Saturday, September 8, 2018

አርበኞች ግንቦት 7 እንኳን ደህና መጣህ




ወያኔ በግዳጅ በጫነው ፖለቲካዊ አደረጃጀት ሳቢያ ህዝባቸውን ለመታደግ ሲሉ ብሄር ተኮር አደረጃጀት ፈጥረው የተንቀሳቀሱ ድርጅቶችን ማክበር ተገቢ ነው ፣ በተለይም የእውነት ለታደጉትና እየታደጉ ለሚገኙት ፡፡ ሁሉን በአንዲት ታላቅ ሀገር ስም ፣ ሁሉን በኢትዮጵያዊነት ጥላ ደምረን እንሰራለን የሚሉ ድርጅቶች ሲገኙ ደግሞ ክብራችን ሌላ ጋት ይጨምራል ፡፡

አስጊ ጫፍ ላይ የተንጠለጠለችውን ኢትዮጵያ ወደ መሃል ስቦ ሚዛኗንና ሚዛናዊነትን ለማስጠበቅ እሰራለሁ የሚለውን አርበኞች ግንቦት 7ን ማበረታታትና መደገፍ የውዴታ ግዴታ ሆኗል ፡፡ ለምን ? ነባራዊው የፖለቲካ ሁኔታ የሚነግረን ጥቂት የአንድነት ወይም ኢትዮጵያዊያን ሃይሎች በየትየለሌ ብሄር ዘመም ድርጅቶች ተውጠው መገኘታቸውን ነው ፡፡ ብሄር ተኮር ድርጅቶች እድል አግኝተው ምርጫ ቢያሸንፉ እንኳ በኢትዮጵያ ላይ የሚኖራቸው የመጨረሻ ግብ ግልፅ አይደለም ፡፡ ኢትዮጵያ እንዳትፈራርስ ዋስትና የሚሰጥ ጠንካራ የፖለቲካ ፕሮግራምም የላቸውም ፡፡

ሌላው ቀርቶ ኢትዮጵያዊነትን እያዜመ የሚገኘው < አዲሱ ኢህአዴግ > እንኳ የአቅጣጫና የርዕዮት መስመሩን አላሻሻለም ፡፡ አራቱ እህት ድርጅቶች ሜጀር ተግባራቸውም ሆነ ቀጣይ ግባቸው ብሄር ተኮር ድልድይ መገንባት ይሆናል ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን የሚጠቃቅሱት በማይነር አስተምህሮት ነው ፡፡ በዚህ ስሌት ኢትዮጵያነት እንደምን ገዝፎና አሸንፎ ሊወጣ እንደሚችል ግልፅ አይደለም ፡፡ ከአቅጣጭ አንፃርም ኢህአዴግ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መንገዱን እንደማይለቅ ዶ/ር አብይ በቅርቡ መናገራቸው ይታወሳል ፡፡ በልምድ እንዳየነው ደግሞ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ዘብነት ወይም ጥብቅና ለብሄሮች እንጂ ለኢትዮጵያዊ ዜግነት አይደለም ፡፡

በብሄር ብቻ ሳይሆን በሃሳብ እና በአመክንዮ የሚወዳደሩ ጠንካራና ብስል ድርጅቶች ያስፈልጉናል ፡፡ በብሄርም ሆነ በዜግነት ማሰብ የወገንተኝነት መዳረሻ አለው ይባላል ፤ ትክክል ነው ፡፡ ፍትሃዊ ትክክለኝነት የሚመነጨው ግን የአግላይነት ድንበር ሲነሳ ነው ፡፡ የብሄር እሳቤ ትልቁ በሽታ ቀስ በቀስ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል ወደፈጠረው የአሳማዋች ፍልስፍና የማዳረሱ ክፋት ነው ፡፡ እንደሚታወቀው በአኒማል ፋርም አብዮት ያነሱት አሳማዋች የመጀመሪያ መፈክራቸው ውብ ነበር ፡፡ < ሁሉም እንስሣት እኩል ናቸው > እያሉ ነበር የሚዘምሩት ፣ ለውጡን በሙሉ ልብ ለመደገፍ የቆሙት ፡፡ እየዋለ እያደር ግን ብሄራዊ መፈክራቸው ወይም ህገ መንግስታቸው  < እኛ የተሻልን ነን > በሚሉ አሳማዋች ተቀይሮ ALL ANIMALS ARE EQUAL BUT SOME ANIMALS ARE MORE EQUAL THAN OTHERS የሚለውን ዘረኛ አንቀፅ ተሸካሚ ሆነዋል ፡፡ ሃሳቡን የማይደግፉ ሁሉ ትምክህተኛ እየተባሉ ተዘልፈዋል ፣ እንዲሸማቀቁ ተደርጓል ፣ ከመኖሪያ ቀያቸውም ተፈናቅለዋል ፡፡ የብሄር እሳቤ ትልቁ በሽታ < እኔ ከሌሎች የተሻልኩ ነኝ > የሚል ስስታም ተቀጥላ ስለሚያመነጭ ለዘወትር ብጥብጥና ግጭት መንሳኤ መሆኑ ነው ፡፡

ይህን በመሰሉ 40 እና 50 ድርጅቶች ተውጦ ፖለቲካን መስራት ደግሞ ያሰጋል ፡፡ መቼም ቢሆን ስነልቦናዊ መረጋጋትን ፈጥሮ በኢኮኖሚውም ሆነ ማህበራዊ ሰልፍ ወስጥ ራስን ለማስገባት ያስቸግራል ፡፡ የዳር ተመልካቹን ፣ የምናገባኝ አቀንቃኙን ፣ ባለግዜዎቹ  ይዘውሩት ባዩን ያበራክታል ፡፡ ሀገር ሰልላ እንድትሞትም አሉታዊ ሚና ይጫወታል ፡፡ ለዚህም ነው ፖለቲካው በቋንቋና ብሄር ብቻ ሳይሆን በሃሳብ ይሞገት የሚባለው ፡፡ ሃገር የሚያሳድገውና የሚያስከብረው ለሁሉም የሚጠቅም የዳበረ ሃገራዊ ሃሳብ ሲመነጭ ነው ፡፡ ሃሳብ ሳይገደብ ሊፈስና ሊመነጭ የሚችለው ደግሞ አጥር ሲፈራርስ ነው ፡፡ ከጠባብና የሚያፍን ክፍል ወጥቶ ማለቂያ በሌለው መስክ ላይ እንደልብ መሯሯጥ ሲቻል ፡፡

ህዝቡ በቅርቡ የተገኘውን ለውጥ የደገፈው ኢትዮጵያዊነት ከፍ ብሎ ስለተዘመረለት ነው ፡፡ በኢትዮጵያዊነት ውስጥ አንድነት ፣ ሰላምና ፍቅርን አበለፅጋለሁ ብሎ ስላሰበ ነው ፡፡ ይህ ከፍታ ደረጃውን ጠብቆ ይጓዝ ዘንድ እንደምሶሶ ጠልቀው የተቸነከሩ ድርጅቶች እዚህና እዚያ መታየት ይኖርባቸዋል ፡፡

ተወደደም ተጠላ ኢትዮጵያ ታላቅ ሀገር ናት ፡፡ የሚመጥናት ትልቅነቷን ጠብቆ ከተቻለም አልቆ የሚጓዝ ድርጅት ነው ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን ዳግም ለማንገስ ተስፋ ከተጣለባቸው ድርጅቶች አንዱ አርበኞች ግንቦት 7 ነው ፡፡ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ ኢትዮጵያዊያን ስለ ኢትዮጵያዊነት ሆ ! ብለው ቢዘምሩ ሳያፍርና ሳይሸማቀቅ የግጥምና ዜማ ድርሰት ለማበርከት መዘጋጀት ስለሚችል ነው ፡፡ ሌላ ጠንካራ ህብረ ብሄራዊ ድርጅት እንደ አማራጭ እስኪወጣ ድረስም ግንቦት 7 እንዳይደናቀፍ አጥርና ጋሻ ሆኖ መመከት ያስፈልጋል ፡፡ ይህ ድርጅት በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ወስኖ ወደ ኢትዮጵያ መግባቱ ትልቅ ትርጉም አለው ፡፡ ከመሰል ድርጅቶች ጋር ህብረት ፈጥሮ ስለሚንቀሳቀስም የተፈጠረው ኢትዮጵያዊነት እሳቤ እንዲቀጣጠልም ይረዳል ፡፡ ቢያንስ በዘውገኞች የተከበቡ ዜጎች ተስፋ እንዳይቆርጡ ተስፋ እና ዋስትና ይፈጥራል ፡፡ አርበኞች ግንቦት 7 በትክክለኛው ግዜና ቦታ የተገኘ ድርጅት ስለሆነ እንኳን ደህና መጣህ ሊባል ይገባል ፡፡