Wednesday, July 11, 2012

‎አልጀዚራ ነፍስ ፍለጋ የለኮሰው ሻማ ይዳፈን ይሆን ?‎





እድሜ ለአልጀዚራ አንድ የሞተ ታሪክ ነፍስ ዘራ፡፡ ታዋቂው የኖቤል ተሸላሚና የፍልስጤም መሪ ያሲር አራፋት ህዳር 11 ቀን 2004 በፓሪስ በሚገኝ አንድ ወታደራዊ ሆስፒታል ውስጥ ነበር የሞቱት፡፡ በወቅቱ የሞታቸው መንስኤ ተደፋፍኖ ስለነበር ‹  ይሄ በሽታ ነው የገደላቸው ›  ለማለት አልተቻለም፡፡ ይህም በርካታ መላምቶች እንዲወለዱ አደረገ፡፡  ጉበት፣ ካንሰር፣ የደም መታወክና ኤድስ የሚሉት በጣም ጎልተው ይሰሙ ነበር ፡፡ እነሆ ከስምንት ዓመታት ቆይታ በኃላ አራፋት የሞቱት ፓሎኒየም በተባለ ሬዲዮ አክቲቭ ንጥረ ነገር ተመርዘው መሆኑ ተደረሰበት፡፡ ምርምራው የተካሄደው ስዊዘርላንድ በሚገኘው የሬዲዮ ፊዚክስ ተቋም በመሆኑ ዜናው አጠራጣሪ የሚሆንበት መንገድ ዝግ ነው፡፡ በምርመራው የአራፋት ልብሶች፣ ደም፣ ሽንት፣ ምራቅና ላብ ሳይቀሩ ተካተዋል፡፡ የተቋሙ ኃላፊ ዶ/ር ፍራንኮይስ ቦችድ ውጤቱን በይፋ ያረጋገጡ ሲሆን ምርምሩን ይበልጥ ማጠናከር ካስፈለገ የአራፋትን ሬሳ ሊመረመር ይችላል ብለዋል፡፡  እናም አራፋት የሞቱት በተፈጥሮ በሽታ ሳይሆን በከፍተኛ ደረጃ በተቀነባበረ የወንጀል ድርጊት ነው፡፡ አራፋትን ማን ገደላቸው ? ፍልስጤም፣ ፈረንሳይ፣ እስራኤል፣ አሜሪካ ወይስ ሌሎች ?

ሲታከሙበት የነበረው የፈረንሳይ ወታደራዊ ሆስፒታል አሟሟታቸውን ለምን ደበቀ ?  እውነት የፍልስጤማዊያን ኃላፊዋችስ ምስጢሩን አያውቁም ነበር ?  በቀጣይ የሚደረገው ዓለማቀፍ ምርመራ  የተጠያቂ ግለሰቦችንና ሀገሮች ዱካ ላይ ይደርስ ይሆን ?  ይህ ወንጀልስ በቀጣዩ የሰላም ድርድሮች ላይ ምን ተጽዕኖ ያስከትላል ?  እንግዲህ ተቀብሮ የነበረው ጉዳይ ሳጥን ፈንቅሎ በመውጣት ሌላ የቀዝቃዛ ጦርነት ሊያስከትል አሞጥሙጧል፡፡

አልጀዚራና ሱሃ አራፋት
 
የስዊዘርላንዱን የሬዲዮ ፊዚክስ ተቋም ጨምሮ አልጀዚራና የያሴር አራፋት ባለቤት ሱሃ አራፋት ይህን ፈታኝ የምርመራ ስራ ዕውን ለማድረግ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ የምርመራው ስራ አሰልቺና ከባድ ዘጠኝ ወራትን ጠይቋል፡፡ የአራፋት የአሟሟት መንስኤ ከአሉባልታዋች ባለፈ ተጨባጭ ማስረጃ ላይ የተደገፈ አለመሆኑ ሲቆጨው የነበረው አልጀዚራ ኃላፊነቱን ወስዶ ጉዳዩ እንደ አዲስ እንዲነሳ ማድረጉ የሚገርም ነው፡፡ ግዜው በራቀ ቁጥር ተጨባጭ ማስረጃ ለማግኘት የሚደረገው ጥረት እየሳሳ እንደሚሔድ ይታወቃል፡፡ ግን እስካሁን ግልጽ ያላደረጉትን አስተማማኝ የምርመራ ፍንጭ በማግኘታቸው ሊሆን ይችላል ሀ ብለው የጀመሩት፡፡ በርግጥም የጋዜጠኝነት ፈታኝ ተግባር የሆነውን የምርመራ ዘገባ ለመስራት እውቀት፣ ብልሃት፣ ትዕግስት፣ ድፍረትና መስዋትነት ይጠይቃል፡፡

 ‹‹ የምርመራ ዘገባ  ሰዋች ወይም ድርጅቶች በምስጢር ሊይዙት የሚሽቱን ዓይነተኛ ጉዳይ በግል የስራ ውጤትንና ተነሳሽነት መዘገብ ነው ፡፡ እያንዳንዷን ዝርዝር ጉዳይ በጥልቀት የመፈተሸ፣ እውነታን የማፈላለግና ስነልቦናዊ ብቃትን ይጠይቃል፡፡ ጋዜጠኛውን የሚጠረጥረውን ወይም ዋጋ ይኖረዋል ብሎ ያሰበውን ጉዳይ ቀርቦ የመመርመር ብቻ ሳይሆን ከቀጣዩ ውጤት አንጻር የመተንተን ስራም ያከናውናል፡፡ ጉዳዩ ከጽሁፍ ማስረጃዋች ጋር ብቻ ሳይሆን እወቅና ከገኘ የህክምና ውጤት፣ ሳይንሳዊ ውጤቶች፣ ማህበራዊና ህጋዊ ድንጋጌዋች ወዘተ ጋር ሁሉ ሊተሳሰር ይችላል ›› / የጋዜጠኝነት ፈታኝ አጀንዳዋች ፤ አለማየሁ ገበየሁ ፤ ገጽ 16 /

በርግጥ የምርመራው ዘገባ ዋናውን ምዕራፍ ገለጸ እንጂ የመጨረሻው ውጤት ላይ አልደረሰም ፡፡ ይህ ምዕራፍ ግን ልክ  ለአንድ  የህንጻ  ግንባታ ትልቁን ሚና እንደሚጫውተው ‹‹ መሰረት ›› ግዙፍ መደላድል መፍጠሩ የማይታበል ነው፡፡ ቀጣዩን ስራ ለማከናወን የተዘረጋው አስፋልት ወደ መጨረሻው ፌርማታ ለማድረስ ፈጥነትንም ምቾትንም ታሳቢ ሊያደርግ ይችላል ፡፡ 

ለመሆኑ የምርመራው ስራ እንዴት ተጠንስሶ ወደ ውጤት ተቀየረ ?  ሱሃ አራፋት ሁኔታውን እንደሚከተለው ትገልጸዋለች
‹‹ በመጀመሪያ እኔ ተጨማሪ ምርመራ እንዲደረግ የሄድኩበት ሁኔታ አልነበረም፡፡ ከስምንት ዓመታት ቆይታ በኃላ ለምን አስፈለገ  ? ብለህ መጠየቅህ አይቀርም፡፡ ሆኖም የአልጀዚራ ጣቢያ ወደኔ መጥተው ምርመራ ማከናወን እንደሚፈልጉ ገለጹልኝ ፡፡ እናም አልጀዚራ ሌሎች ያልወሰዱትን ኃላፊነት ሊወስድ ነው ማለት ነው፡፡ ይሄ ብሄራዊ ስራ ነው፡፡ በዓለም ላይ ከፍተኛ ዝናና አቅም ያለው የምርመራ ተቋም ሊያስሱ ነው፡፡ በመሆኑም የፈረንሳይ ሆስፒታል የሰጠኝን ልብሶችና ቁሳቁሶች በሙሉ ሰጠዋቸው፡፡ የሴት ልጄንም ዘረመል ወሰዱ፡፡ ዘረመሉን ከባለቤቴ ልብስና ጸጉር ያገኙትን ነገር የማነጻጸር ስራ አከናወኑ፡፡ ውጤቱም ተመሳሳይ ሆነ፡፡

‹‹ ይህን ስራ የጀመርነው ከዘጠኝ ወራት በፊት ነበር፡፡የባለቤቴን ንብረቶቸ፣ የህክምና መድሃኒቶች፣ ሰዓቱን፣ የአንገት ሀብሉን በሙሉ ፈትሸዋል፡፡ በመጨረሻም ከፍተኛ መጠን ያለው ፓሎኒየም በደሙ፣ በልብሶቹ፣ በባርኔጣው፣ በውስጥ ልብሱ ሳይቀር ንጥረ ነገሩ ተገኝቷል፡፡ ይህ ደግሞ የሚገኘው በበለጸጉ ሃገሮቸ ብቻ ነው፡፡ አሁን አራፋት የሞተው በተፈጥሮ ህመም ሳይሆን በወንጀል መሆኑን መግለጽ እንችላለን፡፡ ከዚህ በኃላ የፍልስጤምን መንግስት እኔንም ሆነ ህዝቡን እንዲረዳ የምጠይቀው የባለቤቴ ሬሳ እንዲመረመር ፍቃድ እንዲሰጠኝ ነው፡፡ ሀኪሞች ትክክለኛውን አጥንት ካመጣሁ ንጥረ ነገሩ እንደሚገኝ ገልጸውልኛል፡፡ ሌላው ቢቀር ሬሳውን የከበበው አፈር ላይ እንኳ ሊገኝ ይችላል ፡፡ ሆኖም በፍጥነት መከናውን አለበት ››

ፓሎኒየም ምንድነው ?
ፓሎኒየም 210 በዓለማችን በቀላሉ ከማይገኙ ማዕድናት ውስጥ ይመደባል፡፡ በመጀመሪያ የተገኘው እኤአ በ1898 ሜሪ እና ፔሪ ኩሪ በተባሉ ሳይንቲስቶች ነበር፡፡ እነሱም ለሀገራቸው ክብር ሲሉ የማዕድኑን የመጀመሪያ ስም ከሀገራቸው Poland ጋር ለማስተሳሰር ሞክረዋል፡፡ በተፈጥሮ ከመሬት የላይኛው ክፍል ላይ በጥቂቱ የሚገኝበት ሁኔታ ያለ ሲሆን ለኒውኩለር ማብላሊያነትም በሰው ሰራሽ ዘዴ ሊመረት ይችላል፡፡ የፖሎኒየም አነስተኛ ንጥረ ነገር ማለትም 0.04 ኦውንስ ሰውን ለመግደል በቂ ነው፡፡ በተለይም ጉበት፣ ኩላሊትና የአጥንት ውስጥ ፈሳሽን በከባዱ የሚያጠቃ ሲሆን በከፍተኛ ደረጃ የማስታወክ፣ የጸጉር መሳሳት፣ የጉሮሮ ማበጥና መገርጣትን ያስከትላል፡፡

በነገራችን ላይ በዚህ ንጥረ ነገር የሚሞቱ ሰዋች በጣም አነስተኛ ሲሆኑ የቀድሞው የሶቭየት ህብረት መኮንና ሰላይ የነበረው አሌክሳንደር ሊቲቬንኮ በጉዳዩ የመጀመሪያው ሟች መሆኑ ተመዝግቧል፡፡ ለስለላ ተቋማት ይሰራ የነበረው ይህ ሰው ከሀገሩ ተሰዶ በእንግሊዝ ጥገኝነት አግኝቶ ይኖር ነበር፡፡ ከዚያም ጋዜጠኛ ሆኖ ከቼቼኒያ ጎን በመቆም ሩሲያን የሚቃወሙ ሁለት መጻህፍትን አሳትሟል፡፡ በሞስኮ ትያትር ቤት የተከናወነውን የጠለፋ ድራማና ለሌሉች የሽብር ተግባራት ተጠያቂው ፑቲን መሆናቸውንም ይገልጽ ነበር፡፡ ህዳር 2006 ታሞ ከሶስት ሳምንታት በኃላ ሞተ፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ በፖሎኒየም የሞተ ተብሎ መነጋገሪያ ሆነ፡፡ እንደውም ሳይንቲስቶች የኒውክለር ሽብር ተጀመረ በማለት ስጋታቸውን ገልጸው ነበር፡፡ ሰላዩ የሞተው የሚጠጣው ሻይ ውስጥ ንጥረ ነገሩ ተጨምሮበት ሲሆን የሞተውም በሚታወቁ የቀድሞው ጓደኞቹ አማካኝነት ነው፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ኃላ ላይ የሩሲያን ዲፕሎማሲ ላለማበላሸት በሚል ክሱን አዳፍኖታል፡፡

ሱሃ አራፋትን በጨረፍታ



 
ሱሃ በዌስት ባንክ ከሚኖሩ ሀብታም የክርስትያን ቤተሰቦች የተገኘች ናት፡፡ አባቷ ዳውድ አል ታዊል የባንክ ባለሙያ ሲሆን፣ እናቷ ሪሞንዳ አልታዊል ፓለቲከኛና የሚዲያ ሰው ነበሩ ፡፡ ትምህርቷን በፍልስጤም ግዛት ውስጥ ከተከታተለች በኃላ ለተጨማሪ ትምህርት ፓሪስ ወደሚገኘው ስርቦኔ ዩኒቨርስቲ አቅንታለች፡፡

አራፋት ሱሃን ያገኟት ጆርዳን በሚገኘው የአል ውህዳት ስደተኞች ካምፕ ውስጥ እኤአ በ1985 ነበር፡፡ ያኔ ዕድሜዋ በሃያዋቹ መጀመሪያ ሲሆን አራፋት 58 ሻማ ለኩሰዋል፡፡ የስራ ግንኙነታቸው ቀስ በቀስ ዳበረ፡፡ ሱሃ አራፋት ከፈረንሳይ ባለስልጣናትና ፓለቲከኞች ጋር ሲገናኙ ረዳትና አስተርጓሚ ሆና ትሰራ ነበር፡፡ በ1989 ተጋቡ ፤ ግንኙነቱ ግን ምስጢራዊ ነበር፡፡

አራፋትን ካገባች በኃላ ክርስትናን ወደ እስልምና በመቀየር ወደ ፒኤልኦ ጠቅላይ መምሪያ ቱኒዝያ አመራች፡፡ የሁለቱ ጋብቻ ህዝብ ያወቀው በ1992 አራፋት በሊቢያ በረሃ ከአውሮፕላን ተከስክሰው ሱሃ ልትጠይቃቸው ባቀናችበት ግዜ ነበር፡፡ ሀምሌ 24 ቀን 1995 ሴት ልጅ ወለደች፡፡ አራፋት በ1993 የሞቱትን እናታቸውን ለማስታወስ በሳቸው ስም ዛህዋ ሲሉ ሰየሟት፡፡ ሱሃ አራፋት ከሞቱ በኃላ በቱኒዚያ ለትንሽ ግዜ ተቀምጣለች፡፡ ይሁን እንጂ ከቱኒዝያው መሪ ሚስት ለይላ ቢን አሊ ጋር በመጣላቷ ወደ ማልታ ሄዳ ለመኖር ተገዳለች፡፡ በአሁኑ ግዜም ከፍልስጤም መንግስት ድጎማ ትቀበላለች፡፡

በቀድሞው ታሪክ ውስጥ ፈረንሳይና ፍልስጤም ምን ብለው ነበር ?
 
የፈረንሳይ ባለስልጣናት በሀገራቸን ህግ መሰረት የግለሰቦችን ምስጢር ማውጣት አንችልም በሚል መንስኤው እንዲደበቅ አድርገዋል፡፡ ትንሽ ቆይተውም የአራፋትን የህክምና ፋይል መስጠት የሚቻለው ለቅርብ ዘመዶች ብቻ ነው በሚል ለአጎታቸው ለናስር አል ኪድዋ ሰጥተውት ነበር፡፡ በወቅቱ ሚስታቸው ሱሃ ፍቃደኝነቷ አልተጠየቀም፡፡ ከዚያ ደግሞ የፍልስጤም የካቢኔ ጸሀፊ ሀሰን አቡ ሊድህ የአራፋትን ሙሉ የህክምና መረጃ ማግኘታቸውንና ታሪካዊ መረጃ መሆኑን በመግለጽ በዚሁ መሰረት መንግስታቸው አሰፈላጊ ርምጃዋችን እንደሚወስድ ተናግረው ነበር፡፡ ይህ ንግግር ለህዝቡ ዝርዝር መረጃ መስጠትን ያካትታል፡፡
ይሁን እንጂ መረጃው ለህዝቡ ስላልተገለጸ አራፋት የሞቱት እስራኤል መርዛቸው ነው የሚል ወሬ በሀገሪቱ ውስጥ ተሰራጨ፡፡ አስቀድሞ አራፋትን ሲከታተሉ የነበሩት ሀኪም አሽራፍ አል ኩርዲም ምናልባት ለአራፋት ሞት የተሻለው ምክንያት ይህ ሊሆን ይችላል በማለት ግምታቸውን ሰነዘሩ፡፡ የአራፋት አጎት አል ኪድዋ እስራኤል መርዛ ለመግደልዋ ምንም አይነት መረጃ የለም በማለት ተከራከሩ፡፡ በወቅቱ የእስራኤል መገናኛ ብዙሃን የአራፋት ሞት ኤድስ ነው በማለት ይዘግቡ ነበር፡፡ ምናልባት አራፋት ከመሞታቸው በፊት የፈረንሳይ  ሀኪሞች አራፋት አነስተኛ የቀይ ደም ሴልና ከፍተኛ ነጭ ደም ሴል እንደታየባቸው መግለጻቸውን መሰረት በማድረግ ‹‹ ይሄ ይሆናል ›› የሚለውን ግምት እንዲያሰፋው አድርጎ ሊሆን ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ ሆን ተብሎ ፡፡

ለአራፋት ሞት የእስራኤል እጅ አለበት ?
አልጀዚራ የቀድሞውን የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስቴር ሽሎም ቤንአሚንን አነጋግሮ ነበር፡፡
‹‹ አራፋትን በደንብ አውቀዋለሁ ለማለት ርግጠኛ አይደለሁም፡፡ የተደረጉት የሰላም ሂደቶች በሙሉ ለእኔ ውስብስብ የሆነ ሰውን የመፈለግ ሂደት አድርጌ ነው የምቆጥረው፡፡ ሎይድ ጆርጅ ከአይሪሽ መሪ ዲቫለራ ጋር መደራደር ሜርኩሪን በሹካ እንደማንሳት ያህል ነው ብሎ ነበር ፤ በቃ አራፋት ማለት ይህ ነው፡፡ የማይጨበጥ ነው ፡፡ በፍፁም በሩን አይዘጋም - በፍጹም በሩን አይከፍትም፡፡ ሁልግዜ የሚናገረው ለፍቺ የሚያስቸግርና አሻሚ ነው፡፡ ስምምነት እንደሚፈልግ ግልጽ ነው ፡፡ ነገር ግን ለስምምነቶቹ የሚያስቀምጣቸው ቅድመ ሁኔታዋች ምን እንደሆኑ በፍጹም ግልጽ አይደለም፡፡

‹‹ ጤንነቱን በተመለከተ ገና ወጣት እያለ ታማሚ መሆኑ ይነገርለታል፡፡ እስራኤል ለአራፋት ሞት ማንኛውንም ነገር ታደርጋለች የሚል እምነት ውስጤ የለም፡፡ በሌላ በኩል የአራፋት መኖር ከፓለቲካ አኳያ ለኤሪያል ሻሮን እንደ ትልቅ ንብረት ነው የሚቆጠረው፡፡ ››

ብዙዋች አራፋት የካምፕ ዴቪድን ስምምነት ባለመቀበላቸው ጥርስ ውስጥ መግባታቸውን ይስማማሉ፡፡ የረጅም ግዜ የአራፋት አማካሪ የነበሩት ሞሀመድ ራሺድ በተለይም ኢሁድ ባራክ በምርጫ ከተሸነፉና የክሊንተን ቡድን ከቢሮው ከለቀቀ በኃላ አጣብቂኝ ውስጥ እንደሚወድቅ ገልጬላቸው ነበር ይላሉ፡፡ ኤርያል ሻሮንን ባናገርኩበት ግዜ አንተን አልፈልግህም ለአለቃህ ግን ቀጣዩ ግዜ ከባድ እንደሚሆን ንገራቸው ብለውኝ ነበር የሚሉት አማካሪው ስለዚህ በመርዝ ይገደላሉ የሚል እምነት አለኝ ብለዋል፡፡ ጉብኝት በሚያደርግበት ግዜ ፕሮቶኮልም ሆነ ምግብ ቀማሽ የለውም የሚሉት  አማካሪው ለ32 ዓመታት ሳውቀው ብቻውን አይበላም ሲሉ አስተያየታቸውን አጠናክረዋል፡፡

ለሱሃ ጥሪ የተሰጠው ምላሽ
 
የሱሃን ጥሪ ተከትሎ የፍልስጤም መንግስት ሁለት መሰረታዊ ምላሾችን አሰምቷል፡፡ የመጀመሪያው ምርመራውን ያጠናክረው ዘንድ የያሲን አራፋት ሬሳ / ቤተሰቦቹ ፍቃደኛ ከሆኑ / እንዲመረመር ፍቃደኛ መሆኑን ማረጋገጥ ሲሆን ሁለተኛው በጉዳዩ ላይ ዓለማቀፍ ምርመራ እንዲደረግ ለዓለማቀፉ ማህበረስብ ጥያቄ ማቅረቡ ነው ፡፡ የፍልስጤምን ጥያቄ ተከትሎ ቱኒዝያ ፣የአረብ ሊግና ሀማስ ምርመራው ሳይውል ሳይድር እንዲጀመር እየጠየቁ ይገኛሉ ፡፡  ሌላው ዓለም ግን ልክ እንደተፈራራ ወይም የሁኔታውን አደገኛነት በመገንዘብ ሊሆን ይችላል እስካሁን ዝምታው ላይ እንደተኛ ነው፡፡

ምን ይጠበቃል ?
 
እናስ መጨረሻው ምን ሊሆን ይችላል ? ልክ እንደ ሩሲያው ሰላይ የአራፋትም ነገር ተዳፍኖ ይቀር ይሆን ? አለሁ አለሁ የሚሉት የአለማቀፉ ፍርድ ቤትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችስ ኃላፊነታቸውን በምን መልኩ ለመወጣት ይዘጋጃሉ ? ሱሃ አራፋት ላይ እየተነሱ የሚገኙት ጥያቄዋች አቅጣጫውን ይለውጡት ይሆን ?  ቱኒዚያ የተባረሩትን መሪዋን በሙስና ስለምትከስ ሱሃንም ለጥያቄ እንፈልጋታለን እያለች ነው ፡፡ የፈረንሳይ ጋዜጦች አራፋት በባንክ ያሰቀመጡትን ገንዘብና የዝውውር ሁኔታን በተመለከተ  የሱሃ እጅ ይጣራ እያሉ ይመስላል ፡፡ እነዚህ ነገሮች ዓላማቸው ምን ይሆን ?  

የአራፋት ነፍስ ግን ትጣራለች  - ቢያንስ  ለኛም ሀገር  የምርመራ ጋዜጠኛነት ተሞክሮ እያስተማረ የሚገኘው አልጀዚራ የለኮሰውን ሻማ ያጠፋዋል ማለት ያስቸግራል፡፡

No comments:

Post a Comment