Tuesday, June 11, 2013

No Dam , No Victory !‎




‹‹ No Money , No Funny ! ››  ሲሉ ነበር ፈረንጆቹን የምናውቃቸው ፡፡ የሙርሲ ሀገር ሰዎች ደግሞ ‹‹ No Nile , No Egypt ! ›› የሚል መዝሙር  ማቀንቀን  ጀምረዋል ፡፡ ይህን ፈሊጣዊ አባባል በጓድ መንግስቱ ዘመን ብንቃኘው ‹‹ እናት ሀገር ወይም ሞት ! ›› ወይም ‹‹ ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር ! ›› የሚል አቻ ምንዛሪ እናገኝበታለን ፡፡

በውስጥ ችግሮች የተጠላለፉት የግብጹ መሪ መሀመድ ሙርሲ በሙሉ አፋቸው ‹‹ አንዲት ጠብታ ውሃ እንኳ አንፈቅድላቸውም ! ›› ብለዋል ፡፡ በጣም የሚገርመው የማይፈቀድልን ውሃ የራሳችን ንብረት መሆኑ ነው ፡፡ ነው ‹ አንዲት ጠብታ አፈር እንኳን ወደ ዉጭ እንዲወጣ አልፈቅድም › በማለት ጫማ አስወልቀው ያስጠረጉ የሀገራችንን መሪ ታሪክ ለመድገም አስበው ነው ? ይህ የተደረገው ደግሞ በሰው ሳይሆን በራስ ኀብት ነው ፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊም በአንድ ወቅት ‹‹ የአባይ ግንባታ ለአንዲትም ደቂቃ ቢሆን አይቋረጥም ! ›› ብለው ነበር ፡፡

አንዲት ጠብታ !
አንዲት ደቂቃ !

ግብግቡን አያችሁት - ማለቴ የውጥረቱን ስስነት ፡፡ መቼም በ ‹ አንፈቅድላቸውም ! › እና በ ‹ አይቋረጥም ! › መካከል እንደ አባይ ወንዝ የረዘመ የእልህ ክፍተት አለ ፡፡ እነዚህ የተንቦረቀቁ ሀሳቦች እንደምን ሊቀራረቡ እንደሚችሉ ማሰብ ለግዜው ግርታ ይፈጥራል ፡፡ እውነቱ ግን የተራራቀው አባባሉና መፈክሩ እንጂ መሬት ላይ ሊለካ የሚችለው ተጨባጭ ተግባሩ አይመስለኝም ፡፡ ምክንያቱም እንደ ግብጾች ቁጣ ከሆነ እኛ ‹ የሬሳ ማጠቢያ የሆነውን ውሃ ለለመነ አይከለከልም › የምንለውን ቅዱስ ብሂል ባለመረዳት አንዲት ኩባያ እንኳ ለጥማታችን ሊሰጡን አልፈቀዱም ፡፡ እንደ ስነ ጽሁፍ ተማሪነት ሰሙን ወደ ጎን ትተን ወርቁን የምንፈልግ ከሆነ ግን የሚሊኒየሙ ግድብ 21 ከመቶ ያህል ተከናውኗል … ተደፈርን በሚል ስሜት ደማቸውን ያንተከተከው የቅልበሳ ስራም ተከናውኗል ፡፡ አንድ አምስተኛ የተከናወነው ስራ ቀስ በቀስ አንድ አራተኛ … አንድ ሶስተኛ … የሚባለውን ስሌት ተከትሎ የግድቡ ገላ እየፈረጠመ መሄዱ አይቀርም ፡፡

ይህም ሲሆን ፉከራው ፣ ቀረርቶው ፣ ዛቻውና ውጥረቱ እየጮኀ - በዝምታ / contradictory / ይቀጥላል ባይ ነኝ ፡፡ ምክንያቱም የሚጮህ ውሻ ሁሉ ፈሪ ቢሮጥለት እንጂ እንደማይናከስ ከልምድ ይታወቃልና ፡፡ በርግጥ የግብጽ ጋዜጦች ‹ ዉሾቹ ይጮሃሉ ፣ ግመሎቹ ጉዟቸውን ቀጥለዋል › የሚል አናዳጅና ነገር አቀጣጣይ ዘገባዎችን ማፋፋማቸው ይጠበቃል ፡፡

‹ እውን ደርግ አለ ? › የሚለውን ታሪካዊና ወጥ አባባል እያስታወስን ‹ እውን ግብጾች አይናከሱም ? › የሚል በአሽሙር የተንጋደደ ጥያቄ ወርወር እናድርግ ፡፡ ርግጥ ነው ድንገት ከኃላ ተደብቆ እግር ስር የሚጮህ ዉሻ እንኳ ቀልብ ይገፋል ፡፡ በዚህም ምክንያት ከቆመ ስልክ እንጨት ጋር ሊያጋጭ ወይም በኮብልስቶን ካልተቀየረ ሹል የወንዝ ድንጋይ ላይ በደረት ሊደፋ ይችላል ፡፡ በተቃራኒው ግብጽ በቀጣይ ልታደርሰው የምትችለው ጉዳት እንደ ሶርያ ከተማ ያፈራርሰናል ብሎ ማሰብ ግን አጓጉል ስጋት ነው የሚሆነው ፡፡

እኮ ለምን ?
ከ 500 በላይ የሚደርሱት ተዋጊ አውሮፕላኖቻቸው በሶ ጨብጠዋል ?
ከ 1 ሺህ በላይ የሚቆጠሩት ተወንጫፊ ሚሳይሎቻቸው በቀፎን ተጨባብጠዋል ?
እነ ኤፍ 16 ፣ ሚግ 17 ፣ ሚግ 21 ፣ አልፋ ጄት ፣ ሚራዥ ፣  የኬሚካል ጦር መሳሪያዎቻቸው ምን ይጠብቃሉ ? መባሉ ግድ ነው ፡፡ እኮ ታዲያስ ?

1 . ለነገርም ሆነ ለአውሮፕላን መንደርደሪያነት እጠቀምባታለሁ የምትላት ሱዳን ግድቡ ጠቃሚ መሆኑን በመረዳት ለሀገራችን ድጋፏን ሰጥታለች ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አንዴ በሞሉት ነዳጅ ከ 1 እስከ 3 ሺህ ኪ.ሜ የሚጓዙት ተዋጊ ጀቶች ግድቡ ጋ መድረስ ቢችሉ እንኳን ሀገራቸው ለመመለስ አይችሉም ፡፡ ርግጥ ነው እንደ አልቃይዳ እዛው እየፈነዳን እናልቃለን ካሉ ምርጫቸው ነው ፡፡ ይህን ምርጫ ለመጠቀም ካሰቡ የኛ የቤት ስራ ገና ድንበራችን እንዳለፉ በመቃወሚያ መልቀም ነው ፡፡ የጋሽ አልበሽር ሀሳብ ነገ ሊቀየር ከቻለስ ? የሚል ስጋት ሚዛን ከደፋም መፍትሄ አይጠፋም ፡፡ ሰውየው በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት በወንጀል ስለሚፈለጉ አንጠልጥለን እንደምንሰጣቸው አስረግጠን ማስረዳት ነው ፡፡

2 . የግብጽ መንግስት ስር ነቀል ለውጥ የሚፈልገውን ህዝብና ወግ አጥባቂዎችን አስተባብሮ ለጥፋት ዓላማ ለመሰማራት ይከብደዋል ፡፡ ምንም እንኳ ህዝቡ አንድ ሆኖ በአባይ ጉዳይ እንዲያተኩር እየቀሰቀሰ ቢሆንም ፡፡

3 . ግብጽ የራሷን የችግር ቁልል ወይም ተሰርቶ የማያልቅ የቤት ስራ ገና አጽድታ አልጨረሰችም ፡፡ ግድቡን አፈራርሳለሁ የሚለው የግብጽ መንግስት በህዝባዊ ተቃውሞ ወይም ባደፈጠው ጦር ሰራዊት ሊፈራርስ አይችልም ማለት አያዋጣም ፡፡

4 . ግድቡ የግብጽንና ሱዳንን ጥቅሞች በከፋ መልኩ የማይጎዳ መሆኑን ሀገራቱን ያካተተውና የገለልተኞች ስብስብ የሆነው አጥኚ ቡድን አረጋግጧል ፡፡ ይህ ውሳኔ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ እንደ ቋሚ ህግ ወይም መመሪያ ሊያገለግል የሚችል ነው ፡፡ ህግን ጥሶ ወደ ጦርነት መግባት ደግሞ ዓለማቀፍ ውግዘትን እንጂ ድጋፍን አያስገኝም ፡፡

5 . ቢያዋጡንም ባያዋጡንም እነ ቻይና ፣ እስራኤልና አሜሪካ የኛ አጋር እንደሆኑ የመገመት ወይም የመፈረጅ አባዜ በምድረ ግብጽ እየተስፋፋ ነው ፡፡ ይህ ጉዳይ ለእኛ መልካም አጋጣሚ ለሚያስፈራሩት ደግሞ ስጋት ይፈጥራል ፡፡ በዚህ ግዜ የሚገኘውን ‹ ቲፕ › መቀበል ይጠቅማል ፡፡

6 . በታሪክ አይን ኢትዮጽያን መተናኮስ ወይም በሃይል ማስገበር ብዙ መስዋዕትነት ሊያስከፍል እንደሚችል ይታወቃል ፡፡ ስለዚህ ግብጾች ክተት ከማወጃቸው አስቀድሞ የጦርነቱን የመጨረሻ ውጤት ከወዲሁ አስልተው መነሳት ይኖርባቸዋል ፡፡

7 . በአፍሪካ ህብረት የላቀ ክብር ያገኘውን የኢትዮጽያ ጦር ሰራዊት ፣ በተመድ ዶላር ብቻ ሳይሆን ኒሻን የተከፈለውን ጦር ሰራዊት አቅም አሳንሶ ማየት የሚቻልበት አግባብ የለም ፡፡ ግዜውም አይፈቅድም ፡፡


እነዚህን የመሳሰሉ ተጨማሪ ምክንያቶችን መዘርዘር ይቻላል ፡፡ ይሁን እንጂ ግብጽ ውክልናንም ሆነ ሰላማዊ የክርክር መድረክን በመጠቀም ልትናከስ የምትችልባቸው አግባቦች አይኖሩም ማለት አይቻልም ፡፡ አንደኛው ራሳቸው እንደተናገሩት በራሳቸውም ሆነ በሌሎች የውጭ ሃይሎች የሽብር ተግባር መፈጸም ነው ፡፡ እንደውም አስፈሪውና ለእውነት የቀረበው ይኀኛው መንገድ ነው 

፡፡ ሁለተኛው ኢትዮጽያ ከአበዳሪ ድርጅቶች ጋር በቂ ገንዘብ እንዳታገኝ የማግባባትና የማሳመን ስራ ማከናወን ይሆናል ፡፡ ይህም በጣም ሊተገበር ይችላል ፡፡ እንዴት ከተባለ ሀገሪቱ ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማሲና የነገር ልምድ አካብታለች ፡፡ በሌላ አነጋገር ያደፈ ቢሆንም እጇ ረጅም ነው ፡፡ ግድቡ ጉዳት የለውም የሚለው የኛ መፈክርና እንዴት እንደፈራለን የሚለው የእነሱ ‹ ባላባታዊ ቁጣ › ደግሞ በቀላሉ እንዳንግባባ ያደርገናል ፡፡ ተከብሮ የኖረውን የሳዳትና የናስር መርህ እናስጠብቃለን ሲሉ እኛ ደግሞ የአጼ ቴዎድሮስንና የሚኒልክን ሀገራዊ ተጋድሎና ዝና እንደግማለን እንላለን ፡፡ ይህ ክፍተት በራሱ ለጋሽ ሀገሮችና አበዳሪ ድርጅቶች ወደ አንዱ ወገን እንዳያጋድሉ ያስፈራቸዋል ፡፡ ጭቅጭቁ የሰላም ማረጋገጫ ወይም ዋስትና አልሰጠንም እንዲሉ በር ይከፍትላቸዋል ፡፡ በሌላ አነጋገር ለኛ የተቆለፈው እጃቸው ነገም እንደተከረቸመ ይቀጥላል ማለት ነው ፡፡

አሁን ‹ No Money , No Funny › ወይም ‹ No Money , No Dam ›  የእውነት በኛ ላይ እንዳይሰራ ወይም በብሂሉ ተጠልፈን እንዳንቆም መስጋት አግባብ ይሆናል ፡፡ በርግጥ መሃንዲሱም እኛ ፣ የገንዘብ ምንጩም እኛ መሆናችን ቀደም ብሎ የተገለጸ ነው ፡፡ የግብጾች ትንኮሳ ፣ እብሪትና ማን አለብኝነትም የህዝቡን ቁጭት ለማቀጣጠል የሚያስችል ክብሪት እንደሚፈጥርም ይገመታል ፡፡ መንግስት አሪፍ ከሆነ አጀንዳውን ለሀገራዊ መግባባት ሊጠቀምበት ይችላል ፡፡

እንደዛም ሆኖ ግን ‹ ተራራው የግድብ ብር ›  ላይ ለመድረስ ምስኪኗ የወር ደመወዛችንና የአንዳንድ ባለሃብቶች ለቀቅ ያለ ልግስና ብቻ የትም አያደርሰንም ፡፡ በመሆኑም ያልታዩ አዳዲስ ስልቶች ያስፈልጉናል ፡፡ ለዚህም ስልት መሳካት ቆራጥ ርምጃዎችና ‹ እናት ሀገር ወይም ሞት ! › የሚሉ አመራሮች ያስፈልጋሉ ፡፡

እኮ ለምን ? ምን ሊያደርጉ ?

ብዙ ብዙ ነገሮችን ለማድረግ መጠበብ ያስፈልጋል ፡፡ ቢያንስ ሁለት ክፉ ምሳሌዎችን እንደ ማሳያ ልወርውር ፡፡

. አንደኛ ትንሽ ትልቁ በሙስና እየበላ የሚገኘውን ገንዘብ ጠንክሮ በማስመለስ ለግድቡ እንዲውል ማድረግ ፡፡ ሁለት መቶ ደርሷል የተባለውን ተጠርጣሪ እንደ ትራንስፎርሜሽኑ የተለጠጠ ዕቅድ በመቶ እጥፍ በማሳደግ ካቴና የሚያጠልቀውን የሌባ ቁጥር ከፍ ማድረግ ፡፡

. ሃብታም ባለስልጣናት ለፖለቲካው ልዕልና ሲባል ዘብጥያ የማይወርዱ ከሆነ እንኳ ቢያንስ በአንድ ነገር መደራደር ፡፡ ሰርቀው ካጠራቀሙት በርካታ ገንዘብ በርካታ እጁን እንዲያዋጡ ማድረግ ፡፡ ይህ ጥያቄ ጋሼ ትልቁና እትዬ ትልቋንም ይመለከታል ፡፡ እነሱም ከኛ እኩል የወር ደመወዛችንን ለገስን ሲሉ ‹ Shame › አይዛቸውም እንዴ ?  Really , It is not a joke !

No Dam , No Joke !
No Dam , No Justice !
No Dam , No Victory !
One  Nile  , More Togetherness !