Wednesday, December 18, 2013

ሊቨርፑል በገና ዋዜማ





ሰማዩ እጅግ ከፍቶታል ...

እንዲህ መሆን ከጀመረ ቆየ ።

አምቆ የያዘውን ጥቁር እባጭ የመሰለ ነገር ዘርግፎ ቢጨርሰው ሰላም ባገኘ ነበር ። ግና ቁጣ እንዳስበረገገው የአበሻ ህጻን ቆይቶ - ቆይቶ ነው ጠብ የሚያደርገው - ርግጥ ነው እንደ ህጻን ችክ ያለ ማላዘን አይታይበትም ።

ተጠሪነቱ ለደመናው ይሁን ለምድሪቱ ያልታወቀው ብርድ ግን የተሰጠውን ተልዕኮ በአግባቡ እየተወጣ ይገኛል ። አንዳንዴ በግልጽ እንደ ውሻ ይናከሳል ... አንዳንዴ እንደ ስለታማ ቢላ አካልን ይሰነጥቃል ። በግላጭ በሚያገኛቸው ጆሮ ፣ አፍንጫና የእጅ ጣቶች ላይ ደግሞ ጥቃቱ ለጉድ ነው ። እንደ ንብ ነድፎ - ነድፎ በረዶ ቤት የተቀመጡ ዕቃዎች ያደርጋቸዋል ።

ምድሪቱ ጉንጭ ላይ ስስ ፈገግታ ይታያል ...

ዓላማና ግቧ ግን ሙሉ ፊቷ ላይ ሳቅ እንደፈንዲሻ እንዲተራመስ ማስቻል ነው ። እናም ግብግብ ላይ ናት ። በረዶው ፣ ንፋሱ ፣ ብርዱ ፣ ዝናብና ጭጋጉ የቱንም ያህል ጥቃት ቢያደርስብን የገና በዓላችንን ከማድመቅ አይገድብንም የሚሉት ሊቨርፑዲያንስ ሙሉ ከተማውን ሞልተው ይሮጣሉ ። ሩጫቸውን ከንግድ ቤቶች የሚወጣው የገና ሙዚቃ ያግዛቸዋል ። ታላቅ ቅናሽ እያሉ በማይክራፎን የሚያላዝኑት ሱቆችም በረከቱ እንዳያመልጣቸው አጥብቀው ይወተውታሉ ። እዚህ እንደ እኛ ሀገር ዶሮና በግ ጥጋቸውን ይዘው አይጮሁም ። ሳርና ችቦ የሚቸረችሩ ወቅታዊ ነጋዴዎች ማየት አይቻልም ፤ አየሩ በተነጠረ ቅቤ ፣ በኮባና ኩበት ጢሳጢስ የተሞላ አይደለም ።

በርግጥም አየሩን የተቆጣጠሩት አብረቅራቂ መብራቶችና ሙዚቃዎች ናቸው ። መኖሪያ ቤቶች ፣ ህንጻዋችና « ሲቲ ሴንተር » የተባለው የገበያ ቦታ ለአይን በሚማርኩ የመብራት ውጤቶች ተንቆጥቁጧል ። ከሱቆቹ በተጨማሪ እዚህም እዚያም የተለያዩ የሙዚቃ ስራዋችን የሚያሳዩ ግለሰቦች እንደ አሸን ፈልተዋል ። ትላልቅ ሴቶች ሳይቀር አኮርዲዮን እጥፍ ዘርጋ እያደረጉ ሳንቲም ይሰበስባሉ ። ሁለት ሶስት ሆነው ቆርቆሮን እንደ ከበሮ በመጠቀም የመንግስት ማርሽ ባንድን የሚያስንቁ ሰዋችም ይታያሉ ። በአርሞኒካ ብቻ የብዙዋቹን ትዝታ የሚያማልል ፣ እንዲሁም ከውሻው ጋር ቁጭ ብሎ የሚመስጥ መሳሪያ የሚጫወት ሌላ ሰው በሌላ ክንፍ አይታጡም ።

በስነስርዓት ማይክራፎንና ኪቦርድ አዘጋጅቶ የፈረንጆቹን ሙዚቃ የሚጫወት አንድ አፍሪካዊ ግን ብዙ ግዜ የብዙዋችን ትኩረት ሲስብ ተመልክቼያለሁ ። ተመልካቹ ክብ ሰርቶ አፉን ከፍቶ ፣ አንገቱን ግራና ቀኝ እየናጠ ይመለከተዋል ። አንዳንዶቹ ደግሞ መሃል ገብተው ይወዛወዛሉ ። ይህን ሰው X – Factor አያውቀውም ወይስ X – Factor / የእንግሊዞች ታዋቂ አይዶል ሾው / አንጋሎ የተፋው ነው ? ድምጹ ብርዱንና ውሽንፍሩን በታትኖ ከጆሮ የሚደርሰው ሳይደናቀፍ ነው - አይጎረብጥም ። የዳጎሰ ልምድ ያለው መሆኑ ለተራ ሰውም ግልጽ ነው  - አንዳንዶች ሊወኒልን ሪቼ እያሉ ይጠሩታል ። በርግጥም የታዋቂውን አቀንቃኝ አንድ ሙዚቃ ሲያቀነቅን ነበር ፣

Good bye  ይለዋል ታዳሚውን እንደሚሰናበት ሁሉ  

I wanted you for life
You and me
In the wind
I never thought there come a time
That our story would end
It’s hard to understand
But I guess I’ll have to try
It’s not easy
To say good bye ... good bye ... good bye ..


ሙዚቃውን ሲጨርስ ታዲያ የሚሰሙት ጭብጨባ አንድ ትልቅ ቲያትር ቤት የታደሙ ያህል ነው ። ከዚያም ፊት ለፊት ባስቀመጠው ሻንጣ ውስጥ የእንግሊዝ ነጭና ቀይ ሳንቲሞች ሲንቦጫረቁ ይሰማል ።

አፍሪካዊው አቀንቃኝ

ሙዚቃ ወዳዱ የሊቨርፑል ነዋሪ ሲጋራውን እያቦነነ ፣ ሀምበርገሩን እየገመጠ ፣ የሚጠጣውንም እየተጎነጨ ያዳምጣል ። የዚህ ከተማ ሃምሳ የሚደርሱ አቀንቃኞች በምድረ እንግሊዝ ብቻ ሳይሆን በዓለማቀፍ ደረጃም ትልቅ ስም ያላቸው ናቸው ። ሙዚቃዋቹ ለጆሮ በደረሱበት ዘመን በሽያጭ ረገድ ቁጥር አንድ በመባላቸው ከተማዋ በጊነስ ቡክ ላይ የሙዚቀኞች ሀገር ለመባል አስችሏታል። በ1960 የተመሰረተውን The Beatles ብቻ ለአብነት ማንሳት ይቻላል ። አራቱ የቡድኑ አባላት ጆን ሊኖን ፣ ፓውል ማካትኒ ፣ ጆርጅ ሀሪሰን እና ሪጎን ስታር በ1962 « Love Me Do » የሚለውን አልበም እንደለቀቁ ነበር ታዋቂነትን የተጎናጸፉት ። ሮሊንግ ስቶን ሙዚቀኞቹን የምንግዜም ትልቅ አርቲስቶች ብሏቸዋል ። ታይም መጽሄት በበኩሉ የሃያኛው መቶ ክፍለዘመን መቶ ተጽዕኖ ፈጣሪ ብሎ ከዘረዘራቸው ግለሰቦች መካከል አስፍሯቸዋል ። የፈረደበት ጊነስ ቡክ ወርልድ የሙዚቀኞቹን « Yesterday » የተባለው ሙዚቃ ከሶስት ሺህ አርቲስቶች በላይ ከእንደገና ተጫውተውታል ይለናል ። አስደናቂው ነገር እንዲህ ተደጋግሞ የተዘፈነበት ሌላ ሙዚቃ አለመኖሩ ነው ።

በከተማው መሃል ለገና እየቀረበ ያለው ሌላው ስጦታ የግለሰቦች « ምትሃታዊ » ስራ ነው ። ለነገሩ አስማት ይባል ሌላ ጥበብ በድፍረት መናገር ቸግሮኛል ። እስኪ አንድ አጭር « ሾው » በጽሁፍ እንከታተል ፤

 አንድ ሰው ሻንጣ ይዞ መጣ ።
ከሻንጣው ውስጥ የሚያብረቀርቅ ልብስ አውጥቶ ለበሰ ።
 አናቱ ላይ  ቀንድ ያለው ማክስ አጠለቀ ።
ፊቱንም ልብሱን የመሰለ ነገር ተቀብቶታል ።
የልብሱን ቀለም የመሰለች ብትር አወጣ ።
ዙሪያ ገባውን ማትሮ በፈገግታ እጁን አወዛወዘ ።
በአካባቢው መንኮራኮር የለም እንጂ ወደ ላይ ለመምጠቅ የመጨረሻ ሰላምታ የሚሰጥ ነበር የሚመስለው ።
 መሬቱ ላይ ጥቁር ጨርቅ አነጠፈ ።

የፈራነው ደረሰ ?

እንዴ ? ... ዱላውን ተሞርኩዞ በአየር ላይ ቁጭ አለ ። በቃ ! ... ይወርዳል ብለን ብንጠብቅ - ብንጠብቅ ቁጭ እንዳለ ቀረ ። መቼም ይህ ሰው ሊንሳፈፍ የቻለው ጭንቅላቱን « ጨረቃ ላይ ነህ » ብሎ በማሳመኑ ሊሆን አይችልም ። ብዙዋቹ በጥበቡ በመገረም ሳይሆን በፍርሃትና በጥራጣሬ ነበር የሚመለከቱት ። እንዴት ሊሆን ቻለ ? ሰውነቱ ውስጥ የቀበረው ነገር ይኖር ይሆን ? በዜና ያልሰማነው ምን የሚያንሳፍፍ መሳሪያ ተገኘ ? መልስ አልነበረም ። ሳንቲም ወርወር ሲያደርጉለት ብቻ እጁን በአፉ እየሳመ ፈገግ ይላል ። ከዚያ ውጪ ኮስተር ስላለ ጥሩ ቀራጺ የሰራው ሃውልት ነው የሚመስለው ።

ተንሳፋፊው ሰው

 « ይገርማል » እያልኩ ሌላውን የገበያ አቅጣጫ መከተል ጀመርኩ ። የማስበው ስለ ምትሃት ነበር ። አስማት ጥበብ ነው ፣ ሳይንስ ነው ፣ ፈጣን የጭንቅላት ጨዋታ ነው ፣ በባዕድ አምልኮ ጋር የተገናኘ መንፈሳዊ ስራ ነው ... ብዙ ብዙ ይባላል ። ድንገት አባባ ተስፋዬ ሳህሉ በአእምሮዬ ጔዳ ብቅ አሉ ። በቴሌቪዥን መስኮት የምትሃት ጥበብ እያሉ ገመድ ሲቌጥሩና ሲፈቱ ፣ ጨርቅ ሲያሳዩና ሲሰውሩ  ብዙዎቻችን ተመልክተናቸዋል ። ምናልባትም ለአስማትና ምትሃት ያለን የእውቀት ጥግ ያንን ያህል በመሆኑ ሊሆን ይችላል አድናቆታችን አለቅጥ የሚረዝመው ።

ስለ አስማት የሚያውጠነጥነው አእምሮዬ ተጨማሪ ነገር የፈለገ ይመስል ከሌላ ምትሃተኛ ጋር ተገጣጠምኩ ። ይሄኛው ደግሞ በሙሉ ልብስ ዝንጥ ያለ ነው ። የያዛትን ዣንጥላ አንዴ ይደገፋታል ፣ ሌላ ግዜ ይዘረጋታል ። እየሰራ ያለውን ነገር በግልጽ እንድትረዱት ለማድረግ የግድ ስዕላዊ ገለጻ መጠቀም አለብኝ ። ለምሳሌ ያህል መደገፊያው ራቅ ያለ ምርጥ ሶፋ ላይ እግራችሁን አንፈራጣችሁ ቁጭ ብላችኃል እንበል ። ቀስ ተብሎ ሶፋው ከስራችሁ ሸርተት ቢደረግ ቁጭ እንዳላችሁ ትቀራላጭሁ ወይስ ሚዛን ስለማይኖራችሁ ትወድቃላችሁ ? መልሱ ግልጽ ነው ። እንግዲህ ይህ ምትሃተኛ አየር ላይ የተቀመጠው ሶፋው ከተነሳበት በኃላ መሆኑ ነው ። ሙሉ ሚዛኑን እየተቆጣጠረ ያለው በሁለት እግሩ ነው ። እስኪ ሞክሩት ።
ወገብዋ እንክትክት ቢል ግን የለሁበትም ።

አየርን ተደግፎ መቀመጥ

ከገበያው ግርግር ወጥቼ አስገራሚ ስነጥበብ ያረፈባቸውን ህንጻዋች ፣ ሙዚየሞችና የስዕል ጋለሪዋች እየተመለከትኩ ስጔዝ እግሬን አልበርት ወደብ አካባቢ አገኘሁት ። እየቸኮልኩ ነበር ። ምክንያቱም እዚህ ሀገር የሚጨልመው ከቀኑ አራት ሰዓት / በእኛ 10 /  ጀምሮ በመሆኑ ብርሃንን መሻመት አለብኝ ። ጠዋት አንድ ሰዓት ሆኖም ጨለማው እንደተዘፈዘፈ ነው ። ካላወቁ ጠዋት ቀጠሮ ይዘው እንኴ « እረ አልነጋም » ብለው ይተኛሉ ። አስራ ሁለት ሰዓት ሲሆን የምሽት ስንብትንና የመንጋት መምጣትን ወፎች በጨኀት አያበስሩም ። ለነገሩ የቤት ርግብ እንጂ ወፍ ይኑር አይኑር ርግጠኛ መሆን አልቻልኩም ። ውስን ወፎች ቢኖሩ እንኴ እንቅልፋሙን ሰው የመቀስቀስ ግዴታ የሌለባቸው ይሆናል ። ምክንያቱም ይህ ዴሞክራሲ የበዛበት እንግሊዝ ነውና ። ስለዚህ ጠዋት ስራ ገቢ ከሆኑ ሰዓት ሞልተው ጆሮዎ ስር አላርሙን በወፍ ዜማ ማስጮህ ይኖርቦታል ።

ይሄ የመምሸት ነገር ግን እንደሚመስለኝ ቀን ያለ ሰዓቱ ወደ ምድር የሚወረወረው ተፈጥሯዊ ሬንጅ በማግስቱም ከመሬት ለመላቀቅ የሚገጥመው ፍትጊያ ቀላል አይደለም ። እጅ ላይ የፈሰሰ የበረሃ ሙጫ በሉት ። « ወግድልኝ » ብትሉትም ሙጭጭ ብሎ እየተሳበ የሚልመጠመጥ ። እናም እስከ የካቲት ድረስ ጸሃይ ብቻ ሳትሆን ቀንም ራሱ ብርቅ ይሆናል ነው የሚባለው ።

በስመዓም ... አልበርት ወደብ በጣም ይጎበኛል ። ከጥንታዊነቱም ከዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሰጪነቱ አኴያ ሊሆን ይችላል ። በ1846 ነው የተገነባው ። ይሁን እንጂ ቡና ቤቶች ፣ ሱቆች ፣ ሆቴሎች ፣ የባህር ትራንዚትና የአለማቀፍ ባርነት ሙዚየሞች እንዲሁም የ ዘ ቢትልሶችን ታሪክ አቅፎ ይዟል ። በግዜውም በያዘው ሰፊ ቦታና ተግባር ከዓለማችን ቁጥር አንድ ነበር ።

የከተማው አዛውንቶች ታዲያ ዉሻ እያስከተሉ ነው ወደቡን የሚጎበኙት - በልብስ ያጌጡ ውሾች ። ውሾቹ ግን የሌላ ሀገር ምርጥ ተሞክሮ እጥረት ያለባቸው ነው የሚመስሉት ። ምክንያቱም መናከስ፣ ማስደንገጥ ቢያንስ መጮህ የተባለውን የዘመዶቻቸውን ቌንቌ የት እንዳደረሱት አይታወቅም ። ማንም ቢያባብላቸውና ቢደባብሳቸው ግድ የላቸውም ። የሚታያቸው ቶሎ ብሎ የውስጥ ገላቸውን ፈርከስከስ አድርጎ ማቅረቡ ነው ። ዉሻ ካልጮኀ ደግሞ በግ ሊመስል ይችላል ። የሀገሬ ሰው ግድጔድ ቆፍሮ ቀብሮ ፣ ቢቻል ተርብ እያበላ አሳድጎ ዉሻው ጸጉረ ልውጥ ሰው ጅርባ ላይ ፊጥ ሲልማ መመልከት ይፈልጋል ። አለዚያማ እንደ አውደልዳይ ዉሻ መንገድ ላይ ይጣላል ። የዚህ ሀገር ዉሾች ውሎአቸው መኪናና ቡናቤት አዳራቸው ደግሞ ሳሎን ነው ። ውሻ የሚያሳድጉበት ዋና አላማም ሰውንም ሆነ ሌባ ማስደንገጥ አይመስልም ። ታዲያ ምንድነው ከተባለ የእንስሳት ፍቅር ወይም ሆቢ ብሎ ማለፍ ይቻላል ።

         እንዳልኴችሁ የሊቨርፑል ወደብ ከተማዋ እንድታድግ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጔል ። ይህን ወደብ ጨምሮ ስድስት የሚደርሱ አካባቢዋችም በዩኔስኮ የዓለም ቅርስ መዝገብ ውስጥ የሰፈሩ ናቸው ። ታዋቂው ብዕረኛ ቻርልስ ዲከንስም  ወደቡን « ሃብታሙና ማራኪው » በማለት ነበር የገለጸው ።

አልበርት ዶክ 

በነገራችን ላይ ዳንኤል ዴፎ ፣ ዋሽንግተን ኢርቪንግ ፣ ቻርልስ ዲከንስና ሌሎች ታዋቂ የጥበብ ሰዋች ሊቨርፑልን ጎብኝተዋል ። ደጋግሞ በመጎብኘት ምናልባትም አስራ ሁለት ግዜ ዲከንስን የሚያህል የለም ። ደራሲው ደጋግሞ የሚመጣው መጽሀፎቹን ለመጻፍ ይረዳው ዘንድ አንዳንድ ነገሮችን ለመመርመር ፣ መድረክ ላይ ተጋብዞ ለመናገርና የራሱን ስራዎች ለማንበብ ነው ። እንደሚታወቀው ሃያ የሚደርሱ መጽሀፍትን ለአንባቢያንን አበርክቶ ነው ያለፈው ። ስነጽሁፍ በኮሌጅ የተማረም Great expectation , Oliver twist , A tale of two cities , Hard times እና The pick wick papers የተባሉ ስራዎቹን አይረሳም ። እኔ በወቅቱ ዲክንስ ከአደፍርሱ ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ ጋር ይመሳሰልብኝ ነበር ። ሁለቱም ቃላትን አጥብቀው የሚወዱ ፣ በቃላት መራቀቅ የሚፈልጉ « Wordy » የሚባሉ አይነቶች ናቸው ። ጹሁፉን በአግባቡ ተረድተን የቤት ስራችንን ለመስራት በጣም እንቸገር ነበር ። አደፍርስንስ ስንት ግዜ ነው እየጀመርኩ የተውኩት ? የቁጠኛውን ዳኛቸውን ባላውቅም ዲክነስ ፍጹም የመድረክ ተናጋሪና ተከራካሪ እንደነበር መዛግብት ያስረዳሉ ። ዲክነስ እንደ ንግግሩ ሁሉ ጹሁፎቹ ለጥቅስ የሚበቁ ናቸው ። ለዛሬ ግን የሚከተለውን ላስታውስለት ፣

« No one is useless in this world who lightens the burden of another . »

ከአልበርት ወደብ አካባቢ ሆኖ ጀምስ መንገድ ላይ የሚገኘው የአልቢዎን ሀውስ ይታያል ። ይህ ህንጻ ሲነሳ ደግሞ ሊቨርፑልና ታይታኒክ የተባለችው ታሪካዊ መርከብ የነበራቸውን ጥብቅ ቁርኝት መረዳት ያስችላል ። እንደሚታወቀው ከመርከቧ የፈት ገጽ ላይ ታይታኒክ ከሚለው ጽሁፍ በታች Liver Pool የሚል ጽሁፍ ይታያል ። ይህ የሆነው የካምፓኒው ጽ/ቤት / አልቢዎን  ሀውስ / እዚህ በመገኘቱ መርከቧ የተመዘገበችው በከተማው ስም ስለሆነ ነው ።

የታይታኒክ ማዋለጃ ቤት

ታይታኒክ የተጸነሰችውም ሆነ የመጨረሻውን ዲዛይን የያዘችው በሊቨርፑል ይሁን እንጂ ነፍስ ዘርታ መንቀሳቀስ በጀመረችበት ወቅት ሊቨርፑልን ማየት አልቻለችም ። ሌላው ቁርኝት ከመርከቧ ሰራተኞች 90 ያህሉ በተለይም ታይታኒክ ከበረዶ ጋር ስትጋጭ የተመለከቱትን ሁለት ሰዋች ጨምሮ የተቀጠሩት ከሊቨርፑል መሆኑ ነው ። ፊልሙን ባየነው መሰረት የሰውየው አጯጯህ  እንዴት ነበር ? « የበረዶ ቌጥኝ ይታየኛል ! ... የበረዶ ቌጥኝ ይታየኛል ! ... » ምን ዋጋ አለው አንዳንዶች ዘግይቶ ሪፖርት አድርጔል በማለት ከርፋፋ ሲሉት ሌሎች ደግሞ ስራውን በአግባቡ የተወጣ ጀግና ያደርጉታል ። መርከቧ ስትሰምጥ ምንም ሳያቌርጡ ሲዘፍኑ የነበሩ ሙዚቀኞችን እንዲሳፈሩ ያደረጋቸው ወኪል የሚገኘውም በሊቨርፑል ነው ። ባይሆን የሙዚቀኞቹ ነገር እጅግ ይገርማል ። ሰው ህይወቱን ለማትረፍ ላይ ታች ሲራኮት የእነሱ ነፍስ ግን በሙዚቃው ሃይል ውስጥ ተውጦ ነበር ። ሊቨርፑልና የሙዚቃ ፍቅርን በማያያዝ እነዚህ ሰዎች ሊቨርፑዲያን ነበሩ ማለት አይቻል ይሆን ? አላውቅም ። የመርከቧ የሞተር ክፍል / Engine / የተሰራውም ሊቨርፑል በሚገኝ ድርጅት ነው ። ለታይታኒክ ሞተር ክፍል ሰራተኞች መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በዋተር ፍሮንት ሃውልት ቆሟል ።

ይህ ታሪካዊ ህንጻ በአሁኑ ወቅት ምን እየተሰራበት እንደሆነ ባላውቅም / ምናልባትም ለሽያጭ ቀርቦ ይሆናል / እንደ ታሪካዊነቱ በአግባቡ የተያዘ አይመስልም ። ሶስቱ በግማሽ ጨረቃ ቅርጽ የተሰሩት የፊት ለፊት በሮቹ ተዘግተዋል ። በጎን በኩል የሚገኘውም እንደዚሁ የታሸገ ነው - የዚህኛው ልዩነቱ ከበሩ ጀርባ የቆሻሻ ክምር መታየቱ ነው ። ምናልባትም የታይታኒክ ቅርጽ ይኖረው ይሆን በሚል ጥርጣሬ ራቅ ብዬ አጠናሁት ። ባለ ሶስቱ ፎቅ ህንጻ በምንም ተዓምር መርከቢቷን አይመስልም ። እረ ታይታኒክ ቅንጡ ህንጻ ነበረች ። ለነገሩ ለግንባታዋ የፈሰሰው ዶላር ቀላል አይደለም -  7.5 ሚሊየን ። 3547 ሰዎችን አሳፍራ በኩራት ነበር ባህሩን የምትሰነጥቀው ። አጠቃላይ ቁመቷም ቢሆን 11 ፎቅ ርዝመት ካለው ህንጻ ጋር የሚተካከል ነው ። ውስጧስ ቢሆን ዘመናዊ ሆስፒታልን ጨምሮ ምን የሌላት ነገር አለ ?

ህንጻውን እየራቅኩት ስሄድ በሆነ ነገር ላመሳስለው እየፈለኩ ነበር ። በል ቻዎ ስለው የታይታኒክ ማጀቢያ የሆነው የሴሊንዲዮን my heart will go on የሚለው ዜማ ከየት አባቱ እንደመጣ አላውቅም ። ውስጤ ለአፍታ ያህል የተንጫጫ መሰለኝ ፣

Every night in my dream
I see you , I feel you
That is how I know you go on
Far across the distance
And spaces between us
You have come to show you go on
Near , far , wherever you are
I belive that the heart does go on
Once more you open the door
And you’re here in my heart
And my heart will go on and on


እቺ ከአየርላንዱ ደብሊን እና ከጀርመኗ ኮሎኝ መሃል የምትገኝ መካከለኛ ከተማ የፊልም አምራች ድርጅቶችንም ቀልብ መግዛት የቻለች ናት ። captain America , In the name of the father , Sherlock holmes , Fast and furious 6 , Harry potter and the dealthy hallows የተባሉ ትላልቅ ስራዋችን ጨምሮ በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ፊልሞች ተቀርጾባታል ።

ዛሬ እነዚህ ታሪካዊ ቦታዋች በሙሉ ዋና ትኩረታቸው የፊልም ኢንዱስትሪውንና ጊነስ ቡክን መሳብ ሳይሆን በቅርቡ የሚከበረውን የገና በዓል ደማቅ ማድረግ ይመስላል ። Remember , if Christmas isn’t found in your heart , you won’t find it under a tree . የሚለው አባባልም ለበዓሉ የሚሰጠውን ግዙፍ ክብር አመልካች ነው ። ለማንኛውም መልካም ገና ይሁንላቸው ማለት ይገባል ።

ግልባጭ ፣
ጥቂት ቆይቶ ብቅ ለሚለው አትዮጽያዊው ገና ።

Wednesday, December 11, 2013

አሳዛኙ የመንግስት ሰራተኛ




የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር መረጃ እንደሚጠቁመው ኢትዮጽያ ውስጥ ከአንድ ሚሊየን በላይ የመንግስት ሰራተኞች ይገኛሉ ፡፡ እነዚህ ሰራተኞች አባቴ ለሚሉት መንግስት አቋርጠው የማያውቁት ጥያቄ ‹ ኑሮ ስለከበደኝ ደመወዝ ጨምርልኝ ! › የሚል ነው ፡፡ በቀደመው አሰራር ሰራተኞች በየሁለት አመቱ ጥቂትም ብትሆን የእርከን ጭማሪ ያገኙ ነበር ፡፡ ይህም ሁልግዜ ከፊታቸው የተንጠለጠለ የተስፋ ዳቦ እንዳለ ስለሚጠቁማቸው ለመጨበጥ ይተጉ ነበር ፡፡  / ርግጥ ነው በአንድ ወቅት 320 ብር የነበረውን ደመወዝ 420 ፤ 3152 የነበረውን የመምሪያ ኃላፊ ደመወዝ 4343  ያስገባ ጭማሪ ተከናውኗል  ፤ ያው በወሩ ጭማሪው ሻጭና አከራይ እጅ ተገኘ እንጂ /

‹‹ በመርህ ደረጃ ኑሮ እየከበደ እንደሚሄድ እገነዘባለሁ ፤ ግና በተወሰነ ርቀት ብር መጨመሩ ሳይንሳዊና አዋጪ አይደለም ! ›› የሚለው ኢህአዴግ ሰራተኛው ማደግ የሚገባው የሚታይና የሚቆጠር ሀገራዊ እድገት ሲያበረክት ነው በሚል የቆየው አሰራር ላይ ‹ ታሽጓል › የሚል ወረቀት ለጥፎ ነበር - በአራት ነጥብና በቃል አጋኖ በመታገዝ  ፡፡
‹‹ ታዲያ እስከዛስ ችግሩን እንዴት እንቋቋም ? ›› አባቴ የሚሉት ሰራተኞች ባገኙት የስብሰባ አጋጣሚ ሁሉ ጥያቄያቸውን ወረወሩ ፡፡

‹‹ በረሃብና በስቃይ ቀቀለን እኮ ?! ›› በየኮሪደሩና በየመሸታው ቤት ይህን ስሜት የተነፈሱት ደግሞ ኢህአዴግን የእንጀራ አባት ብለው የደመደሙት ናቸው ፡፡

የደመወዝ ጥያቄ ከለውጥ መሳሪያዎች አንጻር

መንግስት ለሁሉም ወገኞች በቂ ምላሽ መስጠት የሚቻለው ሳይንሳዊ አሰራርን በመዘርጋት ነው በሚል የጥናት ቁፈሮ ጀመረ ፡፡ ማዕድንን ፈልጎ ለማውጣት አታካች አመታትን አሳልፏል ፡፡ በመጨረሻም ቢፒአር / Business Process Reengineering / የተባለ የከበረ ድንጋይ መገኘቱ ይፋ ሆነ ፡፡ ከወጪ ፣ ግዜ ፣ ጥራትና ደረጃ መመዘኛዎች አንጻር አሰራሩ ቀልጣፋ ፣ ፍትሃዊና አንጀት አርስ መሆኑ ተነገረለት ፡፡ ሰራተኞች የፍልስፍናውን ሀሁ በየተቋማቸው በሶስት ቀን ጥልቅ ጥናት ከአኩዋ አዲስ ጋር አጣጣሙት ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ብዙዋቹ ቀድመው መማር የፈለጉት ስለ ደመወዝ የሚያትተውን ምዕራፍ ነበር ፡፡ ይህ ምዕራፍ ግን እዚህ ጥራዝ ውስጥ አልነበረም ፡፡ እንደውም ትንሽ ቆይቶ ሀሴትን ሳይሆን መርዶን ማዘሉንም አበሰረ ፡፡ ጥቂት የማይባሉትን ከእኔ አሰራር ጋር መጓዝ አትችሉም ፣ የትምህርት ዝግጅታችሁ በቂ አይደለም ፣ አመለካከት ሲቀነስ የተንጠለጠለ ብቃት እኩል ነው  C  ማይነስ በሚል ከስራ ዉጪ አድርጓቸዋልና ፡፡ በአንዳንድ መ/ቤትማ ብቀላና ፖለቲካ ስራቸውን ሰርተዋል ፡፡

ከአውሎ ንፋሱ የተረፉት ጥናቱን ተግባራዊ ለማድረግ ማበረታቻና የደመወዝ ጭማሪ የግድ ያስፈልጋል የሚል ዳግማዊ ጥያቄ ከማንሳት አልተቆጠቡም ፡፡ መንግስትም የሰራን ለመሸለምና ለማሳደግ የሚቻለው የዚህን ተከታይ ሳይንስ እውን በማድረግ ነው በሚል ሌላ ቁፋሮ ውስጥ ገባ ፡፡ ከአመታት በኃላም ሚዛናዊ የውጤት ተኮር / Balanced Score Card / ስርዓትን አስተዋወቀ ፡፡ በዘጠኝ ደረጃዎች የተዋቀረው ውጤት ተኮር ከስትራቴጂ ግንባታ ጀምሮ እስከ ክትትልና ግምገማ ድረስ የሚዘረዘር ነው ፡፡ ጥናቱ እንደ አሹ ቤት ስጋ የሚያስጎመዥ ነው ፡፡ በደረጃ ሰባት ላይ የሚገኘው ‹‹ አውቶሜሽን ›› የእያንዳንዱን ፈጻሚ ስራ መመዝገብና መተንተን የሚችል በመሆኑ ሰራተኛውን ከለጋሚው ለመለየት የሚያስችል ነው ተብሏል ፡፡ በሌላ አነጋገር አጭበርባሪው ፊርማ ፈርሞ ሹልክ ማለት ወይም መድረክ ላይ በሚያቀርበው አስመሳይ ተውኔት ብቻ ተላላ ሃላፊዎችን መሸወድ አይቸልም ፡፡ ፋብሪካና ኢንድስትሪ ውስጥ ባይሆንም ከቢሮ የሚታደለውን ስራ ቆጥሮ ይረከባል በኃላ ደግሞ ቆጥሮ ያስረክባል -  ይህ ማለት ግን የሚሰራው ንብረት ክፍል ውስጥ ነው ወይም ከጥበቃ ስራ ጋር በስተደቡብ ይዋሰናል ማለት አይደለም ፡፡ በፍጹም ፡፡ ርግጥ ነው ሳይንሱ አንድ ኃላፊ እንደ ጥበቃም እንደ ንብረት ክፍል ኤክስፐርትም ሁለገብ እንዲሆን ያበረታታል ፡፡ እንግዲህ በዚህ ምክንያት ነው ሳይንሱ ስራና ሰራተኛን ያገናኛል የተባለለት ፡፡

በመሆኑም ምርጥ ፈጻሚዎች ተገቢውን ሽልማትና የደመወዝ እድገት ለማግኘት እንዲችሉ በመነገሩ ስራው ተጧጧፈ ፡፡ በአንዳንድ ተቋማት የምርጥ ፈጻሚዎችና ምርጥ አመራሮች ፎቶግራፍ ሳይቀር መለጠፍ ጀመረ ፡፡ አመቱ መጨረሻ ላይ ሽልማትና ዕድገት የሚጠበቅ ቢሆንም መንግስት እፍርታም ሆነ ፡፡ ለምርጦች እውቅና ከመስጠት ይልቅ በርካታ ምክንያቶችን መደርደርን ‹‹ ደረጃ አስር ›› አደረገው ፡፡ ግምገማው ትክክል አይደለም ፣ በተቋሙ መሰረታዊ ለውጥ ካልመጣ ሰራተኞችም የተለየ አፈጻጸም ሊኖራቸው አይችልም … የሚሉትን እንደ ዋና ዋና ማሳያነት ማነሳሳት እንችላለን ፡፡

ዛሬ አገር ጥለው የሄዱት የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር አቶ ጁነዲን ሳዶ በአንድ ወቅት የመንግስት መ/ቤቶች ቢፒአርን እንዴት እንደሚጠቀሙበት በቂ ትኩረትና ዝግጅት ሳያደርጉበት ወደ እንቅስቃሴ በመግባታቸው መፍትሄ ሊያመጣ አልቻለም በማለት መግለጫ ሰጡ ፡፡ ለነገሩ ጆሮ ለባለቤቱ ባዳ ነው እንዲሉ ሆኖ እንጂ ቢፒአርና ቢኤስሲ ስልጠና ሲሰጥ ብዙ ቸግሮች መኖራቸውን መስማት ነበረባቸው ፡፡ አንደኛው ችግር በስልጠናው ወቅት ከሰራተኛው የተነሱ መሰረታዊ ጥያቄዎችን አሰልጣኞች በበቂ ሁኔታ መመለስ አለመቻላቸው ነው ፡፡ እናም አሰልጣኞች ወዴት እየሄዳችሁ ነው ? ሲባሉ ‹‹ ያልገባኝን ነገር ላልገባቸው ሰዎች ልነግርን ነው ›› አሉ ተብሎ እስካሁንም ይቀለዳል ፡፡

የመንግስት ሰራተኛው ሁለቱን የለውጥ መሳሪያዋች ለማስፈጸም ዛሬም እየተንገታገተ ቢሆንም ቃል በተገባለት የደመወዝ ጭማሪና በሳይንሳዊ አሰራሮቹ መካከል ያለው ተጨባጭ ቁርኝት ሊገለጽለት አልቻለም ፡፡ ብዙ ተቋማት ውስጥም የለውጡ ስራ መሬት የወረደ ፣ የሚታይና የሚቆጠር ከመሆን ይልቅ አንዳንዶች ‹ ኮስሞቲክ › እያሉ እንደሚጠሩት ሳምንታዊ ቅጽ መሙላት ፣ ደረት ላይ ባጅ ማድረግ ፣ ጠረጼዛ ላይ ስምና የስራ ድርሻን ማስተዋወቅ እየሆነ መጥቷል ፡፡ የአዲሱ አሰራር ግብ ይህ አይደለም ፤ ሰራተኛው አዲሱ አሰራር / ሳይንስ / ህይወቴን ለመቀየር የሚያስችል መሰረት የለውም የሚል ድምዳሜና የጥርጣሬ ዳርቻ ላይ አዳርሶታል ፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ መርፌ ከለገመ ቅቤ መብሳት አይችልም የሚባለውን ብሂል ይኮረኩራል ፡፡

አድጎ ያላደገው የውሎ አበል

ሌላው የመንግስት ሰራተኞች መሰረታዊ ጥያቄ የውሎ አበል ጉዳይ ነው ፡፡ እንደሚታወቀው ከ1993 ዓ.ም ጀምሮ ሲሰራበት የቆየው የውሎ አበል ክፍያ ዝቅተኛው 35 ከፍተኛው ደግሞ 70 ብር ነበር ፡፡ ይህ ክፍያ በተለይም ከ 2000 ዓም በኃላ አስቂኝ ገጽታ ይዞ ነበር ፡፡ ሰራተኛው እንደነገሩ የቆመ አልቤርጎን በ70 ብር ተከራይቶ ምግብ ሳይበላ ነበር በፈጣሪ ቸርነት ስራውን ሲሰራ የቆየው ፡፡ ይህ ችግር የመስክ ሰራተኞች መኪና ውስጥ እንዲያድሩ ፣ በየሄዱበት ዘመድ ብቻ ሳይሆን ዘመዳቸው ድንገት የተዋወቃቸውን ሰዎች እንዲፈልጉ ፣ አንድ አልጋ ለሁለትና ሶስት ሆነው እንዲከራዩ አድርጓቸዋል ፡፡

ከስንት አቤቱታ በኃላ አዲሱ የውሎ አበል ታህሳስ 27 ቀን 2004 ዓም በሚኒስትሮች ም/ቤት ቀርቦ ጸደቀ ፡፡ በዚህ ግዜ አልጋ ብቻ ሳይሆን ኑሮ ጣራ ያለፈበት በመሆኑ አበሉ ከፍተኛ እንደሚሆን ተጋኖ ተወርቶለት ነበር ፡፡ መንግስትም ለማስተካከያ 465 ሚሊየን 838 ሺህ ብር ተጨማሪ ማድረጉን ገለጸ ፡፡ ይህ ትልቅ የሚመስል ገንዘብ ሲተነተን ግን የብዙዎቹን አንገት አስደፋ ፡፡ አበሉ ወረዳን ፣ ዞንና ዋና ከተሞችን ብቻ ሳይሆን የደመወዝ እርከንንም ከፋፍሎ የሰራ ሆነ ፡፡ ለምሳሌ ያህል እስከ 2248 ብር ደመወዝ የሚከፈላቸው ሰራተኞች ሃዋሳ ከሄዱ 182 ብር ፣ ከ2249 እስከ 3816 ብር ደመወዝ የሚያገኙ 192 ብር ፣ ከ3817 ብር በላይ ደመወዝ ተከፋዮች ደግሞ 201 ብር ያገኛሉ ፡፡ ይህ በዋና ከተማ ደረጃ በመሆኑ ትልቁ ክፍያ ነው ፡፡ ሰመራ ፣ ባህርዳር ፣ ድሬደዋ ወዘተ ሲጓዙ ደግሞ የገንዘቡ መጠን እየቀነሰ ይመጣል ፡፡ ትንሹ የአበል ክፍያ እንደቅድም ተከተሉ 83 ፣ 92 እና 101 ብር ነው ፡፡

ብዙ የተወራለት የአበል ጭማሪ የወቅቱን የሆቴሎች የአገልግሎት ዋጋ ፍጹም ያላገናዘበ ነው ፡፡ አንድ ተራ አልጋ 90 እና 100 ብር በሚጠራበት በአሁኑ ወቅት 111 ብር ይዞ ከቤተሰብ መራቅን የመሰለ መሳቀቅና ቅጣት ከየት ይገኛል ? ይህ መስተካከልን የሚጠይቅ አንደኛው ችግር ሲሆን ሁለተኛው  ለመስክ የሚወጣን ሰራተኛ በአበል ማበላለጡ ተገቢ ያለመሆኑ ጉዳይ ነው ፡፡ አልጋውና ምግቡ እንደሆነ ለሁሉም እኩል ነው ፤ ታዲያ - የቢሮ ቢሮክራሲ ጫካና በረሃ ድረስ አብሮ እንዲጓዝ መፍቀድን ምን አመጣው ? በስራው ውጤት ከመጠበቅና ከፍትሃዊነት አንጻርም  ፍጹም የማይጠቅምና ትክክል ያልሆነ  አሰራር ነው ፡፡

የተጋነነ የታክስ መጠን

የኑሮ ውድነቱ ጫና በደመወዝ ጭማሪም ሆነ በውሎ አበል ማካካስና ማስተካከል ያልቻለው የመንግስት ሰራተኛ በመንግስት አይን እንቁላል የሚጥል ዶሮ ነው ወይም ሳያንገራግር የሚታለብ ላም ፡፡

የመንግስት ሰራተኛ እንደሌሎች ነጋዴዎች ወይም ባለሀብቶች የስራ ግብርን ለማስቀረት ፣ ለማስቀነስ ፣ ለማጭበርበር የሚያስችል መሰረት የለውም ፡፡ ምክንያቱም ግብሩ የሚቆረጥበት ገና ደመወዙን ከመቁጠሩ በፊት ነውና ፡፡ ዜጎች ግብር የመክፈል ግዴታ ያለባቸው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ሁሉም  ዜጋ ግብርን መክፈል ያለበት ፍትሃዊና እኩል በሆነ አግባብ መሆኑ አያጠያይቅም ፡፡ ይሁን እንጂ ትንሹ ደመወዝተኛ ትልቅ ግብር እንዲከፍል መደረጉ ያሳምማል ፡፡ በአመት ብዙ መቶ ሺህና ሚሊየን ብር የሚያስገቡት ነጋዴዎች ግብር በዛብን ብለው በመደራደርና በማስቀነስ ከገቢያቸው ጋር የማይመጣጠን ገንዘብ እየከፈሉ ጉልበት በሌለውና መድረሻ ቢስ በሆነ  ዜጋ ላይ መጨከን አግባብ አይደለም ፡፡

አንድ ምሳሌ እንውሰድ ፡፡ በህጉ ቀመር መሰረት ከታክስ ነጻ የሚሆኑት እስከ 150 ብር ገቢ ያላቸው ዜጎች ናቸው ፡፡ ከ 151 እስከ 650 ብር የሚያገኝ ሰው 10 ከመቶ ፣ ከ651 እስከ 1400 ብር የሚያገኘው 15 ከመቶ ፣ ከ1401 እስከ 2350 ብር የሚያገኙ 20 ከመቶ ፣ ከ2351 እስከ 3550 ብር የሚያገኙ 25 ከመቶ ፣ ከ3551 እስከ 5000 ብር የሚያገኙ 30 ከመቶ ፣ ከ5000 ብር በላይ የሚያገኙ ደግሞ 35 ከመቶ ይቆረጥባቸዋል ፡፡ ርግጥ ነው በሁሉም ስሌት ላይ ተቀናሽ የሚሆኑ ጥቂት ገንዘቦች አሉ ፡፡

በወር 3817 ብር ደመወዝ የሚያገኙት አቶ ፍርድ ያጣው 30 ከመቶ የግብር እዳ ሲከፍሉ  አንድ ሺህ 145 . 10 ያጣሉ ፡፡ በቀመሩ መሰረት 412 .50 ሳንቲም ሲቀነስላቸው 732 .60 በየወሩ ግብር ይከፍላሉ ማለት ነው ፡፡ ከዚህ ላይ ሰባት ከመቶ የጡረታው ሲወራረድ  267 .19 ይቀነስባቸዋል ፡፡ በአጠቃላይ ግብርና ጡረታው 999 .79 ስለሚያሳጣቸው ለግዜው ኪሳቸው የሚገባው ገንዘብ 2818 ብቻ ነው ፡፡ ለግዜው ያልኩት ድምር ውስጥ ያልገቡ መዋጮችን በማስቀረቴ ነው ፡፡

እዚህ ላይ ሶስተኛው የፖለቲካ አማራጭ ይሁን መንገድ እከተላለሁ የሚሉትን የአቶ ልደቱ አያሌውን ሀሳብ ማድነቅ ግድ ሊል ነው ፡፡ እኚህ ፖለቲከኛ በአንድ ወቅት ለመንግስት ሰራተኛ ደመወዝ ከመጨመር ይልቅ የተጋነነውን ታክስ መቀነስ ይጠቅማል ብለው ነበር ፡፡ እሳቸው ያነሱት ከኢንፍሌሽንና ከነጋዴው ነጣቂ እጆች ለማስቀረት በሚል ቢሆንም እኔ ደግሞ ከፍትሃዊነት አንጻር ጭምር የሚለውን እጨምርበታለሁ ፡፡ አህያውን ፈርቶ ዳውላውን ለመንግስት ሰራተኛው መስራት አይኖርበትም ….

የአቶ ፍርድ ያጣው የበዙ ቃል ኪዳኖች

በ80 ቢሊየን ብር ወጪ 5250 ሜጋዋት እንዲያመነጭ እየተገነባ ያለው ታላቁ የህዳሴ ግድብ የገንዘብ መሰረቱን ሀገር ቤት ነው ያደረገው ፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ የስራው 24 ከመቶ ተጠናቋል ፡፡ ለግንባታው ቃል ከተገባው 10 .2 ቢሊየን ብር ሊሰበሰብ የቻለው ግን 5.2 ቢሊየን ብር ብቻ ነው ፡፡

ቃል የገቡ ሰዋችና ድርጅቶች ሀሳባቸውን ለምን አጠፉ ? ወይም ለመክፈል ለምን መዘግየት ፈለጉ ? ብዙ የመላ ምት ምክንያቶችን መደርደር ይቻላል ፡፡ በጣም የሚያስገርመው ግን የመንግስት ሰራተኛ እንደሌሎቹ ቃሌን አጥፋለሁ ወይም ‹ ይብራብኝ › ቢል እንኳን አለመቻሉ ነው ፡፡ ምክንያቱም አንድ ሰራተኛ ሙሉ ደመወዙን በአመት ለመክፈል ቃል ከገባ ልክ እንደ ግብሩ ደመወዙን ከመጨበጡ በፊት በሂሳብ ክፍል ተቆርጦ ስለሚወሰድበት ፡፡ ስለዚህ አሁንም የመንግስትን ሰራተኛ ታማኝ ፣ ማምለጫ የሌለው ፣ ሳያንገራግር የሚታለብ ወዘተ ልንለው እንችላለን ፡፡ የህዳሴ ግድብ ግንባታ 76 ከመቶ ገና የሚቀር በመሆኑ ለቀጣይ አራትና አምስት አመታት አሁንም እንደ መርግ ከተጫነው ኑሮ ጋር የተለመደውን ክፍያ ቃል እየገባ ወይም ቃል እየተገባለት እንደሚከፍል ሳይታለም የተፈታ ነው ፡፡

አሁንም የ3817 ብር ደመወዝተኛውን አቶ ፍርድ ያጣውን እናምጣቸው ፡፡ የወር ደመወዛቸውን በአመት ለመክፈል ቃል ከገቡ በየወሩ የሚያስቆርጡት 318 ብር ይሆናል ፡፡ በግብርና ጡረታ 999 ብር ያጡት እኚህ ሰው ከግድቡ መዋጮ ጋር ሲደመርላቸው 1317 ብር ያስከረክማሉ ፡፡ በኪሳቸው የሚገኘው የተጣራ ገንዘብ ደግሞ ወደ 2500 ያሽቆለቁላል ፡፡

እንደሚታወቀው የሚኒስትሮች ም/ቤት የጤና መድህን ኤጀንሲ ማቋቋሚያ አዋጅን በ2003 አጽድቋል ፡፡ የኤጀንሲው አላማ በየተቋማቱ የጤና መድህን የሚስፋፋበትን መንገድ ማመቻቸት ነው ፡፡ ለዚህ ደግሞ የመንግስት ሰራተኞች ከደመወዛቸው ላይ 3 ከመቶ መዋጮ ያደርጋሉ ፡፡ ይህም ስርዓት በቅርቡ እንደሚጀመር በየተቋሙ ኦሪየንቴሽን ተሰጥቷል ፡፡ በመሆኑም የደመወዛቸው ሶስት ከመቶኛ ሲሰላ 114 ብር ነው ፡፡ ከደመዛቸው ላይ የሚያስቆርጡት ገንዘብ 1431 ሲመጣ ኪሳቸው የሚቀረው የተጣራ ብር ደግሞ 2386 ይደርሳል ፡፡ አቶ ፍርድ ያጣው አንገታቸውን አቀርቅረው ስለሚኖሩ ቤት አከራያቸው ለረጅም ግዜ ታሪፍ አልጨመሩባቸውም - በመሆኑም ለሁለት ክፍል ቤት በየወሩ 1200 ብር ይወረውራሉ ፤ ይህም የተጣራ ደመወዛቸውን 1186 ያደርሰዋል ፡፡ ከቤት ኪራይ ጫና ብቻ ሳይሆን ከአንዳንድ አከራዮች ግፍ ለመገላገል ኮንዶሚኒየም የተመዘገቡ ቢሆንም እድላቸውም እንደ ኪሳቸው ‹ ድሃ › ሆኖ አስካሁን ስማቸውን አዲስ ልሳን ጋዜጣ ላይ ሊመለከቱት አልቻሉም ፡፡

በቅርቡ የአዲስ አበባ መንግስት አዲስ ደንብ በማውጣቱ ለሁለት መኝታ ቤት በየወሩ 561 ብር ባንክ ማስቀመጥ ግዴታ ሆኖባቸዋል - በዚህም ምክንያት የተጣራ ደመወዛቸው 625 ብር ብቻ ነው ፡፡ ‹ ዘመድ አዝማድ  ለ4 ሺህ ጥቂት የጎደለው ብር  ይገሸልጣል እያለ ቢያማኝም እኔን ማቆሚያ የሌለው መዋጮ ደህና አድርጎ እየገሸለጠኝ ነው › የሚሉት  አቶ ፍርድ ያጣው በየቀኑ ለሚጨምረው ወርሃዊ አስቤዛ ፣ ለልጆች ት/ቤት  ፣ ለልብስና ጫማ ፣ ለትራንስፖርት ፣ ለእድር ፣ ለህክምና ፣  የመሳሰሉትን ክፍያዎችን እንዴት እንደሚሸፍኑ ፈጣሪ ብቻ ነው የሚያውቀው ፡፡ እንግዲህ ምርኮኛው ፣ የሚታለበውና ምስኪኑ የመንግስት ሰራተኛ በአስማት ነው የሚኖረው የሚባለው ለዚህ ነው ፡፡

ተረት ተረት  ?

መንግስት የመንግስት ሰራተኛውን ድካምና ጥረት ብቻ ሳይሆን የኑሮ ውድነቱንም ጫና ግንዛቤ ወስጥ በማስገባት ሰበቦቹን ከርክሞ በቂ የሚባል የደመወዝ ጭማሪ ማድረግ ይጠበቅበታል ፡፡ ሁለት ዲጂት እያደግን ባለንበት ወቅት ይህ አይቻልም የሚባል ከሆነ ደግሞ አንድ ዲጂትን በተግባር ማዋል ያቃተውን ሰራተኛ ለዚህና ለዚያ አዋጣ የሚለውን ልመናና ግዴታ መገደብ ይኖርበታል ፡፡ ቢያንስ ጥያቄውን ‹ አዋጅ › ከማድረጉ በፊት ገቢና ወጪውን ለአፍታ ያህል ማመዛዘንና ማስላት ይጠበቅበታል ፡፡

የላም በረት ? !