Saturday, January 18, 2014

የቴዲ አፍሮ አዝመራ ...

 


ለእኔ ቴዲ አፍሮ የቲፎዞ ግፊያ ወይም የአጋጣሚ አውሎ ንፋስ ድንገት እሽኮኮ አድርጎት ከፍ ካለው ማማ ላይ ከሰቀለው በኃላ ሳያጣራ ለማድነቅ ወይም ለመውቀስ በሚቸኩለው የትየለሌ አበሻ ዘንድ እልልታን በወደቀ ዋጋ የሸመተ ሰው አይደለም ። ቴዲ አይን ፣ ህሊናና ልቦና ተነጣጥለው ሳይሆን ተዛምደው በሚያዩትና በሚሰማቸው ጥልቅ ትዕይንት የሚመሰጡበትና የሚደነቁበት የጥበብ ማሳ ነው ።
ማሳው ቸልተኛና ቀሽም አርሶአደር ባወጣው ያውጣው ብሎ እንደሰራው ጎስቌላ መሬት የተመሰቃቀለ ምስል የሚታይበት አይደለም ። ማሳው ሰልፍ ማሳመር እንደሚችሉት የሩቅ ምስራቅ ወታደሮች ህብርና ከቃላት በላይ መግለጫ የሚፈልግ ውበት ተሰናስሎ የሚታይበት ክቡር ኪናዊ መድረክ ነው ። ማሳው ጥልቀት ባላቸው የግጥም ሀሳቦችና ሸናጭ ዜማዎች ውህደት ምናብ ሰራቂ እንቅስቃሴዎች የሚታይበት መስክ ነው ።
አዝመራው በስልጡኑ ገበሬ ቴዲ ሲፈልግ ለሙዚቃ የሚሆን ገብስ ፣ ሲፈልግ ለመጽሀፍ መድብል የሚያገለግሉ ስንኞች ተዘርቶ የበቀለበት ነው ። ይህ አዝመራ እንደሌሎች የኪነት ገበሬዎች ገጣሚ ተፈልጎ ስንኝ እስኪመተርና የዜማ አድባር እስኪለመንበት ድረስ በአረም የሚሞላና በከብቶች ኮቴ የሚደፈር አይደለም ። ይህ አዝመራ እንደ ብዙዎቹ የሀገራችን ምስኪን የኪነት ገበሬዎች የሰማይን ዝናብ ጠብቆ በአመት አንዴ ብቻ የሚዘራበት አለመሆኑ ሌላኛው መገለጫው ነው ። የቴዲ አዝመራ ወቅታዊና አስቸኴይ ጉዳዮች ሲፈጠሩ በተሰጥኦ ቅመም የተሰራውን የምርጥ ግጥምና ዜማ እንክብል ውጦ የፌሽታ ፈንዲሻን እነሆ በረከት የሚል ነው ።
ሁሌም ባለመስመር ፣ ሁሌም በንፋስ ኮርኴሪነት ደፋ ቀና እያለ የሚያባብል ፣ ውርጭና ዶፍ  ቢያስቸግረው እንኴን እንደ ሱፍ አበባ ብርሃንና ፍቅርን የሚከተል ነው ።
ይህ ማሳ በመስመር እንደተዘራበት ሰብል ደስ ይላል የሚባልበት ብቻ አይደለም ። ማሳው ላይ የሰርከስ ኦርኬስትራ ልዩ ልዩ ብልሃቶችንና ጥበቦችን የሚያንጸባርቁበትም እንጂ ። ለቢራ የደረሰው የገብስ አዝመራ አስካሪነቱን ብቻ ሳይሆን አዝናኝነቱንም ለምግብነት ከበቀለው ገብስ ጋር ተወያይቶ የሚግባበት የፍቅርና የመቻቻል ገመድ አለው ። ለብዙ ጥቅም የሚውለው የስንዴ አዝመራ በልምድ አናሳ ግምት የተሰጠውን የጔያ ሰብል የሚያገልበት ወይም የባቄላውን አዝመራ « ፈሳም » እያለ የሚያሸማቅቅበት ምዕራፍ የለውም ።
ነጭ ጤፍን የሀብታም ወይም የባለግዜ ቦለቄውን የድሃ ወይም የተጨቌኝ ተወካይ በማለት እያላገጠ የሚያሽካካበት ግዜም ያጥረዋል ። የአዝመራው መስመር በነጠላ መስመር ብቻ ያልተዘረጋውም አንድም ከዚህ አኴያ ነው ። የሰብሎችን ህብርና ስብጥር በልዩ ልዩ ቅርጾች እየወከለ፣ እየገለጠ የሚታይ የኦርኬስትራው ወይም የሰርከሱ መሪ መድብል ነው ።
የቴዲ አዝመራ ደርሶ ሲበላ የመጨረሻ ግቡ በ « ጥጋብ » ደስታን መፍጠር አይደለም ። ፈጣን ምናብ ያለው ገና እህሉን እያላመጠ ፣ ቆይቶ የሚገባውደግሞ በስተመጨረሻም ቢሆን ይሄ ምግብ ከምን ተሰርቶ እንዴት ሊጣፍጥ ቻለ ? እንዴት አንጀትን ያርሳል ? እያለ እንዲያንሰላስልና ብዙ እንዲጠይቅ ማድረጉ ነው ። አዝመራው ፍቅርና ሰላምን ፣ መቻቻልና ብሄራዊ እርቅን ፣ የሃይማኖትና ፖለቲካ እኩልነትን ፣ ፍትሃዊነትንና ሰብዓዊነትን ፣ ቅንነትንና ጀግንነትን በጣም በተኴለና ወጣ ባለ መንገድ ለምናብ አድራሽ ነው ።
ስር በሰደደ ሙያዊ እውቀትና ፍቅር የተያዘው የቴዲ አዝመራ ከአመት አመት የሚሰጠው ምርት እያደገ የመምጣቱን ያህል አፈንጋጭነቱና ልዩ አተያዩ አለርጂ የፈጠረባቸው ግለሰቦችና ቡድኖች በሚገኘው ጠባብ የስህተትም ሆነ የመዘናጊያ ቀዳዳ ሾልኮ በመግባት አንካሴያቸውን ከመወርወር ተቆጥበው አያውቁም  ። እናም አሁንም ለብዙ ግዜኛ መሆኑ ነው ሰብሉ ላይ ልክ እንደ ነጭ ርግብ የተምች ፣ ነቀዝና ፌንጣ ሰራዊት አንገታቸው እየተሳሙ ተለቀዋል ።
በርግጥ መቼ ይሆን በፍቅር አረዳድ ራሳችንን የምንችለው ?
አዝመራው ግን ውርጭና ዶፍ ቢያስቸግረውም እንደ ሱፍ አበባ ብርሃንና ፍቅርን የሚከተል ነው ...


 

Thursday, January 9, 2014

« ግልጽነት የሚሻው ግልጽ ደብዳቤ »


አቶ ግርማ ካሳ ሰሞኑን በዘ ሀበሻ ድረ ገጽ ላይ  « ግልጽ ደብዳቤ ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም » የሚል ጦማር ጽፈው አንብበናል ። የደብዳቤው ዋና አላማ በ 2007 ዓ.ም ለሚደረገው ብሄራዊ ምርጫ አንድነት የተባለው ድርጅት በተለይም ከመድረክ ፣ መኢአድ ፣ አረና ፣ ኢዴፓና ሰማያዊ ፓርቲዎች ጋር ውህደት ፈጥሮ ስልጣን በቃኝ የማያውቀውን ድርጅት መታገልን ይመለከታል ።

በርግጥ ግልጹ ደብዳቤ ያስፈለገው የተቃዋሚዎችን ዳግማዊ የአንድነት ትንሳኤ አስረግጦ ለማሳየት ነው ወይስ ለምልጃነት የሚል ገራገር ጥያቄ በእግረ መንገድ ካነሳን ምላሹ የኃለኛው ሃሳብ ሆኖ እናገኘዋለን ። እዚህ ላይ ነው እንግዲህ « ግልጽነት የሚሻው ግልጽ ደብዳቤ » የሚል የመጻፊያ ርእስ ድንገት ብቅ የሚለው ። ፕሮፌሰር መስፍን በኢህአዴግ ዘንድ እጅግ የሚፈራውና የተገለለውን የይቅርታ መንፈስ በሀገሪቱ ዳመና ላይ ለማርበብ ወይም በፖለቲካው አጠራር የብሄራዊ እርቅን አጀንዳ ደጋግሞ ርእሰ ጉዳይ በማድረግ ወደ ተጨባጭ ምዕራፍ ለመለወጥ የተጉ ምሁር መሆናቸው ይታወቃል ። ይህንንም በሚያደርጉት ንግግር ብቻ ሳይሆን ያሳተሟቸውን በርካታ መጽሀፍት በማንበብም መረዳት ቀላል ነው ።

አጠያያቂው ጥያቄ ፣ አቶ ግርማም እንደነገሩን ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ሰማያዊ ፓርቲን ከመሰረቱት አንደኛው በመሆናቸውና የመጀመሪያውም መሪ ስለነበሩ « ግልጹ ደብዳቤ » ሌላው ቢቀር ያለ ግልባጭ ቀጥታ ለእሳቸው የመጻፉ ነገር ነው ። በአሁኑ ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መሆናቸው ይታወቃል ። ይህ ደብዳቤ መጻፍ የነበረበት ቀጥታ ለወቅታዊው የፓርቲው አመራር ወይስ ወደጎን ለቀድሞው ቁልፍ ሰው ?

ይህም ጥያቄ ሌላ ጥያቄ ይወልዳል ። አቶ ግርማ ፓርቲውን አነጋግረው ጥሩ ምላሽ አላገኙም ማለት ነው ? ከሆነ የጻፉት ግልጽ ደብዳቤ እስከሆነ ድረስ ለአንባቢው ይኀው የኃላ ታሪክ መገለጽ ነበረበት ። ርግጥ ነው አቶ ግርማ ውስጥ ያለውን ነገር ሊነግሩን ባይፈልጉም የግልጹ ደብዳቤ አንዳንድ ሀረጎች በራሳቸው ችግር መኖሩን እየጮሑ የሚያሳብቁ ናቸው ።

አቶ ግርማ ፈገግ ብለው አሉ ።

1 . « የሰማያዊውን ነገር በርስዎ ጥዬዋለሁ ። ያሳምኗቸውና ያግባቧቸው ዘንድ እጠይቃለሁ »

አቶ ግርማ ኮስተር ብለው አሉ ።

2 . « ምክርዎትን አልሰማ ብለው የተናጥል ጉዞ ከቀጠሉ ምርጫው የእነርሱ ይሆናል »  ጥርሳጨውን እያንቀጫቀጩና ሳይታወቃቸው ጠረጤዛ እየደለቁ ... « ጉዳዩ የፌዝና የቀልድ ወይንም የግለሰቦች ተክለሰውነት የመገንባት ሳይሆን የአገር ህልውናና ደህንነት ነው ... »  በማለት ቀጠሉ ።

ልብ በሉ አምስት ሳንቲም አላጋነንኩም ። ያደረኩት የአቶ ግርማ ቃላቶች ደምና ስጋ እንዲለብሱ ማድረግ ነው ወይም ቃላቶቹ የሚወክሉትን አካላዊ እንቅስቃሴ አስደግፎ ማቅረብ ብቻ ነው ። ታዲያ እንዴት ነው ጎበዝ ማነው እያፌዘና እየቀለደ ያለው ? እረ ማነው ፖለቲካን ለተክለ ሰውነት መገንቢያ ጥቅም እያዋለ የሚገኘው ? የሚሉ ጥያቄዎች ውስጣችን እየተንጫጫ እንዴት ነው ሆዳችንን የማይቆርጠን ... ለዚህም ነው ግልጹ ደብዳቤ ሊነግረን ያልፈለገው ወይም የደበቀን ነገር በመኖሩ የግልጽነቱን አላማ ስቷል የሚያስብለው ።

 አንባቢ « ነገርን ከስሩ ውሃን ከጥሩ » ብሎ ይመረምርና ይታዘብ ዘንድ በቂ የመረጃ ትጥቅ ሊኖረው ይገባል ። አቶ ግርማ እንዳሉት የማስታረቅና የመሸምገል ልምድ ያላቸው ፕሮፌሰር መስፍን በተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ያለውን ጠባብም ሆነ ቦርቃቃ ልዩነት ከምን ተነስተው ምን ደረጃ ላይ አደረሱት ? የሚል ምናባዊ ቢጋር አዘጋጅቶ እንዲንቀሳቀስም ይረዳው ነበር - አንባቢው ። ግና ቢጋሩ እንዳይነደፍ ግልጹ ደብዳቤ ውስጥ unግልጽ የሆኑ እንክርዳዶች መንገድ ዘግተዋል ።

ነገር ሰነጠቅክ አትበሉኝ እንጂ ደብዳቤው ውስጥ የኢህአዴግን የመሰለ « ረጅም ሪሞት ኮንትሮል » የተመለከትኩ መስሎኛል ። በመጀመሪያ ለዚህ ጽሁፍ ዓላማ የተዘጋጀውን « ሪሞት ኮንትሮል » ብያኔ እንስጠው ።

ሀ . የተለየ ትርጉም ካልተሰጠው በስተቀር በዚህ ጽሁፍ ውስጥ « ሪሞት ኮንትሮል » ማለት ገባ ወጣ የማይል የህንድ ፊልም አክተር ማለት ነው ። የህንድ ዋና አክተር በገጀራ አንገቱ ቢከተከት ፣ በላውንቸር ጥይት ደረቱ ቢቦደስ ለግዜው ቢደማ ፣ ለግዜው ቢሰቃይ እንጂ በፍጹም አይሞትም ። የህንድ አክተር እንደ ፈጣሪ በሶስተኛው ቀን ባይሆንም እንደ እባብ ከሞተ በኃላ አፈር ልሶ በመነሳት ተመልካቹን ጉድ የማሰኘት አቅም አለው ።

የኢህአዴግ ህንዳዊ አክተር የሆነት አቶ መለስ ይኀው ሞተውም ቢሆን ሀገር እየገዙ ፣ ሰራዊት እያዘዙ ፣ ቦንዳዊ መልዕክታቸውን ከሚያማምሩ ጥቅሶች ጋር እያስተላለፉና « ሌጋሲ » የተባለ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማቸውን እያዘጋጁና እየተወኑ ናቸው ። በሪሞት ኮንትሮል ። ብዙ ግዜ ታዲያ የህንድ ፊልም ተመልካች የአክተሩን ልዩ ተግባር እያደነቀ መመሰጥና ማጨብጨብ እንጂ ለምንና እንዴት በሚሉ ገሪባ ጥያቄዎች መጨናነቅ አይፈልግም ። እናም ኢህአዴግ ማለት በአራት ጎሳዎች ውህደት የተሰራ ድርጅት ነው የሚለው ትምህርት እንዴት እንደተደለዘ ሳይታወቅ ኢህአዴግ ማለት መለስ መሆኑ ከተረጋገጠ ቆየ ።

ታዲያ በአቶ ግርማ ደብዳቤ ውስጥ የታየው ሪሞት ኮንትሮል ምንድነው ? ከተባለ ነገሩን ከኢዴፓ ለመጀመር ይቻላል ። ኢዴፓን ለረጅም ግዜ የመሩት አቶ ልደቱ አያሌው ፖለቲካ ርስት አይደለም በማለት ከሳርና ስፖንጅ የተሰራውን ወንበራቸውን ለምክትላቸው ለአቶ ሙሼ ሰሙ ማስተላለፋቸው ይታወሳል ። በሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ሳይሆን በሶስተኛ የፍልስፍና መንገድ የሚታወቁት አቶ ልደቱ ከፖለቲካ ርቀው በቅርቡ ወደ መዶለቻው ሰፈር /ፖለቲካ / መቀላቀላቸውን በዜና ሰምተናል ። አቶ ግርማ ለግልጽ ደብዳቤያቸው ማጠናከሪያ ይሆን ዘንድ « አቶ ልደቱ አያሌው ለአድማስ ጋዜጣ በሰጡት አስተያየት ኢዴፓ ከአንድነት ጋር አብሮ ለመሆን የመፈለግ አዝማሚያ ሳይኖረው እንደማይቀር አስባለሁ » ብለው ጽፈዋል ። ልብ አድርጉ ባለሙሉ ስልጣኑን አቶ ሙሼን አይደለም የገለጹት - ከጨዋታው የራቁ የመሰሉትን አምባሰደር ልደቱን እንጂ። እዚህ ሀሳብ ውስጥ የህንድ አክተርም በሉት ሪሞት ኮንትሮልን እንደ ቀጭኔ አንገቱን አስግጎ አልታያችሁም ?

ሁለተኛው ሪሞት ኮንትሮል ራሱ ሰማያዊ ፓርቲ አካባቢ የሚሸት ነው ። አቶ ግርማ « የርስዋ ድርጅት ሰማያዊ ፓርቲ ሀገር ቤት ጥሩ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ድርጅቶች ከጥቂቶቹ መካከል አንዱ ሆኗል » በማለት ነበር ለፕሮፌሰሩ የሚገልጹት ።

ኃይለ ቃል ፣ የርስዎ ድርጅት

ምዕራፍ አንድ ፣ አሁን የአመራር አባል ላልሆነ ሰው እንዲህ እንዲገለጽ የቌንቌ / ሰዋሰው /  ስርዓታችን ይፈቅዳል ?

መካከለኛ ምዕራፍ ፣ የርስዎ ደርጅት የሚለው አነጋገር በጣም ለማጠጋጋት እንደሚያስቸግር ቁጥር ከመሃል ዝቅ ብሎ የወረደ ቢሆንም ድሮ የመሰረቱት ለማለት ተፈልጎ ነው ብለን ብናፏቅቀው ምን ያህል ያስኬደናል ?

መደምደሚያ ፣ የርስዋ ድርጅት ማለት ሳናጠጋጋው እረ እንደውም ከሩቅ በሪሞት ኮንትሮል ብንነካካው ትርጉሙ አሁንም ከጀርባ ሆነው የሚመሩት ማለት ይሆን ?


የገምጋሚው ማስታወሻ ፣ ግልጽነት ሳይቀድም ይቅር ለእግዚአብሄር መባባል ትርጉም ያጣል ። የግልጽነትን ድልድይ ሳይረግጡ ከአንድነት ቅጥር ግቢ መድረስ ያስቸግራል ። ደብዳቤውም ግልጽነት ያንሰዋል ። በደብዳቤው እንድንግባባ ተጨማሪ የማፍታታት ስራ እንዲሰሩ ይነገራቸው ። በቂ ነው ብለው ካሰቡ ግን ላጺስ ከኢህአዴግ ተውሰው ርዕሱን በአስቸኴይ ይደልዙት ። ለባለይዞታው ይመለስ ብለናል ።