Sunday, June 7, 2020

የእንግሊዝ ሃውልቶች አዲስ ፈተና …




ኤድዋርድ ኮልስቶን የብሪስቶል ነዋሪዋች ኩራት ነበር ። ሲበዛ ቅን ነው ይሉታል - ተወላጆቹ ። ኋላ ላይ ከተማዋን እየተቀላቀሉ የመጡ ጥቁሮችና ሌሎች ግን የክፋት መጨረሻ እንደሆነ ነው የሚሰማቸው ። ከነጋዴ ቤተሰቦቹ በ 1636 ተወልዶ በ 1721 ዓም አረፈ ። እዚህ ከተማ ላይ ሃውልት የቆመለት በ 1895 ሲሆን መሰረታዊው ምክንያት በጎ አድራጊነቱ ነው ። በኖረበት ዘመን ለበጎ አድራጊ ድርጅቶች ከ 71 ሺህ ፓውንድ በላይ ለግሷል ። ለትምህርት ቤቶች ፣ ለእምነት ተቋማትና ለሆስፒታሎችም በመርዳት ስሙ ይጠቀሳል ። አንዳንዶች የገንዘብ ምንጩ ቱባ ነጋዴ በመሆኑ ነው ይበሉ እንጂ ብዙዋችን የሚያስማማው ጥቁሮችን በመሸጥ ያካበተው ነው ።

የዚህ ሃውልት ህጋዊነት ለበርካታ ግዜ የብርስቶል ከተማን ህዝብ አወያይቷል ፣ አጨቃጭቋል ። የሰውየው ሌጋሲ ለምሳሌነት አይበቃም በሚል የሃውልቱን መቆም የሚቃወሙት ሰሚ ሳያገኙ ቆይተዋል ። ዛሬ ከ 125 አመታት በኋላ ‹ ታላቁ › ኤድዋርድ ኮልስቶን አደባባይ ላይ በትዝብት እንደቆመ አልቀጠለም ። ዘረኝነትን በሚቃወሙ / Black Lives Matter / ሰልፈኞች እንደ በሬ በገመድ ተጠልፎ እንዲወድቅ ተደርጓል ። ከወደቀ በኋላ እንደ ሳዳም ሁሴን ሃውልት ተረግጧል ፣ ተተፍቶበታል ፣ ተረግሟል ። እንደ ጆርጅ ፍሎይድ ገዳይ አንገቱ ተረግጦ ‹ መተንፈስ አልቻልኩም › እንዲል ተጠብቋል ። በመጨረሻም ድሮ ባህር አቋርጠው አውሮፓና አሜሪካ የመጡ ጥቁሮችን ያስታውስ ዘንድ ይመስል ወደ ባህር ተጥሏል ።

ኤድዋርድ ኮልስቶን በ1689 ጥቁሮችን እያስመጣ በመሸጥ በሚታወቀው / Royal African Company / ድርጅት ውስጥ ምክትል ሃላፊ ነበር ። በዚህ ካምፓኒ ውስጥ እየሰራ 84 ሺህ 500 የሚደርሱ ጥቁሮችን በመርከብ አጓጉዟል ። ከዚህ ውስጥ 23 ከመቶ ወይም 19 ሺህ 300 ያህሉ ወደብ ሳይደርሱ መንገድ ላይ በውሃ እጥረት ፣ በተቅማጥና በንጽህና ጉደለት ሞተዋል ። ይህ ሰው ሌላም የሚታወቅበት ጉዳይ አለ ። በ 70ቹ እድሜው የፓርላማ አባልነቱን ተጠቅሞ የባሪያ ንግድ እንዲስፋፋ ፔቲሽን እስከ ማሰባሰብ ደርሷል ።

እንግሊዝ ለህብረተሰቡም ሆነ ለሀገር ጥሩ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ተብለው የሚታሰቡ / በክፉም ሆነ በደግ /  ስመጥር ዜጎችን ሃውልት በማቆም በቀጣዩ ትውልድ እንዲታወሱና እንዲዘከሩ የማድረግ የረጅም ግዜ ባህል አላት ። አንዳንድ መረጃዋች እንደሚጠቁሙት በመላው ሀገሪቱ ከ828 የሚበልጡ ሃውልቶች በተለያዩ ከተሞች ቆመዋል ። እስካሁንም አንዳቸውም ላይ በተቃውሞ መልኩ የመፍረስ አደጋ አላጋጠማቸውም ። ነገር ግን ከቅርብ ግዜ ወዲህ ያልተለመዱ ትችቶችን ያስተናገዱ ሃውልቶች ታይተዋል ። ሁለተኛ አለም ጦርነትን ለማስታወስ በተደረግ ዝግጅት ላይ አንዳንድ ሃውልቶች ላይ ACAB የሚል ጽሁፎች ተነበዋል - All Cops are Bastars የሚል ትርጉሙ እንደያዙ ተገምቷል ።በቅርቡ ለንደን ውስጥ በተደረገው ሰላማዊ ሰልፍም የቀድሞው የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትር ዊንስተን ቸርችል ሃውልት ላይ ዘረኛ ነበር የሚል ጽሁፍ ተለጥፎበት ነበር ።

በአንድ በኩል « የባሪያ ንግድ ውርስ ነው » በሌላ በኩል « አይደለም የበጎ አድራጎነት ምልክት ነው » እየተባለ ሲያጨቃጭቅ የኖረው ሃውልት መፍረሱ የእንግሊዝን መንግስት አስቆጥቷል ። የሆም ሴክሬቴሪ ሃላፊ ፕሪቲ ፓታል ድርጊቱን አሳፋሪ በማለት ተጠርጣሪዋቹን እንፋረዳለን ብለዋል ። በነገራችን ላይ ኤድዋርድ ኮልስቶን በብርስቶል ከተማ በስሙ የኮንሰርት አዳራሽ ፣ ጎዳና እና ትምህርት ቤት ተሰይመውለታል ። ትግሉ እነዚህም እንዲፈርሱ ይዋጋል ወይስ ባፈረሰው ሃውልት ተጠያቂ እስከመሆን ይደርሳል ? እየከረረ ከመጣው የእንግሊዝ ተቃውሞ አንጻር ይህን ጥያቄ በቀላሉ መመልስም ሆነ እንደዋዛ መተውም የሚቻል አይሆንም ።

No comments:

Post a Comment