Sunday, July 22, 2012

‎ጠ/ሚ/ር መለስ ሲመለሱ ….‎



መቼም ዓለም የተቃርኖ ሙሌት ናት፡፡ ብርሃን ስንል ጨለማ፣ ሰማይ ስንል ምድር፣ ጎፈር ስንል ዘውድ፣ ደስታ ስንል ሀዘን፣ ህይወት ስንል ሞት የሚባሉት የቁርጥ ቀን አዛማጆች በአእምሮአችን ሳይጠሩ ከተፍ ይላሉ ፡፡

ከዚህ እውነት አንወጣም ፡፡

እንደሚታወቀው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ታመው ህክምና በመከታተል ላይ ናቸው ፡፡ እሳቸው ባይናገሩም ሌሎች ግን ስለሳቸው ከላይ በተገለጸው እውነት መሰረት ሀሳባቸውን ይሰነዝራሉ ፡፡ የመንግስት ኃላፊዋች ድነው ይመለሳሉ ሲሉ ሌላው ህመሙ አስጊ ስለሆነ አይተርፉም ይላል፡፡ ክርክሩ ይጡዝ እንጂ ነባራዊውን እውነት የሚዳኘው ፈጣሪ ነው፡፡ አሁንም አንዳንዶች ወሳኙ ሀኪሞች ናቸው ሊሉ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ሁለቱ ጫፎች መሳሳብ ስላለባቸው ፡፡ ሁለቱ ጫፎች ለስነፍጥረትም ሆነ ለቴክኖሎጂው መሰረት መሆናቸውም ይታወቃል ፡፡

እኔም ሁለቱን ጫፍ ተንተርሼ በአቶ መለስ ዙሪያ ወግ ለመሰለቅ አሰብኩ ፡፡ አቶ መለስ ድነው ቢመለሱና አያድርግባቸውና አቶ መለስ ቢያርፉ በሚሉት ሀሳቦች ላይ ፡፡ ቆይቼ ሳስበው ‹ ቢያርፉ › የሚለው ሀሳብ ከይሲ ሆኖ ተሰማኝ ፡፡ ደግሞስ እኔ ማነኝና ይህን ለማወቅም ሆነ ለመገመት ስልጣን የተሰጠኝ ፡፡ ደግሞስ ግዜው ነው ወይ ? ሲል ውስጤ ሞገተኝ ፡፡ ስለዚህ ቀናውን ሞፈር ጨብጬ የወግ ማሳዬን መተርተር እንደሚሻል ወሰንኩ ፡፡

እነሆ ከጎፈር ዘውድን መረጥኩ / ስልጣን ስለሆነ / ፤ እነሆ ከሰማይ ምድርን ሻትኩ / መቼትን ስላስታወስኩ / ፤ እነሆ ከሞት ህይወትን ጠራሁ ፡፡ እናም አቶ መለስ በህይወት ሲመለሱ ምን ያደርጋሉ ? ምን እንሰማለን ? የሚሉ ምናባዊ ትንታኔዋችን እያነሳሁ እጥላለሁ ፡፡

ምዕራፍ አንድ የሚጀምረው አውሮፕላን ውስጥ ነውና አቶ መለስ በኢትዮጽያ አየር መንገድ ወደ አዲስ አበባ እየተመለሱ ነው፡፡ ሻምፓኝ ተከፍቶ እየተጠጣ ነው ፡፡ ጎምቱ ባለስልጣናት መለስን ከበው በማያስቀው ሁሉ ይስቃሉ ፡፡ አራት ቦታ የተቆረጠው ኬክ ገና አልታደለም ፡፡ በእያንዳንዱ ቁራጭ ላይ የሰፈሩት ጽሁፎች ሲገጣጠሙ ‹‹ ረጅም ዕድሜ ለመለስ ›› የሚል መልዕክት ያስተላልፋሉ ፡፡

ሲፈራ ሲቸር የቆየው የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ማይኩን ይዞ ወደ አቶ መለስ ጠጋ ሲል የሚያውካኩ ድምጾች መጥፋት ጀመሩ ፡፡
‹‹ እንኳን ለዚህ አበቃዋት ጠ/ሚ/ር ››
‹‹ አመሰግናለሁ ! ››

የጋዜጠኛው ድምጽ ባይሰማም  የሆነ ጥያቄ ወረወረ፡፡ ያው ከመልሱ እናገኘው የለ ?! መልሱም ተከተለ ፡፡

1 . እንደሚገባኝ የመታከሙ ተልዕኮ የተሳካ ነበር ማለት ይቻለል፡፡ ይህን አባባል በሶስት መልኩ መንዝሮ ማብራራት የተሻለ ሳይሆን አይቀርም ፡፡ ቁልፉና ማጠንጠኛው አንድ ሰው በተለይም አንድ የሀገር መሪ ታሞ መዳን መቻሉ ነው ፡፡ ይህን የመዳን ጥያቄ ደግሞ ጠንካራ የሚያደርገው የታማሚው መሪ ግለኛ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን የታማሚውን መጨረሻ የሚጠብቁ ብዙ ሚሊዮን አይኖች መኖራቸው ነው ፡፡ ርግጥ ነው 90 ከመቶ ያህሉ ይህ በሽተኛ መሪ እንዲድን ለሚቀርበው ፈጣሪም ሆነ ጣዖት መለማመኑ ይጠበቃል ፡፡ አስር ከመቶው ግን ከቁጥሩ በላይ ያበጠ ፍላጎት እንደነበረው አምናለሁ ፡፡ በጣም የሚገርመው በዚሁ አሃዝ ውስጥ የሚካተተው ጥቂት ማህበረሰብ የሚናገረው ርግጠኛ የመሆኑ ጉዳይ ላይ ነው  ፡፡

ለምሳሌ ያህል  ‹ መለስ ከዳነ ከምላሴ ጸጉር ይነቀል › ብሎ ይነሳል ፡፡ በርግጠኝነት የሚያወራው ሞቱን ብቻ ሳይሆን የሕመሙንም መንስኤ ነው ፡፡ የያዘው የጭንቅላት ዕጢ የሚያፈነዳው እንጂ ለቀዶ ጥገና የሚመች አይደለም ብሎ ይደመድማል ፡፡ ወይ በሌላ ገጹ በድብቅ ያበሉት መርዝ ለጥቂት ግዜ ብቻ ነው የሚያላውሰው እንደሚል አይጠረጠርም ፡፡ ስለሆነም ጥቂቶች ካወሩት ሚሊዮን አሉባልታና ሚሊዮን ክፉ ምኞት አንጻር ህክምናው የተሳካ ነበር ለማለት ያስደፍራል ፡፡

በሁለተኛ ደረጃ መታየት ያለበት እኔን ሲያክሙና ሲንከባከቡ ከነበሩ ዶክተሮች አንጻር የሚተነተን ነው ፡፡ እንደምታውቀው መሪዋች ሲታከሙ ለማዳን የሚኖረውን ከፍተኛ ጥንቃቄ ያህል ከውስጥ በጣም ያረገዘ ነገር ግን የማይታይ ስጋት ይኖራል ፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የተጠራቀመው ስጋት የሚጫነው ደግሞ ሀኪሞች ላይ ነው ፡፡ ሀኪሞች ሌላ ዓላማ ላነገቡ ሰዋች፣ ቡድኖች ወይም መንግስታት ማለት ይቻላል ተገዢ ወይም ተንበርካኪ ባይሆኑ እንኳን ኃላፊነታቸው በራሱ ስጋት ላይ ሊጥላቸው ይችላል፡፡ ከስጋትም አልፎ በጥቂት ነገር ሊሳሳቱ ይችላሉ ፡፡ ከተሳሳቱ ደግሞ ተበላሸህ ነው ፡፡ አለቀ ፡፡ ዛሬ ኤሪያል ሻሮን፣ ሙባረክና ሌሎች መሪዋች ምን ያህል ኮማ ውስጥ እንወደቁ ማየት ይቻላል ፡፡ እና ህክምናው ውስጥ ያለውን ጦርነት በድል ከመወጣት አንፃር ተልዕኮው የተሳካ ነበር ማለት እችላለሁ ፡፡

በሶስተኛ ደረጃ መቀመጥ ያለበት የተሞክሮ ቅመራ ወይም የቴክኖሎጂ ሽግግር ሂደት ነው ፡፡ የታከምኩበት ሀገር የምታራምደው ርዕዮት ምንም ይሁን ምን በህክምና ዘርፍ የደረሰችበት ደረጃ ከፍተኛ ነው ፡፡ ይህን ቴክኖሎጂ ወደ ሀገራችን እንዲገባ በማድረግ ተሞክሮውን በማጥናትና በመቀመር ማስፋፋት ይኖርብናል ፡፡ ይህን በማድረጋችን ለህክምና የምናወጣውን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ ማዳን ይቻላል ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የያዝነውን ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ ተጨማሪ ምርኩዝ ይሆንልናል ፡፡

2. ጠ/ሚ/ር መለስ ቤተመንግስት ከገቡ በኃላ ከእንደገና በነገሮችና በሁኔታዋች ሊወጠሩ እንደሚችሉ ይገመታል ፡፡ የመጀመሪያ ተግባራቸው በየደረጃው መግለጫዋችን መስጠት ይሆናል ፡፡

ሀ . ለህዝብ ፤

አቶ መለስ ህዝቡ በሃሳብም ሆነ በጸሎት ላደረገላቸው ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋና ያቀርባሉ የሚለውን እንደ አርእስተ ዜና እንውሰደው ፡፡ ድርጅቱ መራራውን የትጥቅ ትግል ሲያደርግ ከጎን እንደነበር ፣ ሰላም ሰፍኖ የልማት ግንባታው ከቀጠለ በኃላም አለኝታነቱን እንዳረጋገጠ ወደፊትም የኩሩውንና የቀናኢውን ህዝብ ድጋፍ እንደማይለያቸው አስረግጠው መናገራቸውን ደግሞ ርዕሱን የሚያፍታታው ዝርዝር ሃሳብ ይሆናል ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጅምሮች አሉና፡፡ ቢያንስ የአባይ ግድብ ማለቅ አለበት ፡፡ ቢያንስ ህዝቡ በቀን ሶስት ግዜ መብላት አለበት ፡፡ ስለዚህ ህዝቡ መሪውን  አሳፍሮ እንደማያውቅ የታሪክን ሰበዝ በማውጣት ንግግራቸውን ሊያጠናክሩት ይችላሉ ፡፡ ይህ ደግሞ የኃላ ታሪክ / Background / መሆኑ ነው ፡፡ ማለትም የአጼ ዮሀንስ  ‹ ሀገርህ እናትህ፣ ዘውድህ፣ ሚስትህ…  › የሚለው ገዳይ ጥቅስ የተዘጉ ልቦች ዳር እንዲንኳኳ ይደረጋል ፡፡ በሌላ በኩል የአጼ ሚኒሊክ ‹ ጉልበት ያለህ በጉልበት ርዳኝ … › የምትለው ትሁት ስንኝ ይጨመርበታል ፡፡ በላዩ ላይ ወርቅ የመሳሰሉ አዳዲስ መፈክሮች ጣል ይደረግበታል ‹‹ ጸረ ህዝብም ሆኑ ጸረ ጤንነቶች ከመንገዳችን አያደናቅፉንም ! ››

ለ . ለፓርቲ አባላት ፤

ጠንካራ ሀሳቦችና ጉዳዮች የሚመዘዙት በዚህ ክፍለ ግዜ እንደሚሆን ይጠበቃል ፡፡ ስብሰባውን ፈታ ለማድረግ በ ‹‹ ሞት ›› ላይ አንድ ሁለት ቀልዶችን ወርወር ማድረግ ማን ይከለክላቸዋል ፡፡ አሁን የታየው ውጥረት ከኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት፣ ከህወኃት ክፍፍልና ከ97ቱ ምርጫ ቀጥሎ ሊቀመጥ የሚችል የፈተና ምዕራፍ በመሆኑ ትልቅ የጠቆረ ቦታ ይኖረዋል ፡፡ በመሆኑም በህወኃት ክፍፍል ግዜ የተባለውን ቁም ነገር በማስታወስ ‹‹ ሞት ለምሳ ሲያስበን ለቁርስ አድርገነዋል ›› ሊሉ ይችላሉ ፡፡ ካስፈለገ ደግሞ ከኢትዮ ኤርትራ ጦርነት የትዝታ ኮሮጆ ውስጥ የጄኔራል ሳሞራን ብሂል በማውጣት

 ‹‹ በሽታ አካልን ማገርጣትና ማሰቃየት ይችልበታል ፤
እኛ ደግሞ ሰንኮፉን በጽናት አስነቅለን ቆመን መሄድ እንችላለን ›› ቢሉ ወፈ ሰማይ ካድሬ እስከ ሻይ እረፍት አይስቅም ብሎ መከራከር አያዋጣም ፡፡ በርግጥ ሁሌም የሚጠራጠሩ አንዳንድ ሰዋች ከቀልዱ ጀርባ ምን ተደግሷል በሚል በመተርጎምና በመተንተን ቀኑን ሊያሳልፉት ይችላሉ ፡፡  ‹ በርግጥ ለምሳ ያሰቡ እነማን ናቸው ? …. ሰንኮፎቹስ ?  .. ›

አቶ መለስ በነካ እጃቸው ሰምና ወርቅ ያለው ምስጋና በማቅረብ የቤቱን ሙቀት ሊያግሉት ይችላሉ ፡፡ ‹‹ እዛ ድረስ መጥተው የጠየቁኝ የቁርጥ ቀን ወዳጆቼ አሉ ፡፡ ይህ ማለት ግን በስራ መብዛት ወይም የአውሮፕላን ወጪ በማጣት ያልመጡ ጓዶች ሁሉ እኔን አልጠየቁኝም ወይም ለእኔ አያስቡም ማለት አይደለም ! ››

‹ እዛ ድረስ ሄደው የጠየቁት በርግጥ አባካኝ ናቸው ወይስ የቁርጥ ቀን ልጆች ? አሁን ማን ይሙት የአውሮፕላን ወጪ የሚከብደው ኃላፊ የቱ ነው ? ጉድ ነው ይሄ ነገር ! … › ሌላ ምናባዊ ሀሳቦች ይፈለፈላሉ ፡፡ ይህን መሰል ፍም በራሱ ፓለቲካ ሰፈር ውስጥ መለኮስና እንዳይጠፋም በአባላቱ ምላስ እንዲርገበገብ ማድረግ ጠቃሚ ነው ፡፡ አስፈላጊ ከሆነ ተርከክ ያለው ፍም ላይ ‹ በቆሎ › ይጠበስበታል ፡፡ በቆሎ ከጠፋ እንኳን ሰብሰብ ብለው ወይ ተረት ወይ ትዝታን እያወሩ ይሞቁታል ፡፡

3 . የወ/ሮ አዜብ መስፍን ሹፌር ቤተመንግስት አካባቢ በተነሳው የስልጣን ሹክቻ በመስጋት በቱርክ አድርጎ ግሪክ መግባቱን አንዳንድ የመገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል ፡፡ ይህ ወሬ እውነት ከሆነ አቶ መለስ በቀጣይነት ለሚንደረደሩበት ርዕሰ ሀሳብ ጥሩ መረጃ ይሆናል ፡፡ ዜናው እውነት ካልሆነ ወደ ርዕሰ ጉዳዩ የሚያሰገባው መንገድ የተለየ መሆኑን ልብ ይሏል ፡፡ እናም አቶ መለስ የሾፌሩን ስም ጠርተው  ‹ ምን መሆኑ ነው ግን ? የኛ የስልጣን ሹክቻ የሚያሰጋው እሱ ባለስልጣን ነው እንዴ ? › የሚል ጥያቄ ወርወር ያደርጋሉ ፡፡ ወዲያው ደግሞ  ‹‹ የዚያች የጥንቸሏ ብጤ መሆኑ ነው ?!  ነብር ነው ዝሆን እየታደነ ይያዝ ሲባል እሷ እግሬ አውጪኝ ትላለች ፡፡ እንስሳትም ምን ሆነሽ ነው የምትፈረጥጪው ?  አዋጁ እንደሆነ አንቺን አይመለከትም ሲሏት ዝሆን አለመሆኔ እስኪረጋገጥ ለምን ፍዳዬን አያለሁ ነበር ያለችው ! ›› በማለት ላነሱት ጥያቄ ማብራሪያ ይሰጣሉ ፡፡ አቶ መለስ ፊታቸውን ከስከስ አድርገው ይቀጥላሉ ፡፡

‹‹ በርግጥ ሰው ወጣ ሲል የሰው በር ለማንኳኳት የቋመጡ ሰዋች እንደነበሩ ተሰምቷል ፡፡ የዉጪዋቹስ መቼም ግርግር ለሌባ ይመቻል ! የሚባለውን ብሂል አሁን ነው መጠቀም ያለብን ለማለት ነው ፡፡ በጣም የሚገርመው የቤታችን ጉድ ነው ! አንዳንዱ የተሰጠውን ስራ አድምቶ ሳይሰራ ነው ወደ ላይ መንጠልጠል የፈለገው ፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ተገፍቶና ባዶ ተስፋ ተሸክሞ ነው ››

ከዚህ በኃላ የደፈረሰው ይጠራ ዘንድ፣ ለአቅመ ጠላ ያልደረሰው መጠጥ መቼ፣ እንዴትና በነማን እንደተጠነሰሰ ይታወቅ ዘንድ ተከታታይ ሂስና ግለሂሶች ይካሄዳሉ ፡፡ በመሃሉ የሚፈረጥጡ ጥንቸሎችም አይጠፉም ፡፡ ነገሩ ሀገሪቱ ውስጥ እንደሚወራው ጠንካራ ከሆነ ድርጅቱ ለፓለቲካ ጸበል ሁለት -  ሰባት  ‹ ሸንኮራ › መውረዱ አይቀርም ፡፡

እንግዲህ ይህ ሲያልቅ ነው አዳዲስ ነገሮች የሚፈልቁት ፡፡  በመጀመሪያ መግለጫው ፤

. ‹ ከናፋቂነት ተፈወስን ! › የሚል ሀሳብ ላይ ይሽከረከር ይሆናል ፡፡ ከዚህ በፊት ጠባቂነት፣ ተሃድሶ፣ መበስበስ ወዘተ የሚሉ ምጡቅ መግለጫዋች ስለነበሩ እንዳይደገሙ ጥንቃቄ ስለሚደረግ ማለት ነው ፡፡

. ውስጥ ለውስጥም ሆነ ይፋ በሆነ መግለጫ ሹም ሽሮች ሊከናወኑ ይችላሉ ፡፡ በሹም ሽሩ ከዚህ ቀደም በአቅም ማነስና በእጅ አመል ቀንዳቸውን የተመቱ ሁሉ አሁን የኤሊን ገጸ ባህሪ ወክለው ይጫወታሉ ፡፡

. የከፋ ነገር የተገኘባቸው / ለአብዮቱ ያልተመቹ / ደግሞ ፈጽሞ አልመው ወደማያውቁት የቃሊቲ ዓለም ይወረወራሉ ፡፡ ጎበዝ ከሆኑ ‹ ህይወት ከቪላ  በኃላ › ወይም  ‹ የአብዮታችን  ያልተገረዘ መጋዝ › በሚል አንድ አስደናቂ መጽሀፍ ሊደርሱ ይችላሉ ፡፡

4 . ከምስጋና ፣ መወቃቀስና ሹም ሽር በኃላ አዳዲስ ቃላቶችና አባባሎች የሚፈጠሩ ይመስለኛል ፡፡ እነ ተንበርካኪነት፣ 
ተስፋፊነት፣ ጠባቂነት፣ ተቸካይነት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ የልማት ሰራዊት እና የመሳሰሉት ተመሳሳያቸውን ወይም ተቃራኒያቸውን የሚያፈሩበት ሁኔታ ይኖራል ፡፡ ከዛም እንደ አካሄድ … እንደ አሰራር… ስብሰባ እንደ ስብሰባ … እያሉ ሃሎ ሃሎ መንፋት ነው ፡፡ በአነጋገር አንድ ዓይነት ልብስ የለበሰ  …

እስኪ  ያወራሁትን ምን ያህል እንደማውቀው ለማረጋገጥ የሆነ መልመጃ ልሞክር ፡፡ < ከላይ በተገለጹት ቃላቶችና የአሰራር ይትበሃሎች ቢያንስ ሁለት ቃላቶችን መስርት ? >

. በቃላት ራስን መቻል !
. የቃላት ሰራዊት ማፍራት !


Sunday, July 15, 2012

‎ፈሳዊ ጉዳያችን‎



ፈስ ሳይንሳዊ በሆነ አካሄድ ወጥ ትርጉም እንዳለው ይታወቃል ፡፡ ነገር ግን በወንዶችና ሴቶች ዓይን ነጥለን ካየነው ሁለት የተለያዩ ትርጉሞች መስጠቱ ግድ ነው ፡፡

ከሴት አኳያ --   አሳፋሪ ተረፈ ምርት
ከወንድ አኳያ --- ከወንድ ጋር የተቆራኘ፣ ራስን መግለጫና መጨረሻ የሌለው የመዝናኛ ምንጭ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡

ፈስ ግዜና ቦታ አይመርጥም ፡፡ አንዳንድ ሰዋች ወንዶች ከሴቶች ይልቅ ብዙ ግዜ ይፈሳሉ ይላሉ ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ወንዶች በስብሰባ ፣ ስራ ቦታ፣ በእምነት ተቋማት፣ በየመንገዱ ያለርህራሄ ይተኩሱታል ማለት ነው ፡፡ በሌላ በኩል ይህ አባባል እውነት ከሆነ ሴቶች ፈስን በጣም በመቆጠብ መጨረሻ ላይ ግን አስገምጋሚ ጋስ ያስወነጭፋሉ እንደ ማለት ነው ፡፡

የፈስ ሽታ የሚመጣው አነስተኛ መጠን ካላቸው የሃይድሮጅን ሰልፋይድ ጋስና መርካፕታን ከተባለው ንጥረ ነገር ድብልቅ ነው ፡፡ እነዚህ ድብልቆች ሰልፈርን ይዘዋል፡፡ ምግብ ውስጥ ብዙ ሰልፈር ካለ የፈስ ሽታም ጠንካራ እየሆነ ይሄዳል፡፡ አንድ ሰው በቀን በአማካኝ ግማሽ ሊትር የሚደርስ ፈስ ሊያመነጭ ይችላል፡፡ ፈስ ወደ ፈሺው አፍንጫ ቶሎ ከመድረስ ይልቅ ከ 13 እስከ 20 ሰከንድ ሊቆይ ይችላል፡፡ ፈስ በድምጽ ፍጥነት የሚጓዝ ቢሆን ኖሮ ሽታውንም ወዲያው ማጣጣም በተቻለ ነበር ፡፡

ልብ ብላችሁ ከሆነ በሴቶች ሽንት ቤት ውስጥ የፈስ ድምጽ የሚሰማው በእንግዳ ስሜት በጣም አልፎ አልፎ ነው፡፡ ፈስ ከተሰማ ይህን አድራጊዋ ፣ የሰሙ ሰዋች ከአካባቢው እስኪርቁ ድረስ እዛው ልትደበቅ ትችላለች፡፡ በወንዶች ሽንት ቤት ግን ፈስ የበዓል ማዳመቂያ ወይም የጀግንነት ምልክት ይመስል በከፍተኛ ድምጽ ሲንጓጓ ነው የሚውለው ፡፡

በነገራችን ላይ በየትኛውም የዓለም ማዕዘን የምትገኝ ሴት ብዙ የሚያበሳጫትና መታገስ የማትፈልገው ነገር አለ ከተባለ በፈስ ጉዳይ ነው ፡፡ በጥንት ዘመን ወንድ ልጆች አስር አመት ሲሞላቸው ያላቸውን ብቃትና ጥንካሬ ከሚለኩባቸው መንገዶች አንዱ የሚፈሱት ፈስ ምን ያህል ርቀት ድረስ ይሰማል የሚል ነበር ፡፡ አንዳንድ አካባቢ ፈስ በአደባባይ ቢፈሳም የሚያስጨንቅ ጉዳይ አይደለም ፤ አንዳንድ አካባቢ ደግሞ መሸማቀቅ ይስከትላል ፡፡ በአንድ ወቅት ፕሬዝዳንት ኦባማ ንግግር እያደረጉ ‹ ጠ ረ ረ ረ ር ር …. › የሚል ድምጽ ይሰማሉ ፡፡ ንግግራቸውን ገታ አድርገው ወደ ታች ካዩ በኃላ ‹‹ sorry for the gas ! ›› ብለው ንባባቸውን ቀጠሉ ፡፡ ወደ ታች ዝቅ ብለው ሲመለከቱ የሌላ ነገር ድምጽ ሳይመስላቸው  አልቀረም ፡፡ አንድ የኛ ሀገር መሪም ንግግር እያደረጉ ፈሳቸውን አንጣረሩት፡፡ ደንገጥም ሳይሉ ንግግራቸውን ቀጠሉ ፡፡ ምናልባት በለሆሳስ ነው የፈሳሁት ብለው አስበውም ይሆናል ፡፡ ግን ማይክራፎኑ ገዳዩን አጋኖ ቁጭ አደረገው ፡፡ ምናልባትም ከጆርጅ ቡሽ ጋ ጓደኝነት ይኖራቸው ይሆናል ፡፡ ቦብ ውድዋርድ የተባለ ጸሀፊም የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ በፈስ ነክ ቀልዶች በእጅጉ እንደሚንፈቀፈቁ ጽፏልና ፡፡

 
ዴይሊ ሜል የተባለው ጋዜጣ ደግሞ የሚላዊ ፕሬዝዳንት ቢንግዋ ሙታኒካ በየአደባባዩ መፍሳትን ህገ ወጥ ድርጊት በማድረግ ቅጣት እንዲጣል ሀሳብ ማቅረባቸውን ይነግረናል፡፡ እንደ ጋዜጣው አስተያየት ከሆነ ህጉ የተረቀቀው ህዝቡ ኃላፊነት የሚሰማውና በስነ ምግባር የታነጸ እንዲሆን ከማሰብ አንጻር ነው ፡፡

ሳቅ አለም አብራህ ትስቃለች፣ ፍሳ ለግዜውም ቢሆን ሁሉም ሳቃቸውን ያቆማሉ የሚል ቀልዳዊ አባባል አለ ፡፡ ወፍ የምትጮኀው እንዳገሯ ነውና ወደኛ ስንመጣ ፈስ በቀላሉ ‹‹ ፈሳም ! ›› የሚል ስድብ ያሰጣል፡፡ ‹‹ ይሄ ፈሳም ነው ! ›› ከተባለ ለቁም ነገር የማይበቃ፣ ፈሪና የሚናቅ መሆኑን  ሊጠቁም ይችላል ፡፡ እናም ለመፍሳት ግራና ቀኝ መመልከት ፣ ከተለቀቀም በኃላ ምን ያህል ይሸት ይሆን ? ብሎ አፍንጫን እንደ ውሻ ወደፊት መቀሰር ፣ ይታወቅብኝ ይሆን ? ብሎ አይንና ጆሮን ወደ ጎን ማሽሟጠጥ ይከተላል፡፡

ፈስን ጋስ ነው ብሎ የሚቀበል ትውልድ ገና አልመጣም ፡፡ ህጻናት እንኳን ፈሰኛን የሚያወግዙበት ስነ ግጥም አለቻቸው ፡፡
ፈስ ፈሶ ፈሳራራ
ቆርጦ ቆርጦ ደም ያሳራ
ደሙ ሲረጋ በለው ባለንጋ
አለንጋው ሲበጠስ
ምንቄው ይበጠስ ! / ምንቄ ግን ምንድነው ? /

ወደ አማራው ክልል ስንጓዝ ደግሞ ፈስ ሃይለኛ የጦር መሳሪያ ሆኖ ያገለግላል ፡፡ የቆሎ ተማሪዋችና ደብተራዋች ‹ የጎዳቸውን › ሰው ለማጥቃት በወፍ ቋንቋቸው ይደጋግማሉ ፡፡ ይህን ቋንቋ ከአዲስ ኪዳን ማውጫ ተውሰን  ‹‹ የደብተራ ወንጌል ›› ወይም  ‹‹ የደብተራ ስራ ›› ፤ አሊያም ከብሉይ ኪዳን ተነስተን  ‹‹ መጽሀፈ ደብተራ ›› ወይም  ‹‹ ትንቢተ ደብተራ ››  ለማለት እንኳን የሚያስቸግር ይመስለኛል ፡፡ ብቻ ከመጽሀፍ ቅዱስ ክልል ውጪ ቢሆንም የዋሉበት ድግምት አያሳፍራቸውም ነው የሚባለው ፡፡ ያ - በግዕዝ ቋንቋ የተቃመበት ሰው ታዲያ ቀኑን ሙሉ ለዚያውም ቦታ ሳይመርጥ እንደ አህያ ዘረጥ - ዘረጥ ሲያደርግ ይውላል፡፡ አቤት መሳቀቁ አይታያችሁም ፡፡

‹‹ ወይ ጉድ  ያ- የተበላሸ ባቄላ እኮ ነው ?! …
‹‹ አዬ አያ እንትና ያ - የማልወደውን ሻሜታ ግቶኝ ግቶኝ  !…
መጨረሻ ላይ እውነትን መካድ ሁሉ ሊመጣ ይችላል ፡፡ ‹‹ አይ ይህ ሆዴ … ሆዴ እኮ ነው እንዲህ የሚጮኀው ?  … ››
አህያ የሚለው ቃል የአለቃ ገብረሃና ቀልዶችን አስታወሰኝ ፡፡ ሴትየዋ በእንስራ ውሃ ተሸክማ ቁልቁል ትወርዳለች ፡፡ ቁልቁለቱ በጣም ያዘቀዘቀ በመሆኑ ዘጭ - ዘጭ እያለች በፍጥነት እንድትወርድ ያስገድዳታል ፡፡ በዚህ ግዜ ፈሷ ያመልጣትና ዛጥ ዛጥ ታደርገዋለች ፡፡ ይሄኔ ድምጽዋን ከፍ አድርጋ  ‹‹ አንተ ጊዮርጊስ አሁንስ እንደ አህዮቹ ልታደርገኝ ነው ? ›› ትላለች ፡፡
 ‹‹ እ.ህ.ህ ! … ›› እያለ ጉሮሮውን የሚጠራርግ ሰው ድምጽ ሰምታ ዘወር ስትል አለቃን አየች ፡፡
 ‹‹ ውይ አለቃ ! መቼ መጡ ? ›› አለች የምንተፍረቷን
‹‹ ጊዮርጊስ አህዮቹን ይዞ የወረደ ግዜ ! ›› ሲሉ ኩም አደረጓት

ለነገሩ በዚህ ረገድ አለቃም ኩም የሚሉበት አጋጣሚ ጥቂት አይደለም ፡፡ ልዩነቱ ሌሎቹን እንደሚተርቡ ሁሉ በራሳቸው ላይም መቀለድ መቻላቸው ነው ፡፡ አንድ ወቅት እንዲህ ሆነ ፡፡ የቅርብ ዘመዳቸው ስለሞተ አልቅሰው ፣ ቀብረው ቢደክማቸውም ወደ ቤታቸው መሄድ አልቻሉም ፡፡ ማታ ራት ተበልቶ ተጎዝጉዞ ከለቀስተኛ ጋር በመደዳ ይተኛሉ ፡፡ ትንሽ ቆይተው ግን ፈሳቸው መጣባቸው ፡፡ ይሄኔ ቀስ ብለው ያለ ድምጽ ሊፈሱ አስበው ቂጣቸውን በእጃቸው ከፍተው ቢለቁት ‹ ጠ ረ ረ ረ ር … ! › ብሎ አጋለጣቸው ፡፡ እናም ምነው አለቃ ትልቅ ሰው አይደሉም እንዴ ?! ወዘተ የሚሉ አፋጣጭ ጥያቄዋች ከመወርወራቸው በፊት            ‹‹ አዬ እድሌ መልግጌ አባስኩት አይደል ? ›› በማለት ለቀስተኛውን አሰፈገጉት ፡፡

 
በአንድ እጁ የጀግንነት በሌላኛው የፍርሃት ችቦ ለኩሶ የሚጓዘው ፈስ በተረብ፣ በተረት፣ በአባባል፣ በጥናትም የደለበ ነው ፡፡ የጥናቱን ካዝና ስንከፍተው 96.3 ከመቶ የሚደርሱት ወንዶች ፈስ እንደሚፈሱ ሲያምኑ የሴቶች ቁጥር 2.1 ከመቶ ብቻ መሆኑን እንረዳለን ፡፡ ወንዶች በአማካኝ በቀን 12 ግዜ በመፍሳታቸው ከ 1.5 እስከ 2.5 ሊትር ጋስ ያጣሉ ፡፡ ይህ መጠን አንድ አነስተኛ ፊኛን ለመሙላት በቂ ነው ፡፡ በሌላ በኩል ሴቶች በአማካኝ በቀን ሰባት ግዜ ሲፈሱ ከ 1 እስከ 1.5 ሊትር ጋስ ያስወጣሉ ፡፡

በዓለማችን ታዋቂ ፈሳም ተብሎ የተመዘገበው ጆሴፍ ፓጁል እ.ኤ.አ በ1892 በፓሪስ ከተማ የፈስ ትዕይንት ያቀርብ ነበር ፡፡ ድርጊቱን የሚጀምረው የሆነ ታሪክ እያወራ ሲሆን ይህንንም የተለያዩ ድምጾች ባሉት አሰገራሚ ፈሱ ማጀብ ይችላል፡፡ ይህ ሰው በላስቲክ ውስጥ ሲጋራ ካስገባ በኃላ ላስቲኩን በቂጡ ቀዳዳ ውስጥ በመጨመር ያጨሳል ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ዋሽንቱን ቂጡ ላይ ከሰካው ላስቲክ ጋር በማያያዝ የሀገሪቱን ብሄራዊ መዝሙር ይጫወታል ፡፡ በዚህ ድርጊቱ ከወንዶች ይልቅ ፈስ የሚጠሉት ሴቶች በጣም እንደሚስቁ ተዘግቧል፡፡ አንዳንዶች እንደውም ሳቅ በማብዛታቸው እየታመሙ ወደ ሆስፒታል እሰከመወሰድ ደርሰዋል ፡፡

ከፈስ ጋስ ውስጥ ከ 50 እስከ 60 ከመቶው ናይትሮጂን፣ ከ30 እስከ 40 ከመቶው ካርቦን ዳይኦክሳይድ እንዲሁም ከ 5 እሰከ 10 ከመቶው የሚደርሰው ሚቴን ነው ፡፡ ሚቴን ጋስ መሬት ውስጥ የተቀበረ ፈንጂ እንዲፈነዳ ምክንያት መሆኑ ይታወቃል ፡፡ አንድ ጥናት ብዙ ለመፍሳት ምክንያት ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ በምግብ ግዜና ከምግብ ውጪ ብዙ ማውራት መሆኑ ታውቋል ይለናል፡፡ ፈስን በከፍተኛ ደረጃ በማመንጨት በኩል ትልቅ ሚና የሚጫወቱ ምግቦች የአበባ ጎመን፣ ሽንኩርት፣ ነጭ ሽንኩርት፣ ጎመን፣ ዳቦ፣ ባቄላ፣ ነጭ የወይን ጠጅ እና አትክልትና ፍራፍሬዋች ናቸው፡፡

በነገራችን ላይ ከከብቶችና ከበጎች ፈስ የሚወጣው የሚቴን ጋስ በመላው ዓለም 35 ከመቶ ያህል በመሆኑ የመሬት ሙቀት እንዲጨምር፣ የኦዞን ሌዪር ቀዳዳ እንዲሰፋ ትልቅ አስተዋጽኦ ያደርጋል ፡፡ በመሆኑም ለዓለማችን ትልቁ ስጋት አሸባሪነት ሳይሆን የላሞች ፈስ ሳይሆን አይቀርም ፡፡


                                                                

Wednesday, July 11, 2012

‎አልጀዚራ ነፍስ ፍለጋ የለኮሰው ሻማ ይዳፈን ይሆን ?‎





እድሜ ለአልጀዚራ አንድ የሞተ ታሪክ ነፍስ ዘራ፡፡ ታዋቂው የኖቤል ተሸላሚና የፍልስጤም መሪ ያሲር አራፋት ህዳር 11 ቀን 2004 በፓሪስ በሚገኝ አንድ ወታደራዊ ሆስፒታል ውስጥ ነበር የሞቱት፡፡ በወቅቱ የሞታቸው መንስኤ ተደፋፍኖ ስለነበር ‹  ይሄ በሽታ ነው የገደላቸው ›  ለማለት አልተቻለም፡፡ ይህም በርካታ መላምቶች እንዲወለዱ አደረገ፡፡  ጉበት፣ ካንሰር፣ የደም መታወክና ኤድስ የሚሉት በጣም ጎልተው ይሰሙ ነበር ፡፡ እነሆ ከስምንት ዓመታት ቆይታ በኃላ አራፋት የሞቱት ፓሎኒየም በተባለ ሬዲዮ አክቲቭ ንጥረ ነገር ተመርዘው መሆኑ ተደረሰበት፡፡ ምርምራው የተካሄደው ስዊዘርላንድ በሚገኘው የሬዲዮ ፊዚክስ ተቋም በመሆኑ ዜናው አጠራጣሪ የሚሆንበት መንገድ ዝግ ነው፡፡ በምርመራው የአራፋት ልብሶች፣ ደም፣ ሽንት፣ ምራቅና ላብ ሳይቀሩ ተካተዋል፡፡ የተቋሙ ኃላፊ ዶ/ር ፍራንኮይስ ቦችድ ውጤቱን በይፋ ያረጋገጡ ሲሆን ምርምሩን ይበልጥ ማጠናከር ካስፈለገ የአራፋትን ሬሳ ሊመረመር ይችላል ብለዋል፡፡  እናም አራፋት የሞቱት በተፈጥሮ በሽታ ሳይሆን በከፍተኛ ደረጃ በተቀነባበረ የወንጀል ድርጊት ነው፡፡ አራፋትን ማን ገደላቸው ? ፍልስጤም፣ ፈረንሳይ፣ እስራኤል፣ አሜሪካ ወይስ ሌሎች ?

ሲታከሙበት የነበረው የፈረንሳይ ወታደራዊ ሆስፒታል አሟሟታቸውን ለምን ደበቀ ?  እውነት የፍልስጤማዊያን ኃላፊዋችስ ምስጢሩን አያውቁም ነበር ?  በቀጣይ የሚደረገው ዓለማቀፍ ምርመራ  የተጠያቂ ግለሰቦችንና ሀገሮች ዱካ ላይ ይደርስ ይሆን ?  ይህ ወንጀልስ በቀጣዩ የሰላም ድርድሮች ላይ ምን ተጽዕኖ ያስከትላል ?  እንግዲህ ተቀብሮ የነበረው ጉዳይ ሳጥን ፈንቅሎ በመውጣት ሌላ የቀዝቃዛ ጦርነት ሊያስከትል አሞጥሙጧል፡፡

አልጀዚራና ሱሃ አራፋት
 
የስዊዘርላንዱን የሬዲዮ ፊዚክስ ተቋም ጨምሮ አልጀዚራና የያሴር አራፋት ባለቤት ሱሃ አራፋት ይህን ፈታኝ የምርመራ ስራ ዕውን ለማድረግ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ የምርመራው ስራ አሰልቺና ከባድ ዘጠኝ ወራትን ጠይቋል፡፡ የአራፋት የአሟሟት መንስኤ ከአሉባልታዋች ባለፈ ተጨባጭ ማስረጃ ላይ የተደገፈ አለመሆኑ ሲቆጨው የነበረው አልጀዚራ ኃላፊነቱን ወስዶ ጉዳዩ እንደ አዲስ እንዲነሳ ማድረጉ የሚገርም ነው፡፡ ግዜው በራቀ ቁጥር ተጨባጭ ማስረጃ ለማግኘት የሚደረገው ጥረት እየሳሳ እንደሚሔድ ይታወቃል፡፡ ግን እስካሁን ግልጽ ያላደረጉትን አስተማማኝ የምርመራ ፍንጭ በማግኘታቸው ሊሆን ይችላል ሀ ብለው የጀመሩት፡፡ በርግጥም የጋዜጠኝነት ፈታኝ ተግባር የሆነውን የምርመራ ዘገባ ለመስራት እውቀት፣ ብልሃት፣ ትዕግስት፣ ድፍረትና መስዋትነት ይጠይቃል፡፡

 ‹‹ የምርመራ ዘገባ  ሰዋች ወይም ድርጅቶች በምስጢር ሊይዙት የሚሽቱን ዓይነተኛ ጉዳይ በግል የስራ ውጤትንና ተነሳሽነት መዘገብ ነው ፡፡ እያንዳንዷን ዝርዝር ጉዳይ በጥልቀት የመፈተሸ፣ እውነታን የማፈላለግና ስነልቦናዊ ብቃትን ይጠይቃል፡፡ ጋዜጠኛውን የሚጠረጥረውን ወይም ዋጋ ይኖረዋል ብሎ ያሰበውን ጉዳይ ቀርቦ የመመርመር ብቻ ሳይሆን ከቀጣዩ ውጤት አንጻር የመተንተን ስራም ያከናውናል፡፡ ጉዳዩ ከጽሁፍ ማስረጃዋች ጋር ብቻ ሳይሆን እወቅና ከገኘ የህክምና ውጤት፣ ሳይንሳዊ ውጤቶች፣ ማህበራዊና ህጋዊ ድንጋጌዋች ወዘተ ጋር ሁሉ ሊተሳሰር ይችላል ›› / የጋዜጠኝነት ፈታኝ አጀንዳዋች ፤ አለማየሁ ገበየሁ ፤ ገጽ 16 /

በርግጥ የምርመራው ዘገባ ዋናውን ምዕራፍ ገለጸ እንጂ የመጨረሻው ውጤት ላይ አልደረሰም ፡፡ ይህ ምዕራፍ ግን ልክ  ለአንድ  የህንጻ  ግንባታ ትልቁን ሚና እንደሚጫውተው ‹‹ መሰረት ›› ግዙፍ መደላድል መፍጠሩ የማይታበል ነው፡፡ ቀጣዩን ስራ ለማከናወን የተዘረጋው አስፋልት ወደ መጨረሻው ፌርማታ ለማድረስ ፈጥነትንም ምቾትንም ታሳቢ ሊያደርግ ይችላል ፡፡ 

ለመሆኑ የምርመራው ስራ እንዴት ተጠንስሶ ወደ ውጤት ተቀየረ ?  ሱሃ አራፋት ሁኔታውን እንደሚከተለው ትገልጸዋለች
‹‹ በመጀመሪያ እኔ ተጨማሪ ምርመራ እንዲደረግ የሄድኩበት ሁኔታ አልነበረም፡፡ ከስምንት ዓመታት ቆይታ በኃላ ለምን አስፈለገ  ? ብለህ መጠየቅህ አይቀርም፡፡ ሆኖም የአልጀዚራ ጣቢያ ወደኔ መጥተው ምርመራ ማከናወን እንደሚፈልጉ ገለጹልኝ ፡፡ እናም አልጀዚራ ሌሎች ያልወሰዱትን ኃላፊነት ሊወስድ ነው ማለት ነው፡፡ ይሄ ብሄራዊ ስራ ነው፡፡ በዓለም ላይ ከፍተኛ ዝናና አቅም ያለው የምርመራ ተቋም ሊያስሱ ነው፡፡ በመሆኑም የፈረንሳይ ሆስፒታል የሰጠኝን ልብሶችና ቁሳቁሶች በሙሉ ሰጠዋቸው፡፡ የሴት ልጄንም ዘረመል ወሰዱ፡፡ ዘረመሉን ከባለቤቴ ልብስና ጸጉር ያገኙትን ነገር የማነጻጸር ስራ አከናወኑ፡፡ ውጤቱም ተመሳሳይ ሆነ፡፡

‹‹ ይህን ስራ የጀመርነው ከዘጠኝ ወራት በፊት ነበር፡፡የባለቤቴን ንብረቶቸ፣ የህክምና መድሃኒቶች፣ ሰዓቱን፣ የአንገት ሀብሉን በሙሉ ፈትሸዋል፡፡ በመጨረሻም ከፍተኛ መጠን ያለው ፓሎኒየም በደሙ፣ በልብሶቹ፣ በባርኔጣው፣ በውስጥ ልብሱ ሳይቀር ንጥረ ነገሩ ተገኝቷል፡፡ ይህ ደግሞ የሚገኘው በበለጸጉ ሃገሮቸ ብቻ ነው፡፡ አሁን አራፋት የሞተው በተፈጥሮ ህመም ሳይሆን በወንጀል መሆኑን መግለጽ እንችላለን፡፡ ከዚህ በኃላ የፍልስጤምን መንግስት እኔንም ሆነ ህዝቡን እንዲረዳ የምጠይቀው የባለቤቴ ሬሳ እንዲመረመር ፍቃድ እንዲሰጠኝ ነው፡፡ ሀኪሞች ትክክለኛውን አጥንት ካመጣሁ ንጥረ ነገሩ እንደሚገኝ ገልጸውልኛል፡፡ ሌላው ቢቀር ሬሳውን የከበበው አፈር ላይ እንኳ ሊገኝ ይችላል ፡፡ ሆኖም በፍጥነት መከናውን አለበት ››

ፓሎኒየም ምንድነው ?
ፓሎኒየም 210 በዓለማችን በቀላሉ ከማይገኙ ማዕድናት ውስጥ ይመደባል፡፡ በመጀመሪያ የተገኘው እኤአ በ1898 ሜሪ እና ፔሪ ኩሪ በተባሉ ሳይንቲስቶች ነበር፡፡ እነሱም ለሀገራቸው ክብር ሲሉ የማዕድኑን የመጀመሪያ ስም ከሀገራቸው Poland ጋር ለማስተሳሰር ሞክረዋል፡፡ በተፈጥሮ ከመሬት የላይኛው ክፍል ላይ በጥቂቱ የሚገኝበት ሁኔታ ያለ ሲሆን ለኒውኩለር ማብላሊያነትም በሰው ሰራሽ ዘዴ ሊመረት ይችላል፡፡ የፖሎኒየም አነስተኛ ንጥረ ነገር ማለትም 0.04 ኦውንስ ሰውን ለመግደል በቂ ነው፡፡ በተለይም ጉበት፣ ኩላሊትና የአጥንት ውስጥ ፈሳሽን በከባዱ የሚያጠቃ ሲሆን በከፍተኛ ደረጃ የማስታወክ፣ የጸጉር መሳሳት፣ የጉሮሮ ማበጥና መገርጣትን ያስከትላል፡፡

በነገራችን ላይ በዚህ ንጥረ ነገር የሚሞቱ ሰዋች በጣም አነስተኛ ሲሆኑ የቀድሞው የሶቭየት ህብረት መኮንና ሰላይ የነበረው አሌክሳንደር ሊቲቬንኮ በጉዳዩ የመጀመሪያው ሟች መሆኑ ተመዝግቧል፡፡ ለስለላ ተቋማት ይሰራ የነበረው ይህ ሰው ከሀገሩ ተሰዶ በእንግሊዝ ጥገኝነት አግኝቶ ይኖር ነበር፡፡ ከዚያም ጋዜጠኛ ሆኖ ከቼቼኒያ ጎን በመቆም ሩሲያን የሚቃወሙ ሁለት መጻህፍትን አሳትሟል፡፡ በሞስኮ ትያትር ቤት የተከናወነውን የጠለፋ ድራማና ለሌሉች የሽብር ተግባራት ተጠያቂው ፑቲን መሆናቸውንም ይገልጽ ነበር፡፡ ህዳር 2006 ታሞ ከሶስት ሳምንታት በኃላ ሞተ፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ በፖሎኒየም የሞተ ተብሎ መነጋገሪያ ሆነ፡፡ እንደውም ሳይንቲስቶች የኒውክለር ሽብር ተጀመረ በማለት ስጋታቸውን ገልጸው ነበር፡፡ ሰላዩ የሞተው የሚጠጣው ሻይ ውስጥ ንጥረ ነገሩ ተጨምሮበት ሲሆን የሞተውም በሚታወቁ የቀድሞው ጓደኞቹ አማካኝነት ነው፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ኃላ ላይ የሩሲያን ዲፕሎማሲ ላለማበላሸት በሚል ክሱን አዳፍኖታል፡፡

ሱሃ አራፋትን በጨረፍታ



 
ሱሃ በዌስት ባንክ ከሚኖሩ ሀብታም የክርስትያን ቤተሰቦች የተገኘች ናት፡፡ አባቷ ዳውድ አል ታዊል የባንክ ባለሙያ ሲሆን፣ እናቷ ሪሞንዳ አልታዊል ፓለቲከኛና የሚዲያ ሰው ነበሩ ፡፡ ትምህርቷን በፍልስጤም ግዛት ውስጥ ከተከታተለች በኃላ ለተጨማሪ ትምህርት ፓሪስ ወደሚገኘው ስርቦኔ ዩኒቨርስቲ አቅንታለች፡፡

አራፋት ሱሃን ያገኟት ጆርዳን በሚገኘው የአል ውህዳት ስደተኞች ካምፕ ውስጥ እኤአ በ1985 ነበር፡፡ ያኔ ዕድሜዋ በሃያዋቹ መጀመሪያ ሲሆን አራፋት 58 ሻማ ለኩሰዋል፡፡ የስራ ግንኙነታቸው ቀስ በቀስ ዳበረ፡፡ ሱሃ አራፋት ከፈረንሳይ ባለስልጣናትና ፓለቲከኞች ጋር ሲገናኙ ረዳትና አስተርጓሚ ሆና ትሰራ ነበር፡፡ በ1989 ተጋቡ ፤ ግንኙነቱ ግን ምስጢራዊ ነበር፡፡

አራፋትን ካገባች በኃላ ክርስትናን ወደ እስልምና በመቀየር ወደ ፒኤልኦ ጠቅላይ መምሪያ ቱኒዝያ አመራች፡፡ የሁለቱ ጋብቻ ህዝብ ያወቀው በ1992 አራፋት በሊቢያ በረሃ ከአውሮፕላን ተከስክሰው ሱሃ ልትጠይቃቸው ባቀናችበት ግዜ ነበር፡፡ ሀምሌ 24 ቀን 1995 ሴት ልጅ ወለደች፡፡ አራፋት በ1993 የሞቱትን እናታቸውን ለማስታወስ በሳቸው ስም ዛህዋ ሲሉ ሰየሟት፡፡ ሱሃ አራፋት ከሞቱ በኃላ በቱኒዚያ ለትንሽ ግዜ ተቀምጣለች፡፡ ይሁን እንጂ ከቱኒዝያው መሪ ሚስት ለይላ ቢን አሊ ጋር በመጣላቷ ወደ ማልታ ሄዳ ለመኖር ተገዳለች፡፡ በአሁኑ ግዜም ከፍልስጤም መንግስት ድጎማ ትቀበላለች፡፡

በቀድሞው ታሪክ ውስጥ ፈረንሳይና ፍልስጤም ምን ብለው ነበር ?
 
የፈረንሳይ ባለስልጣናት በሀገራቸን ህግ መሰረት የግለሰቦችን ምስጢር ማውጣት አንችልም በሚል መንስኤው እንዲደበቅ አድርገዋል፡፡ ትንሽ ቆይተውም የአራፋትን የህክምና ፋይል መስጠት የሚቻለው ለቅርብ ዘመዶች ብቻ ነው በሚል ለአጎታቸው ለናስር አል ኪድዋ ሰጥተውት ነበር፡፡ በወቅቱ ሚስታቸው ሱሃ ፍቃደኝነቷ አልተጠየቀም፡፡ ከዚያ ደግሞ የፍልስጤም የካቢኔ ጸሀፊ ሀሰን አቡ ሊድህ የአራፋትን ሙሉ የህክምና መረጃ ማግኘታቸውንና ታሪካዊ መረጃ መሆኑን በመግለጽ በዚሁ መሰረት መንግስታቸው አሰፈላጊ ርምጃዋችን እንደሚወስድ ተናግረው ነበር፡፡ ይህ ንግግር ለህዝቡ ዝርዝር መረጃ መስጠትን ያካትታል፡፡
ይሁን እንጂ መረጃው ለህዝቡ ስላልተገለጸ አራፋት የሞቱት እስራኤል መርዛቸው ነው የሚል ወሬ በሀገሪቱ ውስጥ ተሰራጨ፡፡ አስቀድሞ አራፋትን ሲከታተሉ የነበሩት ሀኪም አሽራፍ አል ኩርዲም ምናልባት ለአራፋት ሞት የተሻለው ምክንያት ይህ ሊሆን ይችላል በማለት ግምታቸውን ሰነዘሩ፡፡ የአራፋት አጎት አል ኪድዋ እስራኤል መርዛ ለመግደልዋ ምንም አይነት መረጃ የለም በማለት ተከራከሩ፡፡ በወቅቱ የእስራኤል መገናኛ ብዙሃን የአራፋት ሞት ኤድስ ነው በማለት ይዘግቡ ነበር፡፡ ምናልባት አራፋት ከመሞታቸው በፊት የፈረንሳይ  ሀኪሞች አራፋት አነስተኛ የቀይ ደም ሴልና ከፍተኛ ነጭ ደም ሴል እንደታየባቸው መግለጻቸውን መሰረት በማድረግ ‹‹ ይሄ ይሆናል ›› የሚለውን ግምት እንዲያሰፋው አድርጎ ሊሆን ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ ሆን ተብሎ ፡፡

ለአራፋት ሞት የእስራኤል እጅ አለበት ?
አልጀዚራ የቀድሞውን የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስቴር ሽሎም ቤንአሚንን አነጋግሮ ነበር፡፡
‹‹ አራፋትን በደንብ አውቀዋለሁ ለማለት ርግጠኛ አይደለሁም፡፡ የተደረጉት የሰላም ሂደቶች በሙሉ ለእኔ ውስብስብ የሆነ ሰውን የመፈለግ ሂደት አድርጌ ነው የምቆጥረው፡፡ ሎይድ ጆርጅ ከአይሪሽ መሪ ዲቫለራ ጋር መደራደር ሜርኩሪን በሹካ እንደማንሳት ያህል ነው ብሎ ነበር ፤ በቃ አራፋት ማለት ይህ ነው፡፡ የማይጨበጥ ነው ፡፡ በፍፁም በሩን አይዘጋም - በፍጹም በሩን አይከፍትም፡፡ ሁልግዜ የሚናገረው ለፍቺ የሚያስቸግርና አሻሚ ነው፡፡ ስምምነት እንደሚፈልግ ግልጽ ነው ፡፡ ነገር ግን ለስምምነቶቹ የሚያስቀምጣቸው ቅድመ ሁኔታዋች ምን እንደሆኑ በፍጹም ግልጽ አይደለም፡፡

‹‹ ጤንነቱን በተመለከተ ገና ወጣት እያለ ታማሚ መሆኑ ይነገርለታል፡፡ እስራኤል ለአራፋት ሞት ማንኛውንም ነገር ታደርጋለች የሚል እምነት ውስጤ የለም፡፡ በሌላ በኩል የአራፋት መኖር ከፓለቲካ አኳያ ለኤሪያል ሻሮን እንደ ትልቅ ንብረት ነው የሚቆጠረው፡፡ ››

ብዙዋች አራፋት የካምፕ ዴቪድን ስምምነት ባለመቀበላቸው ጥርስ ውስጥ መግባታቸውን ይስማማሉ፡፡ የረጅም ግዜ የአራፋት አማካሪ የነበሩት ሞሀመድ ራሺድ በተለይም ኢሁድ ባራክ በምርጫ ከተሸነፉና የክሊንተን ቡድን ከቢሮው ከለቀቀ በኃላ አጣብቂኝ ውስጥ እንደሚወድቅ ገልጬላቸው ነበር ይላሉ፡፡ ኤርያል ሻሮንን ባናገርኩበት ግዜ አንተን አልፈልግህም ለአለቃህ ግን ቀጣዩ ግዜ ከባድ እንደሚሆን ንገራቸው ብለውኝ ነበር የሚሉት አማካሪው ስለዚህ በመርዝ ይገደላሉ የሚል እምነት አለኝ ብለዋል፡፡ ጉብኝት በሚያደርግበት ግዜ ፕሮቶኮልም ሆነ ምግብ ቀማሽ የለውም የሚሉት  አማካሪው ለ32 ዓመታት ሳውቀው ብቻውን አይበላም ሲሉ አስተያየታቸውን አጠናክረዋል፡፡

ለሱሃ ጥሪ የተሰጠው ምላሽ
 
የሱሃን ጥሪ ተከትሎ የፍልስጤም መንግስት ሁለት መሰረታዊ ምላሾችን አሰምቷል፡፡ የመጀመሪያው ምርመራውን ያጠናክረው ዘንድ የያሲን አራፋት ሬሳ / ቤተሰቦቹ ፍቃደኛ ከሆኑ / እንዲመረመር ፍቃደኛ መሆኑን ማረጋገጥ ሲሆን ሁለተኛው በጉዳዩ ላይ ዓለማቀፍ ምርመራ እንዲደረግ ለዓለማቀፉ ማህበረስብ ጥያቄ ማቅረቡ ነው ፡፡ የፍልስጤምን ጥያቄ ተከትሎ ቱኒዝያ ፣የአረብ ሊግና ሀማስ ምርመራው ሳይውል ሳይድር እንዲጀመር እየጠየቁ ይገኛሉ ፡፡  ሌላው ዓለም ግን ልክ እንደተፈራራ ወይም የሁኔታውን አደገኛነት በመገንዘብ ሊሆን ይችላል እስካሁን ዝምታው ላይ እንደተኛ ነው፡፡

ምን ይጠበቃል ?
 
እናስ መጨረሻው ምን ሊሆን ይችላል ? ልክ እንደ ሩሲያው ሰላይ የአራፋትም ነገር ተዳፍኖ ይቀር ይሆን ? አለሁ አለሁ የሚሉት የአለማቀፉ ፍርድ ቤትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችስ ኃላፊነታቸውን በምን መልኩ ለመወጣት ይዘጋጃሉ ? ሱሃ አራፋት ላይ እየተነሱ የሚገኙት ጥያቄዋች አቅጣጫውን ይለውጡት ይሆን ?  ቱኒዚያ የተባረሩትን መሪዋን በሙስና ስለምትከስ ሱሃንም ለጥያቄ እንፈልጋታለን እያለች ነው ፡፡ የፈረንሳይ ጋዜጦች አራፋት በባንክ ያሰቀመጡትን ገንዘብና የዝውውር ሁኔታን በተመለከተ  የሱሃ እጅ ይጣራ እያሉ ይመስላል ፡፡ እነዚህ ነገሮች ዓላማቸው ምን ይሆን ?  

የአራፋት ነፍስ ግን ትጣራለች  - ቢያንስ  ለኛም ሀገር  የምርመራ ጋዜጠኛነት ተሞክሮ እያስተማረ የሚገኘው አልጀዚራ የለኮሰውን ሻማ ያጠፋዋል ማለት ያስቸግራል፡፡

Saturday, July 7, 2012

‎እውነት ድንጋዩ ማነው ?‎


አመክንዮ ተኮር ዳሰሳ


‹‹ ድንጋይ ራስ ! ›› ያስባል ተብሎ ለሚታሰበው ፍጡር ክፉ ስድብ ነው ፡፡ ለነገሩ ህይወት ካላቸውም ሆነ ከሌላቸው መካከል የማያስቡ በርካታ ቢሆኑም የድንጋይ ክፉ ተምሳሌትነት ግራ ያጋባል፡፡ በግ ራስ ! … ዛፍ ራስ ! … ለምን አልተባለ ይሆን ? በድንጋዮች ወገን ሆነን ብናስብ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው የሚሆንብን ፡፡

ከድንጋይ ስር የማይለየው ሰው ድንጋይን ማንቋሸሹ ለድንጋዮች አይዋጥም፡፡ ድንጋይ በመሬት፣ በጨረቃ፣ በባህር፣ ሌላው ቢቀር በሰው ሆድ ዕቃ ውስጥ አለ፡፡ መኖሩ ብቻ ሳይሆን መገለጫው በርካታ ነው፡፡ ድንጋይ ! እያለ የሚያንቋሽሸው ዘመናዊው ሰው የድንጋይ ቤት ውስጥ ለመቀመጥ ዕድሜ ልኩን ይለፋል፡፡ የአንድ መኪና ድንጋይ ዋጋ ጣራ ነካ እያለ እዬዬውን ያቀልጠዋል፡፡ የከበረ ድንጋይ በመሻት እርስ በርሱ ይጨራረሳል፡፡ ካባ ውስጥ ወዛም ድንጋይ ለመፈለግ አካባቢውን በፈንጂ ያሸብራል፡፡ በኮብል ስቶን ስራ ሲሰማራ ድንጋይ ዳቦ ሆነ በማለት ይፈላሰፋል ፡፡ ለአጥር፣ ለመንገድ፣ ለመጸዳጃ ቤት ወዘተ ውበት መፍጠሪያ ያለ ድንጋይ አይታሰብም ፡፡ ሲሞት ድንጋይ መሃል መቀበሩ አላረካው ብሎት የድንጋይ ህንጻ ይገነባል፡፡ ድንጋዩም ላይ እነሆ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ ሲል በድንጋይ ፊውቸር ቴንስ ጥቅሶችን ይጠቃቅሳል ፡፡

ይህን ሁሉ ድርጊት አርቀው የሚያስቡ ድንጋዮች በሰው አላዋቂነት …. ትንሽ ዕውቀት አደገኛ ነው እያሉ ማሽሟጠጣቸው ይጠበቃል፡፡ በተለይ እሱ ራሱ አፈር ከሆነ በኃላ ወደ ድንጋይ የመለወጥ ዕድሉ የሰፋ መሆኑን አለመገንዘቡ ያበሽቃቸዋል፡፡ እናም የመሰዳደቢያ ፈሊጣቸው ሰው ነው፡፡ ‹‹ ሰው ራስ ! ››… የተባለ ድንጋይ ራሱን ከመፈረካከስ ወደ ኃላ እንደማይል አይታያችሁም ?

በርግጥ ለድንጋይ ክብር የነሳው ዘመናዊው ሰው እንጂ የጥንቱ አይደለም፡፡ የጥንቱማ ቤቱ፣ ጠመንጃው፣ ክብሪቱ፣ ምጣዱ፣ ወረቀቱ… ድንጋይ ነበር ፡፡ ለድንጋይ ክብር የማይፋቅ ተዓምራትን አበርክቷል፡፡ የግብጹ ፒራሚድ፣ የሮሙ ላተርንና የአክሱሙ ሀውልቶች ሌሎችም ዛሬም ድረስ የሰውና የድንጋይ ጥምረትን ያሳብቃሉ፡፡ ድንጋይ ራስ ! እያለ የሚሳደበው ዘመናዊው ሰው በጥንቶቹ ሰዋች ተአምር ዛሬም እየተደመመ ነው፡፡ ተዓምራቶቹን ፈልቅቆ መነሻቸውንና ውበታቸውን ለማወቅ ቢፍጨረጨርም እንቆቅልሹ ባሰበው መልኩ አልተፈታለትም፡፡ ታዲያ ሰው ድንጋይን በቅጡ ሳያውቅ እንዴት የስድብ መጠሪያ አደረገው ? እስኪ እስካሁን አጥንቶ ምላሽ ያላገኘባቸውን ጥቂት የድንጋይ ጉዳዮች እያነሳን እንጫወት፡፡

ኮስታሪካ

በ16ኛው መቶ ክ/ዘመን በደቡብ ምዕራብ ኮስታሪካ ልዩ ልዩ መጠን ያላቸው ድንጋዮች ነበሩ፡፡ ድንጋዮቹ ትሪያንግል፣ ሬክታንግልና ክብ ቅርጽ ያላቸው ነበሩ፡፡ አብዛኛዋቹ ድንጋዮች የተገኙት በድኩዊስ ወንዝ አካባቢ ሲሆን የተፈጠሩት በ400 CE እንደሚሆን አርኪዋሎጂስቶች ገምተዋል፡፡ ይሁን እንጂ የኮስታሪካ ሙዚየም እስካሁን በሀብትነት የመዘገባቸው 130 ያህሉን ነው፡፡ ሌሎችማ በዘመናዊው ሰው ግልብ ፍላጎት ተፈረካክሰዋል -  ድንጋዮቹ መሃል ጌጣጌጥ ይገኛል በሚል፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ለጌጥነት በመኖሪያ ቤት፣ በአትክልት ቦታዋችና በየቤተክርስትያናት ተበታትነዋል፡፡

የዛሬውን ሰው እያነጋገረ ያለው ጉዳይ ድንጋዮቹ እንዴት ተፈጠሩ ? የሚለው ነው ፡፡ የአንዱ ድንጋይ ክብደት 16 ቶን ሲደርስ ፍጹማዊ ክብነቱ ጂኦሜትሪን ያሳጣል፡፡ ያኔ ደግሞ ስርዓት ያለው የሂሳብ ትምህርት አይታሰብም፡፡ አንዳንድ ተመራማሪዋች ቀራጺዋች ለዝናና ለጌጥ የሰሯቸው ናቸው በማለት ገምተዋል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በወቅቱ የነበሩ ሰዋች በከፍተኛ ደረጃ የማቅለጥ ግንዛቤ ነበራቸው ? የሚል ጥያቄ ያስከትላል፡፡ ምናልባት ድንጋዩን በአሸዋና በቆዳ አቅልጠው በማለስለስ ከበረደ በኃላ ክብ ገጽታ ለፈጥር ይችላል ይላሉ፡፡ የግራናይቱ ድንጋይ ከዲኪዋስ ወንዝ 40 እና 50 ኪሎ ሜትር ርቆ በሚገኝ ተራራ ላይ እንደነበር ታውቋል፡፡ እና ቀራጮቹ ድንጋዩን ሰርተው እንዴት ወደሌላ ቦታ አዘዋወሯቸው ? የሚለውም ጥያቄ ምላሽ አላገኘም፡፡ ምክንያቱም አንዱ ድንጋ|ይ ከ16 ቶን በላይ ስለሚከብድና በወቅቱ ዘመናዊ በሆነ መንገድ መጠቀም ስለማይታሰብ ነው፡፡

ኢትዮጽያ

ከ7 እሰከ 9 የሚገመቱት የአክሱም ሀውልቶችም ከጥበባቸው በላይ ርዝመታቸውና ግዝፈታቸው እስካሁንም እያጠያየቀ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እንዴት ተጓጓዙ ? እንዴትና በየትኛው መሳሪያ ደጋፊነት እንዲቆሙ ተደረገ ? በአበሾች ወይስ በሌሎች ? ለሚሉት ጥያቄዋች የሚሰጠው ምላሽ ያው አንጀት የማያርስና የግምት ትራስን የተደገፈ ነው፡፡ የጢያ ትክል ድንጋይ በቅርስነት የተመዘገበ ሃብት ነው፡፡ አካባቢው የመቃብር ቦታ እንደነበር ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ በሀውልቱ ላይ የተቀረጹት ምስሎች ግን ያው በፈረደበት ግምት እየተመተሩ ነው፡፡ የሳርና የዘንባባ ምልክቶች ልምላሜና ሀብትን… በወንድ ብልት መሰል የተቀረጹት ሀውልቶች የጀግንነትና የዘር መራባትን ሊጠቁሙ ይችላሉ በሚል፡፡ 

ኔዘርላንድ

በደች ግዛት በሆነቸው ድሬንዝ በፐ ቅርጽ የተሰሩ ድንጋዮች በብዛት ይታያሉ - ዶሊሚን ይሏቸዋል፡፡ ድንጋዮቹ ቀብር አካባቢ የሚገኙ ሲሆን ቱሪስቶች በብዛት ይጎበኙዋቸዋል፡፡ 53 ዶሊሚን የተመዘገቡ ሲሆን 52ቱ በድሬንዝ ይገኛሉ፡፡ ትልቁ ድንጋይ 22 ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን የ47 ድንጋዮች ቅንጅት ነው፡፡ አንዱ ድንጋይ 3 ሜትር ቁመትና 20 ቶን ክብደት አለው፡፡ ይህ ሁሉ ሁኔታ እነዚህን ድንጋዮች ማን ሰራ ? መቼ ? ለምንና እንዴት ? የሚሉ ጥያቄዋችን ያጭራል፡፡ ሳይንቲስቶች ዶሊሚን የተገነቡት በበረዶ እየተንሸራተቱ ነው ብለው ያስባሉ - በበረዶ ዘመን፡፡ የሚገነቡትም ገበሬዋች ሲሆኑ የባህላቸው አካል ስለሆኑ ነው፡፡ ሌላው ወገን በእንጨት እየተንከባለለ እንደሚጓዝ ይናገራል፡፡ ነገር ግን የሞቱ ሰዋች ለምን በተለመደው መልኩ ሊቀበሩ አልተፈለገም የሚለውን ጥያቄ መመለስ አልተቻለም፡፡

ዘመናዊው ሰው ስለ ድንጋዮች በቂ መረጃ ባያገኝም የጥንቱ ሰው በተግባር ተኮር እንቅስቃሴ የተከበበ ይመስላል፡፡ ጥናት፣ ምርምር ፣ኮንፈረንስ በሚሉ መሰረተ ሃሳቦች ግዜውን ከመግደል ይልቅ ያሰበውን ለመስራት ይተጋል፡፡ የበጀት፣ የአቅም፣ የግዜ ፣ የተነሳሽነት ጥያቄዋችን አካብዶ ሳያነሳ ድርሻውን ተወጥቷል፡፡ በዚህ እውነታ ስር የፈበረካቸው ምርጥ ተግባራት ለዘመናዊው ሰው ፈተና ፈጥረዋል፡፡ ዳናውን ለማግኘት ሌት ተቀን ቢያጠና ተጨባጭ እውነት አልያዘም፡፡ ጠብ ያለው ውጤት የግምት መልሱ ብቻ ነው፡፡ ለዚህ ዓላማ… ለዚህ ጥቅም… ለዚህ ተልዕኮ በዚህ ዓይነት ሰዋች ተሰርተው ይሆናል ይለናል፡፡ ከዚሁ ጎን የጥንት ሰዋችን የአሰራርና የእምነት ፍልስፍና በእሱ መነጽር ብቻ እየተመለከተ ኃላቀርነታቸውን ይነግረናል፡፡ ስለ ድንጋይ ክብር ሳይገነዘብ ወይም ምኞቱን ከሟላ በኃላ እየረሳ ድንጋይ ራስ ! እያለ ይሳደባል፡፡ ይህ ደግሞ ድንጋይ ራስ ! የሚለው ስድብም ግምታዊ ሊሆን እንደሚችል ጠቋሚ ነው፡፡

ዘመናዊው ሰው ትልቁ ድንጋይ  ውስጥ ወርቅ ይገኛል እያለ መፈረካከሱ ግለኝነቱንና አላዋቂነቱን ያቃጥራል፡፡ የቱሪስት መስህብ እያለ ገንዘብ ይሰበስብባቸዋል፡፡ ለዚህ ሁሉ የሃብት፣ የሞራልና የታሪክ ፍላጎቶች መሰረቱ የጥንት ሰው ነው፡፡ የጥንት ሰው ደግሞ ለድንጋይ ታላቅ ክብር አለው፡፡ በዚህ እሳቤ ድንጋይ ራስ ! የሚል ስድብ አይጠቀምም፡፡ ይህን ሁሉ ሃሳብ / logic / ብናገጣጥመው አንድ ስዕል እናገኛለን፡፡ ሊሳደብ የሚችለው አፍ ያለው ሰው ወይስ አንደበቱ የማይታየው ድንጋይ ? የትኛውስ ነው ትክክል ?…. ድንጋይ ራስ ! የሚለው ሰው ወይስ ሰው ራስ ! የሚለው ድንጋይ ?….

Tuesday, July 3, 2012

እየተወገዘ የሚለመልም …




‹‹ የት ተፈጠረ ? ›› የሚለው ጥያቄ ሲነሳ ብዙዋች ይጣሉበታል፡፡ ገሚሱ ትውልድ ሃገሩ ኢትዮጽያ ነው ሲል ሌላው የመን መሆኑን ያስረዳል፡፡ ኢትዮጽያ እና የመን ‹‹ የኔ ነው ›› እያሉ የሚከራከሩበት በስንት ነገር ነው ጃል ?! ላለፉት 3ሺ ዓመታት በታላቋ ንግስት ሳባ የታሪክ ጉተታ ውስጥ ገብተው የሃሳብ ልብሳቸውን ሲቦጫጭቁ ነበር፡፡ በርግጥ ትግሉ በአዳፍኔና በጨበጣ መጠዛጠዝን ያለመ አልነበረም፡፡ ስልቱ ዞር ያለ ነበር፡፡ ለምሳሌ ያህል

የደረጀ ጥናታዊ ጽሁፍን - እንደ ጦር ማምረቻ ሰፈር
የቁፋሮ ምርምርን - እንደ ፈንጂ
ነባራዊ ማስረጃ የሆኑትን ማለትም ቤተ መንግስትን - እንደ ዘመቻ መምሪያ
መዋኛ ገንዳን - እንደ  መርከብ
ሳባዊ ጽሁፍን - እንደ ፕሮፓጋንዳ ክፍል
የሚነገሩ ትውፊቶችን - እንደ ሚዲያ ተቋም ሳይጠቀሙ አይቀርም፡፡ ደግነቱ ሁለቱም ወገኖች ወደ ዓለማቀፉ ፍርድ ቤት ሳይሄዱ ወይም የመሄድ ፍላጎት ሳያሳዩ ሳይንቲስቶች የአሸናፊነቱን ካባ ለኢትዮጽያ አልብሰዋል፡፡ አሁንም በነካ እጃቸው የዚህን ተክል መፈጠሪያ ቢወስኑ ጥሩ ነው፡፡ ለነገሩ የመጀመሪያ መባል ታሪካዊ ትርፍ ካለው እንጂ ይሄኛው ተክልስ አጨቃጫቂ ባህሪ አለው፡፡

ይህ ተክል የት ተፈጠረ ብቻ ሳይሆን መቼ ተገኘ ? የሚለውም ሀሳብ ላይ ስምምነት አልተገኘም፡፡ ገሚሱ በ13ኛው ሌላው በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሚል ሀሳብ አለውና፡፡ ተክሉ ኢትዮጽያም ይፈጠር የመን ከዚያ ወዴት አቀና ለሚለው ጥያቄ ግን ተመራማሪዋቹ ተመሳሳይ ምላሽ አላቸው፡፡ ወደ ሶማሊያ፣ ማላዊ፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ አረብ፣ ኮንጎ፣ ዚምባብዌ፣ ዛምቢያና ደቡብ አፍሪካ የሚል፡፡

ለረጅም ዓመታት የሳይንቲስቶችን ቀልብ የገዛው ተክል መጠን ሰፊ ጥናት ሲደረገረበት ቆይቷል፡፡ አንዳንዶቹ አደገኛ ሌሎች ለስላሳ ወይም የማይጎዳ የሚል ፍረጃ ቢሰጡትም የአፍቃሪዋቹ ቁጥር በእጅጉ ከመበራከት ያገዳቸው ሁኔታ የለም፡፡ መልከ መልካሙ  ቅጠል በየሀገሩ የተለያየ ስያሜ ቢሰጠውም ከቤት መድፊያ አንጻር ተመሳስሎ ይንጸባረቅበታል፡፡ በኢትዮጽያ ጫት፣ በአረብ ጃት፣ በየመን ካት ወይም ጋት፣  በሶማሊያ ጃድ፣ በኬንያና ታንዛንያ ሚራ ይባላል፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ በኢትዮጽያ ወይም በየመን በቀለ የሚባልለት ‹ ካት . በብዙ ሀገሮች ዘንድ እንደ እርኩስ መንፈስ ተቆጥሮ / በርግጥ ቀደም ባሉት ግብጻዊያን የሰማይ ቤት ምግብ እንደሆነ እምነት አላቸው / የህግ አጥር ቢበጅለትም እንደ ጀት በፈጠነ ሩጫው ገብኝቱን ከማጠናከር ወደ ኃላ አላለም፡፡  የቅርብ ግዜ መረጃዋች እንደጠቆሙት ከሆነ ‹ ጃድ › በእንግሊዝ፣ ጣሊያን፣ አምስተርዳም፣ ካናዳ፣ አውስትራሊያ፣ ኒውዚላንድና አሜሪካ ታይቷል፡፡

ጫት እንደ ክፉው ሰይጣን በቀን ሺህ ግዜ ይወገዛል ፡፡ አደንዛዥነቱ፣ የሱስ ተገዢ ማድረጉና የስራ ባህልን መጉዳቱ፣ ከጥርስ ጀምሮ በተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ላይ ጉዳት ማስከተሉ፣ አልፎ አልፎም የአእምሮ ስርዓትን በማፋለስ ለቀውስነት እንደሚዳርግ ሳይንሳዊ እውነታዋችን ዋቢ በማድረግ የማስጠንቀቂያ አታሞ ይደለቅለታል፡፡ በተቃራኒው ጎን ደግሞ ሺ ግዜ ይሞገሳል ፣ ይገጠምለታል ፣ ይጠቀስለታል ‹ የቃመ ተጠቀመ ፣ ያልቃመ ተለቀመ › ዓይነት ...

ዛሬ የከተማን ህጻን ጅብ ይበላሃል ብለው ቢያስፈራሩት ባማረ መልኩ ይስቅቦታል፡፡ ምክንያቱም ከተሞች ጅብን የሚያሳድር ጫካቸውን በሚያስፈራሩ ሰዋች መነጠቃቸውን ያውቃልና፡፡ እንደ ህጻናቱ ሁሉ ወጣቱም ሆነ አዛውንት የቂማ ስራዊት በጫት ላይ የተመሰረቱ አስጊ ዜናዋችን የሚያዳምጠው ጫት እየቃመ ነው፡፡ ከመደንገጥ ይልቅ ፈገግ ይላል፡፡ ፈገግታው መቼም ለምጸት እንጂ ለኮረኮረው እውነታ ቅርብ ሆኖ አይመስልም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ምጸቶች ደግሞ ኅልቆ መሳፍርት የሆነ ፍቺ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ እንደው ሲያቀብጠኝ እንደሚከተለው እያሰበ ይሆን እላለሁ ?

እሳቤ አንድ፣

ደራሲው በመጣጥፉም ሆነ በግጥሙ ጫት እንዴት ትውልድን እያደነዘዘና እየገዘገዘ መሆኑን በሚያስጨበጭብ መልኩ ይገልጸዋል፡፡ የተጨበጨበለትን ስነጽሁፍ የደረሰው ግን ኮባውን ትራስ፣ እንጨቱን መፋቂያ፣ ቅጠሉን መስተፋቅር አድርጎ ነው፡፡

እሳቤ ሁለት፣

ጋዜጠኞች በአንደኛው መታወቂያቸው ሀሳቡን ደጋግመው ወቅጠውታል፡፡ ምናልባት የቀራቸው ‹‹ በርጫ ›› የሚል ቋሚ አምድ ወይም ፕሮግራም ማስጀመር አለመቻላቸው ነው፡፡ በሁለተኛው መታወቂያቸው ላይ ‹‹ ለዚች ዓለም ዱካክና ድብርት ሳትበገር ሀቃራህን ፍታ ! ›› የሚል ጽሁፍ በትልቁ ይታያል፡፡ ይህ ጽሁፍ የሚገኘው ‹ ብሄር › የሚለው ሰረዝ ላይ ነው፡፡

እሳቤ ሶስት፣

ሙዚቀኛው ምርጥ ግጥምና ዜማን ለማፍለቅም ሆነ ለመምረጥ ተመስጦ ፍቱን መሳሪያ መሆኑን ያምናል፡፡ ተመስጦውን ተግባራዊ ለማድረግ ግን ዮጋን ሳይሆን በለጬን አስበልጧል ፡፡ በህንድ የተመሰረተው ዮጋ ሂንዱዚም፣ ቡዲሂዝም፣ ጄይኒዝም፣ ሲኪዝም በተባሉ የእምነት እቅፍ ውስጥ ያደገ ነው፡፡ ታዲያ በዮጋ ለሰዓታት ተቆራምዶ የማይታወቅ የ< ኢዝም > ባህር ውስጥ ሰምጦ ማን ይንቦጫረቃል ? ከማያውቁት መልዓክ የሚያውቁት ሰይጣን እንዲሉ ይልቅ ሳቅ፣ ደመቅና ቦርቀቅን አስቀድሞ ጨመቅና ደንዘዝን ለሚያስከትለው ቅጠል የአውሊያን መንገድ ማሳየት ይበልጣል ፡፡

እሳቤ አራት፣

መንግስት በአደባባይ ያወግዘዋል ፤ ከበስተኃላ በጫት የሚገኘው የውጭ ምንዛሪ እንዴት የሆነ እጥፍ መጨመር እንደሚገባው ከብጤዋቹ ጋር እየገመገመ አቅጣጫ ያስቀምጣል፡፡

አስደሳች ማስተካከያ ፤ ደራሲ፣ ጋዜጠኛና ሙዚቀኛ የሚለው ሀሳብ ፊት ‹‹ አንዳንድ ›› የምትል ሚዛናዊ ማድረጊያ ቃል እንዳለች በውስጠ ዘ ይታወቅልኝ !!

ታዲያ እንዲህ እየተወገዘ የሚለመልም ተክል እንዴት የአጋሮቹ ቁጥር ሊቀንስ ይችላል ?  ‹ ሚራ ›  የሚያስገኘው ጥቅም ከፍተኛ ከመሆኑ አንጻርም በእርሻ ክፍለ ዘርፍ ውስጥ ግዛቱ ሰፊ እየሆነ ነው ፡፡ ለምሳሌ በየመን 40 ከመቶ የሚሆነው የውሃ አቅርቦት በመስኖ የሚጓዘው የጫት ተክልን ሊያለማ ነው፡፡ በ2001 በተደረገ ጥናት የየመን አርሶአደር ከአንድ ሄክታር ፍራፍሬ 0.57 ሚሊዮን ሪያል ሲያገኝ የጫቱ ገቢ ግን 2.5 ሚሊዮን ሪያል ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ጫት የሚበቅልበት 8ሺህ ሄክታር በ2000 ዓ.ም 103 ሺህ ሄክታር ደርሷል፡፡ ኢትዮጽያ በምትልከው ጫት በዓመት ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ እያገኘች በመሆኑ እንደ ቃሚው ሁሉ የእርሻ መሬቱም ግዛቱን እያሰፋ መጥቷል፡፡
 

የጫት አርሶ አደሮቹም በየግዜው ቃለ መጠይቅ ሲደረግላቸው ፤ ከፍተኛ ገቢ አግኝተንበታል … አነስተኛ ውሃ ነው የሚፈልገው… የማይበጠስ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቁርኝት አለው / በሰርግ፣ በለቅሶ፣ በጸሎት ወዘተ ወቅት ይቃማል / … እንደ ሌሎች ሰብሎች ጉልበታችንን አይበላም… እንደ ምግብም ያገለግላል… ወዘተን የሚገልጹት በታላቅ መተማመን ነው ፡፡ 
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ  አንድ ተጠቃሽ ቀልድ ትዝ አለኝ ፡፡ አንዳንዶች እውነት ነው ቢሉትም እኔ አስተማማኝ መረጃ ባለማግኘቴ ጉዳዩን ብቻ አነሰዋለሁ ፡፡ ሀረር ውስጥ በቀረበ አንድ የ ‹ ልጅ ቀለብ ይቆረጥልኝ › ክስ ፍርድ ቤቱ የተከሳሹን ወርሃዊ የደመወዝ ገቢ መሰረት በማድረግ ቀለብ እንዲቆረጥ ውሳኔ ይሰጣል ፡፡ ሆኖም ተከሳሽ በፍርድ ቤት የተቆረጠበት የገንዘብ መጠን ፈጽሞ አልዋጽልህ ይለዋል ፡፡ ስለሆነም የይግባኝ አቤቱታ ለይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ያቀርባል ፡፡ ተከሳሹ በይግባኝ አቤቱታው ላይ ቅሬታውን ሲያሰማ ‹‹ የተከበረው ፍርድ ቤት በዚህ የኑሮ ውድነት ደመወዝ ከምግብና ከበርጫ እንደማታልፍ እየታወቀ …. ›› ብሎ በመናገሩ ፍርድ ቤቱ  የቀለብ መጠኑን ሲወስን  ‹‹ በርጫን ›› ግምት ውስጥ ማስገባት እንደነበረበት በአጽንኦት ተከራክሯል ፡፡  
ታዲያ ጫትንና እንደ አንዳንዶች አገላለጽ ‹  ጫታም ትውልድን › እንዴት ነው ማረቅ  የሚቻለው ?  ሲሰድቡትም ደስ የሚል ፣ ሲቅሙትም ደስ የሚል ነገር እንደምን ማጥፋት ይቻላል ? ለምሳሌ ጫትን ሳንቲም አድርገን ብንወስደው በሁለቱም ፊቱ አንድ አይነት ምስል ነው ያለው ፡፡ ወይ ጎፈር ወይ ዘውድ፡፡ ሁለቱንም ምስሎች በግድ እንኳን ብናጠፋ ሳንቲሙ ሳንቲም የመባሉ ጉዳይ ያበቃለታል፡፡  ጫት የማይነገር ከፍተኛ ክብር እንዳለውም ማወቅ ይገባል፡፡ የውጭ ምንዛሪ በማምጣት የቡና ተከታይ በመሆኑ እስካሁንም የብር ሜዳሊያ አጥላቂነቱን የነጠቀው ምርት የለም፡፡ ወደፊት የኢኮኖሚ ዋልታ በርጫ በርጫ… ተብሎ አይዘፈንለትም ብሎ መከራከር ጠባብ ዕድል እንደመያዝ ያስቆጥራል፡፡

‹ ለሁሉም ግዜ አለው ! › የተሰኘውን የጠቢቡ ሰለሞንን ምሳሌ የተዋሰው የሚመስለው ‹ ጫት › በኢትዮጽያ ሌላ ታሪክ መፍጠር ችሎ እንደነበር ስንቶቻችን እናውቃለን ?  ነገርን ከስሩ ውሃን ከጥሩ ነውና አጭር ትረካ ላስከትል …

 በአንድ ወቅት ዶ/ር እያሱ ኃ/ስላሴን ለማነጋገር ካሳንችስ ወደሚገኘው ክሊኒካቸው አምርቼ ነበር ፡፡ ሀኪሙ በመደበኛ ከሚሰጡት የህክምና አገልግሎት ውጪ በስነ ተዋልዶና በኤችአይቪ ዙሪያ ምሽት አካባቢ ለህብረተሰቡ ትምህርት ይሰጣሉ፡፡ በተጨማሪም የምርምር ስራዋችን ያከናውናሉ፡፡ በወቅቱ እኔን የሳበኝ በጫት ቅጠል ላይ ያደረጉት ምርምር ነበር ፡፡ መጀመሪያ በኢትዮጽያ ጫት በሚበቅልባቸው አካባቢዋች በመዘዋወር የጫትን አጠቃላይ ባህሪ አጠኑ፡፡ በተለይም የአደንዛዥነቱና የምርቃና ደረጃው ምን ያህል ነው ?  አንዱ ከሌላው እንዴት ይለያል ?  የሚለውን ማለት ነው፡፡ እሳቸው እንደነገሩኝ ጫት ከተቆረጠ ከ48 ሰዓታት በኃላ የማነቃቃት ኃይሉን ያጣል ፡፡ ከዚህ አንጻር ጫት ከነማሪዋናና ኮኬይን ጋር ተጨፍልቆ የሚሰደበውና የሚወገዘው አለኃጢያቱ ነው እንዴ ?  የሚል ጥያቄ ማንሳት ነውር የለውም ፡፡

እናም በአንጻራዊነት ለስላሳ ከሚባለው ዕጽ የምርምር ውጤታቸውን ይፋ አደረጉ ፡፡ የጫት ቪኖ ተሰራ !! የቪኖው የአልኮልነት መጠን ከአስካሪ መጠጦች ደረጃ ጋር ሲነጻጸር ዝቅ ያለ ነበር ፡፡ ይህንንም ደረጃ መዳቢዋች በመሄድ እንዲረጋገጥ አድርገዋል፡፡ እኔም ታሽገው ከተቀመጡት ቪኖዋች ለሙከራ ስለተሰጠኝ ማጣጣም ችያለሁ ፡፡ ወደ ጫት የተጠጋው መዓዛ በስሱ ነው የሚታይበት ፡፡ እንደ መደበኛው ቪኖ ጉሮሮ ላይ የሚያግደው ነገር ሳይኖር ቁልቁል ከብለል ይላል ፡፡ የዶክተሩ እቅድ ሰፊ ነበር ፡፡ ምርቱን በስፋት ወደ ውጭ በመላክ ለራሳቸውም ሆነ ለሀገር የገቢ ምንጭነት ማሳደግ ፡፡ ሆኖም ከመድሃኒትና ቁጥጥር መ/ቤት ጋር በግዜው መግባባት ላይ መድረስ አልቻሉም ፡፡ ዛሬ ባለሙያው ምን ደረጃ ላይ እንዳሉ አላውቅም ፡፡ በመሆኑም በኢትዮጽያ የተፈጠረው የጫት ቪኖ እውቅና ሳያገኝ ተድበስብሶ ቀርቷል ፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ እነ የመን ኮፒ ፔስት ከተጠቀሙ ሌላ የጭቅጭቅ ምዕራፍ ሊከፈት አይደል ? ይልቅ ዛሬ- ዛሬ በጣም የምታስፈራው ቻይና ናት ፡፡  ሀገራችን ብቅ ጥልቅ የሚሉት ዜጎቿ አሳምረው መቃምና መጨበስ ጀምረዋል ፡፡ ታዲያ ተከታዩ ጉዳይ ቪኖ አይደለም የድሃ ውስኪ መስራት ላይ አያነጣጥርም ማለት አይቻልም ፡፡ 

ዞሮ ዞሮ የቪኖው ሀሳብ  በራሱ ገራሚ ነው ፡፡ ምነው ቢሉ ቪኖው በዓለም ማህበረሰብ ዘንድ ቅቡልና ካገኘ  ‹ አደገኛ › ፣ ‹ እርኩስ › ፣ ‹ የጥፋት ቀለሃ ›  ወዘተ የሚሉ ቅጥያዋችን አራግፎ ለውዳሴ ይበቃል ፡፡ ቪኖው አሪፍ ጣዕም ስላለው እንደ ‹ ወይን ሃረጊቱ › እና የ ‹ ሾላ ፍሬነሽ › ሊገጠምለት ወይም ሊዘፈንለት ላለመቻሉስ ርግጠኛ የሚሆን ማን አለ ?

የጫት ብይን ምን ይሁን ታዲያ ?
.  እየተወገዘ የሚለመልም
.  እየተነቀፈ አጋር ያደመቀው
.  ሳይዋጋ የሚማርክ  ፡፡