Thursday, August 3, 2017

የድርሰት ሰማይን ያደመቁ ብዕረኛ

ደራሲ አማረ ማሞ ብዙ አልተባለላቸውም ። ግን ለስነጽሁፍ ብዙ ሰርተዋል ፤ በእጅጉ ደክመዋል ። እጣ ፈንታ ሊሆን ይችላል ። አንዳንድ ያደለው በአንድ ጥሩ ስራ ስማይ ላይ ሊወጣ ይችላል ። የዚህ አይነቱ እድለኛ ባለቲፎዞም ስለሚሆን ክበባቱ ፣ ሚዲያውና ማስታወቂያው እንኮኮ ያደርገዋል ።

በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ደራሲ፣ አርታኢና ተርጓሚ አማረ ማሞ ማናቸው ተብሎ አልተመረመሩም ። እኚህ ሰው ስነጸሁፍ ፍቅራቸው ብቻ ሳይሆን ህይወታቸው በመሆኑ ኖረውብታል ማለት ይቻላል ። የኢትዮጽያ መጻህፍት ድርጅት ስነጽሁፍንና ደራሲዎችን ለማሳደግ አይነተኛ ሚና ተጫውቷል ። እሳቸው ደግሞ በድርጅቱ ውስጥ ም/ስራ አስኪያጅ ነበሩ ።

በድርጅቱ አሳታሚነት ለንባብ ይበቁ የነበሩ መጻህፍትን የሚያስታውስ አንባቢ የአቶ አማረን ድርሻ በአግባቡ ለመረዳት አያዳግተውም ። የነባርና እጩ ደራሲዋችን የአሳትሙልኝ ረቂቅ ጽሁፎችን በመለየት ፣ የተለየውን ደግሞ የአርትኦት ስራ በማከናወን በድርሰት ላይ የማዋለድና ጥሩ ቁመና የመፍጠር ህክምና አበርክተዋል ።

እንዴት ላሳትም ወይም በምን መልኩ ልጻፍ ወይም የመሳሰሉ ጥያቄዋችን አንግቦ ቢሯቸው ጎራ የሚሉትን ጥበብ አፍቃሪዋች ውሃ የሚያነሳ ምላሽ ለመስጠት አያነቅፋቸውም ። የኢትዮጽያ መጻህፍት ድርጅት ከስራ ውጪ ከሆነ በኋላ እንኳ አቶ አማረን ኪነጥበባዊ እድሞሽ ላይ ማግኘት ቀላል ነበር ። በስነጽሁፋዊ ውይይቶችም ሆነ ህትመት ምርቃቶች ላይ ከፊት በመገኘት ልምዳቸውንና ሃሳባቸውን ሳይሰላቹ አጋርተዋል ።

አቶ አማረ የበርካታ መጻህፍት ደራሲና ተርጓሚ ናቸው ። ዶን ኪሆቴ ፣ አሳረኛው ፣ እሪ በይ ሃገሬ ፣ የእውነት ብልጭታ ፣ የቀለም ጠብታ እና የልብ ወለድ ድርሰት አጻጻፍ የተስኙ ስራዋችን በጥቂቱ መጠቃቀስ ይቻላል ።

እውነቱን ለመናገር የልብ ወለድ ድርሰት አጻጻፍ የተሰኘው ስራቸው ብቻ ሽልማት የሚገባው ነው ። በ1960ዎቹ የታተመው ይህ ስራ የብዙ ድርሰት አፍቃሪያንን አይኖች የገለጠ ነው ። እንደሚታወቀው ኮሌጅ/ዩኒቨስቲ የመግባት እድል ያላጋጠማቸው የሀገራችን ደራሲዎች ጥቂቶች አይደሉም ። ብዙዎቹ ታዲያ መጽሀፉን እንደ አንድ ተቋም ክብር በመስጠት የልቦለድ ባህሪና ምንነትን እንዲሁም እንዴት መቀሸር እንደሚገባው የተረዱት ይህን መጽሀፍ በማንበብ ነው ። ለመጽሀፉ ምስጋና ይግባውና ጠንካራ ምናብና ብእር ያላቸው ደራሲዎች መፈጠር ችለዋል ።

ይህ መጽሀፍ ድንበር ያጠረው አልነበረም ። ሌላው ቀርቶ በኮሌጆችና/ዩኒቨስቲዎች ለስነጽሁፍ ትምህርት አጋዥ በመሆን ለመምህራኑም ሆነ ለተማሪዎች ትልቅ ግብዓት ፈጥሯል ። በነገራችን ላይ የራሳቸውን ማንዋል አዘጋጅተው ወይም አጋዥ ስራ አሳትመው የሚያስተምሩ ውለተኛ መምህራን ቁጥር እጅግ አነስተኛ ነው ። የቲያትር ኮርስ ሲሰጥ የፋንታሁን እንግዳ የተውኔት መጽሀፍ ነው ትልቅ ድርሻ የሚወስደው ። ተማሪ እየተናጠቀ ኮፒ ለማድረግ ይራወጣል ። በዚህ ረገድ ደበበ ሰይፉና ዘሪሁን አስፋው የሚታሙ አይመስለኝም ። ርግጥ ነው ብርሃኑ ገበየሁም ኋላ ላይ ተቀላቅሏል ። መሰረታዊ ስነጽሁፍ ለኮሌጅ ተማሪዋች በተለይ የአፍሪካ ስነጽሁፍን አስመልክቶ ግን ብዙ ያልተዘመረለት መምህር አለ ። መክነህ መንግስቱ የሚባል ። ርግጠኛ ባልሆንም ከኮተቤ ወደ ዩኒቨርስቲ የተዘዋወረ ይመስለኛል ። በርካታ ድርስት ነክ ስራዎችን በእንግሊዘኛ ቋንቋ አሳትሟል ። ተማሪዎችም የእሱን ስራዎች መነሻ በማድረግ የአፍሪካን ስነጽሁፍን ለማወቅና ለመመርመር አግዟቸዋል ።

የአቶ አማረ ስራ ግን ኮሌጅ ለረገጠውም ላልገባውም ፣ ለጀማሪውም ለመምህራንም ፣ ለስነጽሁፍ አድናቂም ለተመራማሪውም ዛሬም ድረስ የውለታ ሃውልት ሆኖ ቆሟል ። እንግዲህ እዚህ ሃውልት ላይ ነው ሰሞኑን የክብር ካባ እና የወርቅ ብእር የተሰቀለው ። በሸላሚው ድርጅት ማለትም በንባብ ለህይወት የፌስ ቡክ ገፅ ላይ « አይናቸውን ያልጨፈኑ የድርሰት ሰማያችንን ያደመቁ ኮኮብ ሆነው ሆነው በመገኘታቸው የዓመቱ የወርቅ ብዕር ተበርክቶላቸዋል » የሚል ጽሁፍ ይነበባል ።

ግሩም ምስክርነት ሆኖ ስላገኘሁት ደስ ብሎኛል ። በርግጥም የድርሰት ሰማያችንን ለማድነቅ የተጉ በርካታ ጸሐፊያን አሉን ። አቶ አማረ ግን ኮኮቦቹ ከመታየታቸውም በፊት ጧፍ ሆነው ተገኝተዋል ። ብዙዎችን አርመዋል ... ኮትኩተዋል ... በርካቶችም የጧፉን ብርሃን ተከትለው  መንገድ አግኝተዋል ።


ንባብ ለህይወት በአጭር እድሜው አምባሳደር ዘውዴ ረታ ፣ አዳም ረታንና አማረ ማሞን የወርቅ ብዕር ተሸላሚ አድርጓል ። መልካም ጅምር ስለሆነ ለረጅምና ላልተቆራረጠ ጉዞ ብርታቱን እንዲሰጣችሁ እመኛለሁ ። ብርታቱ ግን እንደ አማረ ማሞ ብዙ ሰርተው ያልተነገረላቸውን ብዕረኞችን  ለማፈላለግ ጭምር እንዲሆን ማድረግ ይገባል ።

No comments:

Post a Comment