Monday, September 3, 2012

ጥቁርና ነጭ ንግግሮች




የጠ/ሚ/ር መለስ ስርዓተ ቀብር ከመርዘሙና በተፈጥሮ ዝናብ ከመታወኩ በስተቀር የተዋጣለት ነበር ፡፡ በርግጥ ወደ መጨረሻ አካባቢ የጣለው ዝናብ ከሰሜን ኮሪያው ፕሬዝዳንት ኪም ጆንግ ኢል  ቀብር አንጻር ከታየ ‹ ጥቂት ነው  › የሚባል ዓይነት ነው ፡፡ የያኔው ቀብር ሶስት ሰዓታት ሲፈጅ ኃይለኛ በረዶ አልተለየውም ነበር ፡፡ እንዲያም ሆኖ ትንሽ ትልቁ፣ ሲቪል ሰራዊቱ መንገድ ላይ ወጥቶ አንብቷል ፡፡ የሀገሪቱ ጋዜጣም ኃይለኛውን ዝናብ ‹‹ የገነት ዝናብ ›› ሲል ጠርቶታል፡፡ በሀገራችን ባህል ቀብርን ዝናብ እንዲያውክ ባይፈለግም አንድ እናት  ‹‹ ለመለስ ፈጣሪም አለቀሰለት! ›› በማለት አዛማጅ ትርጉም ሰጥተውታል ፡፡
የመሸኛ ስነስርዓቱ የአቶ መለስን የተሳካ የመሪነት ተግባር በታዋቂ ሰዋች ማስመስከር ላይ ያነጣጠረ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ሁሉም ተናጋሪዋች የአቶ መለስን ተክለ ሰውነት በተመቻቸው መንገድ ገልጸውታል ፡፡ ሳቢ ንግግሮችንም አድምጠናል ፡፡አልፎ አልፎ ግን የመስካሪዋቹን ውብ ቋንቋና ከቋንቋው ጀርባ ያለውን ጉዳይ ያለቦታው እያነጻጸርኩ ከጥቁርና ነጭ ምስሎች ጋር ተላትሜያለሁ፡፡
 
ለምሳሌ ዩዎሪ ካጉታ ሙሴቬኒ ምስክርነታቸውን ሲገልጹ የነበሩት ወረቀት ሳያነቡ ነው ፡፡ ጣፋጭ ንግግራቸው ብቻ ሳይሆን ተክለ ቁመናቸውም ፊልም ከሚሰራ ካው ቦይ ጋር ይመሳሰላል ፡፡ ታዲያ እንዲህ እንዳፈዘዙኝ ስልጣን ወደያዙበት 1986 በሀሳብ አፈናጠሩኝ፡፡ ያኔ ‹‹ ማንኛውም የአፍሪካ መሪ በስልጣን ከ10 ዓመት በላይ መቆየት የለበትም ›› በማለት በይፋ ተናግረው ነበር ፡፡ ዛሬ ረስተውት ይሆን ? ይኀው እሳው በስልጣን ላይ 26 ዓመታቸው ፣ ለነገሩ ይሄ የአፍሪካ መረዎ በሽታ ነው ። 
 
አቶ ኩማ ደመቅሳ ኦማር ሀሰን አህመድ አልበሽርን ‹‹ ፊልድ ማርሻል ›› እያሉ ሲያስተዋውቁ ሰማው ልበል ?  ‹‹ ፊልድ ማርሻል ›› መድረሳቸውን መቼ ሰማሁና ?! እኚህ መሪ ከ2003- 2009 ባሉት ግዜያት ከአምስት መቶ ሺህ በላይ ሰዋች ማስገደላቸውንና በተመድ ከሚፈልጉ  መሪዋች አንዱ መሆናቸውን ግን አውቃለሁ ፡፡ አፍሪካዊያን መሪዋች ግን ይህን ክስ አልተቀበሉትም ፡፡ ‹  በሰው ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ የሚፈተፍቱ ነጮ ›  በኛ ጉዳይ አያገባውም ይላሉ - ከሳሾቹን ፡፡ እርዳታ በሚፈልጉ ግዜ ደግሞ ነጫጭባ የሚቸውን ነጮጭ ወደ መላዕክትነት ይቀይራሉ ፡፡ እናም አልበሽር መኪና ፈርቶ ዳር ዳሩን እንደሚጓዝ ገጠሬ ጥግ ጥጉን ሲጓዙ ዘመናት አስቆጥረዋል  ፡፡ ግን ነጻነትን እንዴት ይሆን የሚተረጉሙት ?
አሜሪካዊቷ አምባሳደር ሱዛን ራይስ ጥቁርና ነጭ ብቻ ሳይሆን ቀይ ቀለምንም ጨምረው የተናገሩ ብልህ ዲፕሎማት ናቸው ፡፡ ልብ በሚነካው ሀዘናዊ ቋንቋ የወ/ሮ አዜብ መስፍንን ልብ ኮርኩረዋል ፡፡ አሜሪካና አቶ መለስ የነበራቸውን ጥብቅ ቁርኝት መግለጻቸው ብቻ ሳይሆን ታላቋ ሀገር ዛሬም ለኢህአዴግ ቀኝ እጅ ሆና እንደምትቀጥል ማረጋገጣቸው ሁለተኛው ቀለም ነው ፡፡ ኢህአዴጎች ዲፕሎማሲያዊ ግባችንን እንደ ምርጫችን 99 ከመቶ አሳካን ብለው የሚያስቡትም ይህንኑ ይመስለኛል ፡፡
 
እኚህ ብልህ ዲፕሎማት የመጡት የሀዘን ተካፋይ ለመሆንና የሽብርተኞችን ጉሮሮ አንቃ የቆየችውን ምስራቃዊ ሀገር ‹ አይዞሽ › ለማለት ብቻ አይደለም ፡፡ ለሀገሪቱ አባታዊ ቡራኬ ለመስጠትም ጭምር እንጂ ፡፡ ቡራኬው በፓለቲካዊው ጎዳና ላይ ምን እንደሚጓዝና እንዴት እንደሚንቀሳቀስም አቅጣጫ ያስቀምጣል ፡፡ ይህን አቅጣጫ በንግግራቸው መጨረሻ አካባቢ በገደምዳሜ ጠቁመውታል ፡፡ ሀገራችን ዴሞክራሲን፣ የሰብዓዊ መብት አያያዝና የሲቪክ ማህበራትን እንቅስቃሴ አጠናክራ እንድትቀጥል በመናገር ፡፡
ትንሽ ደቂቃ የቆየው የወ/ሮ አዜብ መስፍን ንግግርም ብዙ ሰዓታት ሊያወያይ የሚችል ፍቺ ያቀፈ ይመስላል ፡፡ ‹‹ የመለስ ፓሊሲና ስትራቴጂ እስካልተበረዙ ድረስ ዓላማው እውን ይሆናል ›› የሚል ሀሳብ ፈንጥቀዋል ፡፡  ‹ ድርጅቱ ያለምንም ለውጥ ያለውን አሰራር ይዞ ይቀጥላል ›  ከሚለው የሃላፊዋቹ አስተሳሰብ ጋር የእሳው ንግግር ለምን ተቃረነ ? ወይም ስጋት ያደረበት መሰለ ብሎ መጠየቅ በርካታ ሚስጢሮን ሊያስገኝ ይላል ።
 
ይበልጥ ትኩረቴን የሳበው ግን በአቶ መለስ ምንነት ላይ የተነገረው ንግግር ነው ፡፡ ‹‹ መለስ ቢል ቦርድ እንዲለጠፍለት ፣ ሃውልት እንዲቆምለት አይፈልግም ! ›› የሚለው ፡፡ ቀደም ብሎም መለስ ስለ ራሱ ማውራትም ሆነ እንዲወራለት አይፈልግም የሚል ሀሳብ ከትግል አጋሮቹ ተንጸባርቋል ፡፡ ታዲያ በእለቱ አቶ መለስ እንዴት ሲገለጹ ነበር ? ለተገላጩ ይሰጡት የነበሩት ቅጽሎች ከላይ የተጠቀሰውን ሀሳብ ያከበሩ አይመስልም ፤ ገደል የከተቱ እንጂ ፡፡ ካድሬዋቹ የማንነት ብቻ ሳይሆን የድርጅት ገጽታ ግንባታ እየሰሩ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም ጥንቃቄን  ‹ ዞር በል ባክህ ! › ያሉት ያስመስላል ፡፡ በዕለቱ ንግግሮች ውስጥ አቶ መለስ በርካታ መለዮና ካፖርት አጥልቀው ነበር :: ብዙዎቹ ግን በልካቸው የተሰፉ አልነበረም ። ተንቦርቅቀው ያስጠላሉ ። አንዳንዶን እንጥቀሳው ።
 
የህዳሴ መሃንዲስ
የለውጥ ጠንሳሽ
የተስፋ አባት
የድሃ አባት
ታላቁና በሳሉ
ገናና መሪ
ተወርዋሪ ኮኮብ
ብልሁና አስተማሪው
የቁርጥ ቀን ታጋይ
ብርቅዬ የአፍሪካ ልጅ
ባለ ራዕይ
የህግ ምሁር
የወታደራዊ ሳይንስ ቁንጮ
ሳይንቲስት
ዴሞክራሲያዊ እሴቶችን ያከበረ መሪ
ሆደ ሰፊ መሪ
ለዓለም አቀፍ ህግ ራሱን ያስገዛ መሪ
አፍሪካዊ መሪ
ህዝባዊ መሪ
የጸረ ደህንነት አርበኛ መሪ
የአፍሪካ ቃል አቀባይ
ህዝባዊ ፍቅር የተላበሰ መሪ
የማይናወጥ የዓላማ ጽናት ያለው መሪ በሚሉ ሀሳቦች ተገልጸዋል ፡፡ በርግጥ አንድ ሰው ይህን ሁሉ ሊሆን አይችልም ፣ ከሆነ ደግሞ የዓለም አስደናቂው መጽሀፍ ላይ መስፈር ነበረበት :: ፖለቲከኞቹ ጊነስ ቡክ ላይ ማስመዝገብ ትተው ሰው ሲሞት ይህን ሁሉ ካፖርት ማሽከም ማዕረግ መሆኑ ነው ?
 
እንደዚህ ዓይነት ምስል መፍጠርም ለማንነታቸው ሌላ ትርጉም የሚያሰጥ ነው የሚሆነው ፡፡ ለምሳሌ ያህል የሰሜን ኮሪያው ኪም ጆንግ ኢል  50 የሚደርሱ ልዩ ልዩ መጠሪያዋች ነበሩት ፡፡ ጓድ ሊ /መንበር ፣ የላቀው ሊ/መንበር ፣ የኛ አባት ፣ የተለየው ጄነራል ፣ የሀገሪቱ ጭንቅላት ፣ ጀግናው ፣ የሁሌም ባለድል ፣ የ21ኛው ክ/ዘመን መሪ ኮኮብ ፣ አስገራሚው ፓለቲከኛ የሚሉት ከብዙ ጥቂቶቹ ናቸው ፡፡ ይህ መሪ ግን በተግባር ከነሂትለርና ስታሊን ጋር የሚነጻጸር አምባገነን እንደነበር የፓለቲካ ምሁራን አረጋግጠዋል ፡፡
 
ኢዲያምን ዳዳንም ማስታወስ ይቻላል ፡፡ ይህ መሪ ራሱን የሚጠራው ‹‹ የተከበረው የእድሜ ልክ ፕሬዝዳንት ፣ ፊልድ ማርሻል አልሀጂ ዶክተር ኤዲያሚን ፣ በምድር ላይ የሚገኙ እንስሳትና በባህር ውስጥ የሚገኙ አሳዋች ሁሉ ጌታ ፣ የእንግሊዝን መንግስት በመላው አፍሪካ በተለይም በኡጋንዳ ያሸነፈ ›› በሚል ነበር ፡፡ ታዲያ የአቶ መለስስ ከዚህ በምን ይለያል ? 
 
እናም ጎበዝ ግራና ቀኝ ማየት የሚገባው መስቀለኛ የትራፊክ መንገድ ላይ ሲቆም ብቻ አለመሆኑን ደጋግሞ ማሰብ ያስፈልጋል ፡፡