በሚጎዳ መልኩ መወሰኑን ተገንዝቤያለሁ፡፡

የመለስ ደብዳቤ

በክፍፍሉ ወቅት መለስ ለኦህዴድ ደብዳቤ ሲጽፍ የኢህአዴግ ማህተሞች በውህዳኑ እጅ ስለነበሩ በህወሃት ማህተም ይጠቀም ነበር፡፡ ይሄን በተመለከተ በደብዳቤው መጨረሻ ያሰፈረው ሃሳብ ዘና የሚያደርግ ነው፡፡ ‹‹ አንጃው ማህተሞቹን ህገወጥ በሆነ መንገድ ስለዘረፈ የኢህአዴግን ማህተም ላሰፍር አልቻልኩም›› ይልና ‹‹ የመንግስት ማህተም ያለበት ደብዳቤ ከዚህ ቀደም ጽፌ በናንተ በኩል ሂስ ስለቀረበብኝ ፣ ማህተም የሌለው ደብዳቤ መጻፍም የሚያስከትለውን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባት በኢህአዴግ ሊቀመንበርነቴ በምጽፈው ደብዳቤ ላይ የማሰፍረው ማህተም በማጣቴ፣ በህወሀት ማህተም ለመጠቀም ተገድጃለሁ››

ነጭ ካፒታሊዝም

ከሁሉም በላይ ግን ከዚህ ድርጅት ጋር መቀጠል የለብኝም ብዬ እንድወስን ያስገደደኝ ፣ ኢህአዴግ የሚመራበትን ርዕዮተ ዓለም እንደቀየረ በተገለጸ ጊዜ ነው፡፡ በስብሰባው ‹‹ ማርክሲስት ሌኒኒስት አለ ወይ?›› የሚል ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡ ‹‹ የሶሻሊዝም ጉዳይ ቀረ ወይ?>>
‹‹ ማርክሲስት ሌኒንስት ከ1983 ዓም ጀምሮ የለም፡፡ ሰዋች ቢኖሩም እንደ ቡድን ኢህአዴግን የሚመራ ርዕዬተ ዓለም መሆኑ ቀርቷል፡፡ ሶሻሊዝምን በተመለከተ ከ1983 ጀምሮ ጠረጼዛ ስር ደብቀነዋል፡፡ ከምዕራባዊያን ድጋፍ ለማግኝትና የኢትጽያ ሀዝብ በደርግ የተነሳ ስለጠላው ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምናራምደው›› አለ መለስ
‹‹ እስከ መቼ››
‹‹ ይሄ የኔ ጉዳይ አይደለም፡፡ እስከ ልጅ ልጅ ሊዘልቅ ይችላል፡፡ ምናልባት በልጆቼና በልጅ ልጆቼ ዘመን ሊሆን ይችላል፡፡›› አለ መለስ ሲመልስ
‹‹ ይሄን መቼ ወሰናችሁ?›› ተብሎ ሲጠየቅ ደግሞ ‹‹ ከ1983 ዓም ጀምሮ ነው›› አለ፡፡ ብዙ ሰው ነው ብግን ያለው፣ ምክንያቱም የኢህአዴግ ፕሮግራም እንዲህ አይልማ፡፡ እኔማ ቅ-ጥ-ል አልኩ፡፡ ለካ አስር አመት ሙሉ አታሎን ነበር፡፡



‎የእኛ የእያሱና የመንግስት ‹‹ ቲፕ ››‎






ቲፕ ይሰጣሉ ? ከሰጡ ውስጥዋ የሚቀር አሳማኝ ምክንያት አለ ? ወይስ ስለዚህ ጉዳይ በአንክሮ አስበው አያውቁም ፡፡ ምናልባት አንዳንድ ምክንያቶቸን ላስታውስዋ….

1 . አስተናጋጆች አነስተኛ ደመወዝ ስለሚከፈላቸው
2 . አስተናጋጆች መልሱን በዕቃ ስለሚያቀርብልዋትና የዕቃው ራቁትነት ስለሚያሳፍርዋት
3 . ለሚያገኙት ሸጋ መስተንገዶ ክብር መግለጫነት
4 . ለትውውቅ ወይም ለጠበሳ
5 . ሌሉች ሰዋች ስለሚያደርጉት
6 . ክፉ አይደለሁም የሚል ማስታወቂያ ለማሰራት
7 . ሃይማኖታዊ መርህን ለማስከበር

በርግጥ ከዚህ የተለየም  ምክንያት ሊኖርዋት ይችላል፡፡ ቲፕ ቅርጽና ይዘቱን ሳናወዳድር ጥንትም እንደነበር አንዳንድ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ የእቴጌ ምንትዋብ ልጅ የሆነው ዳግማዊ እያሱ በስልጣን ዘመኑ ትምህርትን የተመለከተ ቲፕ ነበረው፡፡
ዳግማዊ እያሱ በአንድ ወቅት ‹‹ መማር የሚፈልግ ሁሉ በነጻ ከቤተመንግስት መመገብ ይችላል ›› የሚል አዋጅ አስነገረ ፡፡

ለመሆኑ እያሱ ቲፕ ለመስጠት ምን አሳሰበው?
መመዘኛው ምንድነው?
ቲፑን ለነማን ሰጠው?
እነሆ እያሱ እንደሚከተለው ተናገረ ፤

 ማንም ሰው በትምህርቱ ወደፊት ገፍቶ ከተወሰነ ደረጃ ላይ ሲደርስ፣ ይበልጥ በተሟላ ገበታ ላይ በክብር ተቀምጦ  መመገብ ይፈቀድለታል !!!

 ተራ ምግብ የሚሰጣቸው ማንበብና መጻፍ ብቻ የሚችሉ ናቸው !!!


በሳይንሳዊ ጥናቱ  ቀጥሎ ወዳለው ደረጃ የተሸጋገረ ሁሉ ከመደበኛው ማዕድ ጋር ጠላ ይሰጠዋል !!!

ነገር ግን በእውቀቱ ከላቀ ደረጃ ላይ የደረሰ ሰው፣ ለምሳሌ ቅኔ ከተቀኝ፣ ከምግብ ጋር ጠጅ ይቀርብለታል !!!

የቅኔን ሳይንስ ጨርሶ ወደ መጻህፍት ጥናት የተሸጋገረ ሁሉ የመጨረሻው ምርጥ ማዕድ ይቀርብለታል !!!

እንደሚታወቀው በቀድሞው  የኢትዬጽያ ባህል መሰረት ጠጅ ለመጠጣት የሚፈቀድላቸው በህብረተሰቡ ውስጥ ከፍ ካለ የታዋቂነት ደረጃ ላይ የሚገኙ ብቻ ናቸው፡፡

ባለንበት ዘመንም ጥሩ የሰራ ይሸለማል የሚል መፈክርን የያዙ ቲፕ መሰል ጥናቶች ብዙ ጊዜ ይፋ ሆነዋል፡፡ በጣም ጥቂቶቹ ይጠቀሱ ቢባል እንኳን ወንድማማቾቹን ቢፒአርና ቢኤስሲን እማኝ ማድረግ ይቻላል፡፡
እነሆ መንግስት እንደሚከተለው ተናገረ፤

የውጤት ተኮር ስርዓትን ያለምንም ማበረታቻ ተግባራዊ ለማድረግ መሞከር የሰራተኛውን ተነሳሽነት የሚያዳክምና የተቋሙን አፈጻጸም የሚጎዳ ነው፡፡ በዚሁ መሰረት ከአማካኝ አፈጻጸምና በላይ የሚገኙ ሰራተኞች የተለያዩ መጠን ያለው ማበረታቻ ክፍያ ያገኛሉ፡፡ ቢኤስሲ መ/ቤቶችን ያጥለቀለቀ ቢሆንም ትጉሃን ግን እስካሁን አልተሸለሙም ፡፡

ለመሆኑ መንግስት ቲፕ ይውቃል ?
ካወቀ ቲፕ ይሰጣል ?
ከሰጠ መቼ ይሰጣል ?
እረ ለመሆኑ እንዴት ይሰጣል ?
እኮ ለነማን ይሰጣል ?
ውስጡ ያለው አሳማኝ ምክንያት ምንድነው ?
ልክ ከላይ በዝርዝር እንደገለጽነው ‹‹ እንደ እኛ ›› እያነጻጸራችሁ የምትመልሱ ከሆነ ብዙ ፈገግታ አጫሪ ምላሾች ብቅ ጥልቅ እንደሚሉባችሁ አሰብኩ፡፡

ለምሳሌ በተራ ቁጥር 4 ዓይን ካሰባችሁ ‹‹ ሰዋች እሱን መስለው ሲተዋወቁት ወይም ሲጠብሱት ›› የሚል ምላሽ ታገኛላችሁ፡፡ ከፈለጋችሁ በዚሁ ስሌት ቀጥሉ…….

እረ የቲፕ ያለህ !!!!
እረ የጠላ ያለህ !!!!
እረ የጠጅ ያለህ !!!!
እረ የማዕድ ያለህ !!!!
ለመሆኑ ቲፕ ምንድነው ???????????????????????