Saturday, July 15, 2017

የአማረ አረጋዊ ልዩ ዋንጫ


አቶ አማረ አረጋዊ የኢትዮጽያ ፕሬስ ባለውለታ መሆናቸውን በማገናዘብ ሰሞኑን የእውቅና ሽልማት አግኝተዋል ። አንዳንዶች አቶ አማረ ከኢትዮጽያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት ሽልማት ማግኘታቸውን አልወደዱትም ። ለምን ሲባሉ ሁለት ምክንያቶችን ያቀርባሉ ። የመጀመሪያው ምከር ቤቱ የማይገባውን ስራ በመስራቱ የሚል ነው ። የምክር ቤቱ ቀዳሚ ስራ የፕሬስ ነጻነት እንዲረጋግጥ ብሎም በስርጭት ወቅት ክህዝብ የሚቀርብ አቤቱታ ካጋጠመ እንዲታረም ማድረግ ነው  ። ከዚህ አንጻር አባላትን ለመሸለም የሚያስችል ህጋዊ ማእቀፍ እንደሌለው ይገልጻሉ ።

ሁለተኛው ምክንያት የአመራር አባል የሆነን ግለሰብ መሸለም በሽልማቱ አካሄድ ላይ ተጽእኖ እንዲፈጠር እድሉን ያሰፋል የሚል ነው ። የአቶ አማረ አመራር አባልነት በሽልማቱ አካሄድ ላይ ችግር ይፈጥራል የሚለው ህሳብ እንኳን በቀላሉ ቅቡልና የሚያገኝ አይመስለኝም ። ምክንያቱም የምክር ቤቱ አባላት በበርካታ እውቀት ጠገብ ድርጅቶች የታቀፈ ነው ።  ፎርቹን ፣ አዲስ አድማስ ፣ ሸገር ፣ ኢቢሲ ፣ ዛሚ ፣ ካፒታል ፣ ኢትዮጽያ ፕሬስ ኤጀንሲ ፣ ኢጋማ ፣ ኢትዮ ቻናል ፣ ቁም ነገር እና ሌሎች ማህበራት ይገኙበታል ። ሲጀመር እነዚህ ቡድኖች ጥራት ያለው ማንዋል አይኖራቸውም ማለት ይከብዳል ። ሲለጥቅ በግልጽ ፣ በማያሻማና ዴሞክራት በሆነ መልኩ የፈልጉትን የሚመርጡበት ስነ ሰርዓት ይኖራቸዋል ተብሎ ይጠበቃል ።

የሆኖ ሆኖ አቶ አማረና ድርጅታቸው ከዚህ በፊትም አንድ ሀገራዊ ምርጫ አሸንፈው መጭበርበራቸውን ለሚያውቅ ለእኔ አይነቱ ሰው የአሁኑ ምርጫ አሸናፊነት ብዙም ላያስገርመው ይችላል ።

እንዴት ተጭበረበሩ ?

የቀዳማዊ ሃይለስላሴ የሽልማት ድርጅት ከተረሳ በርካታ አመታት በኋላ በሀገራችን አንድ የሽልማት ድርጅት ተቋቁሞ ነበር ። የኢትዮጽያ ስነጥበባትና መገናኛ ብዙሃን ድርጅት የሚባል ። ይህ ድርጅት በ 1994 ዓም ላካሄደው የሽልማት ተግባር አስቀድሞ ነበር በየዘርፉ ሊዳኙ ይችላሉ ብሎ ያመነባቸውን ግለሰቦች የመረጠው ። እናም የመጀመሪያው ትውውቅ ቀን በስብሰባ ማዕከል ተጠርተን በአቶ እቁባይ በርሄ የአሰራር መግለጫና ወፍራም አደራ ተሰጥቶን በየቡድናችን ስራውን ማሳለጥ ጀመርን ።

ጋዜጠኞችን ለመምረጥ ታሪካዊውን እድል ያገኘነው አምስት አባላት ነበርን ። ስብጥሩ ደግሞ ሁለት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አንጋፋ መምህራን ፣ አንድ የኢቲቪ አንጋፋ ጋዜጠኛ / ከእንግሊዘኛው ክፍል / ፣ አንድ የአትዮጽያ ሬዲዮ አንጋፋ ጋዜጠኛ እና እኔ ነበርን ።

ቢሮአችን ዩኒቨርስቲ ውስጥ ሆኖ ደከመን ሰለቸን ሳንል ተጋን ። ሊቀ መንበራችን ልምድ ያለው ሰው በመሆኑ እንዴት መሄድ እንዳለብንና ምን የተሻለ ስራ ማከናወን እንደሚኖርብን መንገድ አመላካች ነበር ማለት ይቻላል ። መጠይቆች ተሰርተው በመንግስትና በግልሚዲያ ተቋማት ተበተኑ ። የዚህ መጠይቅ ውጤት ተሰብስቦ እስኪቀመር ድረስ ደግሞ በየዘርፉ ያሉ ጋዜጠኞችን መዘርዘር ጀመርን ። የዳኞች ስብጥር ሁሉንም አካባቢ የሚወክል በመሆኑ ብዙም አልተቸገርንም ነበር ። ከዚያም በእያንዳንዱ ጋዜጠኛ ላይ ውይይትና ክርክር ይደረጋል ። ብዙ መቶዎችን ወደ መቶ ፣ መቶዎቹን ወደ ሃምሳ ፣ ሃምሳውን ወደ ቀጣዩ ግማሽ በመውሰድ ለፍጻሜ መድረስ ቻልን ። በመሃሉ ግን ‹ የስነጥበብ ዘርፍ ዳኞች እየጨረሱ ናቸው እናንተ ምን እያደርጋችሁ ነው ? › የሚለው የነ አቶ እቁባይ ጭቅጭቅ እረፍት ነሺ ሆነብን ። የኛ ጥያቄ ታዲያ ‹ በአጭር ግዜ የሚጨርሱት ምን አይነት ስልት ቢከተሉ ነው ? › የሚል ነበር ። በጥራት እሰራለሁ ብሎ ለሚነሳ ቡድን እያንዳንዱን እጩ በተጨባጭ አቅሙን መፈተሽ ግድ ይለዋል ። የራሱን ግምት ብቻ ሳይሆን የባለሙያውን አስተያየት ምርኩዝ ማድረግ ይኖርበታል ። ይህ ደግሞ ግዜ ይፈልጋል ።

በእውነት ከባድና አታካች ስራ ነበር ። ብዙ ግዜም የተሻሉትን ለመምረጥና ለማበላለጥ ስንቸገር ድምጽ መስጠቱ ነበር የሚገላግለን ። እናም በርካታ ወራት ከደከምን በኋላ የተሸላሚዎችን ስም ዝርዝር ከነ ምክንያቱና ማብራሪያው ጽፈን አስረከብን ።

ተጠባቂው ቀን ደረሰ ።

ሸራተን ሆቴል ልዩው ስነ ስርአት ሲካሄድ የመረጥናቸው ሁለት ሰዋች ተሰርዘው የማናውቃቸው ሁለት ጋዜጠኞች ክብሩንና 20ሺ ብሩን በእጃቸው ወሰዱት ፣ በአንገታቸው አጠለቁት ። የእኛ እንገት ግን በሃፍረት፣ በቁጭትና በህዘን አቀረቀረ ። ሁለት ዳኞችን አግኝቼ ስለ ሁኒታው አነጋገርኳቸው - እንደኔ ድንጋጤ አስክሯቸው ነበር ። ያ ሁሉ ልፋታችን ገደል ገባ ። « የዳኞች የመጨረሻ ውሳኔ የመጨረሻ ነው » በተባልነው ዲስኩር ላይ ለማላጋጥ ሞከርኩ - ይህን ማድረግ ግን አልቻልኩም ፤ ምክንያቱም በግልጽ ያላገጠብኝ እሱ መሆኑን ሰለተረዳሁ ።

ለዳኞች የተሳትፎ ወረቀት በሚሰጥበት ቀንም በነበረው አሰራር ላይ ውይይት ስለነበር በአጭበርባሪው ምርጫ ላይ የማላገጥ እድል አገኘሁ ። የተሰማኝን ሁሉ ተነፈስኩ ። ነገር ግን በእኔ ሀሳብ ላይ ምላሽ ወይም አስተያየት የሰጠ አልነበርም ። አንዱ በአንዱ ሲስቅ... እንደማለት ።

በእነ እቁባይ በርሄ ከተሰረዙት ተሸላሚዎች መካከል ብዙ ወንድማገኝ እና ሪፖርተር ጋዜጣ ይገኙበታል ። የተተኩት ደግሞ በኢትዮጽያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ የነበሩት ሳሙኤል ፍቅሬ እና የሃይለራጉኤል ታደሰ ባለቤት የሆነችው ሂሩት ናቸው ።

ያኔ ታዲያ ሪፖርተርን እንደ ጋዜጣ እንዲሸለም ያጨነው ህትመት ላይ ካሉ ጋዜጦች ጋር በማወዳደር ነበር ። ለማወዳደሪያነትም ተነባቢ ፣ አሳታፊ ፣ ወቅታዊ ፣ ተጽእኖ ፈጣሪ የሚሉና ሌሎች የጋዜጠኝነት መርህና መመሪያዎችን መሰረት እድርገናል ። ይህ ማለት የስታፉ ሁለገብ ተሳትፎን ጨምሮ የዋና አዘጋጁ አማረ አረጋዊ ሚና ትልቅ እንደነበር የሚያመላክት ነው ። አቶ አማረ ከ 97 በፊትና በኋላ አንድ አይደለም የሚሉ ሰፊ ሃሳቦች ቢኖሩም ፈተና ለበዛበት የሀገራችን ፕሬስ ያደረገው አስተዋጽኦ በቀላሉ የሚታይ አይደለም ። ትናንት ያጣውን ሽልማት አሁን ማግኝቱ ማስደሰቱ ብቻ ሳይሆን እንደ ልዩ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል ።

No comments:

Post a Comment