Saturday, June 23, 2012

አስገራሚው የ ‹ ከቤ እና የእሙሙ › ፌስቲቫል !‎!‎




ጃፓኖች ትሁትና አይናፋር ናቸው፡፡ ወግ አጥባቂዋች ስለሆኑ በግልጽ ደፍረው ስለ ወሲብ ለመወያየት የሚያስቸግራቸው ይመስላል፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎች እንዲህ ብናስብ አልተሳሳትን ይሆናል፡፡ ግን ስለ ብልት የሚዘፍኑበት፣ የሚለምኑበት፣ የሚቀልዱበት፣ አካፋን አካፋ የሚሉበት ግዜ መኖሩን ለሚያስብ ሊገረም ይችላል፡፡ አላውቃቸውም እንዴ በማለት ?!

የዓለማችን ሀገሮች የራሳቸው የሆነ ልዩ ክብረ በዓል እንዳላቸው ይታወቃል ፡፡

ሳምባ - የብራዚል ፌስቲቫል ሲሆን የሳምባ ዳንስ ውድድር ይከናወንበታል፡፡

ኤል ኮላቻ - የስፔን ፌስቲቫል ሲሆን ገና የተወለዱ ህጻናት ተደርድረው ይዘለላሉ፡፡ ዓላማው ህጻናትን ከኃጢያት ማንጻት ነው፡፡

የጦጣ ቡፌ - በታላይንድ ፌስቲቫል 600 ጦጣዋች 3ሺህ ኪ.ግራም የሚደርስ ፍራፍሬና ቅጠላ ቅጠል እንዲበሉ የሚጋበዙበት ነው፡፡ ዓላማው የራማን ጀግና መምረጥ ነው፡፡

ሆሊ ፌስቲቫል - በህንድ የሚከበር የቀለማት በዓል ነው፡፡ ሰዋች ከኒምና ከተለያዩ ቅጠሎች የቀመሙትን ቀለሞች ይወረውራሉ፡፡ ቀለሙና ፓውደሩ ገንፋንና ትኩሳትን ያድናል ብለው ያምናሉ፡፡

ማስላንታስ - በሩሲያ የሚከበር ነጻ የሆነ የቦክስ በዓል ነው፡፡ ህግ ስለሌለው ግብግቡ የሚያበቃው ተፋላሚው በደም ሲሸፈን ነው፡፡
ላ ቶማቲና - በስፔን በሺ የሚቆጠሩ ሰዋች በቲማቲም ርስ በርስ የሚደባደቡበት ፌስቲቫል ነው፡፡ ይህን ትርዒት 3 መቶ ሺህ ቱሪስቶች ይከታተሉታል፡፡

ሮስዌል - በአሜሪካ ይህ በዓል የሚከበረው ዩፎዋች በሮስዌል ያደረሱትን ጥቃት ለማሰብ ነው፡፡ በዓሉ ሰዋች ልዩ ፍጥረት የሚያስመስላቸውን ማስክ አድርገው በልዩ ልዩ ስፓርታዊ እንቅስቃሴዋች በመወዳደር ነው፡፡

ሃይማኖታዊ መሰረት ቢኖራቸውም በሀገራችንም ጥምቀትና መስቀልን የመሳሰሉ በርካታ ቱሪስት ጠሪ ፌስቲቫሎችን መጠቃቀስ ይቻላል፡፡

ሌላም የትየለሌ ፌስቲቫሎች ሊደረደሩ ይችላሉ፡፡

እነዚህና ሌሎችም ግን ከጃፓን ክብረ በዓሎች ጋር መወዳደራቸው ያጠራጥራል፡፡ በዓሉ የሚያተኩረው በሰው ልጆች አቢይ ብልቶች ላይ ነውና ፡፡ ይህን ክብረ በዓል ድንገት የሚቀላቀል በድንጋጤ ግር ቢለውም እየቆየ ሲሄድ ግን በሳቅ መፈንዳቱና መደሰቱ አይቀርም፡፡ ነገሩ የማይደፈር በመሆኑ በተለይም የጃፓን ቀጣይ ትውልድ ልዩ ሃሳቦችን እንዲያመነጩ ያግዛችዋል ነው የሚባለው፡፡

ቀኑ መጋቢት 15 ነው፡፡

በዕለቱ የወንድንም ሆነ የሴት ብልትን በስሙ ነው የሚጠሩት - አይናፋሮቹ ጃፓኖች፡፡ ለዚህም ነው የፌስቲቫሉ ስያሜም ምንም ሽፍንፍን ሳይደረግ ‹ የወንድ ብልት ፌስቲቫል! ›… ‹ የሴት ብልት ፌስቲቫል ! › እየተባለ የሚጠራው፡፡  ለጽሁፉ አስገራሚነት ፣ ለአውዱ ጥያቄና ማማር ሲባል እኔም ለዛሬ አካፋን አካፋ እያልኩ መጥራት ነበረብኝ፡፡ ግን ከጻፍኩት በኃላ ሸከከኝ ፡፡ የሞራል ጉዳይ መሆኑ ነው፡፡ እናም የወንዱን ‹‹ ከቤ ! ›› የሴትን ‹‹ እሙሙ! ›› እያልኩ የቅጽል ካፓርት ማልበስ አስፈለገኝ፡፡ 
·          
መጋቢት 15 ቀን የከቤ ቀን በተለይ በኮማኪ ከተማ በደማቅ መልኩ ይከበራል፡፡ ከዚህ ክብረ በዓል አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ደግሞ የእሙሙ ፌስቲቫል አለ ፡፡ እነዚህ በዓሎች የ1500 ዓመታት ዕድሜ አላቸው፡፡ የበዓላቱ መነሻዋች ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በአንድ በኩል መሬታቸው ጥሩ ሰብል እንዲሰጣቸው በሌላ በኩል ምርት ብቻ ሳይሆን ልጅ እንዲያገኙ ብልቶችን ወይም የብልት አምልኮዋችን የሚለማምኑበት ስርዓት ነው፡፡

እንደሚታወቀው ጃፓን በዓለማችን አነስተኛ የወሊድ መጠን የተመዘገበባት ሀገር ናት፡፡ በመረጃው መሰረት 1.37 ህጻናት ናቸው ለአንዲት ሴት የሚደርሱት፡፡ ባለፈው ዓመት ስልጣን የያዘው ገዢ መደብ ሴቶች ተጨማሪ ህጻናትን እንዲወልዱ የሚያበረታታ ስጦታ አበርክቷል፡፡ መመሪያውን ተግባራዊ የሚያደርጉ እናቶች ለህጻናቱ ማሳደጊያ በየወሩ 280 ዶላር ይቆረጥላቸዋል፡፡

በእሙሙ ፌስቲቫል ቀን እናቶች ልጆቻቸውን አዘንጠው በፕላስቲክ፣ በእንጨት ወይም በተለያዩ ቁሳቁሶች የተሰሩ ትናንሽ የእሙሙ ምስሎችን ይዘው በዋናው አደባባይ እንዲገኙ ያደርጋሉ፡፡ 40 የሚደርሱ ሰዋች በትልቅ ቅርጽ የተሰራውን እሙሙ  በቃሬዛ መልክ ይዘው ይዞራሉ፡፡ በዕለቱ እናቶች ለልጆቻቸው ጤንነት ይጸልያሉ፡፡ በዓሉ ላይ የተለያዩ ምግቦችና ቢራዋች ይዘጋጃሉ፡፡ በበዓሉ ማብቂያ ላይ ነጭና ሀምራዊ ጣፋጭ ሩዝ ሰዋች ላይ ይረጫል፡፡

በከቤ ፌስቲቫል ቀን ከመቶ ሺህ በላይ የሚሆኑ ጃፓናዊያንና የውጪ ቱሪስቶች በቦታው ይታደማሉ፡፡ በኛ ሀገር በክብረ በዓል ቀን በየመንገዱ፣ ድልድይ፣ ቆርቆሮ፣ የስልክ እንጨት ወዘተ ላይ የሚንጠለጠለው ባንዲራ ነው፡፡ ጃፓኖች በዚሁ ዕለት ከላይ በተገለጹት ቦታዋች ላይ የሚያንጠለጥሉት ሌላው ቀርቶ በአፍንጫቸው ላይ የሚያስሩት የወንድን ብልት ነው ፡፡

ይህ በዓል የሚከበረው እኛ ሀገር ቢሆን ከባንዲራው ጎን ጥቅሶችና መፈክሮች መኖራቸው ግድ ይላል፡፡ እንደው ሳስበው
 ‹‹ ከቤ ለዘላለም ይኑር ! ›› የሚል ጥቅስ ብዙ ሰው የሚይዘው ይመስለኛል፡፡
‹‹ ያለ እሙሙ ተሳትፎ
እንኳን አብዮቱ
አይነጋም ሌሊቱ ›› የሚል ሞጋች ስነ ቃልም ከወግ አጥባቂ ሴቶች ክንድ ላይ ይጠበቃል፡፡
‹‹ አርሜ ኮትኩቼ ያሳደኩት ከቤ
  አምላክ ይመስገነው ደረሰ ከሃሳቤ ›› የሚል መፈክር ደግሞ በአንዳንድ ፍንዳታዋች እጅ ቢጠፋ እንኳን እንደ መዝሙር ሲደጋግሙት ሊሰማ ይችላል፡፡
‹‹ የከቤና የእሙሙን  አቅም አሟጦ በመጠቀም የልማታችንን ቀጣይነት እናረጋግጣለን ! ›› የሚል ካድሬያዊ መልዕክት ይጠፋል ማለትማ የሰማይ ስባሪ የሚያህል ውሸት እንደ መናገር ያስቆጥራል፡፡
ተረቶቻችን፣ አባባሎቻችን፣ ዘፈኖቻችን፣ የወሬ ማጣፈጫዋቻችን፣ ቀረርቶዋችን ሁሉ ከነ ከቤ ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተጋመዱ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ሌላው ቢቀር
ራሰ በረሃ አንገተ ክርክር
ሁለት ልጆች ይዞ በጫካ የሚኖር !
የተባለችውን እንቆቅልሽ ከልጅነቱ ሳይሰማት ያደገ ማን አለ ?  ከፍ እያልን ስንሄድ ተረትና እንቆቅልሾቻችንን በሰምና ወርቅ አጠናክረናቸዋል፡፡ ካስፈለገም የአግቦና አሽሙር ብቃታችንን ከኃላ ኪሳችን እናወጣለን፡፡ ምናለፋችሁ ፌስቲቫሉ ቀውጢ የሚሆን ይመስለኛል፡፡
·          
እናላችሁ በትልቅ ቅርጽ የተሰራው ከቤ ርዝመቱ 25 ሜትር ሲሆን ክብደቱ 280 ኪ.ግራም ይመዝናል፡፡ ቪንሚንሻ ይሉታል ጃፓኖች ይህን ጣዖት፡፡ ይህን ቅርጽ በመሸከም ታዋቂውን አደባባይ መዞር፣ ማጨብጨብ፣ መዘፋፈን ፣ መጸለይ፣ በቅርጹ የተሰራ ሻማ ማብራት የተለመደ ነው፡፡ ድርጊቱ ለአንድ ወይም ለአንድ ተኩል ሰዓታት ይፈጃል፡፡ የጥንት ጃፓኖች የከቤው አደባባይ የዕድገትና የልማት ሁሉ መሰረት ነው ብለው ያምናሉ፡፡ በሌላ አነጋገር እናት የሆነቸው መሬት፣ አባት በሆነው ሰማይ ታረግዛለች፡፡ ይህን ተምሳሌት የሚያቀነቅን ፈላስፋ ማን ነበር ?

በመሆኑም ልጅ የሌላቸውም ሆኑ ተጨማሪ ልጅ የሚፈልጉ ሁሉ በክብረ በዓሉ ላይ በለመለመ ተስፋና ፍቅር ይገኛሉ፡፡ ክብረ በዓሉ በርካታ ቱሪስቶችን እየሳበ በመሆኑ ሀገሪቱ ከፍተኛ ገቢ ታገኛለች፡፡ ነጋዴዋችም በእሙሙና  በከቤ ቅርጽ የተሰራ ከረሜላና ቸኮላታ ይቸበችባሉ፡፡ በእንጨትና በፕላስቲክ ቅርጻ ቅርጾች የተሰሩ ብልቶች፣ የጆሮ ጌጦች፣ የሲጋራ መተርኮሻዋች ይሸጣሉ፡፡ በተለይም ወጣት ሴቶች በወንድ ብልት የተሰራን ከረሜላ በመምጠጥ ራሳቸውን ያዝናናሉ፡፡ የሚገርመው የሁለቱም ጾታዋች ብልቶች ዋጋ እኩል 600 የን ያህል  መሆኑ ነው፡፡ በርካታ ቱሪስቶች ፌስቲቫሉ በተለይም ልጅን ይሰጣል የሚለውን ሀሳብ ባይቀበሉትም ቢራ በመጠጣትም ሆነ ቅርጹን በመምጠጥ፣ በሃገሬው ደስታና እምነት በመደሰት እንዲሁም ከከቤ ጋር የተያያዙ ቀልዶችን በማውራት ይዝናናሉ፡፡

በማይደፈር ነገር መዝናናት ብልግና ነው ሀሴት ?

መቼም የነከቤ ፌስቲቫል ይኑረን  ባይባልም ፣ ጀግንነት ነው እየተባለ የሰው ከቤ የሚቆረጥበትና  የልጃገረዶችን እሙሙ  የሚሰፋበት ሀገር ውስጥ ከመኖራችን አንጻር ለዚህ ወሬ ቢያንስ አክብሮት ሊኖረን ሳይገባ አይቀርም፡፡

ወጣቶች በከቤ የተሰራ ከረሜላ ሲመጡ



ረጅም ዕድሜ ለከቤና ለእሙሙ !!



No comments:

Post a Comment