Sunday, July 22, 2012

‎ጠ/ሚ/ር መለስ ሲመለሱ ….‎



መቼም ዓለም የተቃርኖ ሙሌት ናት፡፡ ብርሃን ስንል ጨለማ፣ ሰማይ ስንል ምድር፣ ጎፈር ስንል ዘውድ፣ ደስታ ስንል ሀዘን፣ ህይወት ስንል ሞት የሚባሉት የቁርጥ ቀን አዛማጆች በአእምሮአችን ሳይጠሩ ከተፍ ይላሉ ፡፡

ከዚህ እውነት አንወጣም ፡፡

እንደሚታወቀው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ታመው ህክምና በመከታተል ላይ ናቸው ፡፡ እሳቸው ባይናገሩም ሌሎች ግን ስለሳቸው ከላይ በተገለጸው እውነት መሰረት ሀሳባቸውን ይሰነዝራሉ ፡፡ የመንግስት ኃላፊዋች ድነው ይመለሳሉ ሲሉ ሌላው ህመሙ አስጊ ስለሆነ አይተርፉም ይላል፡፡ ክርክሩ ይጡዝ እንጂ ነባራዊውን እውነት የሚዳኘው ፈጣሪ ነው፡፡ አሁንም አንዳንዶች ወሳኙ ሀኪሞች ናቸው ሊሉ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ሁለቱ ጫፎች መሳሳብ ስላለባቸው ፡፡ ሁለቱ ጫፎች ለስነፍጥረትም ሆነ ለቴክኖሎጂው መሰረት መሆናቸውም ይታወቃል ፡፡

እኔም ሁለቱን ጫፍ ተንተርሼ በአቶ መለስ ዙሪያ ወግ ለመሰለቅ አሰብኩ ፡፡ አቶ መለስ ድነው ቢመለሱና አያድርግባቸውና አቶ መለስ ቢያርፉ በሚሉት ሀሳቦች ላይ ፡፡ ቆይቼ ሳስበው ‹ ቢያርፉ › የሚለው ሀሳብ ከይሲ ሆኖ ተሰማኝ ፡፡ ደግሞስ እኔ ማነኝና ይህን ለማወቅም ሆነ ለመገመት ስልጣን የተሰጠኝ ፡፡ ደግሞስ ግዜው ነው ወይ ? ሲል ውስጤ ሞገተኝ ፡፡ ስለዚህ ቀናውን ሞፈር ጨብጬ የወግ ማሳዬን መተርተር እንደሚሻል ወሰንኩ ፡፡

እነሆ ከጎፈር ዘውድን መረጥኩ / ስልጣን ስለሆነ / ፤ እነሆ ከሰማይ ምድርን ሻትኩ / መቼትን ስላስታወስኩ / ፤ እነሆ ከሞት ህይወትን ጠራሁ ፡፡ እናም አቶ መለስ በህይወት ሲመለሱ ምን ያደርጋሉ ? ምን እንሰማለን ? የሚሉ ምናባዊ ትንታኔዋችን እያነሳሁ እጥላለሁ ፡፡

ምዕራፍ አንድ የሚጀምረው አውሮፕላን ውስጥ ነውና አቶ መለስ በኢትዮጽያ አየር መንገድ ወደ አዲስ አበባ እየተመለሱ ነው፡፡ ሻምፓኝ ተከፍቶ እየተጠጣ ነው ፡፡ ጎምቱ ባለስልጣናት መለስን ከበው በማያስቀው ሁሉ ይስቃሉ ፡፡ አራት ቦታ የተቆረጠው ኬክ ገና አልታደለም ፡፡ በእያንዳንዱ ቁራጭ ላይ የሰፈሩት ጽሁፎች ሲገጣጠሙ ‹‹ ረጅም ዕድሜ ለመለስ ›› የሚል መልዕክት ያስተላልፋሉ ፡፡

ሲፈራ ሲቸር የቆየው የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ማይኩን ይዞ ወደ አቶ መለስ ጠጋ ሲል የሚያውካኩ ድምጾች መጥፋት ጀመሩ ፡፡
‹‹ እንኳን ለዚህ አበቃዋት ጠ/ሚ/ር ››
‹‹ አመሰግናለሁ ! ››

የጋዜጠኛው ድምጽ ባይሰማም  የሆነ ጥያቄ ወረወረ፡፡ ያው ከመልሱ እናገኘው የለ ?! መልሱም ተከተለ ፡፡

1 . እንደሚገባኝ የመታከሙ ተልዕኮ የተሳካ ነበር ማለት ይቻለል፡፡ ይህን አባባል በሶስት መልኩ መንዝሮ ማብራራት የተሻለ ሳይሆን አይቀርም ፡፡ ቁልፉና ማጠንጠኛው አንድ ሰው በተለይም አንድ የሀገር መሪ ታሞ መዳን መቻሉ ነው ፡፡ ይህን የመዳን ጥያቄ ደግሞ ጠንካራ የሚያደርገው የታማሚው መሪ ግለኛ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን የታማሚውን መጨረሻ የሚጠብቁ ብዙ ሚሊዮን አይኖች መኖራቸው ነው ፡፡ ርግጥ ነው 90 ከመቶ ያህሉ ይህ በሽተኛ መሪ እንዲድን ለሚቀርበው ፈጣሪም ሆነ ጣዖት መለማመኑ ይጠበቃል ፡፡ አስር ከመቶው ግን ከቁጥሩ በላይ ያበጠ ፍላጎት እንደነበረው አምናለሁ ፡፡ በጣም የሚገርመው በዚሁ አሃዝ ውስጥ የሚካተተው ጥቂት ማህበረሰብ የሚናገረው ርግጠኛ የመሆኑ ጉዳይ ላይ ነው  ፡፡

ለምሳሌ ያህል  ‹ መለስ ከዳነ ከምላሴ ጸጉር ይነቀል › ብሎ ይነሳል ፡፡ በርግጠኝነት የሚያወራው ሞቱን ብቻ ሳይሆን የሕመሙንም መንስኤ ነው ፡፡ የያዘው የጭንቅላት ዕጢ የሚያፈነዳው እንጂ ለቀዶ ጥገና የሚመች አይደለም ብሎ ይደመድማል ፡፡ ወይ በሌላ ገጹ በድብቅ ያበሉት መርዝ ለጥቂት ግዜ ብቻ ነው የሚያላውሰው እንደሚል አይጠረጠርም ፡፡ ስለሆነም ጥቂቶች ካወሩት ሚሊዮን አሉባልታና ሚሊዮን ክፉ ምኞት አንጻር ህክምናው የተሳካ ነበር ለማለት ያስደፍራል ፡፡

በሁለተኛ ደረጃ መታየት ያለበት እኔን ሲያክሙና ሲንከባከቡ ከነበሩ ዶክተሮች አንጻር የሚተነተን ነው ፡፡ እንደምታውቀው መሪዋች ሲታከሙ ለማዳን የሚኖረውን ከፍተኛ ጥንቃቄ ያህል ከውስጥ በጣም ያረገዘ ነገር ግን የማይታይ ስጋት ይኖራል ፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የተጠራቀመው ስጋት የሚጫነው ደግሞ ሀኪሞች ላይ ነው ፡፡ ሀኪሞች ሌላ ዓላማ ላነገቡ ሰዋች፣ ቡድኖች ወይም መንግስታት ማለት ይቻላል ተገዢ ወይም ተንበርካኪ ባይሆኑ እንኳን ኃላፊነታቸው በራሱ ስጋት ላይ ሊጥላቸው ይችላል፡፡ ከስጋትም አልፎ በጥቂት ነገር ሊሳሳቱ ይችላሉ ፡፡ ከተሳሳቱ ደግሞ ተበላሸህ ነው ፡፡ አለቀ ፡፡ ዛሬ ኤሪያል ሻሮን፣ ሙባረክና ሌሎች መሪዋች ምን ያህል ኮማ ውስጥ እንወደቁ ማየት ይቻላል ፡፡ እና ህክምናው ውስጥ ያለውን ጦርነት በድል ከመወጣት አንፃር ተልዕኮው የተሳካ ነበር ማለት እችላለሁ ፡፡

በሶስተኛ ደረጃ መቀመጥ ያለበት የተሞክሮ ቅመራ ወይም የቴክኖሎጂ ሽግግር ሂደት ነው ፡፡ የታከምኩበት ሀገር የምታራምደው ርዕዮት ምንም ይሁን ምን በህክምና ዘርፍ የደረሰችበት ደረጃ ከፍተኛ ነው ፡፡ ይህን ቴክኖሎጂ ወደ ሀገራችን እንዲገባ በማድረግ ተሞክሮውን በማጥናትና በመቀመር ማስፋፋት ይኖርብናል ፡፡ ይህን በማድረጋችን ለህክምና የምናወጣውን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ ማዳን ይቻላል ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የያዝነውን ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ ተጨማሪ ምርኩዝ ይሆንልናል ፡፡

2. ጠ/ሚ/ር መለስ ቤተመንግስት ከገቡ በኃላ ከእንደገና በነገሮችና በሁኔታዋች ሊወጠሩ እንደሚችሉ ይገመታል ፡፡ የመጀመሪያ ተግባራቸው በየደረጃው መግለጫዋችን መስጠት ይሆናል ፡፡

ሀ . ለህዝብ ፤

አቶ መለስ ህዝቡ በሃሳብም ሆነ በጸሎት ላደረገላቸው ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋና ያቀርባሉ የሚለውን እንደ አርእስተ ዜና እንውሰደው ፡፡ ድርጅቱ መራራውን የትጥቅ ትግል ሲያደርግ ከጎን እንደነበር ፣ ሰላም ሰፍኖ የልማት ግንባታው ከቀጠለ በኃላም አለኝታነቱን እንዳረጋገጠ ወደፊትም የኩሩውንና የቀናኢውን ህዝብ ድጋፍ እንደማይለያቸው አስረግጠው መናገራቸውን ደግሞ ርዕሱን የሚያፍታታው ዝርዝር ሃሳብ ይሆናል ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጅምሮች አሉና፡፡ ቢያንስ የአባይ ግድብ ማለቅ አለበት ፡፡ ቢያንስ ህዝቡ በቀን ሶስት ግዜ መብላት አለበት ፡፡ ስለዚህ ህዝቡ መሪውን  አሳፍሮ እንደማያውቅ የታሪክን ሰበዝ በማውጣት ንግግራቸውን ሊያጠናክሩት ይችላሉ ፡፡ ይህ ደግሞ የኃላ ታሪክ / Background / መሆኑ ነው ፡፡ ማለትም የአጼ ዮሀንስ  ‹ ሀገርህ እናትህ፣ ዘውድህ፣ ሚስትህ…  › የሚለው ገዳይ ጥቅስ የተዘጉ ልቦች ዳር እንዲንኳኳ ይደረጋል ፡፡ በሌላ በኩል የአጼ ሚኒሊክ ‹ ጉልበት ያለህ በጉልበት ርዳኝ … › የምትለው ትሁት ስንኝ ይጨመርበታል ፡፡ በላዩ ላይ ወርቅ የመሳሰሉ አዳዲስ መፈክሮች ጣል ይደረግበታል ‹‹ ጸረ ህዝብም ሆኑ ጸረ ጤንነቶች ከመንገዳችን አያደናቅፉንም ! ››

ለ . ለፓርቲ አባላት ፤

ጠንካራ ሀሳቦችና ጉዳዮች የሚመዘዙት በዚህ ክፍለ ግዜ እንደሚሆን ይጠበቃል ፡፡ ስብሰባውን ፈታ ለማድረግ በ ‹‹ ሞት ›› ላይ አንድ ሁለት ቀልዶችን ወርወር ማድረግ ማን ይከለክላቸዋል ፡፡ አሁን የታየው ውጥረት ከኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት፣ ከህወኃት ክፍፍልና ከ97ቱ ምርጫ ቀጥሎ ሊቀመጥ የሚችል የፈተና ምዕራፍ በመሆኑ ትልቅ የጠቆረ ቦታ ይኖረዋል ፡፡ በመሆኑም በህወኃት ክፍፍል ግዜ የተባለውን ቁም ነገር በማስታወስ ‹‹ ሞት ለምሳ ሲያስበን ለቁርስ አድርገነዋል ›› ሊሉ ይችላሉ ፡፡ ካስፈለገ ደግሞ ከኢትዮ ኤርትራ ጦርነት የትዝታ ኮሮጆ ውስጥ የጄኔራል ሳሞራን ብሂል በማውጣት

 ‹‹ በሽታ አካልን ማገርጣትና ማሰቃየት ይችልበታል ፤
እኛ ደግሞ ሰንኮፉን በጽናት አስነቅለን ቆመን መሄድ እንችላለን ›› ቢሉ ወፈ ሰማይ ካድሬ እስከ ሻይ እረፍት አይስቅም ብሎ መከራከር አያዋጣም ፡፡ በርግጥ ሁሌም የሚጠራጠሩ አንዳንድ ሰዋች ከቀልዱ ጀርባ ምን ተደግሷል በሚል በመተርጎምና በመተንተን ቀኑን ሊያሳልፉት ይችላሉ ፡፡  ‹ በርግጥ ለምሳ ያሰቡ እነማን ናቸው ? …. ሰንኮፎቹስ ?  .. ›

አቶ መለስ በነካ እጃቸው ሰምና ወርቅ ያለው ምስጋና በማቅረብ የቤቱን ሙቀት ሊያግሉት ይችላሉ ፡፡ ‹‹ እዛ ድረስ መጥተው የጠየቁኝ የቁርጥ ቀን ወዳጆቼ አሉ ፡፡ ይህ ማለት ግን በስራ መብዛት ወይም የአውሮፕላን ወጪ በማጣት ያልመጡ ጓዶች ሁሉ እኔን አልጠየቁኝም ወይም ለእኔ አያስቡም ማለት አይደለም ! ››

‹ እዛ ድረስ ሄደው የጠየቁት በርግጥ አባካኝ ናቸው ወይስ የቁርጥ ቀን ልጆች ? አሁን ማን ይሙት የአውሮፕላን ወጪ የሚከብደው ኃላፊ የቱ ነው ? ጉድ ነው ይሄ ነገር ! … › ሌላ ምናባዊ ሀሳቦች ይፈለፈላሉ ፡፡ ይህን መሰል ፍም በራሱ ፓለቲካ ሰፈር ውስጥ መለኮስና እንዳይጠፋም በአባላቱ ምላስ እንዲርገበገብ ማድረግ ጠቃሚ ነው ፡፡ አስፈላጊ ከሆነ ተርከክ ያለው ፍም ላይ ‹ በቆሎ › ይጠበስበታል ፡፡ በቆሎ ከጠፋ እንኳን ሰብሰብ ብለው ወይ ተረት ወይ ትዝታን እያወሩ ይሞቁታል ፡፡

3 . የወ/ሮ አዜብ መስፍን ሹፌር ቤተመንግስት አካባቢ በተነሳው የስልጣን ሹክቻ በመስጋት በቱርክ አድርጎ ግሪክ መግባቱን አንዳንድ የመገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል ፡፡ ይህ ወሬ እውነት ከሆነ አቶ መለስ በቀጣይነት ለሚንደረደሩበት ርዕሰ ሀሳብ ጥሩ መረጃ ይሆናል ፡፡ ዜናው እውነት ካልሆነ ወደ ርዕሰ ጉዳዩ የሚያሰገባው መንገድ የተለየ መሆኑን ልብ ይሏል ፡፡ እናም አቶ መለስ የሾፌሩን ስም ጠርተው  ‹ ምን መሆኑ ነው ግን ? የኛ የስልጣን ሹክቻ የሚያሰጋው እሱ ባለስልጣን ነው እንዴ ? › የሚል ጥያቄ ወርወር ያደርጋሉ ፡፡ ወዲያው ደግሞ  ‹‹ የዚያች የጥንቸሏ ብጤ መሆኑ ነው ?!  ነብር ነው ዝሆን እየታደነ ይያዝ ሲባል እሷ እግሬ አውጪኝ ትላለች ፡፡ እንስሳትም ምን ሆነሽ ነው የምትፈረጥጪው ?  አዋጁ እንደሆነ አንቺን አይመለከትም ሲሏት ዝሆን አለመሆኔ እስኪረጋገጥ ለምን ፍዳዬን አያለሁ ነበር ያለችው ! ›› በማለት ላነሱት ጥያቄ ማብራሪያ ይሰጣሉ ፡፡ አቶ መለስ ፊታቸውን ከስከስ አድርገው ይቀጥላሉ ፡፡

‹‹ በርግጥ ሰው ወጣ ሲል የሰው በር ለማንኳኳት የቋመጡ ሰዋች እንደነበሩ ተሰምቷል ፡፡ የዉጪዋቹስ መቼም ግርግር ለሌባ ይመቻል ! የሚባለውን ብሂል አሁን ነው መጠቀም ያለብን ለማለት ነው ፡፡ በጣም የሚገርመው የቤታችን ጉድ ነው ! አንዳንዱ የተሰጠውን ስራ አድምቶ ሳይሰራ ነው ወደ ላይ መንጠልጠል የፈለገው ፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ተገፍቶና ባዶ ተስፋ ተሸክሞ ነው ››

ከዚህ በኃላ የደፈረሰው ይጠራ ዘንድ፣ ለአቅመ ጠላ ያልደረሰው መጠጥ መቼ፣ እንዴትና በነማን እንደተጠነሰሰ ይታወቅ ዘንድ ተከታታይ ሂስና ግለሂሶች ይካሄዳሉ ፡፡ በመሃሉ የሚፈረጥጡ ጥንቸሎችም አይጠፉም ፡፡ ነገሩ ሀገሪቱ ውስጥ እንደሚወራው ጠንካራ ከሆነ ድርጅቱ ለፓለቲካ ጸበል ሁለት -  ሰባት  ‹ ሸንኮራ › መውረዱ አይቀርም ፡፡

እንግዲህ ይህ ሲያልቅ ነው አዳዲስ ነገሮች የሚፈልቁት ፡፡  በመጀመሪያ መግለጫው ፤

. ‹ ከናፋቂነት ተፈወስን ! › የሚል ሀሳብ ላይ ይሽከረከር ይሆናል ፡፡ ከዚህ በፊት ጠባቂነት፣ ተሃድሶ፣ መበስበስ ወዘተ የሚሉ ምጡቅ መግለጫዋች ስለነበሩ እንዳይደገሙ ጥንቃቄ ስለሚደረግ ማለት ነው ፡፡

. ውስጥ ለውስጥም ሆነ ይፋ በሆነ መግለጫ ሹም ሽሮች ሊከናወኑ ይችላሉ ፡፡ በሹም ሽሩ ከዚህ ቀደም በአቅም ማነስና በእጅ አመል ቀንዳቸውን የተመቱ ሁሉ አሁን የኤሊን ገጸ ባህሪ ወክለው ይጫወታሉ ፡፡

. የከፋ ነገር የተገኘባቸው / ለአብዮቱ ያልተመቹ / ደግሞ ፈጽሞ አልመው ወደማያውቁት የቃሊቲ ዓለም ይወረወራሉ ፡፡ ጎበዝ ከሆኑ ‹ ህይወት ከቪላ  በኃላ › ወይም  ‹ የአብዮታችን  ያልተገረዘ መጋዝ › በሚል አንድ አስደናቂ መጽሀፍ ሊደርሱ ይችላሉ ፡፡

4 . ከምስጋና ፣ መወቃቀስና ሹም ሽር በኃላ አዳዲስ ቃላቶችና አባባሎች የሚፈጠሩ ይመስለኛል ፡፡ እነ ተንበርካኪነት፣ 
ተስፋፊነት፣ ጠባቂነት፣ ተቸካይነት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ የልማት ሰራዊት እና የመሳሰሉት ተመሳሳያቸውን ወይም ተቃራኒያቸውን የሚያፈሩበት ሁኔታ ይኖራል ፡፡ ከዛም እንደ አካሄድ … እንደ አሰራር… ስብሰባ እንደ ስብሰባ … እያሉ ሃሎ ሃሎ መንፋት ነው ፡፡ በአነጋገር አንድ ዓይነት ልብስ የለበሰ  …

እስኪ  ያወራሁትን ምን ያህል እንደማውቀው ለማረጋገጥ የሆነ መልመጃ ልሞክር ፡፡ < ከላይ በተገለጹት ቃላቶችና የአሰራር ይትበሃሎች ቢያንስ ሁለት ቃላቶችን መስርት ? >

. በቃላት ራስን መቻል !
. የቃላት ሰራዊት ማፍራት !