Friday, February 28, 2014

የባለገሩ ስነቃልና የ « አቶ አለምነው ቤት »


ንደማንኛውም መጽሀፍ በትኩረት ላንብበው ብዬ አይደለም የገለጽኩት ። < እስኪ ትንሽ በአነጋገራችን ልዝናና > በማለት እንጂ ። ድንገት ከመሃሉ ገለጥ ሳደርገው < ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል > ከሚለው ንባብ ጋር ግጥምጥም አልኩ ። < ጎሽ ይዞልሃል > አልኩት በፈገግታ - የምሳሌያዊ አነጋገር መጽሀፉን ።
እናም ከ ሀ እስከ ታች የተዘረዘሩትን አነጋገሮች እንደ ፎቶ አልበም እያገላበጥኩ መጫወት ቀጠልኩ ። የገረሙኝን መቼ ይሆን የተነሱት ይቅርታ መቼ ይሆን የተነገሩት ፣ በየትኛው አካባቢ በማለት caption ብጤ እፈላልግ ነበር ። አንዳንዶቹ ሳይታዘዙ የሰው ብብትን ኮርኩረው በግድ ሳቅ መፍጠር የሚችሉ ናቸው ። ለምሳሌ ያህል ፣
< ለሰበበኛ ቂጥ መረቅ አታብዛበት ! >
< ቢያንጋልሏት ጡት የላት ፣ ቢደፏት ቂጥ የላት ! >
< ምንም ብትሞቺ ፣ እንዴት አደርሽ አንቺ ?! >
< እግዜር ሲቆጣ በዝናብ አር ያመጣ >
< ተደብቃ ትጸንሳለች ፣ ሰው ሰብስባ ትወልዳለች ! >
< አባቴ ትንሽ ነው ፣ ብልቴ ትልቅ ነው የሚል የለም ! >
< ልጅ አባቱን ገደለ ቢለው እረ የኔ ልጅ እንዳይሰማ አለው >
የሚሉት ጋ ስደርስ ከትከት ብያለሁ ።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ አንዳንዶቹ አባባሎች ጥያቄ የሚያስነሱ ... እንደ መጽሀፍ ቅዱስ ቃል አስረጅ የሚፈልጉ ወይም ደግሞ ሃይለኛ ማስተካከያ የሚፈልጉ ሆነው ነው ያገኘኃቸው ።
ለአብነት ያህል < ነገሩ ነው እንጂ ጩቤ ሰው አይጎዳም ! > የሚለው አባባል ድሮ ጩቤ ከጎማ ወይም ከቆዳ የሚሰራ መሆኑን ነው የሚያመለክተው ። ካልሆነ ታዲያ በአሁኑ ግዜ እንቅፋት ፣ የበዛ ሀሳብ ፣ ድንጋጤና ትንታ እንኴን ሰው ለመግደል ፍቃድ አውጥተው እንዴት ሆኖ የሾለ ብረት ሰው ለመግደል የሚያንሰው ?
< ማን ይሙት ጠላት ፣ ማን ይኑር አባት ! >
የሚለው ስነቃል የተደረሰው የእንጀራ እናት ባሳደገችው ባላገር እንደሆነ ግምት አለኝ ። አሊያማ ከአባት በላቀ መልኩ እናቱንና ሀገሩን « እምዬ » የሚለው ኢትዮጽያዊ ተቆጥረው የማያልቁ የእናት ክብር መግለጫ ግጥሞችን እንደ ዝናር ታጥቆ አይደለም እንዴ የሚዞረው ? ድንገትም
< እናቱን ለናቀ ክብሯን ላዋረደው >
መሬት ትዙርበት ጸሃይ አትሙቀው » ብሎ ሊቆጣ እንደሚችል ሁሉ መች አጣችሁት ?
< ለሰው ሞት አነሰው ! >
የሚለው አባባልስ በምንድነው የተሰራው ? በዝሆን ሀሞት መሆን አለበት ። በዚህ ሀሞት እንጀራ ፈርፍረው በግድ ያጎረሱት አንድ ሰው ክፋትንና ጭካኔን ለመግለጽ  አክ - እንትፍ ያለው ሀረግ ይመስላል ። መቼም ሞት አነሰው የሚለን እድሜ ልክ በእስር ይበስብስ ለማለት አይደለም ። ምናልባት የሚረካው ከጀግናውና ሀገር ወዳዱ አጼ ቴዎድሮስ አንድ የጭካኔ ሰበዝ መዞ ሲተገብረው ሊሆን ይችላል ። አጼ ቴዎድሮስ በደግነትና ጭካኔ ተደባልቀው የተሰሩ ንጉስ ነበሩ ። ቁጣ የንዴታቸውን ጣሪያ በሚያግለው ግዜ የሚያቀዘቅዙት የሰው እጅና እግርን አስቆርጠው ነበር - ከዛ ቁራጭህን ይዘህ ሀገር ግባ ነው ። እግር እንደ ዛፍ የሚመለመልበት ዘመን ። ለነገሩ ይህ ዘመን አልፏል ። ዛሬም ግን ሰዎች በድንጋይ ተወግረው ይሞታሉ ፣ አንገታቸው በሻሞላ ይቀላል ፣ ሰውነታቸው ተቀብሮም ከብቶች በላያቸው ላይ ይነዳል ። እዛ ያሉት አጼ ልክም ነው ህግም ነው ይሉሃል - እኛ የምንለው ያዝልን መጀን ! ነው ።
 < ሙቅ ውሃና የሰው ገንዘብ አይጠቅምም  ! >
በመርህ ደረጃ ልክ ነው ። ዳሩ ግን ጂ+1 ውስጥ እየኖሩ ጂ+6 የሚያስገነቡት ፣ ሚሊየን በሚደፍር መኪና የሚንፈላሰሱት ፣ ለልደታቸው ወይ ዱባይ አሊያም አካፑልኮ ደርሰው የሚመጡት ፣ ይህ ካልተመቸ ከፓሪስ ኬክ የሚያሰጋግሩት ልማታዊ ሀብታሞች በኑሮ ሰረገላ ከአያት ተራራ እስከ እስከ ካራማራ የሚንፈላሰሱት ስፍር ቁጥር የሌለውን የሰው ገንዘብ በጥቂት ማግኔታዊ ላባቸው በመሰብሰብ አይደለም እንዴ ? መሰለኝ እንግዲህ !
< ልጅ ቢያስብ ምሳውን ፣ አዝማሪ ቢያስብ ጠላውን ! >
ይህች አባባል ገና ድሮ ጡረታ መውጣት ሲገባት ለሰዎች በተጨመረው የስራ ዘመን ፍዳዋን ትቆጥራለች ። ለማንኛውም የዛሬ ልጅ ከአባቱ የተረፈውን ሳይሆን ከአባቱ ጸሎት በፊት አስቀድሞ የሚጎርስ ፣ እንግዳ አክብሮ ጔዳ የሚሸሸግ ሳይሆን ልክ እንደ ርዕሰ ብሄር እንግዳውን በራሱ ክፍል ውስጥ ተቀብሎ የሚያነጋግር ፣ አንዲት ምሳውን ሳይሆን ለትምህርት ቤት ከሰኞ እስከ አርብ በሁለት ሳህን ስለሚያስቌጥራቸው የምግብ አይነቶች ከፈለገ ከአረብ ቻናል ፣ እንዳማራጭም ኢቢኤስን ቁጭ ብሎ በመቃኘት  መርሃ ግብር የሚነድፍ ነው ። ስለፍቅር ፣ ስለኑሮ ውድነት ፣ ነገር ስላሰከራቸው ጎረቤቶች ፣ ስለተሸራረፉ መብቶች ፣ ስለቀበሌም ሆነ ገዢው ፓርቲ አያውቅም ብለው ፊቱ ካወራችሁ ተሳስታችኃል - ምክንያቱም በሌላ ቀን እርስዎን እንደ ዋቢ ምንጭ በመጥቀስ ለጔደኛው ወይም ለጥቁሩ እንግዳ ገለጻ ሲያደርግ ሊሰሙ ይችላሉና ።
ስለሴትነት ብዙ ተብሏል ። ጥቂቱን ብቻ እንምዘዝ ።
< ሴትና አህያ በዱላ ! >
የወረደ ነው ወይስ የተጋነነ ንጽጽር የሚባለው ?
 < ሴት የወደደ ገሃነም እሳት ወረደ ! >
የመላከ ጊዮርጊስ ?! እናቴን ? እህቴን ? ልጄን ? ሚስቴን ? ያለው ማን ነበር ?
< ሴት ካልወለደች ቌንጣ አትጠብስም ! >
በጉዴ መጣ አሉ እትዬ ዘነቡ - ባለስልጣኗን አይደለም
< ሴት በማጀት ወንድ በችሎት ! >
ወቸው ጉድ ?! ይህን የማህበራዊና ባህላዊ ልምድ ጣጣ ነው ብሎ ማለፍ እንዴት ይቻላል ? ጠንካራ ፖለቲካም ጭምር እንጂ ። ቆይ ግን የወ/ሮ ዘነቡ መ/ቤት በተለይም ሴቶችን በተመለከተው ርዕሰ ጉዳይ ምን እያሰበ ነው ? ለነገሩ እሳቸው ሰሞኑን የግበረ ሶዶማዊያን አጀንዳ ላይ ናቸው ። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ጻጻስ ፍራንሲስ ስለ ጌይ ምን ይላሉ ሲባሉ « እኔ ማነኝ እና ነው ይህን የምዳኘው ? » የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪሙን በበኩላቸው « ግብረ ሶዶማዊያን እንደ ሁለተኛ ዜጋ ብቻ ሳይሆን እንደ ወንጀለኛም እየተቆጠሩ ነው » በማለት ኡኡ ብለው ያውቃሉ  ። ፕሬዝዳንት ሮበርቱ ሙጋቤ በአንድ ወቅት “ ግብረሰዶማዊያን ከአሳማና ከውሾች የከፉ ናቸው » ማለታቸው አይዘነጋም  ። ሚኒስትር ዘነቡ ማን ከማን ያንሳል ብለው ምን ነበር አሉ የተባሉት ? መቼም ይሄ ሁሉ የስነቃል የቤት ስራ እያለባቸው እዛ ውስጥ ከገቡ የጉድ ነው ።
< በሽተኛ ያድርቅህ መጋኛ  ! >
አሁን ነው መሸሽ ። በደጉ ዘመን በነገር ወይም በቦክስ ገጭቶት አሁን ብድሩን የሚመልስ ሰው ይሆን ? ነው ህመምተኛው ሲያቃስት ከእንቅልፉ እየተቀሰቀሰ በቃሬዛ ጤና ኬላ ማመላለስ የሰለቸው አባወራ ? ለነገሩ የአቶ ቦጋለ መብራቱ እና የወ/ሮ ውድነሽ በጣሙ ዘመድም ሊሆን ይችላል ። አቶ ቦጋለ ወጥሮ የያዛቸው የተስቦ በሽታ ለሌላውም እንዳይተርፍ ለመጋኛ ስለት የሚያቀርብ ምስኪን ገበሬ ። ወይ አጨካከን ?! በሽተኛን ፈጣሪ ይዳብስህ በማለት ያጽናኑታል እንጂ እንዴት ይለጥፉበታል ። ግድየለም እንዲህ የሚናገሩት የሰው ልጆች ሳይሆኑ የሰው ገዢዎች መሆን አለባቸው ።
እነዚህን የመሳሰሉ አነጋጋሪ ፣ ተሻሻይ ወይም ተሰራዥ አባባሎች ጥቂት አለመሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል ። ለዚህ ለዚህ የቀድሞው ባህል ሚኒስቴር ከተፎ ስራ ይሰራ ነበር ። የአሁኖቹ እንኴ በፍላጎትና በሞያ ሳይሆን በሹመትና ሽረት ብሎም በአንሚ ደረጃ የተወከሉ ናቸው ስለሚባል  ደረትን ለመንፋት የሚያስችል መሰረት መኖሩ ያጠራጥራል ። ለማንኛውም ግልባጩ ይድረሳቸው ።
ትልቁ እውነት ግን አብዛኛው አባባል ወይም ስነቃል ዘመን ተሻጋሪ መሆኑ ነው ። በነዚህ በርካታ ስነቃል ውስጥ ያልተዳሰሰ ማህበራዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ ፣ ሃይማኖታዊ ፣ ባህላዊ ጉዳዮች አለ ለማለት ያስቸግራል ። ከማጣት እስከ ማግኘት ፣ ከስንፍና እስከ እውቀት ፣ ከጅልነት እስከ ብልሃት ፣ ከፍቅር እስከ ጥላቻ ፣ ከጉንዳን እስከ ዝሆን ፣ ከሸፍጥ እስከ ታማኝነት ፣ ከክብር እስከ ውርደት ፣ ከረሃብ እስከ ጥጋብ ፣ ከልጅ እስከ አባት ፣ ከልደት እስከ ሞት ፣ ከዲያቢሎስ እስከ ክርስቶስ ፣ ከሴት እስከ አማት ፣ ከሹመት እስከ ሽረት ፣ ከፍርሃት እስከ ጀግንነት ፣ ከነጻነት እስከ አምባገነንነት .... ምናለፋችሁ ጥላሁን ገሰሰ ያልዘፈነበት ባላገሩ ያልተቃኘበት ፍልስፍና የለም ብሎ እውቅና መስጠት እንደማጋነን የሚያስቆጥር አይመስለኝም ። እያንዳንዱን ርዕሰ ጉዳይ የሚመለከቱትን ስንኞች እዚህ ገጽ ላይ ፈሰስ ባደርጋቸው እደሰት ነበር ። ብዛታቸው ግን አስፈራኝ ። ማንን መርጦስ ማንን መተው ይቻላል ።
እውነት ይህን ሁሉ የደረሰው ብዙዎቻችን ቀለም አልዘለቀውም የምንለው ባላገር ከሆነ የ < ቀለም >ጉዳይ ማጠያየቁ አይቀርም ። እውነት ይህን ሁሉ ነባራዊ እውነት በቃላት ሸብልሎ ያጎረሰን ባላገር ከሆነ < ባገረስኩ ተነከስኩ > ቢል አይፈረድበትም ።
ማነው ነካሽ ?
አሁን በቅርቡ የሚያስተዳድሩትን ባላገር ያበሻቀጡትና ያዋረዱት የአማራው ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አለምነው እውነት ባላገሩን ያውቁታል ?  ካወቁትስ እንዴት ነው የመዘኑት ? ለማለት ስለምንገደድ ነው ። ለምሳሌ ያህል ሹሙ የእውቀትና የልምድ ሀብት የሚለካው ጫማ በማድረግና ባለማድረግ ነው ብለው የተነሱ አስመስሎባቸዋል ። ከዛው ክልል የተገኙት አጼ ቴዎድሮስ ሀብት ሳያንሳቸው ጫማና ኮፍያ ማድረግ አይወዱም ነበር ። ጀግንነትና የሀገር ፍቅር ከባዶ እግር ጋር አይያያዝም ። አበበ ቢቂላ በሮም የኦሎምፒክ ውድድር ያሸነፈው 11 ቁጥር ማሊያና ቁምጣ አድርጎ እንጂ ጫማ ተጫምቶ አልነበረም ። ማራቶን ከጽናትና ጥበብ ጋር እንጂ ከባዶ እግር ጋር ግንኙነት እንደሌለው ሌላ ማሳያ ሊሆን ይችላል ። ርግጥ መንገዱ በማይመችበት ቦታ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችልም ግምት ውስጥ በማስገባት ።
እናም  < ባላገሩ ባዶ እግሩን እየሄደ የሚናገረው ግን መርዝ ነው  > ማለት አንድም ጭንቅላታቸው ውስጥ የሚውለበለብ የንቀት ባንዲራ መኖሩን በሌላ በኩል ደግሞ ያላዋቂነት መነሻ ይሆናል ። ይኀው መነሻ መድረሻ ይኖረው ዘንድ ደግሞ  < ትምህክተኛ ነው ፣ ለሃጫም ነው > እያሉ ልጥፉን ማወፈር በርግጥም ባዶ እግርን ሳይሆን የጎደለ ወይም በዘይት እጦት የሚንጣጣ ጭንቅላትን ወገግ አድርጎ የሚያሳይ ነው ።
በሀገራችን ታሪክ ትላልቅ ስራ የሰሩ በርካታ የሀገራችን ጀግኖች እንደተግባራቸው ስማቸው በክብር እንዲታወስ ተደርጔል ማለት አይቻልም ። ይሁን እንጂ የታደሉት ደግሞ ስንት የጀግንነት ተግባር ፈጽመው በስማቸው እውቅና አግኝተዋል ። ለምሳሌ ያህል አትሌት ኃይሌ  « ሃይሌ ገብረስላሴ ጎዳና »ን በስሙ ማግኘቱ ያንስበታል ።  አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ሆስፒታል አይደለም  ሰሞኑን ለደነገጠው አየር መንገድ ማስታወቂያ ብትሆን መሳ ለመሳ ናት ። ያም ማርሽ ይቀይራል - እሷም ዙሩ ሲሳሳ አዲስ አቦሸማኔ  ትሆናለች ። ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የራሱን የአገጣጠም ስልት በመፍጠሩ « የጸጋዬ ቤት » የተባለ ስያሜ ተበርክቶለታል ። በዚሁ መሰረት በባዶ ጭንቅላት የሚመረቱ መረን የወጡ ስድቦችን « የአቶ አለምነው ቤት » ብሎ መጥራት  ተገቢ ይሆናል ።
ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው እንዲል ባላገሩ ።

No comments:

Post a Comment