Friday, June 19, 2020

የፍትህ መዶሻ ይዛ ፍትህ የምትጠይቅ ሀገር



ኢትዮጽያ አይኗን በጨው ካጠበችው  ግብፅና አይኗን በአግባቡ መታጠብ ካቃታት ሱዳን ጋር እሰጥ አገባ ከገባች አመታትን አስቆጠረች ። ድርድሩ የፓለቲካውና ዲፕሎማሲውን መንገድ ይከተል በሚል እንጂ በጉንጭ አልፋው ንግግር  ውጤት ይገኛል ተብሎ አይጠበቅም ።

ፈጣጣዋ ግብፅ የቅኝ ግዛቶችን ውል ከትከሻዋ ላይ ማውረድ አትፈልግም ። ከግፈኛዋ እንግሊዝ የተቀበለችውን የውሃ ድርሻ እንደ ጄነራል ክፍ አድርጎታል ። ይህን ማእረግ ወደ ሻምበልነት የሚያወርድ ተጋፊ ሃይልን አትቀበልም ። እናም በእሷ ቀመር የውሃው ባለቤትነት የሚመዘነው ከሚመነጭበት ቦታ ሳይሆን በተፈጥሮ ቀድሞ በያዘ ነው - ላለው ይጨመርለታል የሚባለውን የወንጌል ጥቅስ እንድናስታውስ በማድረግ ።

ሱዳን ከቅኝ ገዢዋ መሃንዲስ የሚበቃትን ያህል ድርሻ ተቀብላለች ። የአባይ ወንዝና የግድቡ ወሬ ሲነሳ የምታዳምጠው አይናር የማይጠፋውን አይኗን እየሞዥቀች ነው ። አይናሩ ሲለቃት ግድቡ ይጠቅመኛል ከኢትዮጽያ ጎን ነኝ ትላለች ። አይናሩ አንቆ ሲይዛት የግብጽ ማስፈራሪያ ነው ቀድሞ የሚሰማት ። ያኔ ግብፅን በአረብኛ ማናገር ትጀምራለች - አቋም እንዲኖራት አትፈልግም ።
እነዚህ ሀገሮች ከያዙት ሀገወጥ ጥቅምም ሆነ ከሚያስተሳስረቸው ፖለቲካዊ ውግንና አንጻር ወደ መሃል ተስበው የሚመጡ አይደሉም ። ወደታች ወርደው የእውነት ባልጩት ላይ ከቆሙ ድንጋዩ ያበቀለው አልጌ አዳልጦ እንደሚጥላቸው ይረዳሉ ። የሚደራደሩት አዲሱን እውነት ለመቀበልና የቆየውን ክብር ለማጣት አይደለም ።

ለዚያም ነው በተለይ ግብፅ ከድርድር ይልቅ አደራዳሪን ምርኩዝ ማድረግ የምትመርጠው ። ለቡራኬ ሰጪዎች ትልቅ ቦታ አላት ። ድሮ ለዚህ ያበቃቻት እንግሊዝ ዛሬ ባትጠቅማትም አሜሪካንን መተካት አላቃታትም ። ትላልቆቹ በስሟ እንዲያስፈራሩላትና የረባሽ ሀገራትን ጆሮ እንዲቆነጥጡላት ትፈልጋለች ። የያዘችው እውነት ለዛሬው አለም ባይሰራም አይኗን አፍጣ አለም መንግስታት ፊት ስሞታ ታቀርባለች ። ጩኸቷን እንዲጮሁላት አጥብቃ ነው የምትሰራው ። አልፋም ትሄዳለች - ሁሉንም አማራጮች እጠቀማለሁ የሚል ማስፈራሪያ በመልቀቅ ።

እንደሚታወቀው የውሃው መነሻም ሆነ የግድቡ መድረሻ ከኢትዮጽያ ነው ወይም ኢትዪጽያ ናት ። በውሃ የመጠቀም አለማቀፋዊ መብቷ ጥያቄ ውስጥ ባይገባም የምትደራደረው ግን በድርድር ተጎጂልን ከሚሏት ፈጣጣ ሀገራት ጋ ነው ። ድርድሩን አለም ይውቅልኝ ፣ ፍትሃዊነቱንም ይገንዘብልኝ የምትለው የሌሎችም አጋር መሆናን ለማሳየት ነው ። ሀገሬ ግን ነገ ጠባ እየከሰሷት ፣ አለፍ ሲልም እያስፈራሯት ፍትሃዊ አካሄዴ ይታወቅልኝ በሚል ባዘነች ።

እንደ እውነቱ ከሆነ ግድቡን ለመስራትም ሆነ ውሃውን ለመሙላት የማንንም ፍቃድ መጠየቅ አያስፈልግም ። መጠንቀቅ ያለብን ሌሎችን በጭፍን ጥላቻ ላለመጉዳታችን ብቻ  ነው ። ከዚያ ውጪ ወንዙም ግድቡም የኛ ነው ። በያዝነው ነገር ላይ መያዛችንን ከማይቀበል ቡድን ጋር ለምን ሃይላችንን እናጠፋለን ? ብለህ ብለህ አልቀበል ካለህ የያዝከውን አስተማማኝ የፍትህ መዶሻ በራስህ ጠረጼዛ ላይ መምታት ተገቢ ነው ። ከዚያ ለፍርድ አፈጻጸም ወደሚመለከተው አካል በየአድራሻው መላክ - ይኅው ነው ። ውሃውን መሙላት ስትጀምር ትላንት አልቀበል ያለህ ሁሉ ሰልፉን ካንተ ጋ ያሳምራል ፤ ቋንቋውንም ይለውጣል ። ዋ ! የሚልህን ረስቶ ‹ እባክህ › ማለት ይጀምራል ። አለም የምታሳየን እውነት ይሄንን ነው ። ከወሬው ቀንሰን ይህን ለማድረግ እንፍጠን ። ያኔ የመታኸው መዶሻ ጠብቆ መግባቱን ቢያንስ ቢያንስ ደግሞ ትክክል መሆኑን ትገነዘባለህ ።

በርግጥ ሌሎችን ተደግፎም ሆነ በራሱ የሚያስፈራራው ቡድን ምንም አያመጣም ብሎ መዘናጋት ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል ። ግልጽ ጦርነት ባይከፍትብህ እንኳ ሌሎችን በገንዝብ በመግዛት ጥቅምህን ለመናድ ሌት ተቀን ይሰራል ። ሱዳን እና የኛ ሀገር ባንዳዋችን በዋናነት እንደሚጠቀም መጠራጠር አይኖርብንም ። ግድቡ ድንበር ላይ እንዲሰራ መደረጉ ምናልባት የሚጎዳንም በዚህ መሰሉ አጣብቂኝ ግዜ ነው ። እናም በአንድ በኩል ግድቡን ለመጨረስ እየተጉ በሌላ በኩል ግድቡንና አካባቢውን በአስተማማኝ መከላከያ ማጠር ያስፈልጋል ። የሀገር ቤቶችን ባንዳዎች እግር በእግር ተከታትሎ ግባቸውን ለማጨናገፍ ፣ የጆሮ ጠቢውን መስሪያ ቤት ሚና ከመቼውም ግዜ በላቀ መልኩ ማሳደግ ተመራጭ ይሆናል ።

No comments:

Post a Comment