Friday, February 28, 2014

የባለገሩ ስነቃልና የ « አቶ አለምነው ቤት »


ንደማንኛውም መጽሀፍ በትኩረት ላንብበው ብዬ አይደለም የገለጽኩት ። < እስኪ ትንሽ በአነጋገራችን ልዝናና > በማለት እንጂ ። ድንገት ከመሃሉ ገለጥ ሳደርገው < ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል > ከሚለው ንባብ ጋር ግጥምጥም አልኩ ። < ጎሽ ይዞልሃል > አልኩት በፈገግታ - የምሳሌያዊ አነጋገር መጽሀፉን ።
እናም ከ ሀ እስከ ታች የተዘረዘሩትን አነጋገሮች እንደ ፎቶ አልበም እያገላበጥኩ መጫወት ቀጠልኩ ። የገረሙኝን መቼ ይሆን የተነሱት ይቅርታ መቼ ይሆን የተነገሩት ፣ በየትኛው አካባቢ በማለት caption ብጤ እፈላልግ ነበር ። አንዳንዶቹ ሳይታዘዙ የሰው ብብትን ኮርኩረው በግድ ሳቅ መፍጠር የሚችሉ ናቸው ። ለምሳሌ ያህል ፣
< ለሰበበኛ ቂጥ መረቅ አታብዛበት ! >
< ቢያንጋልሏት ጡት የላት ፣ ቢደፏት ቂጥ የላት ! >
< ምንም ብትሞቺ ፣ እንዴት አደርሽ አንቺ ?! >
< እግዜር ሲቆጣ በዝናብ አር ያመጣ >
< ተደብቃ ትጸንሳለች ፣ ሰው ሰብስባ ትወልዳለች ! >
< አባቴ ትንሽ ነው ፣ ብልቴ ትልቅ ነው የሚል የለም ! >
< ልጅ አባቱን ገደለ ቢለው እረ የኔ ልጅ እንዳይሰማ አለው >
የሚሉት ጋ ስደርስ ከትከት ብያለሁ ።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ አንዳንዶቹ አባባሎች ጥያቄ የሚያስነሱ ... እንደ መጽሀፍ ቅዱስ ቃል አስረጅ የሚፈልጉ ወይም ደግሞ ሃይለኛ ማስተካከያ የሚፈልጉ ሆነው ነው ያገኘኃቸው ።
ለአብነት ያህል < ነገሩ ነው እንጂ ጩቤ ሰው አይጎዳም ! > የሚለው አባባል ድሮ ጩቤ ከጎማ ወይም ከቆዳ የሚሰራ መሆኑን ነው የሚያመለክተው ። ካልሆነ ታዲያ በአሁኑ ግዜ እንቅፋት ፣ የበዛ ሀሳብ ፣ ድንጋጤና ትንታ እንኴን ሰው ለመግደል ፍቃድ አውጥተው እንዴት ሆኖ የሾለ ብረት ሰው ለመግደል የሚያንሰው ?
< ማን ይሙት ጠላት ፣ ማን ይኑር አባት ! >
የሚለው ስነቃል የተደረሰው የእንጀራ እናት ባሳደገችው ባላገር እንደሆነ ግምት አለኝ ። አሊያማ ከአባት በላቀ መልኩ እናቱንና ሀገሩን « እምዬ » የሚለው ኢትዮጽያዊ ተቆጥረው የማያልቁ የእናት ክብር መግለጫ ግጥሞችን እንደ ዝናር ታጥቆ አይደለም እንዴ የሚዞረው ? ድንገትም
< እናቱን ለናቀ ክብሯን ላዋረደው >
መሬት ትዙርበት ጸሃይ አትሙቀው » ብሎ ሊቆጣ እንደሚችል ሁሉ መች አጣችሁት ?
< ለሰው ሞት አነሰው ! >
የሚለው አባባልስ በምንድነው የተሰራው ? በዝሆን ሀሞት መሆን አለበት ። በዚህ ሀሞት እንጀራ ፈርፍረው በግድ ያጎረሱት አንድ ሰው ክፋትንና ጭካኔን ለመግለጽ  አክ - እንትፍ ያለው ሀረግ ይመስላል ። መቼም ሞት አነሰው የሚለን እድሜ ልክ በእስር ይበስብስ ለማለት አይደለም ። ምናልባት የሚረካው ከጀግናውና ሀገር ወዳዱ አጼ ቴዎድሮስ አንድ የጭካኔ ሰበዝ መዞ ሲተገብረው ሊሆን ይችላል ። አጼ ቴዎድሮስ በደግነትና ጭካኔ ተደባልቀው የተሰሩ ንጉስ ነበሩ ። ቁጣ የንዴታቸውን ጣሪያ በሚያግለው ግዜ የሚያቀዘቅዙት የሰው እጅና እግርን አስቆርጠው ነበር - ከዛ ቁራጭህን ይዘህ ሀገር ግባ ነው ። እግር እንደ ዛፍ የሚመለመልበት ዘመን ። ለነገሩ ይህ ዘመን አልፏል ። ዛሬም ግን ሰዎች በድንጋይ ተወግረው ይሞታሉ ፣ አንገታቸው በሻሞላ ይቀላል ፣ ሰውነታቸው ተቀብሮም ከብቶች በላያቸው ላይ ይነዳል ። እዛ ያሉት አጼ ልክም ነው ህግም ነው ይሉሃል - እኛ የምንለው ያዝልን መጀን ! ነው ።
 < ሙቅ ውሃና የሰው ገንዘብ አይጠቅምም  ! >
በመርህ ደረጃ ልክ ነው ። ዳሩ ግን ጂ+1 ውስጥ እየኖሩ ጂ+6 የሚያስገነቡት ፣ ሚሊየን በሚደፍር መኪና የሚንፈላሰሱት ፣ ለልደታቸው ወይ ዱባይ አሊያም አካፑልኮ ደርሰው የሚመጡት ፣ ይህ ካልተመቸ ከፓሪስ ኬክ የሚያሰጋግሩት ልማታዊ ሀብታሞች በኑሮ ሰረገላ ከአያት ተራራ እስከ እስከ ካራማራ የሚንፈላሰሱት ስፍር ቁጥር የሌለውን የሰው ገንዘብ በጥቂት ማግኔታዊ ላባቸው በመሰብሰብ አይደለም እንዴ ? መሰለኝ እንግዲህ !
< ልጅ ቢያስብ ምሳውን ፣ አዝማሪ ቢያስብ ጠላውን ! >
ይህች አባባል ገና ድሮ ጡረታ መውጣት ሲገባት ለሰዎች በተጨመረው የስራ ዘመን ፍዳዋን ትቆጥራለች ። ለማንኛውም የዛሬ ልጅ ከአባቱ የተረፈውን ሳይሆን ከአባቱ ጸሎት በፊት አስቀድሞ የሚጎርስ ፣ እንግዳ አክብሮ ጔዳ የሚሸሸግ ሳይሆን ልክ እንደ ርዕሰ ብሄር እንግዳውን በራሱ ክፍል ውስጥ ተቀብሎ የሚያነጋግር ፣ አንዲት ምሳውን ሳይሆን ለትምህርት ቤት ከሰኞ እስከ አርብ በሁለት ሳህን ስለሚያስቌጥራቸው የምግብ አይነቶች ከፈለገ ከአረብ ቻናል ፣ እንዳማራጭም ኢቢኤስን ቁጭ ብሎ በመቃኘት  መርሃ ግብር የሚነድፍ ነው ። ስለፍቅር ፣ ስለኑሮ ውድነት ፣ ነገር ስላሰከራቸው ጎረቤቶች ፣ ስለተሸራረፉ መብቶች ፣ ስለቀበሌም ሆነ ገዢው ፓርቲ አያውቅም ብለው ፊቱ ካወራችሁ ተሳስታችኃል - ምክንያቱም በሌላ ቀን እርስዎን እንደ ዋቢ ምንጭ በመጥቀስ ለጔደኛው ወይም ለጥቁሩ እንግዳ ገለጻ ሲያደርግ ሊሰሙ ይችላሉና ።
ስለሴትነት ብዙ ተብሏል ። ጥቂቱን ብቻ እንምዘዝ ።
< ሴትና አህያ በዱላ ! >
የወረደ ነው ወይስ የተጋነነ ንጽጽር የሚባለው ?
 < ሴት የወደደ ገሃነም እሳት ወረደ ! >
የመላከ ጊዮርጊስ ?! እናቴን ? እህቴን ? ልጄን ? ሚስቴን ? ያለው ማን ነበር ?
< ሴት ካልወለደች ቌንጣ አትጠብስም ! >
በጉዴ መጣ አሉ እትዬ ዘነቡ - ባለስልጣኗን አይደለም
< ሴት በማጀት ወንድ በችሎት ! >
ወቸው ጉድ ?! ይህን የማህበራዊና ባህላዊ ልምድ ጣጣ ነው ብሎ ማለፍ እንዴት ይቻላል ? ጠንካራ ፖለቲካም ጭምር እንጂ ። ቆይ ግን የወ/ሮ ዘነቡ መ/ቤት በተለይም ሴቶችን በተመለከተው ርዕሰ ጉዳይ ምን እያሰበ ነው ? ለነገሩ እሳቸው ሰሞኑን የግበረ ሶዶማዊያን አጀንዳ ላይ ናቸው ። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ጻጻስ ፍራንሲስ ስለ ጌይ ምን ይላሉ ሲባሉ « እኔ ማነኝ እና ነው ይህን የምዳኘው ? » የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪሙን በበኩላቸው « ግብረ ሶዶማዊያን እንደ ሁለተኛ ዜጋ ብቻ ሳይሆን እንደ ወንጀለኛም እየተቆጠሩ ነው » በማለት ኡኡ ብለው ያውቃሉ  ። ፕሬዝዳንት ሮበርቱ ሙጋቤ በአንድ ወቅት “ ግብረሰዶማዊያን ከአሳማና ከውሾች የከፉ ናቸው » ማለታቸው አይዘነጋም  ። ሚኒስትር ዘነቡ ማን ከማን ያንሳል ብለው ምን ነበር አሉ የተባሉት ? መቼም ይሄ ሁሉ የስነቃል የቤት ስራ እያለባቸው እዛ ውስጥ ከገቡ የጉድ ነው ።
< በሽተኛ ያድርቅህ መጋኛ  ! >
አሁን ነው መሸሽ ። በደጉ ዘመን በነገር ወይም በቦክስ ገጭቶት አሁን ብድሩን የሚመልስ ሰው ይሆን ? ነው ህመምተኛው ሲያቃስት ከእንቅልፉ እየተቀሰቀሰ በቃሬዛ ጤና ኬላ ማመላለስ የሰለቸው አባወራ ? ለነገሩ የአቶ ቦጋለ መብራቱ እና የወ/ሮ ውድነሽ በጣሙ ዘመድም ሊሆን ይችላል ። አቶ ቦጋለ ወጥሮ የያዛቸው የተስቦ በሽታ ለሌላውም እንዳይተርፍ ለመጋኛ ስለት የሚያቀርብ ምስኪን ገበሬ ። ወይ አጨካከን ?! በሽተኛን ፈጣሪ ይዳብስህ በማለት ያጽናኑታል እንጂ እንዴት ይለጥፉበታል ። ግድየለም እንዲህ የሚናገሩት የሰው ልጆች ሳይሆኑ የሰው ገዢዎች መሆን አለባቸው ።
እነዚህን የመሳሰሉ አነጋጋሪ ፣ ተሻሻይ ወይም ተሰራዥ አባባሎች ጥቂት አለመሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል ። ለዚህ ለዚህ የቀድሞው ባህል ሚኒስቴር ከተፎ ስራ ይሰራ ነበር ። የአሁኖቹ እንኴ በፍላጎትና በሞያ ሳይሆን በሹመትና ሽረት ብሎም በአንሚ ደረጃ የተወከሉ ናቸው ስለሚባል  ደረትን ለመንፋት የሚያስችል መሰረት መኖሩ ያጠራጥራል ። ለማንኛውም ግልባጩ ይድረሳቸው ።
ትልቁ እውነት ግን አብዛኛው አባባል ወይም ስነቃል ዘመን ተሻጋሪ መሆኑ ነው ። በነዚህ በርካታ ስነቃል ውስጥ ያልተዳሰሰ ማህበራዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ ፣ ሃይማኖታዊ ፣ ባህላዊ ጉዳዮች አለ ለማለት ያስቸግራል ። ከማጣት እስከ ማግኘት ፣ ከስንፍና እስከ እውቀት ፣ ከጅልነት እስከ ብልሃት ፣ ከፍቅር እስከ ጥላቻ ፣ ከጉንዳን እስከ ዝሆን ፣ ከሸፍጥ እስከ ታማኝነት ፣ ከክብር እስከ ውርደት ፣ ከረሃብ እስከ ጥጋብ ፣ ከልጅ እስከ አባት ፣ ከልደት እስከ ሞት ፣ ከዲያቢሎስ እስከ ክርስቶስ ፣ ከሴት እስከ አማት ፣ ከሹመት እስከ ሽረት ፣ ከፍርሃት እስከ ጀግንነት ፣ ከነጻነት እስከ አምባገነንነት .... ምናለፋችሁ ጥላሁን ገሰሰ ያልዘፈነበት ባላገሩ ያልተቃኘበት ፍልስፍና የለም ብሎ እውቅና መስጠት እንደማጋነን የሚያስቆጥር አይመስለኝም ። እያንዳንዱን ርዕሰ ጉዳይ የሚመለከቱትን ስንኞች እዚህ ገጽ ላይ ፈሰስ ባደርጋቸው እደሰት ነበር ። ብዛታቸው ግን አስፈራኝ ። ማንን መርጦስ ማንን መተው ይቻላል ።
እውነት ይህን ሁሉ የደረሰው ብዙዎቻችን ቀለም አልዘለቀውም የምንለው ባላገር ከሆነ የ < ቀለም >ጉዳይ ማጠያየቁ አይቀርም ። እውነት ይህን ሁሉ ነባራዊ እውነት በቃላት ሸብልሎ ያጎረሰን ባላገር ከሆነ < ባገረስኩ ተነከስኩ > ቢል አይፈረድበትም ።
ማነው ነካሽ ?
አሁን በቅርቡ የሚያስተዳድሩትን ባላገር ያበሻቀጡትና ያዋረዱት የአማራው ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አለምነው እውነት ባላገሩን ያውቁታል ?  ካወቁትስ እንዴት ነው የመዘኑት ? ለማለት ስለምንገደድ ነው ። ለምሳሌ ያህል ሹሙ የእውቀትና የልምድ ሀብት የሚለካው ጫማ በማድረግና ባለማድረግ ነው ብለው የተነሱ አስመስሎባቸዋል ። ከዛው ክልል የተገኙት አጼ ቴዎድሮስ ሀብት ሳያንሳቸው ጫማና ኮፍያ ማድረግ አይወዱም ነበር ። ጀግንነትና የሀገር ፍቅር ከባዶ እግር ጋር አይያያዝም ። አበበ ቢቂላ በሮም የኦሎምፒክ ውድድር ያሸነፈው 11 ቁጥር ማሊያና ቁምጣ አድርጎ እንጂ ጫማ ተጫምቶ አልነበረም ። ማራቶን ከጽናትና ጥበብ ጋር እንጂ ከባዶ እግር ጋር ግንኙነት እንደሌለው ሌላ ማሳያ ሊሆን ይችላል ። ርግጥ መንገዱ በማይመችበት ቦታ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችልም ግምት ውስጥ በማስገባት ።
እናም  < ባላገሩ ባዶ እግሩን እየሄደ የሚናገረው ግን መርዝ ነው  > ማለት አንድም ጭንቅላታቸው ውስጥ የሚውለበለብ የንቀት ባንዲራ መኖሩን በሌላ በኩል ደግሞ ያላዋቂነት መነሻ ይሆናል ። ይኀው መነሻ መድረሻ ይኖረው ዘንድ ደግሞ  < ትምህክተኛ ነው ፣ ለሃጫም ነው > እያሉ ልጥፉን ማወፈር በርግጥም ባዶ እግርን ሳይሆን የጎደለ ወይም በዘይት እጦት የሚንጣጣ ጭንቅላትን ወገግ አድርጎ የሚያሳይ ነው ።
በሀገራችን ታሪክ ትላልቅ ስራ የሰሩ በርካታ የሀገራችን ጀግኖች እንደተግባራቸው ስማቸው በክብር እንዲታወስ ተደርጔል ማለት አይቻልም ። ይሁን እንጂ የታደሉት ደግሞ ስንት የጀግንነት ተግባር ፈጽመው በስማቸው እውቅና አግኝተዋል ። ለምሳሌ ያህል አትሌት ኃይሌ  « ሃይሌ ገብረስላሴ ጎዳና »ን በስሙ ማግኘቱ ያንስበታል ።  አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ሆስፒታል አይደለም  ሰሞኑን ለደነገጠው አየር መንገድ ማስታወቂያ ብትሆን መሳ ለመሳ ናት ። ያም ማርሽ ይቀይራል - እሷም ዙሩ ሲሳሳ አዲስ አቦሸማኔ  ትሆናለች ። ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የራሱን የአገጣጠም ስልት በመፍጠሩ « የጸጋዬ ቤት » የተባለ ስያሜ ተበርክቶለታል ። በዚሁ መሰረት በባዶ ጭንቅላት የሚመረቱ መረን የወጡ ስድቦችን « የአቶ አለምነው ቤት » ብሎ መጥራት  ተገቢ ይሆናል ።
ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው እንዲል ባላገሩ ።

Tuesday, February 11, 2014

የኢህአዴግ « እብዶች »






ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ
አክቲቪስት የኔ ሰው ገብሬ
ጋዜጠኛ አበበ ገላው


ፊልድ ማርሻል  ኦማር ሀሰን አልበሽር በታሪከኛው ባድመ የተቃቃሩትን ሁለት ሀገሮች ለማስታረቅ ደፋ ቀና እያሉ ነው ። በቅርቡም ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝንና ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ካርቱም ጠርቼ እንዲነጋገሩ አደርጋለሁ ማለታቸው ተሰምቷል ።
ይህን ዜና ሳነብ ትዝ ያለኝ በጦርነቱ ዋዜማና ማግስት በኢህአዴጎች የተጻፈው የቃል መጽሀፍ ነብር ። ርዕሱ « ትዕቢተ ኢሳያስ » የሚል ሲሆን ዋናው ገጸባህሪ ከጥንቱ ኢያጎ ፣ ከዘመናዊው አሰናቀ / በኢቴቪ በመታየት ላይ ያለው የሰው ለሰው ድራማ ተዋናይ /
 በላቀ መልኩ እኩይነትን አሽሞንሙኖ ያሳየ ነበር ። ኢህአዴግ ጨካኝ ቢሆንም በፖለቲካው ሂሳብ አልተዋጣለትም ነው የሚለው ። በደራሲው አስገዳጅነት ማፊያ ፣ ወሮበላ፣ ጋጠወጥ፣ አምባገነን እና እብድ የተሰኙ ባህሪያትን በተናጠልም ሆነ በጋራ እንዲሸከማቸው ተደርጔል ።
በተለይ « እብዱ » የተሰኘው ስያሜ ፈገግ ማድረጉ ግድ ነበር ። ደግሞ በእብድና በአህያ ፈስ ይሳቃል እንዴ ? ካላችሁ « እብድና ብርድ ያስቃል በግድ » የሚባል ስነቃል እንዳለን ማስታወስ ግድ ይሆንብኛል ።
ዞሮ ዞሮ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ የኢህአዴግ አንደኛው እብድ ነበሩ ። አቶ ሃይለማርያም በነገሱ በሶስተኛው ወራቸው በአልጀዚራ የቴሌቪዠን አድራሻ ከኢሳያስ አፈወርቂ ጋር የእንነጋገር ጥያቄ አቅርበው « አይቻልም » የተባሉትም « እብድ » ስለሆኑ ይሆናል ። ምክንያቱም « እብድና ዘመናይ የልቡን ይናገራል »
እነሆ ዛሬ ግን ከ « እብድ » ጋር ቁጭ ብሎ መወያየት ግድ ብሏል ። « እብድ ከወፈፍተኛ ቤት ያድራል » ይልሃል ነገረኛው ስነቃል ። በድርጅቱ የቃል መጽሀፍ ውስጥ « እብድ ቢጨምት እስከ አኩለ ቀን ነው » የሚል ምዕራፍ ባይኖርም የኢህአዴግ ሰዎች እቺን ካርድ መዘዝ ከማድረግ አይቆጠቡም ።
ሁለተኛው እብድ ነፍሱን ይማረውና የኔ ሰው ገብሬ ነው ። እንደ አንዳንድ መገናኛ ብዙሃን ዘገባ የ 29 አመቱ መምህር በዳውሮ ዞን ጣርቻ ከተማ ራሱን አቃጥሎ መስዋዕት የሆነው የፍትህና የነጻነት ጥያቄ በማንሳት ነው ።
ህብረተሰቡና ባለስልጣናት በተሰበሰቡበት አዳራሽ ያለጥፋታቸው ብቻ ሳይሆን ያለፍርድ የታሰሩት ወጣቶች ጉዳይ እንዲታይ እንዲሁም እንዲፈቱ ጠይቌል ነው የሚባለው ። በቂ ምላሽ ያላገኘው ወጣት ራሱ ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ በብዙዎች ፊት ሲቃጠል ሶስት መሰረታዊ ጥያቄዎችን በጩኀት እያሰማ ነበር
ፍትህ
ነጻነት
ዴሞክራሲ
ቱኒዚያው መስዋዕት መሀመድ ቡአዚ ተግባር በየት መጣ ያለው ኢህአዴግ አሁን « ሳይቃጠል በቅጠል » የሚለው ጥቅስ ተመራጭ ሆኖ አገኘው ። የዳውሮ ዞንም ሆነ ሌላው ማህበረሰብ የኔ ሰውን « የኛ ሰው » ከማድረጉ በፊት ማንነቱን  እንዲያውቅ አደረገ ።
መንግስት በቴሌቪዥኑ  የኔ ሰው የአእምሮ ችግር ያለበት እንደነበር በእህቱና በአባቱ እንዲገለጽ አስደረገ  ። ምክንያቱም ስም ይወጣል ከቤት ይከተላል ጎረቤት ተፈጻሚ ይሆን ዘንድ ። በአናቱ ላይ ደግሞ « እብድ የያዘው መልክ አይበረክትም » ሲል ከንፈሩን እየመጠጠ አስተያየቱን በአየር ውስጥ ናኘው ።
እብድን ግን እንደ ሀገር ባህል ሰብሰብ ብላችሁ አትቅበሩ የሚል ህግም ሆነ ጥቅስ አለ እንዴ ? መስዋእቱ vs እብዱ የኔሰው በጥቂት ሹማምንቶች ብቻ ታጅቦ ነው አሉ የተቀበረው ። መቼም ሳይንስ እብደት የማይተላለፍ በሽታ መሆኑን ነው የሚመሰክረው ። ታዲያ ድርጅቱ ምን ነክቶት ነው የህብረተሰቡን የቀብር ባህል የተጋፋው ?  መቼም የሞተ ሰው አያስፈራም - የሟቹ እውነተኛ መንፈስ እንጂ ። 
« ስመሰክርልህ ስመሰክርልህ ዋልኩ ቢለው ስታዘብህ ስታዘብህ ዋልኩ አለ » ደገኛ
ሶስተኛው እብድ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ነው ። አቶ መለስ በካምፕ ዴቪድ በተጋበዙበት የጂ - 8 ስብሰባ ላይ ተሞክሯቸውን በማቅረብ እሞገሳለሁ ብለው እንጂ እሰደባለሁ ብለው እንዴት ይጠብቃሉ ? « Meles Zenawi is dictator .... Don’t talk about food without  freedom » የሚል ወፍራም ቁጠኛ ድምጽ የአዳራሹን አየር ቀየረው ።
አበበ ገላው የሙንታዳር አልዛይድ ጔደኛ ነበር እንዴ ያሰኛል ። ሙንታዳር ትዝ አላችሁ ? ፕሬዝዳንት ቡሽ ባግዳድ ውስጥ ፕሬስ ኮንፈረንስ ሲያካሂዱ ጫማውን ወርውሮ ያስደነገጣቸው የአረብ ጋዜጠኛ ። በርግጥ ሙንታዳር ጫማ በመወርወሩ የመጀመሪያ አልሆነም ። ይህን የመሰለ ድርጊት በህንድ፣ አየርላንድ ፣ አውስትራሊያ ፣ ታይዋን ፣ ሆንግ ኮንግና ፓኪስታን ተደርጔልና ። እንዲህ ያደረገ ኢትዮጽያዊ ጋዜጠኛ ባለመኖሩ ግን አበበ የመጀመሪያ ድርጊቱ ደግሞ አስገራሚና አነጋጋሪ ሊሆን በቅቷል ። ጥቂት ቆይቶም አቶ መለስ በመሞታቸው
« አበበ ገላው መለስን በላው » የሚል ግጥም ተደረሰ ። ኢህአዴግና ደጋፊዎቹ « አበበ ገላው የአእምሮ በሽታ ያለበት ንክ ሰው ነው » በማለት ጉዳዩን ተራ ለማድረግ የመልስ ምት ሰጥተዋል ።
« አበበ ገላው በነካ እጅህ እገሌ የተባለውን ሚኒስትር አስደንግጥልን » የሚለው የፌስ ቡክ ጥያቄ ቀላል አልነበረም ። ኢህአዴግ ግን ለመጀመሪያ ግዜ እብድን ንቆ ወይም ስቆ ለመተው ተቸገረ ። የኢህአዴግ ሰዎች « እንኴን ለገንፎ ለሙቅም አልደነግጥ » የሚል ጥቅስ መኖሩን ዘንግተው ይሆን ?
የጋዜጠኛውን መንገድ የሚከታተሉ ፣ ንግግሩን የሚቀርጹ ፣ ቆይ ጠብቅ አሳይሃለሁ ወይም እገድልሃለሁ የሚሉ ማስፈራሪያዎች ግን እንደ እድገታችን በሁለት አሃዝ እያደጉ ነው ።
ተንጋለው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ እንዲሉ አበው ።