Thursday, February 13, 2020

ተስፋዬ ገብሬ ያስፈልገናል



እናት ኢትዮጽያ ውዲቷ ሀገሬ
በጣም ይወድሻል ተስፋዬ ገብሬ

በዚህና በመሳሰሉት ጥቂት ዘፈኖቹ እኛም እንወደው እናከብረው ነበር ፡፡ ዛሬ ደግሞ ማርቆስ ተግይበሉ በተባለ አጥኚ አማካኝነት / የበጎ ሰው ሽልማት የሚገባው / በስፋት አወቅነው ፡፡ ያልተሰሙ ሙዚቃዎቹን አዳመጥን .... ያልተሰሙ የህይወት ታሪኮቹን ሰማን ... ያልተነገሩ ህመሙን ፣ ህልሙንና ስሜቱን ተጋራን ፡፡

ተስፋዬ ገብሬ በብዙ ቋንቋዋች ዘፍኗል ፡፡ ጥበቡን ለጥበብነት ማቀንቀኑ ብቻ ሳይሆን ብዙ ርምጃ ተጉዞ ስለ ሀገሩ ኢትዮጽያ ለውጩ አለም ሰብኳል ፡፡ የቀለምና ቋንቋ ልዩነት ሰብዓዊነትን በደፈጠጠበት በዛን ወቅት ሙያውን ለማንገስ ፣ ስውነቱን ለማስከበር  ብሎም ሀገራዊ ክብሩን እንደ ሰንደቅ ከፍ አድርጎ ለማውለብለብ የላቀ ሚና ተጫውቷል _ እሱ እንደሚለው በነጮች ሰፈር ብቸኛው ጥቁር አቀንቃኝ በመሆን ፡፡

በአርትስ ወግ ላይ የቀረበው የተስፋዬ ገብሬ ተከታታይ ፕሮግራም አስደሳች፣ አሳዛኝና ልብ የሚነካ ነበር ፡፡ ለሀገሩ፣ ለቤተስቡና ለህዝቡ  የነበረውን ጥልቅ ፍቅር በመለኪያ ቀምሮ ይሄን ያህል ነበር ለማለት ይከብዳል ፡፡ ሀገሩን ውዲቷ እንዳላት ሁሉ አባቱ አቶ ገብሬንም በስም እየጠቀሰ አወድሷል ፡፡ ሌላው ቢቀር የሀገሩ ተራራና ዛፎቹ ምን ያህል እንደናፈቁት እንዲያውቁለት ይመኝ ነበር ፡፡ እስትንፋሱ እስከተቋረጠበት እለት ድረስ ታላቅ ክብር ስለሚገባት ኢትዮጽያ ልብ በሚያርደው ድምፁ አቀንቅኗል ፡፡

ወደድንም ጠላንም የተስፋዬ ገብሬ ዜማና ሀሳብ ዛሬም ያስፈልገናል ፡፡ ለታመመችው ፣ ለቆሰለችው ከዚያም አልፎ ስጋት ተራራ ላይ አቁመው ክኋላ በርግጫ ቁልቁል ለመጣል ላሰፈሰፉት < እንክርዳድ > ልጆቿ የተስፋዬ ዜማና ሀሳብ መታደጊያ መንገድ አለው ፡፡ ተስፋዬ እናት ነው ነው የሚላት ፟ ኢትዮጽያን ፡፡ የላቀች መሆኗን ለማሳየት ውዲቷን ይጠቀማል ፡፡ ይሄ ሁሉ አልበቃ ብሎት በጣም እወድሻለሁ እያለ ነው ፡፡ በጣሊያንኛና በእንግሊዘኛ የሚወዳት ሀገሩን ሌሎች እንዲያውቁለትና እንዲወዷት መፅሀፍ አዘጋጅቷል / ወደፊት ያገባናል ባዮች ካሉ ሊታተም የሚችል / ካሴቱና መፅሃፉ ተሸጦ እንዲሰጥለት የተናዘዘው ደግሞ ውሃና መብራት ለሌላቸው ህዝቦች ነበር ፡፡

በተቃራኒው ዛሬስ ?...  < እቺ ሀገር ...  > እያለ የሚያንጠለጥላት ህዝብ ቁጥሩ ቀላል አይደለም ፡፡ ሀገሩን በእናቱ ለመመሰልም ሆነ ውዴ ብሎ ለመጥራት በራስ የመተማመን ትከሻ አጥቷል ፡፡ ወሽመጡ በራሱ አይናፋርነት ወይም በፖለቲካ ያገባናል ባዮች ሴራና ማስፈራሪያ ተበጥሷል ፡፡ ስለወለደችው ኢትዮጽያ ሳይሆን በማደጎነት ሰለተሾሙለት ክልሎች አብዝቶ ተጨናቂ ሆኗል ፡፡ እውነቱ ግን የሺህ እንጀራ እናቶች ልጥ የአንዷን ወላጅ እናት ፍልጥ ለማሰር አለመቻሉ ነው ፡፡

ዜማችንም ሆን ተግባራችን ከትልቁ ግንድ ወደ ቅርንጫፍች እንዲፈስ መትጋት ግድ ይላል ፡፡ የጋራ እናታችንን አንድም በሞራል  ሲቀጥልም በህግ የምናከብርበት አሰራር በሁሉም አካላት ተግባራዊ መሆን ይኖርበታል ፡፡ ስለጋራ እናታችን ሳናዜም ሰላም እና ብልፅግን መመኝት ከንቱነት ነው ፡፡ እናም በልበ ሙሉነትና ሳንሸማቀቅ የተስፋ
ዬን ዜማ ተውሰን የሚከተለውን ማዜምም መሆንም ይጠበቅብናል ፡፡

እናት ኢትዮጽያ ውዲቷ ሀገራችን
እናስበልጥሻለን ከየክልሎቻችን