Tuesday, February 11, 2014

የኢህአዴግ « እብዶች »






ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ
አክቲቪስት የኔ ሰው ገብሬ
ጋዜጠኛ አበበ ገላው


ፊልድ ማርሻል  ኦማር ሀሰን አልበሽር በታሪከኛው ባድመ የተቃቃሩትን ሁለት ሀገሮች ለማስታረቅ ደፋ ቀና እያሉ ነው ። በቅርቡም ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝንና ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ካርቱም ጠርቼ እንዲነጋገሩ አደርጋለሁ ማለታቸው ተሰምቷል ።
ይህን ዜና ሳነብ ትዝ ያለኝ በጦርነቱ ዋዜማና ማግስት በኢህአዴጎች የተጻፈው የቃል መጽሀፍ ነብር ። ርዕሱ « ትዕቢተ ኢሳያስ » የሚል ሲሆን ዋናው ገጸባህሪ ከጥንቱ ኢያጎ ፣ ከዘመናዊው አሰናቀ / በኢቴቪ በመታየት ላይ ያለው የሰው ለሰው ድራማ ተዋናይ /
 በላቀ መልኩ እኩይነትን አሽሞንሙኖ ያሳየ ነበር ። ኢህአዴግ ጨካኝ ቢሆንም በፖለቲካው ሂሳብ አልተዋጣለትም ነው የሚለው ። በደራሲው አስገዳጅነት ማፊያ ፣ ወሮበላ፣ ጋጠወጥ፣ አምባገነን እና እብድ የተሰኙ ባህሪያትን በተናጠልም ሆነ በጋራ እንዲሸከማቸው ተደርጔል ።
በተለይ « እብዱ » የተሰኘው ስያሜ ፈገግ ማድረጉ ግድ ነበር ። ደግሞ በእብድና በአህያ ፈስ ይሳቃል እንዴ ? ካላችሁ « እብድና ብርድ ያስቃል በግድ » የሚባል ስነቃል እንዳለን ማስታወስ ግድ ይሆንብኛል ።
ዞሮ ዞሮ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ የኢህአዴግ አንደኛው እብድ ነበሩ ። አቶ ሃይለማርያም በነገሱ በሶስተኛው ወራቸው በአልጀዚራ የቴሌቪዠን አድራሻ ከኢሳያስ አፈወርቂ ጋር የእንነጋገር ጥያቄ አቅርበው « አይቻልም » የተባሉትም « እብድ » ስለሆኑ ይሆናል ። ምክንያቱም « እብድና ዘመናይ የልቡን ይናገራል »
እነሆ ዛሬ ግን ከ « እብድ » ጋር ቁጭ ብሎ መወያየት ግድ ብሏል ። « እብድ ከወፈፍተኛ ቤት ያድራል » ይልሃል ነገረኛው ስነቃል ። በድርጅቱ የቃል መጽሀፍ ውስጥ « እብድ ቢጨምት እስከ አኩለ ቀን ነው » የሚል ምዕራፍ ባይኖርም የኢህአዴግ ሰዎች እቺን ካርድ መዘዝ ከማድረግ አይቆጠቡም ።
ሁለተኛው እብድ ነፍሱን ይማረውና የኔ ሰው ገብሬ ነው ። እንደ አንዳንድ መገናኛ ብዙሃን ዘገባ የ 29 አመቱ መምህር በዳውሮ ዞን ጣርቻ ከተማ ራሱን አቃጥሎ መስዋዕት የሆነው የፍትህና የነጻነት ጥያቄ በማንሳት ነው ።
ህብረተሰቡና ባለስልጣናት በተሰበሰቡበት አዳራሽ ያለጥፋታቸው ብቻ ሳይሆን ያለፍርድ የታሰሩት ወጣቶች ጉዳይ እንዲታይ እንዲሁም እንዲፈቱ ጠይቌል ነው የሚባለው ። በቂ ምላሽ ያላገኘው ወጣት ራሱ ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ በብዙዎች ፊት ሲቃጠል ሶስት መሰረታዊ ጥያቄዎችን በጩኀት እያሰማ ነበር
ፍትህ
ነጻነት
ዴሞክራሲ
ቱኒዚያው መስዋዕት መሀመድ ቡአዚ ተግባር በየት መጣ ያለው ኢህአዴግ አሁን « ሳይቃጠል በቅጠል » የሚለው ጥቅስ ተመራጭ ሆኖ አገኘው ። የዳውሮ ዞንም ሆነ ሌላው ማህበረሰብ የኔ ሰውን « የኛ ሰው » ከማድረጉ በፊት ማንነቱን  እንዲያውቅ አደረገ ።
መንግስት በቴሌቪዥኑ  የኔ ሰው የአእምሮ ችግር ያለበት እንደነበር በእህቱና በአባቱ እንዲገለጽ አስደረገ  ። ምክንያቱም ስም ይወጣል ከቤት ይከተላል ጎረቤት ተፈጻሚ ይሆን ዘንድ ። በአናቱ ላይ ደግሞ « እብድ የያዘው መልክ አይበረክትም » ሲል ከንፈሩን እየመጠጠ አስተያየቱን በአየር ውስጥ ናኘው ።
እብድን ግን እንደ ሀገር ባህል ሰብሰብ ብላችሁ አትቅበሩ የሚል ህግም ሆነ ጥቅስ አለ እንዴ ? መስዋእቱ vs እብዱ የኔሰው በጥቂት ሹማምንቶች ብቻ ታጅቦ ነው አሉ የተቀበረው ። መቼም ሳይንስ እብደት የማይተላለፍ በሽታ መሆኑን ነው የሚመሰክረው ። ታዲያ ድርጅቱ ምን ነክቶት ነው የህብረተሰቡን የቀብር ባህል የተጋፋው ?  መቼም የሞተ ሰው አያስፈራም - የሟቹ እውነተኛ መንፈስ እንጂ ። 
« ስመሰክርልህ ስመሰክርልህ ዋልኩ ቢለው ስታዘብህ ስታዘብህ ዋልኩ አለ » ደገኛ
ሶስተኛው እብድ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ነው ። አቶ መለስ በካምፕ ዴቪድ በተጋበዙበት የጂ - 8 ስብሰባ ላይ ተሞክሯቸውን በማቅረብ እሞገሳለሁ ብለው እንጂ እሰደባለሁ ብለው እንዴት ይጠብቃሉ ? « Meles Zenawi is dictator .... Don’t talk about food without  freedom » የሚል ወፍራም ቁጠኛ ድምጽ የአዳራሹን አየር ቀየረው ።
አበበ ገላው የሙንታዳር አልዛይድ ጔደኛ ነበር እንዴ ያሰኛል ። ሙንታዳር ትዝ አላችሁ ? ፕሬዝዳንት ቡሽ ባግዳድ ውስጥ ፕሬስ ኮንፈረንስ ሲያካሂዱ ጫማውን ወርውሮ ያስደነገጣቸው የአረብ ጋዜጠኛ ። በርግጥ ሙንታዳር ጫማ በመወርወሩ የመጀመሪያ አልሆነም ። ይህን የመሰለ ድርጊት በህንድ፣ አየርላንድ ፣ አውስትራሊያ ፣ ታይዋን ፣ ሆንግ ኮንግና ፓኪስታን ተደርጔልና ። እንዲህ ያደረገ ኢትዮጽያዊ ጋዜጠኛ ባለመኖሩ ግን አበበ የመጀመሪያ ድርጊቱ ደግሞ አስገራሚና አነጋጋሪ ሊሆን በቅቷል ። ጥቂት ቆይቶም አቶ መለስ በመሞታቸው
« አበበ ገላው መለስን በላው » የሚል ግጥም ተደረሰ ። ኢህአዴግና ደጋፊዎቹ « አበበ ገላው የአእምሮ በሽታ ያለበት ንክ ሰው ነው » በማለት ጉዳዩን ተራ ለማድረግ የመልስ ምት ሰጥተዋል ።
« አበበ ገላው በነካ እጅህ እገሌ የተባለውን ሚኒስትር አስደንግጥልን » የሚለው የፌስ ቡክ ጥያቄ ቀላል አልነበረም ። ኢህአዴግ ግን ለመጀመሪያ ግዜ እብድን ንቆ ወይም ስቆ ለመተው ተቸገረ ። የኢህአዴግ ሰዎች « እንኴን ለገንፎ ለሙቅም አልደነግጥ » የሚል ጥቅስ መኖሩን ዘንግተው ይሆን ?
የጋዜጠኛውን መንገድ የሚከታተሉ ፣ ንግግሩን የሚቀርጹ ፣ ቆይ ጠብቅ አሳይሃለሁ ወይም እገድልሃለሁ የሚሉ ማስፈራሪያዎች ግን እንደ እድገታችን በሁለት አሃዝ እያደጉ ነው ።
ተንጋለው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ እንዲሉ አበው ።

No comments:

Post a Comment