Saturday, August 18, 2018

በግማሽ ሜዳ መጫወት ...



ሶሎ ጎል ይሉታል ፈረንጆቹ ፡፡ አንድ ተጫዋች በርካታ ባላጋራዎቹን አልፎ ጎል ሲያስቆጥር ፡፡ በጥበብ ፣ አካላዊ ብቃት ፣ ብልጠትና ድፍረት መሞላትን ስለሚጠይቅ ሁሉም ተጫዎቾች ሊያከናውኑት አይችሉም ፡፡ እናም ለግብ አግቢው ከወንበር ተነስቶ የረዘመ ጭብጨባና ክብር መስጠት ግድ ይላል ፡፡

ልክ እንደ ሶሎ < ዋው > የሚያስብል ሌላ ጥበብም እለ በእግር ኳሱ ዘንድ ፡፡ ከግማሽ ሜዳ ኳስን በትክክል መትሮ ጎል ማስቆጠር ፡፡ ይህንም ሲያደርጉ ያየናቸው ጥቂት የዓለማችን ተጫዋቾች ናቸው ፡፡ ጁዋን ካርሎስ ፣ ናቢ ፍቅርና ዋይኒ ሩኒን እንደ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል ፡፡ ኤቨርተንና ዌስትሃም ሲጫወቱ ዋይኒ ሩኒ ያደረገው ምንድነው ? ከክልሉ ወጥቶ ኳሷን ወደ መሃል ያወጣትን በረኛ ሁኔታ በመገንዘቡ ኳሷ ስትደርሰው ቀጥታ ወደፊት አጎናት ፡፡ ዳኛው የተለጋውን ኳስ እንዳይነካ አፈገፈገ ... ሁለት ተጫዋቾች ባለ በሌለ ሃይላቸው ወደላይ ለቴስታ ዘለሉ ... የመጨረሻው ተከላካይ ከሩቅ የተለጋ ኳስ ከሚቆጠርብን በእጄ ለኤሪጎሬ ባስቀራት ይሻላል ብሎ ወደ ላይ ዘለለ – አላገኛትም ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግብ ጠባቂው ወደጎል ሮጦ በማያውቀው ፍጥነት እየተፈተለከ ነበር ፡፡ ልብ አንጠልጣይ ድራማ ካየን በኋላ ኳሷ ከመረቡ ጋ ተሳሳመች ፡፡

ዶ/ር አብይ በእነዚህ አብዶኛ ተጫዎቾች ይመሰላሉ ፡፡ ከግማሽ ሜዳ የጠለዟቸው የፖለቲካ ኳሶች ጅቡቲ ፣ ሱዳን ፣ ግብፅ ፣ ሳዑዲ ፣ ኡጋንዳና ኤርትራ አርፈው ድል አስቆጥረዋል ፡፡ በአንድ በኩል የዲፕሎማሲውን ግንኙነት ሲያጠናክሩ በሌላ በኩል ማንም ሀሳብ ውስጥ ያልነበሩ ዜጎችን ከእስር አስፈትተዋል ፡፡ ወደክልሎች በመጓዝ ጥበብ ፣ ብልጠትና ድፍረት የተሞላበት ሃገራዊ ምክክር አድርገዋል ፡፡ በጎሳና ዘረኝነት ክፋት ተሰነጣጥቆ ሊበተን የነበረውን ኢትዮጵያዊ ትሪ ጠግነዋል ፡፡ የተራራቁ ሰዋች በአንድነት ተሰባስበው ባዛው ትሪ ላይ ማዕድ እንዲቀርቡ ፣ የጋራ ፀሎታቸውም ፍቅር ፣ ሰላምና ኢትዮጵያዊ ድማሬ እንዲሆን መንገድ አሳይተዋል ፡፡ ርቆ የተቀበረው ኢትዮጵያዊነት ክብሩ ተመልሶ ከባንዲራ በላይ እንዲውለበለብ አድርገዋል ፡፡

ዶ/ር አብይ በአጭር ግዜ ውስጥ ያስመዘገቧቸው ድሎች አመርቂና ተስፋ ሰጪ ቢሆኑም እየተጫወቱ የሚገኙት በግማሽ ሜዳ ነው ፡፡ ከትልቁ ጥያቄ አንደኛው ስንቱን ህዝባዊ ጥያቄ ከግማሽ ሜዳ እየመተሩ ማስገባት ይችላሉ ? የሚለው ነው ፡፡ ከትልቁ ጥያቄ ሁለተኛው ስንቱን እግር ሰባሪ ተከላካይ በአብዶ እየሸወዱ ውጤት ያስመዘግባሉ የሚለው ነው ፡፡

ዶ/ር አብይ ብዙ ተከላካዮችን አብዶ ሰርተው አልፈው ጎል የሚያስቆጥሩት ኢትዮጵያዊነትን ከዳር እስከ ዳር ለማሳደግ ነው ፡፡ ይሁንና ጥቂትም ሳይቆይ ሲዳማው ፣ አገው ፣ ጉራጌው በኔ ልክ የተሰፋ ክልል ይገባኛል ብሎ ጥብቆ ሲናፍቅ ታገኘዋለህ ፡፡ ዶ/ር አብይ ብዙ ተከላካዮችን አብዶ ሰርተው አልፈው ጎል የሚያስቆጥሩት  እንደ < ገነት > የምንናፍቀውን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እናይ ዘንድ ጥርጊያ መንገዱን ለመገንባት ነው ፡፡ ይሁን እንጂ ለድሃ ዳቦ እንጂ ነፃ ስርዓት አያስፈልገውም የሚሉ አምባገነኖች በተሰነጣጠቀው መንገዳችን ላይ የሚፈነዳዳ ፈንጂ ከመቅበር ሊቆጠቡ አልቻሉም ፡፡ ዶ/ር አብይ ከመሃል ሜዳ ለግተው ጎል የሚያስቆጥሩት የማሸነፍ ረሃብን ለማስታገስና ሮል ሞዴሎችን ለመቅረፅ ነው ፡፡ ይሁን እንጂ ማጥቃትንም ሆነ መከላከል እርግፍ አድርገው ትተው ጨዋታ የሚያቆሙ ብዙሃንን ታያለህ ፡፡ በሌላ አነጋገር ጨዋታውን አቋርጠው በፎርፌ ማሸነፋችን ይታወጅልን የሚሉ ፡፡ እነዚህ ወገኖች በጥቂት ወይም ሚዛን በማያነሳ ምክንያት ዱላ ፣ ገጀራና ክብሪት አንስተው ቀጣዩን ጥፋት ለማከናወን የማያመነቱ ሆነዋል ፡፡ ነገር ቆስቋሾች ፣ ገዳዳ አክቲቪስቶች ፣ በቀልተኛ ፖለቲከኞች ጃስ ባሏቸው ቁጥር ለምን ? እና እንዴትን ? ሳያነሱ ዘለው ንጹሃንን የሚናከሱ ወገኖቻችን እየበዙ መጥተዋል ፡፡ እነዚህን ሁሉ መግራት ከባድ ነው ፡፡ በአንድ ቀን ምክክርና የእርቅ ጉባኤም አጀንዳውን መዝጋት አይቻልም ፡፡

ጠ/ሚ/ሩ በየክልሉ በዘር ፣ ቋንቋና ሃይማኖት የሚለኮሱ ግጭቶችን ለማብረድና ለማስታረቅ የሚሯሯጡ ከሆነ ሌላውን አንገብጋቢ ስራ መስራት አይችሉም ፡፡ የፖለቲካ መዋቅሩም ሆነ ህዝቡ ጥሩ ጎል አግቢ ስለሆኑ እሳቸውን ብቻ የሚጠብቅ ከሆነ ሽምግልና እንጂ መንግስታዊ አሰራር ውሃ ይበላዋል ፡፡ ለዚያም ነው ጠ/ሚ/ሩ በግማሽ ሳይሆን በሙሉ ሜዳ መጫወት የሚችሉበት ቋሚ አሰራር መፈጠር አለበት የሚባለው ፡፡ ለዚያም ነው ከቅርብም ሆነ ከሩቅ ለግተው ግብ የሚያስቆጥሩ ኮኮቦችን ማፍራት ይገባቸዋል የምለው ፡፡

ርግጥ ነው በሀገራችን ያንዣበበውን ስጋት ለመቅረፍ ክፋትንና ድህነትን ተጭኖና አጥቅቶ በመጫወት ተደጋጋሚ ግቦችን ማስቆጠር ያስፈልጋል ፡፡ አለበለዚያ አቻ መውጣትና መሸነፍም ያጋጥማል ፡፡ አቻ መውጣት ክፋትንና ድህነትን አቅፎ መኖር ነው ፡፡ ወንድም ጋሼ ... ጌታ መሳይ... እያልከው ፡፡ ከተሸነፍክ ያለውድ በግድ < ጅቦች ለዘላለም ይኑሩ ! > የሚል መፈክር ተሸክመህ ትዘልቃለህ ፡፡ እነሱ የሚጥሉትን ቅንጥብጣቢ አያሳጣኝ እያልክ ፡፡ የሰላምና የፍቅርን ኳስ በማራኪ አጨዋወት እስከተቃራኒው ክልል ደርሶ ያማረ ጎል ማስገባት ያስፈልጋል ፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ለዋናው አጥቂ ኳስ አመቻችተው የሚሰጡ ደጀኖች ፣ አጥቂው ሲደክም ጎል ማስቆጠር የሚችሉ ቁርጠኛና ጥበበኛ ተጫዋቾች መሰለፋቸው መረጋገጥ ይኖርበታል ፡፡

በየክልሉ የሚለኮሱ ጎሳዊ ግጭቶችን ለመቀነስና ለመከላከል የተጠናከረ ትምህርትና ስልጠና ግድ ነው ፡፡ ለ27 ዓመታት የዘውጌ ስርዓት በማበቡና ብሄርተኝነት የተሻለ አማራጭ ተደርጎ በመሰበኩ ኢትዮጵያዊነትን በቀላሉ ማስረፅ ሳይከብድ አይቀርም ፡፡ ይህን ስራ የሚሰሩ የሲቪክ ተቋማትን ማስፋፋት ይጠይቅ ይሆናል ፡፡ ተመሳሳይ የፖለቲካ መስመር የሚከተሉ ድርጅቶችንና ቲንክታንኮችን Add እና Tag ማድረግ ግድ ይመስላል ። በውስጥ አሰራር ደግሞ ለንቋሳ አመራሮችን እየሻሩ ፣ ጠንካሮቹ ንቃተ ህሊናን ለማዳበር የሚያስችሉ የምክክር መድረኮችን ረጅም የስራ አካልና ግብ አድርገው እንዲተጉ ማሳሳብ ይጠበቃል ፡፡

ዘረኝነትና ጎሰኝነት አይደለም በአፍሪካ በአውሮፓ መሞት አልቻለም ፡፡ ጉዳት እንዳያደርስ ሸብቦ የያዘው ግን ጠንካራ ህጋቸው ነው ፡፡ ዶ/ር አብይ የፍቅርና ይቅርባይነትን ሎጎ ከፍ በማድረግ አስተዳደራቸው እንዳይንገጫገጭ ማድረግ ቢችሉ ሸጋ ነበር – ድብቁና ውስብስቡ ፖለቲካ ግን በዚህ ቀመር የሚሰራበት አግባብ በእጅጉ የሰለሰለ ነው ፡፡ አሸባሪ ፖለቲከኞችን ፣ የዘረኝነት ፈንጂ ቀማሚዋችን ፣ ብሄርን ከብሄር ለማጋጨት ሃሳብ ፣ ክብሪትና ጥይት የሚያቀብሉ የደም ነጋዴዋችን በአጠቃላይ ህገወጦችን መስመር የሚያሲዙበት ህጋዊ ማእቀፍ ያስፈልጋቸዋል ፡፡

Thursday, August 9, 2018

የኦሕዴድ የነገ ፈተና ...




ስልጣኑ ያለው ኦህዴድ ውስጥ ነው ፤ ኦሮሚያ ልብ ውስጥ ግን ኦነግ ከፍ ብሏል ፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ለዶ/ር አብይ አህመድ ፣ ለአቶ ለማ መገርሳና ለቲም ለማ ከፍተኛ ፍቅርና አክብሮት አለው ፡፡ ማሳያዎቹ ብዙ ናቸው ፡፡ ለምሳሌ በርካታ የሜኔሶታ ነዋሪ የሆኑ ኦሮሞዋች ሁለቱን መሪዎች በላቀ ደስታና የጀግንነት ስሜት ነው የተቀበሏቸው ፡፡ ነዋሪው የወደደው ግን ግለሰቦቹን ወይም የቲም ለማ ቡድንን እንጂ ባልሰልጣናቱ የቆሙበትን ድርጅት ጭምር አይደለም ፡፡ ድርጅታቸው የሰራውን ተግባር ዋጋ ለመስጠት አልፈለገም ፡፡ የዚህ አይነተኛ መገለጫ ደግሞ ከኢህዴድ ባንዲራ ይልቅ የኦነግ መለያ አዳራሹን ማጥለቅለቁ ነው ፡፡

በወቅቱ ባለስልጣናቱ ምን ያህል እንደተገረሙ ወይም ምን እያሰቡ እንደሆነ ማወቅ ቢቻል እንዴት መልካም ነበር ብዬ አስቤ ነበር ፡፡ ግን ስሜታቸውን ደብቀው ወይም ተቆጣጥረው መውጣት ችለዋል ፡፡ አንዳንዶች ይህ ጉዳይ ሜኔሶታ የተፈጸመው ኦነግ ለበርካታ አመታት የፓለቲካ ድልድዩን በእያንዳንዱ ሰው አካል ላይ መገንባት ስለቻለ ነው ይሉ ይሆናል ፡፡ አሁን በቅርቡ እንኳ ኦ ኤም ኤን አዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ ባዘጋጀው ዝግጅትም ላይም የኦነግ ባንዲራ ግዘፍ ነስቶ ታይቷል ፡፡ አዲስ አበባና አካባቢዋ ደግሞ ኦህዴድ እንጂ ኦነግ የፖለቲካ ድልድይ ለመገንባት እድል አልነበረውም ፡፡ ከለውጡ በፊትና በኋላም ቢሆን በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች በተካሄዱ ሰልፎች ላይ የኦነግ ምልክት በዋዛ የሚታይ አልነበረም ፡፡ ታሪካዊና ገራሚ አባባሎችን እንዲሁም ሳቅ ጫሪ መፈክሮችን ሲያውለበልብ ያየነው ህዝብ < ኦህዴድ ደማሪ ድርጅታችን ነው > ለማለት ባይደፍር እንኳ < እናመሰግለን > የሚል ባነር ከፍ ለማድረግ እጁን ምን እንደያዘው አጠያያቂ ነው ፡፡

ነገሩ ፓራዶክስ ይመስላል ፡፡ ቄሮና የፖለቲካ ድርጅቶች ከመላው ህዝብ ጋር በመተባበር ለውጡን አፋጥነውት ይሆናል ፡፡ የትግሉ መስመር በተለይ በኢትዮጵያዊነት ሃዲድ ላይ ዳግም እንዲጓዝ ያደረጉት ግን አብይና ለማ ናቸው ፡፡ የአነዚህን ሰዎች የላቀ ጥረት ዋጋ ሳይሰጡ መጓዝ ይከብዳል _ ኢትዮጵያዊነትን ቸለል ካላሉት በስተቀር ፡፡ የአንደበት ወዳጁ ህልቆ መሳፍርት የለውም ፣ በተግባር ልብ ውስጥ ያለው ማህተም ግን ንባቡ ሌላ እየመሰለ የሚከተሉትን ጥያቄዎች እንደዋዛ እንድንጠይቅ እያደረገ ነው ፡፡ ህዝቡ የምንወዳችሁ እኛ የያዝነውንም ስትወዱልን ነው እያለ ነው ? የድልድይ ሚናነት ስለተጫወታችሁ እናመሰግናለን እኛ ግን ከዚህኛው ወገን ነን እያለ ነው ? ወይስ የቲም ለማ ቡድን ነገ ከኦነግ ጋር እንዲቀላቀል በንግር / Foreshadowing / ቴክኒከ እያመላከተ ይሆን ?

ዶ/ር አብይ ዋና አላማዬ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ማካሄድ ነው ብለዋል ፡፡ መሬት ላይ የሚታየውን እውነት ተከትለን እንበይን ወይም እንገምት ካልን ማለትም ሁኔታዎች በዚሁ መልክ ከተጓዙ በኦሮሚያ የቀጣዩ ምርጫ አሸናፊ ኦህዴድ መሆኑ ያጠራጥራል / ምንም እንኳ የቲም ለማ ቡድን አባላት ወንበር ማግኘት ባይከብዳቸውም / ፡፡ ታዲያ የቡድኑ ልፋትና ጥረት ምንድነው ? ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ? ጥሩ ነው ፡፡ ግን ሽግግሩ ከኢትዮጵያዊነት ቆዳ የተሰራ ጠንካራ ኦህዴድን ለመገንባት የሚያስችል ነው ? ያጠራጥራል ፡፡ ነው ወይስ አንዳንዶች በግልፅ እንደሚሰጉት ኦህዴድ ቀስ በቀስ በህዝባዊ ማእበል እየተሸረሸረና እየተገፋ በኦነግ ሼል ውስጥ ይዋጣል ?

አንድን ሰው ከወደድክ ከነምናምኑ ነው ይባላል ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ መሰረት ፣ ለለውጡ ትልቅ ሚና የተጫወተው ኦህዴድ እውቅና ተነፍጎት የተወሰኑ መሪዎቹ ብቻ የሚወደሱ ከሆነ ድርጅቱ የአደጋ ቀጠና ውስጥ ይገኛል ማለት ነው ፡፡ የድርጅቱ አደጋ ውስጥ መውደቅ ደግሞ የራሱ ጉዳይ ተብሎ የሚታለፍ አይሆንም ፡፡ ምክንያቱም ይህ ድርጅት ለግዜውም ቢሆን አትዮጵያዊነትን በውክልና የተሸከመ ነውና ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ እሳቤ ኦህዴድ < ባለ ተራው > መንግስትም ጭምር ነው ፡፡ እና እንዴትስ ቢያደርጉ ነው ግለሰባዊ ዝናን ተሻግረው ፖለቲካዊ / ድርጅታዊ አሸናፊነትን የሚቀዳጁት ? ነገሩ ቀላል ይምሰል እንጂ የመሆን _ አለመሆን ጥያቄ አለበት ፡፡ የቀድሞው መሪ እንዳሉት ኦህዴድ ሲፋቅ ኦነግ ይሆናል ወይስ ኦህዴድ ሲፋቅ ለመላው ህዝብ አንድነት ይበጃል ?

የኦህዴድ የነገ ፈተና በፍጹም ቀላል አይሆንም ፡፡ ሳይንሳዊ ድጋፍም የሚፈልግ ጭምር ፡፡