Monday, September 25, 2017

ደራሲው ጋዳፊ ለምን ሀሳቡን አልሆነም ?




የሊቢያው መሪ ሙአመር ጋዳፊ ፖለቲከኛ ፣ ሃሳብ አመንጪ እና ደራሲ ነው ። በረጅም የስልጣን ዘመን ቆይታው Escape to hell and others , My vision እና The Green Book የተሰኙ ሶስት ተጠቃሽ መጻህፍትን ለዓለም አበርክቷል ።

አዲስ የፖለቲካ ፍልስፍናውን በመጽሐፍ መልክ ማሳተም የጀመረው በ1975 ነበር ። የዴሞክራሲ ችግር መፍትሄ ፣ የኢኮኖሚ ችግር መፍትሄ እና የሶስተኛው ዓለማቀፍ ቲዎሪ ማህበራዊ መሰረቶች የሚሉ ሶስት ጥራዞችን በተለያዩ ግዜ ጽፏል ። ኋላ ላይ እነዚህን ጥራዞች አንድ ላይ በመሰብሰብ አረንጓዴው መጽሐፍ በሚል ለንባብ አብቅቷቸዋል ።

አረንጓዴው መጽሐፍ ዓለምን ብዙ ያነጋገረና ያከራከረ ስራ ነው ። ይህን መጽሐፍ የተማሩበት የሊቢያ ወጣቶች ብቻ አልነበሩም ። በፈረንሳይ ፣ ምስራቅ አውሮፓ፣ ኮሎምቢያ እና ቬንዚውላ ኮሌጆችና ዩኒቨርስቲዎች ተወያይተውበታል ፤ አውደጥናት ተካፍለውበታል ።

ጋዳፊ የፍልስፍና ውሃ ልኩን በአረንጓዴው መጽሐፍ ለማሳየት ሞክሯል ። በተለይ የምእራቡ ዓለም የዴሞክራሲ፣ ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ አስተምህሮ ጠማማ መሆኑን መነሻ በማድረግ የችግሮቹን መፍትሄ በአማራጭ አተያይ / ሶስተኛው አለማቀፍ ቲዎሪ / ለመተንተን ሞክሯል ።

ጋዳፊ በዚህ ጥራዝ ብዙ ርእሰ ጉዳዮችን ነው የመዘዘው ። በመጀመሪያ ክፍል ምርጫን ፣ የተወካዮች ም/ቤትንና ህዝበ ውሳኔን በእጅጉ ይኮንናል ። እንደርሱ እምነት ዴሞክራሲ የህዝቦች ስልጣን እንጂ የጥቂት እንደራሴዎች ሃብት አይደለም ። ህዝብን እንወክላለን ብለው በፓርላማ በሚሰበሰቡ አባላት ዴሞክራሲ እውን ሊሆን አይችልም ምክንያቱም እነሱ ከተመረጡ በኋላ ለራሳቸው ጥቅም ነው የሚንቀሳቀሱት ። በተለይ ፓርላማው በአንድ ፓርቲ የተዋቀረ ከሆነ የአሸናፊ ፓርቲ ፓርላማ እንጂ የህዝብ ፓርላማ መባሉ አግባብ አይደለም ። ጋዳፊ የወቅቱን የእኛ ሀገርን ፓርላማ ቀድሞ ነው የተቸው ማለት ነው ። እውነተኛው ዴሞክራሲ የሚገኘው በቀጥተኛው የህብረተሰብ ተሳትፎ ነው ። እውነተኛ ዴሞክራሲ ተግባራዊ የሚሆነው ብዙሃኑ በህብረት ወጥቶ ህዝባዊ ኮሚቴ እና ታላቅ የመማክርት ጉባኤ ሲዋቀሩ ነው ። ህዝበ ውሳኔም ቢሆን / Referendum / ዴሞክራሲን የማጭበርበሪያ ዘዴ እንደሆነ ጽፎታል ። ‹ አዎ › ወይም ‹ አይ › ብለው እንዲመርጡ የሚገደዱ ዜጎች ነጻ ሃሳባቸውን እንዲገልጹ አይደረግም ። በመሆኑም ይህ አይነቱ አሰራር ጨቋኝና አምባገነናዊ ነው ሊባል የሚገባው ።

ፕሬስንና ሃሳብን በነጻነት መግለጽን አስመልክቶም የግለሰቦችና የቡድኖች ያልተገደበ መብት እንደሆነ ይዘረዝራል « ፕሬስ ማለት ማንኛውም ሰው ራሱንና አስተሳሰቡን የሚገልጽበት ነው ፣ ሌላው ቀርቶ እብደቱን ጭምር ። የዚህ ሰውየ እብደት የሌላ ሰው ወይም ሰዎች እብደት ነው ተብሎ መቆጠር የለበትም ። በመሆኑም በጋዜጦች የሚወጡ አስተያየቶችን የህዝብን ሃሳብ አደርጎ ጥያቄ ማንሳት መሰረተ ቢስ ነው ፣ ምክንያቱም ጋዜጦች ያተሙት የዚያን ሰውየ አስተያየት ነውና »

በሁለተኛው ክፍል ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ተዳሰዋል ። እንደ ጋዳፊ ሃሳብ ደመወዝተኞች ለቀጠራቸው ግለሰብ ግዜያዊ ባሪያዎች ናቸው ። መሰረታዊ ፍላጎቶች/ ቤት ፣ ትራንስፖርት ወዘተ / በግለሰቦች ቁጥጥር ስር መዋል የለባቸውም ምክንያቱም ብዝበዛንና ባርነትን ያመጣሉና ። በሶሻሊስት ማህበረሰብ ውስጥ ሰዎች የሚሰሩት በሽርካነት እንጂ ለደመወዝ ብለው አይደለም ። በሌላ ሠው ቤት የሚኖሩ ሰዎች ማለትም ኪራይ የሚከፍሉም ሆነ የማይከፍሉት ነጻነት አላቸው ማለት አይቻልም ። መሬት የማንም ሃብት አይደለም ነገር ግን ማንኛውም ሰው በመሬት ላይ ማንንም ሳይቀጥር የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን ይችላል ። የቤት ሰራተኝነት የዘመናዊው ዓለም ባርነት ነው ። እናም የቤት ስራ መከናወን ያለበት በነዋሪዎቹ ነው ።

ሶስተኛው ክፍል ማለትም የሶስተኛው ዓለማቀፍ ቲዎሪ ቤተሰብን ፣ ጎሳን ፣ ብሄርን ፣ ሃገርን ፣ አናሳ ብሄርን ፣ ሙዚቃን ፣ ስፖርትና ሴቶችን ይዳስሣል ። ሌላው ቀርቶ ጥቁር ህዝቦች ወደፊት አለምን / ቀደም ብሎ ቢጫዎች ፣ አሁን ደግሞ ነጮቹ እየገዙ ነው / ይመራሉ ይላል ። ስፖርት ልክ እንደ ጸሎት ግላዊ ጉዳይ መሆኑን ይገነዘባል ። ቦክስ እና ነጻ ትግል ግን የሰው ልጅ ገና ከአረመኔነቱ አለመላቀቁን የሚያሳዩ ድርጊቶች ናቸው ።

ጋዳፊ ቤተሰብ ከመንግስት የበለጠ አስፈላጊ ተቋም እንደሆነ በሚከተለው መልኩ ያምናል  « ቤተሰብ እንደ እጽዋት ነው ። ቅርንጫፍ ፣ ግንድ ፣ ፍሬና ቅጠል ያለው ። እጽዋት የመነቀል ፣ የመድረቅ እና የእሳት አደጋ እንደሚያጋጥማቸው ሁሉ ቤተሰብም ህልውናው በብዙ ነገሮች ይፈተናል ። ያበበ ማህበረሰብ ማለት ግለሰቦች በቤተሰብ ውስጥ ቤተሰቦች ደግሞ በማህበረሰብ ውስጥ ማደግ ሲችሉ ነው ። ቅጠል ለቅርንጫፍ ፣ ቅርንጫፍ ለዛፍ እንዲሉ ግለሰብም በቤተሰብ ውስጥ የጠነከረ ትስሥር አለው ። ግለሰብ ያለ ቤተሰብ ትርጉም የለውም ። የሰው ልጅ እንደዚህ አይነቱን ትስስር ከጣለ ስር የሌለው ሰው ሰራሽ አበባ ነው የሚሆነው »

ጋዳፊ ለጎሳ መራሹ የአፍሪካ ህዝብም ጠቃሚ ስንቅ ያቀበለ ይመስላል ። ማህበራዊ ትስስር ፣ አንድነት ፣ ቅርበትና ፍቅር ከጎሳ ይልቅ በቤተሰብ ይጠነክራል ፤ ከሀገር ይልቅ በጎሳ ይጠነክራል ። ከዓለማቀፍነት ይልቅ በሀገር ይጠነክራል ። ጎሳ ትልቅ ቤተሰብ ነው ... ለጎሳ ትልቁ መሰረት ደም ነው ... ጎሳ አባላቱን የሚከላከለው በመበቀል ነው ። ጎሰኝነት ናሽናሊዝምን ያጠፋል ፤ ምክንያቱም የጎሳ ታማኝነት ከሀገር ታማኝነት የላቀ ነው ። በሀገር ውሰጥ የሚገኙ ጎሳዎች የሚጋጩ ከሆነ ሀገር ችግር ውሰጥ ይወድቃል ። ብሄርተኞች ፍላጎታቸውን በሃይል የሚገልጹ ከሆነና የራሳቸውን ፍላጎት የሚያሰቀድሙ ከሆነ ሰብዓዊነት ላይ አደጋ ይፈጠራል በማለት ስጋቱን ክፍላጎቱ ጋር አዛምዶ መርሁ ላይ አስፍሮታል ።

የአንድ ሀገር ህዝቦች የሚበየኑት በቦታው ላይ በመፈጠራቸው ብቻ አይደለም ። ይህ መሰረታዊ ነገር ሊሆን ይችላል ። ከዚህ በተጨማሪ ግን ለረጅም ግዜ በአንድ ላይ በመኖር የጋራ ታሪክ ፣ ቅርስ እና ተመሳሳይ እጣ ፈንታ ሲኖራቸው ነው ። ህዝቦች ከደም ትስስር ይልቅ ሀገራዊ አንድነትና የኔነትን በጋራ ይዛመዳሉ ።

ሴቶች ከወንዶች እኩል አይደሉም በሚባለው ብሂል ጋዳፊ አይስማማም ። ሴቶች እኩል መስለው የማይታዩበትንም ሳይንሳዊ ምክንያት በዝርዝር አስቀምጧል ። ሴቶች አንስታይ ወንዶች ተባእታይ ናቸው ። ባለሙያዎች እንዳረጋገጡት ሴቶች በየወሩ ደም ሲያዩ ወንዶች አይኖራቸውም ። ሴት ደም ካላየች ነፍሰጡር ናት ። ነፍሰ ጡር ስትሆን ለአመት ያህል ንቁ ተሳታፊ አትሆንም ። ልጅ ስትወልድ ወይም ሲያስወርዳት ደግሞ በ ፒዩፐሪየም / Puerperium / ትሰቃያለች ። ወንድ ይህ ሁሉ ስቃይ አይደርስበትም ። ከወለደችም በኋላ ለሁለት አመታት ታጠባለች ። ጡት ማጥባት ማለት ሴት ከልጅዋ የማትለያይበት በመሆኑ አሁንም ሌሎች እንቅስቃሴዎቿ ይቀንሳል ። በመሆኑም ሌላን ሰው ለመርዳት ቀጥተኛ ሃላፊነት መውሰድ በእሷ ላይ ይወድቃል። ያለ እርሷ ብርቱ ድጋፍ ያ ፍጡር ይሞታል ። ወንድ በሌላ በኩል አያረግዝም ፣ አያጠባም ::

ጋዳፊ በአረንጓዴው መጽሐፍ ታላላቅ ሀሳቦችን አንስቷል ። በክፍል አንድ ስልጣን የህዝብ መሆኑን እንመለከታለን ። ግለሰቦች ሊያብዱ ይችላሉ ይህ ማለት ግን ማህበረሰቡ አብዷል ማለት አይደለም በሚለው ነጥብ ዙሪያ ፕሬስ ሃሳብን መግለጫ ነጻ መሳሪያ መሆኑ ተሰምሮበታል ። በሁለተኛው ክፍል ለኢኮኖሚው ችግር መፍትሄው ሶሻሊዝም መሆኑ ተቀምጧል - በእያንዳንዱ ቤት ወስጥ የሚኖር ዜጋ የቤቱ ባለቤት እንጂ ጭሰኛ መሆን የለበትም የሚል የሚደላ አቋም ይታያል ። የአስቂኝም አስደናቂም ስብስብ በሆነው ሶስተኛ ክፍልም ሴት ከወንድ ታንሳለች ማለት የተፈጥሮ ህግን መካድ ነው የሚል ጠንካራ አቋም ይገኛል ።

ደራሲው ጋዳፊ ከፖለቲከኛው ጋዳፊ ጋር ተጣጥሞ ቢዘልቅ መልካም ነበር ። በተለይ በዙሪያህ የተኮለኮሉ ሰዎች / የተለያዩ ፍላጎት ያላቸው / የስብእና አምልኮ እየገነቡልህ ሲሄዱ ዝም ካልክ መቀበሪያህ እየተማሰ መሆኑ ማወቅ ይገባል ። ። ጋዳፊ መርሁ እንዲዘመር እንጂ እንዲሰራበት ለማድረግ ያልቻለበት አንደኛው ምክንያትም ይሄው ነው ። ጹሑፍህን ደጋግመህ በፍቅር ታነበዋለህ እንጂ ደፍረህ አርትኦት አታደርገውም ። በዚያ ላይ ፍልስፍናን ለማሰብና ለመራቀቅ እንጂ ሆኖ ለመኖር ይከብዳል ።




Wednesday, September 13, 2017

« በፍቅር ሥም » ከጥቅል አደረጃጀት አንጻር



የአለማየሁ ገላጋይን « በፍቅር ስም » ለመተቸት የሚነሳ ሀያሲ በምን ርዕሰ ጉዳይ ስር ልጻፍ ብሎ የሚጨነቅ አይመስለኝም ። መጽሐፉ በዘርፈ ብዙ የሃሳብና የትርክት ሃዲዶች ላይ ስለሚጋልብ አንዱን የታሪክ ሰበዝ መዞ ምልከታንና ሙያዊ ትንተናን ማዋሃድ ይቻላል ።

እኔ እንግዳ በመሰለኝ የመዋቅር አደረጃጀት እና ፍሰት ላይ አተኩራለሁ ። ደራሲው እኔ በተሰኘው የአተራረክ ስልቱ ጽሁፉን የሚጀምረው « በሴት የመከበብን ጥቅም የምናውቀው እኔና ጠቢቡ ሰለሞን ብቻ ነን » በማለት ነው ። የታሪኩ አባት ትንሹ ‹ ታለ  › ነው ። ታለ ይህን የሚነግረን በጥቅሙ በረከት ፈግጎ ነው ። ወጣቱ ታለ በመጽሐፉ መዝጊያ ላይ በተመሳሳይ ዜማ የሚከተለውን ይናገራል « የኛ አስር ደቂቃ በእርሱ / ቹቹ / ስንት እንደሆነ የማውቀው እኔ ነኝ » ታለ ይህን የሚነግረን በህመምና ፀፀት ውስጥ ሰምጦ ነው ።

ታለ የፍቅርና ፀፀት ጥለትን እየለበሰና እያወለቀ የሚዘልቅ ገጸባህሪ ነው ። ደራሲው ይህን የታሪክ ጉዞ የሚያሳየንና የሚነግረን በተለመደው የገጸባህሪ የበቀል/አሸናፊነት ፍትጊያ አይደለም ። የታሪኩ መረማመጃዎች ጥቅል ሰብዕናዋች/ ማንነቶች ናቸው ። አንዱ ጥቅል ቢዘንና አንጓቼ / ባልና ሚስት / ናቸው ። ይህ ጥቅል አውቶብስ በመሰለው ቤተሰባዊ ጎጆ / በነገራችን ላይ የቤተሰቡ መኖሪያ በገጽ 22-23 በአስቂኝ መልኩ ተገልዿል / ውስጥ እንደ ሹፌርና አውታንቲ ሊቆጠር የሚችል ነው ። ሹፌርና ረዳት በሳንቲም መጋጨታቸው አይደንቅም ። አንድ ቤት የሚኖሩ ባልና ሚስት ግን ወንድን ልጅ / ታለን / የግላቸው ለማድረግ የማያባራ ጦርነት መከፈታቸው ያልተለመደ / bizarre / ነው ።

« እግዚአብሄር የሰጠኝን ወንድ ልጅ የገዛ ሚስቴና ልጆቼ ነጠቁኝ » ይላል አባወራው
« ከመላእክት እስከ አጋንንት ደጅ የረገጥኩበትን ልጄንማ አልተውም » ትላለች እማወራ

በዚህ መነሻነት ጥቅሉ እየተፈታ ሌላ ግዜ እየተተረተረ ታሪኩንና የታሪኩን ማህበረሰብ ያናጋዋል ። በስድብና ሽሙጥ አረር ይጠዛጠዛሉ ። የቅናትና ጥርጣሬ ዳመራ በየግዜው ይለኮሳል ። ሰባት ሴት ልጅ መውለዳቸው ያልተዋጠላቸው አባወራ ሰባት ስድቦችን ነው የወለድኩት እስከማለት ይደርሳሉ ። በመልክ ለየት ያሉ ልጆችን ሳይቀር በተጠየቅ ይሞግቷቸዋል ። ጥቁሯን አበባ « ለመሆኑ የአፍሪካ ህብረት ሲቋቋም ተረግዛለች ? » ቀይዋ ስምረትን « መልኳ ሁሉ የእንግሊዝ ነው ፣ እኔ የምለው እንግሊዝ ሲመጣ ነው የተወለደችው ? » ረቂቅን ደግሞ « ይሄ ባኒያንኮ ያልደረሰበት ቦታ የለም » በማለት የነገር ጅራፋቸውን ይተኩሳሉ ። ባልና ሚስቱ በሚታክት መልኩ ይናቆሩ እንጂ ችግር በመጣ ግዜ እንደ ማግኔት ይፈላለጋሉ ፣ ጥቅሉ ማንነት ውስጥ ለአደባባይ አይናፋር የሆነ መተሳሰብ አለ ።

ሁለተኛው ጥቅል ሰባቱ ሴቶች ልጆች ናቸው ። አውቶቡስ በመሰለው ቤት ውስጥ ተሳፋሪ ይምሰሉ እንጂ መኪናው እንዳይገለበጥ ወይም ተበላሽቶ እንዳይቆም ምሶሶ ሆነው የቆሙ ናቸው ። ለምሳሌ የአቶ ቢዘን ጡረታ ስለማያወላዳ እናታቸውን በጉሊት ስራ ይረዳሉ ። በተቃራኒው አባታቸው ጠጅ ቤት ከሰው ጋ ሲጣላ ተሰብስበው ሄደው ወግረው በድል ይመለሳሉ ። ይህም የቢዘን ፍርጎ የሚል ስያሜ ቢያሰጣቸውም አባታቸው በሰፈሩና በየካቲካላው ቤት እንዲፈራ አድርጓል - ከሴት ልጅ ባህሪ አኳያ ግን ያልተለመደ ነው ።

ይህ ጥቅል ገጸባህሪ ለየት የሚልበት ሌላም ጉዳይ አለው ። ቤተሰባቸውን ያፍቅሩ እንጂ ለሌላው እምብዛም ፍቅር የላቸውም ። በተለይ ወንድን በማባረር ተመሳሳይ አቋም ነው ያላቸው ። የርስ በርሳቸው ምክር « እንግባ ቢልሽ አትግቢ ! እንውጣ ቢልሽ አትውጪ ! » ብቻ ነው ። ፍቅር ተፈጥሯዊ ጸጋ ስለመሆኑ ፊት አይሰጡም ። ድንገት ከመካከላቸው አንዷ ፍቅር ሽው ያለባት ግዜ እንኳ መቀመጫ ሲያሳጧት ይታያል ። ወንዳወንዴዋ ቹቹ እንኳ ሰለወደዳት ልጅ እንዲወራ አትፈቅድም ። ይህ ከሴት ልጅ ስስ ልቦናና ተቃርኗዊ ትስስር አንጻር ያልተለመደ ይመስላል ።

ሶስተኛው ጥቅል አራቱ ስፖርተኞች ናቸው ። ደራሲው በዚህ ሃዲድ እንድንጓዝ የፈለገው የልጅነትን ሌላኛው ገጽታ እንድንመለከት ብቻ አይደለም ። እንደ ሽክና አይነት ቀልደኞች ቆምጫጫውን የታሪክ ጉዞ እንዲያለሳልሱት ብቻ አይደለም ። እግርህን ከፍተህ የምትሄደው ጭገርህን ስላላበጠርክ ነው እያለ በግድ መጣላት የሚፈልገውን የ ‹ ቲኔጀር › ሞት አይፈሬነት ለመጠቆም ብቻ አይደለም ። የወንድነት ክትባት የሚፈልገውን ታለን ለማከምም ጭምር ነው ። ስፖርተኞቹ ሰፈር የምታደርሰው ወንዳወንዴዋ ቹቹ መሆኗን ስናስብ ግን በቤተሰቡ ውስጥ ያለውን ሁለተኛ ‹ ቢዛሪ ›ጉዳይ እናጤናለን ።

በሌላኛው ጥቅል አደረጃጀት ውስጥ የተቀረጹት ሶስቱ ወታደሮች ናቸው ። ወታደሮቹ በአፋዊ ገጽታቸው ይለያዩ እንጂ በሀገር ፍቅር ጽናታቸው አንድ ናቸው ። ብዙ ግዜ ለመዝመትና ለመሞት የቆረጡ ናቸው ። ተሸንፈው እንኳን አንዲት ህገር በሚለው መንግስቱ ስም ለመለመን አይሳቀቁም ። መንግስቱን ሳይሆን ታሪካዊ መርሁን አሻግረው ያያሉ ።

የወታደሮቹ ሌላኛው ውክልና ሀገር የገባችበትን ውጥንቅጥ ፈተና ማሳየት ነው ። በማህበረሰቡ ውስጥ አፈሳ ያስከተለውን የፍርሃት ቆፈንና የአስተዳደር መናጋት እንመለከታለን ። ፍርሃት ምንያህል ሀገራዊ ኩይሳ እንደሰራ ለማውቅ የአእምሮ ዝግምተኛው ቹቹ እንኳ መደበቂያ ሲፈልግ መታየቱ ነው ። ሻምበል ጠናጋሻውን ስናስብ ደግሞ ደራሲው ጦር ሰራዊቱ ውስጥ ያነበቡ ፣ የተማሩና ህዝባዊ ፍቅር የተላበሱ ግለሰቦች መኖራቸውን ለመጠቆም ብቻ እንዳልቀረጸው እንረዳለን ። ሻምበሉ ለታሪኩ እንድርድሮሽ መረማመጃነት አገልጋይ ነው ። ሻምበሉ ለታለ ያበረከተው የማይታመን ነገር ግን ጠቃሚ ስጦታ ቀጣዩ ጥቅል ስብእና የደረጀ እንዲሆን አግዟል ።

በዚህ መሰረት ለጥቆ የምናገኛቸው ታለን እና ሲፈንን ነው ። ርግጥ ነው በታለ ውስጥ ቹቹ ፣ በሲፈን ውስጥም ቹቹ አለ ። ቹቹ ‹ ኮመን ዶሚነተር › ነው ። የታለና ሲፈን ፍቅር አይኑን ገልጾ ከፍተኛ ደረጃ / Climax / የደረሰው ሻምበሉ ከከፈለው ጥሎሽ በኋላ ነው ። ጥሎሹ ሲፈን እንድትዝናና ታለ በአዲሱ አለም ላይ አይኑን እንዲከፍት አስችሎታል ።

ሲፈን በርግጥም የአውሊያ ፈረስ ትመስላለች ። ጋልባ ጋልባ ስድስተኛው ጥቅል ገጸባህሪያት ሰፈር የምታደርሰው እሷ ናት ። ደራሲው ይህን በ ‹ ጃክሰኖች › መስሎታል ። አምስቱ ጃክሰኖች የተለያዩ የሙያ ባለቤት ሲሆኑ በሚገናኙበት ጫት ቤት ውስጥ የማያነሱትና የማይጥሉት ርዕሰ ጉዳይ የለም ። እውቀት ጠገብ / ለምሳሌ ከታሪኩ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስላለው የአውሊያ ጉዳይ ተነስቶ አጥጋቢ ምላሽ ሲሰጡ ይታያል / ሆነው በሚፈልጉበት የስራ መስክ መሰማራት ያልቻሉትን የሀገራችንን ምሁራን ይወክላሉ ። ተጠየቃዊ ሙግቶች የክብርና የአደባባይ አጅንዳ ከመሆን ይልቅ በየስርቻው የሚጣሉ የጋን ውስጥ መብራት መሆናቸውንም ያሳያል ።

« በፍቅር ስም » በጥቅል ገጸባህሪያት አደረጃጀት ውስጥ ነው የሚያልፈው ። ጥቅሉ እየተፈታ የሚሰበሰብ ፣ እየተሰብሰብ የሚፈታ ነው ። ጥቅሉ ለታሪኩ መጓጓዣ ምንጣፍ ነው ። የጎሉ ተናጥላዊ ባህሪያት ቢኖሩ እንኳ በአንድም ሆነ በሌላ ምክንያት ጥቅል ውስጥ እንደቀንዳውጣ ወጣ ገባ ማለታቸው አይቀሬ ነው ። ደራሲው ተናጥላዊ ባህሪያትን አጉልቶ ለመለየት የማይረሳ ምልክት ለጥፎባቸዋል ። ለምሳሌ አቶ ቢዘን ባወሩ ቁጥር ‹ ጣ › ይላሉ ። ቹቹ ‹ ቲሽ ! › ማለት ይቀናታል ። የታለ እናት ‹ ኦሆሆይ › በማለት ግርምታቸውን ይተነፍሳሉ ። ሻምበል ሲጠይቅም ሲመልስም ‹ ጥሩ › ን ያስቀድማል ።

እንደ ጥቅልም እንደተናጠልም የሚታየው ታለ ማነው ? ምን ይፈልጋል ? ስንል ወደ ጭብጡ መንደር እንደርሳለን ። በዚህም ረገድ ጥቅል ጉዳዮች ይገኛሉ ። ወንዳወንድነትን ማግኘት በዋናነት ደግሞ አውሊያና ጥንቆላን መዋጋት ። ታለ ህብረተሰቡ « ሴታሴት » ነህ ብሎ ስለፈረደበት ከዚህ የጅምላ ንቀትና ተጽእኖ ለመላቀቅ ያላሰለሰ ትግል ያከናውናል ። ህበረተሰቡ ተፈጥሮውን ተቀብሎ እንኳ እንዲኖር አልፈቀደለትም ። ወንዳወንድ እንዲሆን የተመረጡ ወንዶች ጋር ይውላል ። ወታደር በመሆንና በመሞት ወንድነት የሚገኝ ከሆነ እዘምታለሁ እስከማለት የደረሰ ነው ። የህብረተሰቡን ጥያቄ የተቀበለው ግን ራሱ ህብረተሰቡን በመንቀፍ ነው ። ነቀፌታው ገደብ የለውም እናቱን ፣ አባቱን ፣ ጃክሰኖችን ፣ ሲፈንን ፣ እህቶቹን ፣ ቹቹን ሳይቀር ይተቻል - ያሽሟጥጣል ። ድንኳን መትከልና መንቀል የወንድ ንፍሮ መቀቅልን የሴት ስራ ያደረገው ማነው ? ይላል ። የእንስሣት ሴታ ሴት ይኖር ይሆን እያለ ደግሞ ፈጣሪውን ይሞግታል ።

በሌላ ፊቱ በጥንቆላና ድግምት የእኔን በሽታ ወደ ቹቹ አዙራ ለጥፋተኝነትና ለጸጸት የዳረገችኝ እናቴ ናት በማለት ከእናቱ ጋር የስነልቦና ጦርነት ያካሄዳል ። ሲፈንም ፍቅረኛዬ ሳትሆን በእናቴ እኔን ታገልግል ዘንድ የተመረጠች አውሊያ ናት ብሎ ያምናል ። ሻምበል ይህን ቤተሰባዊ እምነት በማስቀየር የቹቹ በሽታ የአእምሮ ዝግመት ችግር መሆኑን ቢነግረውም አይቀበልም ። ስንት የታገለችለትን እናቱን ፊት ይነሳል ። በርግጥ አውሊያ ልክ እንደ አፈሳው ምን ያህል በሰፈርተኛው እንደሚፈራ እንገነዘባለን ።

ደራሲው በፍቅር ስም ፍቅር አልባ መሆን አለ የሚል ይመስላል ።