Tuesday, July 16, 2013

ጥርስ የሚፍቁ መስሪያ ቤቶች



1 . ‹‹ እንደ ተቋም ጥፋት ስላጠፋን ይቅርታ እንጠይቃለን ›› የሚለው መግለጫ የሚጠበቅ ስለነበር የሚያስገርም አልሆነም ፡፡ አስገራሚ የሆነው የሚጠበቀው መፍትሄ ሊፈታ ያልቻለ እንቆቅልሽ መሆኑ ነው ፡፡ የተጎዳውን ህዝባዊ ስሜት ለመጠበቅ ከሞራልና ህግ አንጻርም ሊሰራበት ያልተቻለን ስልጣንን ለሚሰራ አካል ማስረከብ ግድ ነውና አመራሩ ለራሱ ቀይ ካርድ እንደሚያሳይ ተጠብቋል ፡፡
ግን አልሆነም ፡፡

‹‹ ሁለት ቢጫ ማየት በምንያህል ተሾመ ይብቃ ! ›› ሲል የአቋም መግለጫውን አሰማ ፡፡ ይህ መግለጫ ደረቅ አይሆን ዘንድም ጥቂት የእግር ኳሱና የአመራሩ አባላት በጥፋተኝነት ቅባት እንዲዋዙ ተደረገ ፡፡ የፌዴሬሽኑ አመራር አካላት በህዝብ ለቀረበላቸው የልቀቁ ጥያቄ ‹‹ በክረምት ቤት አይገኝም ! ›› በሚል ሰበብ ለራሳቸው የወራት እድሜን ጨምረዋል ፡፡ በውስጣቸው  ግን  ‹ ይህ ስልጣን በመልቀቅ ሀብታም የሆነው የአውሮፓ ፌዴሬሽን አይደለም ! › ማለታቸው ይገመታል ፡፡

መቼም ይህ ፌዴሬሽን እንደ ሁላችንም ጨዋታ ተመልካች እንጂ መንገድ አመላካች አልሆነም ፡፡ ምንም ስራ እንደሌለበት ፊውዳል ክቡር ትሪቡን ላይ ቁጭ ብሎ ጥርሱን እየፋቀ ይባስ ብሎ ግራና ቀኝ ሰው መኖሩን በመዘንጋት የቆሸሸ ምራቁን ጢቅጢቅ .. በማድረጉ ስንቱን የዋህ ህዝብ ለማዲያትና ለጨጓራ በሽታ ዳረገ ?

2 . አንድ ሰሞን ከነዳጅ መውጣትና መውረድ ጋር ተያይዞ የትራንስፖርት ታሪፍን ለህዝቡ ይገልጽ ነበር ፡፡ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን ድሃዋ አዲስ አበባ በሚያስገርም ሁኔታ ሀብታም ፎቆችን ሳይቀር ማፈራረስ ይዛለችእግረ ጠባቦቹም ሆኑ ሰፋፊዎቹ መንገዶቿ አዲሱን ሰርገኛ ለማስተናገድ በመፈራረስ ሽርጉድ አብዝተዋል ፡፡

ይህ ያልተጠበቀ ግርግር የአዲስ አበባ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮን ያደናገረው ይመስላል ፡፡ አምስትና አስር ሳንቲም መጨመር የሚቻለው በእኔ እውቅና ነው ይል የነበረው ይኀው ተቋም ዛሬ ታክሲዎች 1 . 35 መንገድን 2 . 70 2 .70 መንገድን 3 . 70 በገዛ ፍቃዳቸው ሲያስገቡ ስልጣኑን ማስጠበቅ አልቻለም ፡፡ ለአብነት ያህል ከጦር ኃይሎች /ፍርድ ቤት በልደታ አድርጎ ሜክሲኮ በመድረሱ ብቻ ዋጋው መቶ ፐርሰንት መድረሱ በእጅጉ የሚያስገርም ሆኗል ፡፡

በዚህ ሁሉ የህግ ጥሰትና ዘረፋ መካከል ቢሮው ጋቢ ደርቦ ቁጭ ብሏል ፡፡ ከሶማሌ ባስመጣው ረጅም መፋቂያ ጥርሱን ደጋግሞ እየፈተገ ከራሱ ጋር እሰጥ አገባ ይዟል  ‹‹ ምን ይደረግ ታዲያ ! የልማት ጉዳይ ነው ፡፡ መንገድ በሌለበትስ ታሪፍን እንዴት ከፍና ዝቅ ማድረግ እችላለሁ ? ››
ከደረበው ጋቢ ይሁን ከግድየለሽነቱ ከመብራት ኃይል ቀጥሎ የላቀ የቸልተኝነት ኃይል እያመነጨ ይገኛል ፡፡ ይኀው ቸልታው ግን  ‹ እንኳን እናቴ ሞታ ድሮም አልቅስ አልቅስ ይለኛልየሚለውን የከተማ ነዋሪ ለጉዳት እየዳረገው ነው ፡፡ አዲሱ ሰርገኛ የሚመጣው ከሁለትና ሶስት ዓመታት በኃላ በመሆኑ ይህ ቢሮም እስከዛ ድረስ የአፉን መደገፊያ ላይጥል ነው ማለት ነው :: እስከዛ ድረስ ለሚደርሰው ብዝበዛ ማን እንደሚጠየቅ ለጸረ ሙስና ወይም ለእንባ ጠባቂ ግልባጭ ማድረግ ሳያስፈልግ አይቀርም ፡፡

3 .ገንዘብ በመቆጠባችሁ ብቻ እሸልማለሁ ማለት ከጀመረ አመታት አሳለፈ ፡፡ ስልቱም የልማት አጋር ብቻ ሳይሆን የአዲስ አሰራር መንገድ መሆኑን
ነግሮናል ፡፡

ኬር ! ብለናል ፡፡

አዲስና ዘመናዊ መንገድ ብሎ ካስተዋወቀን አሰራር ውስጥ ኤቲኤም ይገኝበታል ፡፡ ይህ ካርድ የተሰጠን ግዜ ላላፊው አግዳሚው ብቻ ሳይሆን ለራሳችንም አስር ግዜ ከኪሳችን መዥለጥ እያደረግን አስኮምኩመነው ነበር ፡፡

መሰለፍ ድሮ ቀረ ብለናል ፡፡
ብር እንደ አበሻ ጎመን ከቅርባችን ሊቀነጠስ ነው ብለናል ፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህ ማሽኖች በአጭር ግዜ ውስጥ በበሽታ ማስነጠስ ጀመሩ ፡፡ ቀስ በቀስም የሚከበሩ ዋንጫዎች ሳይሆኑ ባዶ ቆርቆሮ መሆናቸውን አስመሰከሩ ፡፡ እንደ ወንድማቸው የመንገድ ስልክ የነሱንም ወገብ በፍልጥ የሚነርት በዛ ፡፡ የአራዳ ልጆች አናታቸውን ከፈት አድርገው ቆሻሻ ይጥሉበት ነበር ፡፡ ይህ ከመሆን ለጥቂት የተረፈው ቆርቆሮዎቹ የቆሙት ጥበቃ ያለበት አካባቢ መሆኑ ነው ፡፡ አልፎ አልፎ የሚሰሩት ደግሞ ሰው ብር በሚፈልግበት ቅዳሜና እሁድ ለጥቂቶች አገልግለው ጎተራቸው ባዶ መሆኑን ያውጃሉ ፡፡
የታመመውን ዘመናዊነት መታደግ የደከመው የኢትዮጽያ ንግድ ባንክ ነው እንግዲህ በአናቱ ላይ ስለ ቁጠባ ሳያሰልስ የሚጨቀጭቀን ፡፡ አንዳንዶች ዘወትር ለስራ የሚጠቀሙትን አንዳንዶች ወር ጠብቀው የሚያገኙትን ደመወዝ ለመቀበል ሲሄዱ ‹‹ እንኳን ደህና መጣችሁ ! ›› የሚለው ትሁት ቃል አይጠብቃቸውም ፡፡ ደንበኛን የማያስቀይመው ንግድ ባንክ ግን ተመሳሳይ ቃል አመንጭንቷል ፡፡

‹‹ ኮንኬሽን የለም ! ›› የሚል
‹‹ ዛሬም ?! ››
‹‹ ምን እናድርግ ? ቴሌ እኮ ነው ?! እጀ ሰባራ አደረገን ! ››
‹‹ ታዲያ ሌላ አማራጭ የለም ? ››
‹‹ ምን ይምጣ ? የለም ! ››
‹‹ ወይ ጌታዬ ምን ይሻል ይሆን ? ››
‹‹ ሌላ ቀን ብቅ ማለት ወይ እስኪመጣ መጠበቅ ነዋ ! ››
‹‹ መቼ ይመጣ ይሆን ? ››
‹‹ እንጃ ! ቴሌም አያውቀው ! ››

ስለ ዘመናዊነት የሚያወራው ባንክ ስራውን ከቴሌ ጋር በጋራ ተስማምቶና ተነጋግሮ እንደጀመረ ይገመታል ፡፡ ግን ጉልቤው በየቀኑ ሲቆነጥጠውና ሲያሸው ሊታገለው ሊቃወመው ሊገስጸው አልደፈረም ፡፡ ስለዚህ ብር አስቀማጩ ባንክ አስር አለቃ የአየሩ አክሮባቲክስ ቴሌ ኮሎኔል መሆናቸውን ለመገመት እንገደዳለን ፡፡ ጂኔራሎቹን ያው መገመት ይቻላል ፡፡
በዚህም ምክንያት አዳራሽ የሞሉት ባለከራባት ሰራተኞች ወንበር ላይ ተለጥጠው ጣራ የነካ ብር ተደግፈው ጥርሳቸውን መፋቅ ይጀምራሉ ፡፡ ትዕግስተኛው ህዝባችን ደግሞ ከመስታውቱ ጀርባ እጅብ ብሎ አፋፋቃቸውን በጥብቅ ይመለከታል ፡፡

‹‹ አለ መፋቂያ ! መፋቂያ  ! … የክትክታየቀረሮየዋንዛ
  የሚያሳምር  … የሚያወዛ ››

የሚል ድምጽ ስማ ስማ አለው ጆሮዬን ::

No comments:

Post a Comment