Friday, August 10, 2012

‎የጀግና መንገድ‎



ኒክ ከባለቤቱ ጋር


--- እጅም እግርም የለውም ፤ ግን የዓለማችን ደስተኛ ሰው ነው ፡፡
--- እጅና እግር አለን ፤ ግን የዓለማችን ሀዘንተኛ ህዝቦች ነን ፡፡
--- < life is greater purpose > በሚል ርዕስ መጽሀፍ አሳትሟል ፡፡
--- < life is knife ! > የሚል ሰፊ ሀሳብ ውስጣችን ቢከማችም ‹ ሆድ ይፍጀው ›  ብለን ለህትመት አላበቃነውም ፡፡

ተቃርኗችን ቢዘረዘር ሰፊ ነው ፡፡ በርግጥ እሱ በአንድ ወቅት እጅግ ተከፍቶና ተስፋ ቆርጦ ራሱን ለማጥፋት ሙከራ አድርጓል ፡፡ ጥያቄውና ጸሎቱ አንድ ነበር ፡፡ ‹ እጅና እግር ስጠኝ › የሚል ፡፡ ሰሚ ባለማግኝቱ በጣም ተከፋ ፡፡ እናም በዚህ የሚደርስበትን ሙከራ መቋቋምና መታገስ ባለመቻሉ ድርጊቱን ፈጸመ ፡፡

ለኛ ተስፋ መቁረጥና መከፋት ብርቅ አይደለም ፡፡ አንዱ ጥያቄ ሳያድግ በላዩ ላይ ሌላ ጥያቄ ስለሚረገዝ የጥያቄዋቻችን ብዛት እንደ ህዝብ ብዛታችን አስጊ ደረጃ ላይ የደረሱ ናቸው ፡፡ ጥያቄዋቻችን ብዙ ህጻናት እንደሚያሳድጉ ቤተሰቦች አእምሯችን ውስጥ ያለ ስርዓት ይንጫጫሉ ፡፡ አእምሯችን ሰላም፣ ፍቅር፣ ፍትህ፣ ነጻነት፣ እንጀራ ወዘተ እያለ ዘወትር ይጠይቃል ፡፡ ከጥያቄዋቻችን መላመድ የተነሳ ነው መሰለኝ ጥያቄዋቹን እንደ ቤት ቁጥር ወይም ታርጋ ከማንነታችን ጋር ለጥፈናቸዋል ፡፡ እንጀራ የሚል ስም አልሰማሁም እንጂ ሰላም ፣ ፍቅር፣ ፍትህና ነጻነት የተባሉ ሰዋች በሺዋች የሚቆጠሩ ናቸው ፡፡ እንዴት ሊሆን ቻለ ? በተጨባጭ ያጣናቸውን ጉዳዮች በምኞት ወይም በመምሰል ለማካካስ ይሆን ? ላይሆንም ይችላል ፡፡

ለማንኛውም ስማቸውን ሳይሆን ከጀርባ ያለውን ማንነት ጠይቀው ምላሽ ያላገኙ ሰዋች መከፋታቸው ይጠበቃል ፡፡ መታገስ ያልቻሉት ውድ ህይወታቸውን በበረኪና፣ በገመድ፣ በጥይትና በመሳሰሉት ለማጥፋት ፈትነውታል ፡፡ ብዙዋች የጥያቄዋቻቸውን ግልባጭ ጆሮ ላለው ለማድረስ ከኬንያ እስከ አሜሪካ ድረስ ተበትነዋል ፡፡ በርግጥ በስደት ህይወት በቂ ምላሽ ያገኙ የታደሉና የተቀደሱ መሆን አለባቸው ፡፡ እስራኤላዊያን ግብጽ ውስጥ ለአያሌ አመታት ኖረው በተፈቀደው ግዜ መመለሳቸውን ያስታውሷልና ፡፡ ጥያቄውን ለሚመለከተው ሁሉ ያላለው የኔ ቤጤ ደግሞ ይሐው በርካታ የእህህ … ክላሲካሎችን እየደረሰ ይገኛል ፡፡ ድምጽ ሳይሆን በቂ ድፍረት ያላቸው ቢያንስ የአይዶል ውድድር ላይ
        ‹‹ እህህ ጠዋት ማታ ዋውዬ
           እህህ ሌሊት ዋውዬ  …. ›› እያሉ ይገኛሉ ፡፡ ‹ ተመስገን › የተሰኘውን ልማዳዊ መዝሙር ጠዋትና ማታ በማቀንቀን የሚታወቁት ቡድኖች ደግሞ  ‹ እነ ፍቅርና ነጻነት › በተሰኙት ስሞች እየተጽናኑ ይመስላል ፡፡

ግን ከባድ ነው ፡፡

በጦርነት ታምሶ የቆየ ቀጠናን እንጂ በጥያቄ የተወጣጠረ አእምሮን በ ‹ ማረጋጋት › መስመር ማስያዝ ይከብዳል ፡፡ በርግጥ ብርቅዬውን ‹ ደስታ › አሁንም በስም መልክ ካልሆነ በተግባር እንዴት መገብየት ይቻላል ? ተስፋ መቁረጥን እንዴት ማከም ይቻላል ?

አዋ ከባድ ነው ፤ በመሆኑም የፈጣሪ ብቻ ሳይሆን የኒክ መንገድም ሳያስፈልገን አይቀርም ፡፡
ቢቻል በአካል ልንጨብጠው ካልሆነ መንፈሱን ልንሞቀው ሳይገባ አይቀርም ፡፡   

እሱ ነው እንደ አማዞን ደን የረዘመውንና የገዘፈውን ተስፋ መቁረጥ ከርክሞ የበረንዳ አበባ ያደረገው ፡፡ እሱ ነው በክፋትና በፌዝ ያበጡ ቦርጮችን አስተንፍሶ የቅርጽ ተወዳዳሪ ያደረጋቸው ፡፡ እሱ ነው የጨካኞችን የደነደነ ልብ ሞርዶ ከውስጣቸው ከርሰ ምድር የሩህሩህነትን እንባ ማፍለቅ እንደሚችሉ እያለቀሱ እንዲያረጋግጡ ያደረገው ፡፡

እሱ ማነው ?

ሙሉ ስሙ ኒኮላስ ጀምስ ቩጂክ ሲሆን ብዙዋቹ የሚጠሩት ኒክ እያሉ ነው ፡፡ ታፍሳስ 4 ቀን 1982 በአውስትራሊያ ሆስፒታል ውስጥ ሲወለድ እጆችና እግሮች እንደሌሉት ታወቀ ፡፡ ወላጆቹ ጤነኛ በመሆናቸው ይህን ክስተት መቀበል አልቻሉም ፡፡ እንዴት ይበላል ? እንዴት ይራመዳል ? እንዴት ይሮጣል ? እንዴት ይማራል ? እንዴት ይጫወታል ? እረ እንዴት ሆኖ እንዴት ይሆናል ?  እናትና አባት ጥያቄዋቹን እያነሱ ምላሽ ሲያጡ ይንሰቀሰቃሉ ፡፡ ሰማይ ምድር ተደፋባቸው ፡፡

ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከትልቅ ችግር ጋር መጋጨት ጀመሩ ፡፡ በአውስትራሊያ ህግ አካል ጉዳተኛ መደበኛው ት/ቤት ውስጥ ገብቶ መማር አይችልም  ፡፡ ቤተሰቦቹ ሳያቋርጡ ‹ የመብት ያለህ ! › እያሉ በመጮሃቸው ግን ህጉ ሊሻሻል ቻለ ፡፡ ኒክም የመጀመሪያው አካል ጉዳተኛ ተማሪ ሆኖ ተመዘገበ ፡፡ እንደ ልጆቹ ወንበር ላይ ሳይሆን ከፍ ያለ ጠረጼዛ ላይ ቁጭ ብሎ ልጥፍ ግራ እግሩ ላይ ባሉት ጣቶች እየታገዘ መጻፍ ለመደ ፡፡

ትንሽ ከፍ እያለ ሲመጣ ግን ከውጪውና ከውስጡ የሚደርስቡትን ጥያቄዋችና ተጽዕኖዋች መቋቋም አልቻለም ፡፡ እኔ እንዴት ከሌሎቹ ልጆች በተለየ መልኩ ተፈጠርኩ ? ለምን የሰዋች መጠቋቋሚያና መሳለቂያ ሆንኩ ? ማለት ጀመረ ፡፡ በብቸኝነትና በመገለል ቆሰለ ፡፡ ስምንት ዓመት ሲሞላው ራሱን ስለማጥፋት ማንሰላሰል የጀመረበት ግዜ ነበር ፡፡ ቢቸግረው በልጅነት ልቡ ‹‹ አምላኬ ለኔም እጅና እግር ስጠኝ ?  ›› በማለት ዘወትር በማልቀስ ይለምን ጀመር ፡፡ ሰሚ አልነበረውም ፡፡ አስር አመት ሲሞላው ራሱን ውሃ ውስጥ አስምጦ  ለመግደል ሙከራ አደረገ ፡፡ ይሁንና በቤተሰቦቹ ጥረት ከሸፈ ፡፡ በአንድ ወቅት እናቱ አንድ አካል ጉዳተኛ እንዴት ህይወቱን እየመራ እንደሚገኝ የሚተርክ ጋዜጣ በማሳየት ታሪኩን አነበበችለት ፡፡ ይህ ታሪክ በዓለም ላይ ያለው አካለ ጉዳተኛ እሱ ብቻ አለመሆኑን አስገነዘበው ፡፡ ቀስ በቀስም እጅና እግር ያላቸው ልጆች የሚያደርጉትን ነገሮች በሙሉ ያለማንም አጋዥነት ማከናወን እንዳለበት በማመን ልምምዶችንና ጥረቶችን ቀጠለ ፡፡

ውጤቱ አስገራሚ ሆነ ፡፡ ጥርሶቹን ማጽዳት፣ ጸጉሮቹን ማበጠር፣ በኮምፒውተር መጻፍ ፣ መዋኘት ፣ ቴኒስ መጫወት፣ ሰልክ ማናገርና ሌሎችንም ያለ እጆችና እግሮች ማከናወን ቻለ ፡፡ ይህም እንደ ተረገመ ፍጥረት ሲመለከቱት የነበሩ ተማሪዋች አሁን እንደ መልዓክ እንዲመለከቱት አስቻለው ፡፡

 
ኒክ በአካውንቲንግና በፋይናንሻል ፕላኒንግ ሁለት ዲግሪዋችን ከያዘ በኃላ በ19 ዓመቱ የህይወቱን ውጣውረድ ለሌሎች የሚያካፍልበት የንግግር መድረኮችን ማዘጋጀት ጀመረ ፡፡ ለዚህ ይረዳው ዘንድም  life with out limbs  የተባለ አትራፊ ያልሆነ ድርጅት አቋቋመ ፡፡ ዛሬ በት/ቤቶች፣ በእምነት ተቋማት ፣ በድርጅቶች፣ በወላጅ አልባ ህጻናት ማሳደጊያዋች፣ በእስር ቤቶች፣ በሆስፒታሎችና በስታዲየሞች እየተገኘ ህይወቱንና ልምዱን በመሳጭ የንግግር ችሎታው ያካፍላል ፡፡ በአፍሪካ፣ ኤሽያ፣ ሰሜን አሜሪካ በሚገኙ ሃያ ሀገራት እየተዟዟረ አስተምሯል ፡፡

ኒክ የህይወትን ቀፋፊ ጎኖች በማሸነፍ የላቁ ሜዳሊያዋችን በየግዜው አጥልቋል ፡፡ በ2005 የአውስትራሊያን የዓመቱ ወጣቶች ሽልማት ያገኘ ሲሆን የራሱን ህይወትና እንቅስቃሴ የሚያሳይ የዲቪዲ ፊልም life is greater purpose በሚል ርዕስ ሰርቶ አሰራጭቷል ፡፡ በ2009   < No arms , No legs , No worries > የሚል መጽሀፍ ከማሳተሙ በተጨማሪ < The Butterfly Circus > በሚል ርዕስ በሰራው ፊልም በአጭር ፊልም የምርጥ አክተር ሽልማት ተቀብሎበታል ፡፡ < Some thing more > የሚል ሙዚቃም  ለቋል ፡፡ የካቲት 12 ቀን 2012 ካኔ ሚያራን የተባለች ቆንጆ አግብቶ ህይወቱን በመምራት ላይ ይገኛል ፡፡

‹‹  ፈጣሪን እጅና እግር በተዓምር ስጠኝ እያልኩ እንደዛ ስለምነው ቢሰጠኝ ኖሮ እንደማንኛውም ሰው የተለመደ ህይወት ነበር የምኖረው ፡፡  በወቅቱ ተዓምር ላገኝ አልቻልኩም ፤ አሁን ስረዳው ግን ለካስ ራሴ ተዓምር ነበርኩ ››  በማለት አድማጮቹን በሳቅ ያፈርሳል ፡፡

እንግዲህ የሰው ፍቅርን፣ ፍትህን፣ የህሊና ነጻነትና ሰላምን ሲመኝ የነበረው ኒክ ማለት ይህ ነው ፡፡
ሰው በስድቡ፣ ንቀቱና ማግለሉ ‹ ንክ › ይሆናል ብሎ ሲጠብቀው ‹ ልባቸው እንዲነካ › ያደረገው ኒክ ይህ ነው ፡፡
ያጣውን ሰላም ፣ ፍቅርና ነጻነት በራሱ የጀግና መንገድ የፈታው ኒክ ይህ ነው ፡፡
እንግዲህ ፍቅር፣ ሰላም፣ ነጻነት፣ ፍትህና እንጀራ የምንለምነው ‹‹ እኛም ›› ይኀው አለን ፡፡

ተቆጥረው የማያልቁት ችግሮቻችን እንደ ኩይሳ አድገው ጫፉ ላይ የታሰረው ሰንደቅ ከኩራት ይልቅ ተስፋ መቁረጥን እያውለበለበ ነው ፡፡ ይህ የኩይሳ ምሶሶ እየደነደነ ይሄድ ወይስ ይገርሰስ ? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ የመኖር ወይም ያለመኖር ምርጫ መሆኑ አያከራከርም ፡፡ እንዴት ?  ለሚለው ጥያቄ ነው እንግዲህ የጀግና መንገድ ያስፈልገናል የሚባለው ፡፡




No comments:

Post a Comment