Thursday, August 9, 2018

የኦሕዴድ የነገ ፈተና ...




ስልጣኑ ያለው ኦህዴድ ውስጥ ነው ፤ ኦሮሚያ ልብ ውስጥ ግን ኦነግ ከፍ ብሏል ፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ለዶ/ር አብይ አህመድ ፣ ለአቶ ለማ መገርሳና ለቲም ለማ ከፍተኛ ፍቅርና አክብሮት አለው ፡፡ ማሳያዎቹ ብዙ ናቸው ፡፡ ለምሳሌ በርካታ የሜኔሶታ ነዋሪ የሆኑ ኦሮሞዋች ሁለቱን መሪዎች በላቀ ደስታና የጀግንነት ስሜት ነው የተቀበሏቸው ፡፡ ነዋሪው የወደደው ግን ግለሰቦቹን ወይም የቲም ለማ ቡድንን እንጂ ባልሰልጣናቱ የቆሙበትን ድርጅት ጭምር አይደለም ፡፡ ድርጅታቸው የሰራውን ተግባር ዋጋ ለመስጠት አልፈለገም ፡፡ የዚህ አይነተኛ መገለጫ ደግሞ ከኢህዴድ ባንዲራ ይልቅ የኦነግ መለያ አዳራሹን ማጥለቅለቁ ነው ፡፡

በወቅቱ ባለስልጣናቱ ምን ያህል እንደተገረሙ ወይም ምን እያሰቡ እንደሆነ ማወቅ ቢቻል እንዴት መልካም ነበር ብዬ አስቤ ነበር ፡፡ ግን ስሜታቸውን ደብቀው ወይም ተቆጣጥረው መውጣት ችለዋል ፡፡ አንዳንዶች ይህ ጉዳይ ሜኔሶታ የተፈጸመው ኦነግ ለበርካታ አመታት የፓለቲካ ድልድዩን በእያንዳንዱ ሰው አካል ላይ መገንባት ስለቻለ ነው ይሉ ይሆናል ፡፡ አሁን በቅርቡ እንኳ ኦ ኤም ኤን አዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ ባዘጋጀው ዝግጅትም ላይም የኦነግ ባንዲራ ግዘፍ ነስቶ ታይቷል ፡፡ አዲስ አበባና አካባቢዋ ደግሞ ኦህዴድ እንጂ ኦነግ የፖለቲካ ድልድይ ለመገንባት እድል አልነበረውም ፡፡ ከለውጡ በፊትና በኋላም ቢሆን በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች በተካሄዱ ሰልፎች ላይ የኦነግ ምልክት በዋዛ የሚታይ አልነበረም ፡፡ ታሪካዊና ገራሚ አባባሎችን እንዲሁም ሳቅ ጫሪ መፈክሮችን ሲያውለበልብ ያየነው ህዝብ < ኦህዴድ ደማሪ ድርጅታችን ነው > ለማለት ባይደፍር እንኳ < እናመሰግለን > የሚል ባነር ከፍ ለማድረግ እጁን ምን እንደያዘው አጠያያቂ ነው ፡፡

ነገሩ ፓራዶክስ ይመስላል ፡፡ ቄሮና የፖለቲካ ድርጅቶች ከመላው ህዝብ ጋር በመተባበር ለውጡን አፋጥነውት ይሆናል ፡፡ የትግሉ መስመር በተለይ በኢትዮጵያዊነት ሃዲድ ላይ ዳግም እንዲጓዝ ያደረጉት ግን አብይና ለማ ናቸው ፡፡ የአነዚህን ሰዎች የላቀ ጥረት ዋጋ ሳይሰጡ መጓዝ ይከብዳል _ ኢትዮጵያዊነትን ቸለል ካላሉት በስተቀር ፡፡ የአንደበት ወዳጁ ህልቆ መሳፍርት የለውም ፣ በተግባር ልብ ውስጥ ያለው ማህተም ግን ንባቡ ሌላ እየመሰለ የሚከተሉትን ጥያቄዎች እንደዋዛ እንድንጠይቅ እያደረገ ነው ፡፡ ህዝቡ የምንወዳችሁ እኛ የያዝነውንም ስትወዱልን ነው እያለ ነው ? የድልድይ ሚናነት ስለተጫወታችሁ እናመሰግናለን እኛ ግን ከዚህኛው ወገን ነን እያለ ነው ? ወይስ የቲም ለማ ቡድን ነገ ከኦነግ ጋር እንዲቀላቀል በንግር / Foreshadowing / ቴክኒከ እያመላከተ ይሆን ?

ዶ/ር አብይ ዋና አላማዬ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ማካሄድ ነው ብለዋል ፡፡ መሬት ላይ የሚታየውን እውነት ተከትለን እንበይን ወይም እንገምት ካልን ማለትም ሁኔታዎች በዚሁ መልክ ከተጓዙ በኦሮሚያ የቀጣዩ ምርጫ አሸናፊ ኦህዴድ መሆኑ ያጠራጥራል / ምንም እንኳ የቲም ለማ ቡድን አባላት ወንበር ማግኘት ባይከብዳቸውም / ፡፡ ታዲያ የቡድኑ ልፋትና ጥረት ምንድነው ? ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ? ጥሩ ነው ፡፡ ግን ሽግግሩ ከኢትዮጵያዊነት ቆዳ የተሰራ ጠንካራ ኦህዴድን ለመገንባት የሚያስችል ነው ? ያጠራጥራል ፡፡ ነው ወይስ አንዳንዶች በግልፅ እንደሚሰጉት ኦህዴድ ቀስ በቀስ በህዝባዊ ማእበል እየተሸረሸረና እየተገፋ በኦነግ ሼል ውስጥ ይዋጣል ?

አንድን ሰው ከወደድክ ከነምናምኑ ነው ይባላል ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ መሰረት ፣ ለለውጡ ትልቅ ሚና የተጫወተው ኦህዴድ እውቅና ተነፍጎት የተወሰኑ መሪዎቹ ብቻ የሚወደሱ ከሆነ ድርጅቱ የአደጋ ቀጠና ውስጥ ይገኛል ማለት ነው ፡፡ የድርጅቱ አደጋ ውስጥ መውደቅ ደግሞ የራሱ ጉዳይ ተብሎ የሚታለፍ አይሆንም ፡፡ ምክንያቱም ይህ ድርጅት ለግዜውም ቢሆን አትዮጵያዊነትን በውክልና የተሸከመ ነውና ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ እሳቤ ኦህዴድ < ባለ ተራው > መንግስትም ጭምር ነው ፡፡ እና እንዴትስ ቢያደርጉ ነው ግለሰባዊ ዝናን ተሻግረው ፖለቲካዊ / ድርጅታዊ አሸናፊነትን የሚቀዳጁት ? ነገሩ ቀላል ይምሰል እንጂ የመሆን _ አለመሆን ጥያቄ አለበት ፡፡ የቀድሞው መሪ እንዳሉት ኦህዴድ ሲፋቅ ኦነግ ይሆናል ወይስ ኦህዴድ ሲፋቅ ለመላው ህዝብ አንድነት ይበጃል ?

የኦህዴድ የነገ ፈተና በፍጹም ቀላል አይሆንም ፡፡ ሳይንሳዊ ድጋፍም የሚፈልግ ጭምር ፡፡


No comments:

Post a Comment