Saturday, September 8, 2012

‎በቀጣዩ መንግስት የሚወራረዱ ሂሳቦች … ?!?‎






አቶ መለስ በሞት ምክንያት ዱላቸውን ለተተኪው መሪ አላቀበሉም፡፡ ዱላው አንዳንዴም እንደ አራት አንዳንዴም እንደ አንድ በሚያስበው ድርጅት እጅ ነው ያለው ፡፡ ከብዙ ፍትጊያም እንበለው የሰከነ ውይይት በኃላ በአንድ ሰው እጅ ውስጥ መውደቁ የግድ ነው ፡፡ ድርጅቱ ለግዜው ባለዱላውን አይወቀው እንጂ እንዴት መሮጥ እንደሚገባው አስቀድሞ ወስኗል፡፡ ይህን መስመርም ለህዝቡ   ‹‹ የመለስ ፖሊሲና ስትራቴጂን ያለ አንዳች ማዛነፍ እናስቀጥላለን ›› በማለት አውጇል ፡፡

በሌላ አነጋገር አየለም መጣ አየለች ፖሊሲው ትክክለኛ በመሆኑ ሃዲዱን ይዘው እንዲጓዙ ይጠበቃል ማለት ነው ፡፡ እንግዲህ አከራካሪው ጉዳይ የሚጀምረው ከዚህ ምዕራፍ ላይ ነው ፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ወገኖች፣ የፖለቲካ ምሁራኖች፣ ጋዜጠኞች፣ ለሚዛናዊ ብይን የቀረቡ ሰዋች የሚሉት አቶ መለስ እንደ ጥንካሬያቸው ሁሉ ደካማ ጎንም ነበራቸው ፡፡ ህዝቡን አንድ አድርጎ ልማቱን በአስተማማኝ መልኩ ለማስቀጠል ከተፈለገ ዱላውን የያዘው ድርጅት ስለ ደካማ ጎናቸውም መስማት ይኖርበታል ፡፡ መስማትም ብቻ ሳይሆን እውነተኛና ተቋማዊ ለውጥ ለመፍጠርም መዘጋጀት ይገባዋል ፡፡

ዱላውን የሚረከበው መንግስት በመስመሩ ወይም በሃዲዱ ላይ የተለመዱትን አሰራሮች ይዤ እሮጣለሁሁ ከሚል ግራና ቀኛ በማየት አማራጮችን መፈተሸ አለበት ፡፡ የድርጅቱ አጋር የሆኑት ሱዛን ራይስ በቀብር ወቅት በዴሞክራሲ ግንባታ ፣ በሰብዓዊ መብት አያያዝና በሲቪክ ማህበራት እንቅስቃሴ ዙሪያ መንግስታቸው ሰፊ ስራ መስራት እንደሚፈልግ ጠቁመዋል ፡፡ ይህን ሃሳብ ጨምሮ ሌሎች መሰረታዊና መፈታት ያለባቸው ጥያቄዋች በብዙሃኑ ህዝብ አእምሮ ውስጥ እየተመላለሱ መሆኑን መረዳት ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም ፡፡

ኢህአዴግ ዘግይቶም ቢሆን / የ97 ምርጫ ደውል / በልማት ዘርፍ ላይ አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ መምጣቱ ይታወቃል ፡፡ ይህን ውጤትም በተሻለ ደረጃ ማሳደግ ይጠበቅበታል ፡፡ አንድ ምሁር የተናገሩትን መሰረታዊ ንግግር ላስከትል ‹‹ ማንኛውም ሀገር በመጀመሪያ መሰረታዊ የሰው ልጆችን መብት በተጻፈ ህግ መደንገግ ይኖርባታል ፡፡ ህጉና ህገመንግስቱ ደግሞ በየዕለቱ በፖለቲከኞችና በባለስልጣናቱ መጠበቅ ይፈልጋል ›› ምሁሩ እንደሚሉት ለዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብቶች ዕውቅና በመስጠት ረገድ የሀገራችን ህገ መንግስትም ሆነ ሌሎች ህጎች የተጋነነ ችግር የለባቸውም ፡፡ ችግሩ እነዚህን እንደ ውሃና እንጀራ የሚያሰፈልጉንን መብቶች እንደ ቤት ጌጦች አስቀምጠን ማየታችን ነው ፡፡ የሚያምር ህግ ነው ከማለት ውጪ ከጥቅማቸው እንድንጋራ በተግባር አልተተረጎመም ፤ ሶስቱ ጉልበተኞች / ስራ አስፈጻሚ፣ ህግ አውጪውና  ተርጓሚው / አስፈላጊ በሆነ ግዜ ሁሉ ሺሸራርፏቸው የማስፈጸም ችግር አለ በሚል ይታለፋል ፡፡

ከሲቪል መብቶች ውስጥ የመናገር ፣ የመጻፍ ፣ የመቃወም ፣ ነጻ የፍርድ ቤት አሰራርና የመልካም አስተዳደር አሰራሮችን ለአብነት ብናነሳ ሰፊ ችግሮች የሚታይባቸው ናቸው ፡፡

መረጃ የሚገኝባቸውና ነጻ ሃሰብ የሚተላለፍባቸው ጋዜጦች በተለይም ከ1997 ምርጫ ወዲህ አደጋ ውሰጥ መውደቃቸውን ጥናቶቸ አረጋግጠዋል ፡፡ ጋዜጠኞች በትልቅ በትንሹ ከመከሰስና ከመዋከብ አልፈው ህትመቶች ስርዓት በሌለው መንገድ እንዲዘጉ ይደረጋል ፡፡ ማተሚያ ቤቶች የፈለጉትን ማተም የማይፈልጉትን ቀይ ማሳየት ጀምረዋል ፡፡ መቼም በራሱ የሚተማመን ፣ ለልማትና ፈጠራ የተጋ ፣ በሀገሩ ተግባር የማይሸማቀቅና ነጻነት የሚሰማው ፣ የሰለጠነ አመለካከት ያለው ህብረተሰብ ለመፍጠር ንባብና ከወቅታዊ መረጃ ጋር የተገኛኙ ዜናዋች ሁሉ አስፈላጊ ግብዓቶቹ ናቸው ፡፡ እነዚህን ግብዓቶች ከመንግስታዊ ሚዲያዋችና ጋዜጦች ማግኘት ይቻላል የሚል የውስጥ አቅጣጫ ካለ የታመመ አሰራር በመሆኑ ቀዶ ጥገና ያስፈልገዋል ፡፡ የታመመው ደግሞ ከህገ መንግስቱ መብቶች ጋር በመቃረኑ ነው ፡፡ መቼም ይህ ህገ መንግስት እያለ ‹  ቻይናም ያደገችው ዴሞክራት ሳትሆን በመሆኑ እንቀጥልበታለን ›  ማለት ወደ ለየለት ህመም መድረስን ያሳብቃል ፤ ምክንያቱም የቻይናን የፕሬስ ፈለግ ለመከተል መጀመሪያ ህገ መንግስቱን በወፍራም ቀለም መደለዝ  ስለሚያስፈልግ ፡፡ በመሰረቱ የግል ጋዜጦችና መጽሄቶች ሁሉ አጥፊ ተልዕኮ አላቸው ከሚለው ጭፍን አመለካከትም መጽዳት ያስፈልጋል ፡፡ የግል ፕሬሱ የተዛነፉና አድሏዊ አሰራሮችን ነቅሶ በማሳየት ረገድ አይነተኛ ሚና እንዳለውም መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ ከዚያ በመለስ የሚታይባቸውን የእውቀትና የአሰራር ችግር ማስተማር ይቻላል ፡፡ ማስተማር ብቻ ሳይሆን መንግስት ንፉግ ሆኖ የቆየበትን መረጃ የመስጠት ግዴታና ኃላፊነት ማሰተከከል ይኖርበታል ፡፡ መንግስትን መተቸት የሚያስፈራና አሳሳሪ መሆን የለበትም ፡፡

ለነገሩ ብዙም አይወራላቸውም እንጂ የመንግስት ጋዜጠኞችም የኤዲቶሪያል ነጻነት የላቸውም ፡፡የሙያው ስነምግባር በሚፈቅደው መልኩ ስራቸውን እንዳይሰሩ ያደረገው የአቅም ችግር ብቻ ሳይሆን የመንግስት የበዛ ጣልቃ ገብነት ነው ፡፡ በዕውቀትና በልምድ የላቁ ጋዜጠኞች የድርጅት አባል እንዲሆኑ ይገደዳሉ ፡፡ ቦታቸውንና የዕለት እንጀራቸውን ላለማጣት ሲሉ ስነ ምግባሩ በማያዘው ጎዳና ውስጥ ገብተው ይዳክራሉ ፡፡ የድርጅት አባል ሆኖ ደግሞ የምርመራ ጋዜጠኝነትን ፣ የመልካም አስተዳደር ችግርን እዘግባለሁ ማለት አይቻልም ፡፡ እረ የድርጅት አባል ሆኖ ህዝባዊ ጋዜጠኛ ነኝ ለማለት ሞራል ይተናነቃል ፡፡ 

ከትንሷ ሀገር ኬፕ ቨርድ እንኳ ብዙ መማር ይኖርብናል ፡፡ ይች ሀገር ከ 2006 ጀምሮ እያሳየች በመጣችው የፕሬስ ነጻነት ከአፍሪካዊው ሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን የዘንድሮው ተሸላሚ ሆናለች ፡፡ እንደሚታወቀው የዓለማችን ሶስት የፕሬስ አፋኝ ሀገሮች ኤርትራ ፣ ሰሜን ኮሪያና ሶርያ ናቸው ፡፡ ቀም ነገሩ እኛስ ? የሚለውን ጥያቄ ጠይቆ በአግባቡ መመለሱ ላይ ነው ፡፡ ፍሪደም ሀውስ ፕሬስ በያዝነው ዓመት የዓለም ሀገራትን ከዲሞክራሲና ከፕሬስ ነጻነት አንጻር በይኗቸው ነበር ፡፡ በዚሁ መሰረት ኢትዮጽያ ከ194 ሀገሮች 176ተኛ ላይ ተቀምጣለች ፡፡ ነጻ ያልሆነች ዞንም ብሏታል ፡፡ ሀገራችን ከአፍሪካ አንጻር እንኳ ደረጃዋ ሲታይ የሚያሳፍር ነው ፡፡ 43ተኛ ናትና ፡፡ ይህች ያልተገዛች ፣ ስለ ነጻነት የምታውቅ ለጎረቤቶቻም ድጋፍ ስትሰጥ የነበረች ሀገር መጨረሻ አፋፍ ላይ መታየት ነበረባት ? 

ባንዲራና መፈክር ያነገቡ ተቃዋሚ ሰልፈኞችን ማየት አልናፈቃችሁም  ? ይህ መሰረታዊ መብት ለምን ኮሰሰ  ?  መቼም የመቃወሚያ ርዕሰ ጉዳይ ጠፍቶ አይደለም ፡፡ በነገራችን ላይ የተቃውሞ ተቃራኒ ወንድም የሆነው ‹ ድጋፍ ወይም ድጋፌ › ግን አልፎ አልፎ ብቅ ከማለት አልተቆጠበም ፡፡ ታዲያ ይህ ድጋፍ መልኩ ወደ ሁለት መቀየሩን ልብ ይሏል ፡፡ መንግስት በደስታ ሲገለፍጥ  አደባባይ ወጥቶ ይጨፍራል ፡፡ መንግስት በሆነ ጉዳይ ሲናደድ አደባባይ ወጥቶ ያስከፋውን ነገር ያወግዝለታል ፡፡ ዞሮ ዞሮ ድጋፍና ተቃውሞ ለዴሞክራሲ ስርዓት ጠቃሚ በመሆናቸው እንደ አቤል እና ቃየን የተለየ ትርጉም አይሰጣቸው ነው ጥያቄው ፡፡

በየመ/ቤቱ በሚካሄድ ስብሰባ ላይ ሰራተኞች ጭብጥ ብለው እንደገቡ ለምን ጭብጥ ብለው ይወጣሉ ? እንዲጠይቁና አስተያየት እንዲሰጡ ሲነገር አንገታቸው ወደ መሬት ያዘቀዝቃል ፡፡ የሚናገሩት ችግር ሳይኖር ቀርቶ ነው ? አንዳንዴ ከሰብሳቢው የተሻለ እውቀት ሳይኖራቸው ቀርቶ ነው ? አይደለም ፡፡ ጠንከር ያለ ሃሳብ ከሰነዘሩ ጀርባቸው ይጠና … የሆነ አመለካከት ተሸካሚ ሳይሆኑ አይቀርም … የእገሌ ደጋፊ ናቸው … የሚለውን ማሰፈራሪያ ወይ በግምገማ ወይ በሌላ አጋጣሚ ስለሚሰሙ እንጂ ፡፡ እናም ቢያውቁም ባያውቁም ይሐው ‹‹ ጎመናን በጤናን ›› በሆዳቸው አሳምረው መዘመር ከያዙ ስንት ዘመን አለፈ ፡፡ እንግዲህ የዴሞክራሲ ስርዓት ከሚፈልገው ግብዓት አንዱ  የሆነው  ‹ ተሳትፎ › ዛሬ ስግግ ያለ ስዕል ያገኘ መስሏል  ፡፡

ፍርድ ቤቶቻችን ፍትሃዊ አሰራርን ማስፈን ግን አልቻሉም  ፡፡ ቀጠሮውና መመላለሱ ወገብ ያነክታል ፡፡  ህገ መንግስቱ የሰጣቸው ነጻ አሰራር ተግባራዊ አልሆነም  ፡፡ አቶ ስዬን የለቀቀው /ቤት በሆነ የፖሊስ ተቋም መንገድ ላይ ሲጠለፍ ተቋሙን ለመክሰስና  የህግ የበላይነትን ለማሳየት አቅም የለውም ፡፡ ፖሊሶች ለበርካታ ግዜያት ስለሰብዓዊ መብት አያያዝ ስልጠና ቢወስዱም ዛሬም አይናችን እያየ  ግለሰቦችን በየአደባባዩ ይወግራሉ  ፡፡እረ በህጉ መሰረት… › ብሎ አስተያየት ለመስጠት የከጀለ ጀርባው ላይ ወፍራም ዱላ ሊያርፍበት ወይም የአይጥ ምስክር ዲንቢጥ ተብሎ  ወደ ጣቢያ ሊጎተት ይችላል ፡፡ ለአንዳንዶቹ  እስረኞችን  አለማክበር ፣ ማንጓጠጥ ፣ መሳደብ የተፈቀደላቸው ይመስላል ፡፡ የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት እንደሚገልጸው ዜጎች ዛሬም በማያውቁት ሁኔታ ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ ፡፡

ኢህአዴግ ብሄር ብሄረሰቦችን የሚገልጸው ‹ ልዩነታችን ውበታችን ነው › በሚል አሪፍ አገላለጽ ነው ፡፡ ይህ ውበት ለባህልና አኗኗር ብቻ ሳይሆን ለአመለካከትና አስተሳሰብም መዋል ይኖርበታል ፡፡ እሱን የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ የሚቃወሙና የሚተቹ  መኖራቸውንም ከልብ መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ የዴሞክራሲም ውበት እዚህ ላይ ነው ፡፡ እኔን ብቻ አዳምጡኝ ወይም ተከተሉኝ ካልሆነ ግን መጥፎ ስምና ታርጋ እለጥፍባችኃለሁ ማለት የዴሞክራቶች ፍልስፍና አይደለም ፡፡ በራስ ድምጽና ዘፈን ብቻ ከመደሰት ይልቅ የሌሎችንም ዜማ ማጣጣም ‹ ልዩነት ውበት ነው › የሚባለው ብሂል አካል መሆኑን መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ በአጠቃላይ የዴሞክራሲውን ግንባታ የሚያኮሰምኑ ተግዳሮቶችን አዲሱ መንግስት መቃኝት ይጠበቅበታል ፡፡
ልዩ ልዩ የሲቪክና የሙያ ማህበራት እንዲደራጁና በልማትና በዴሞክራሲ ግንባታው ውስጥ ትልቅ ሚና እንዲጨወቱ እገዛ ማድረግ ቢቀድምም አምሳያቸውን ፈጥሮ እንዲኮሰምኑ የማድረግ አሰራርን ስንከተል ቆይተናል ፡፡ አዲሱ መንግስት ይህን አካሄድ በድፍረት ተችቶ የተሻለ አቅጣጫ ማሰቀመጥ ይኖርበታል ፡፡


No comments:

Post a Comment