Tuesday, March 11, 2014

እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ?





ፓሰተር የሚለው ቃል ምንጩ ላቲን ሲሆን ትርጔሜውም ጠባቂ ወይም እረኛ ማለት ነው ። እረኛ የሚለው ቃል በመጽሀፍ ቅዱስ ውስጥ 27 ግዜ ተጠቅሷል ።
በሀዲስ ኪዳን መጻህፍት ውስጥም በተለይም ወደ ኦፌሶን ሰዎች/ 4 ፡ 11 / በሀዋርያት ስራ / 20 ፡ 28 / እና የጼጥሮስ መልዕክት / 5 ፡ 2/ ላይ ፓስተር የሚለው ቃል ከመምህርነት ጋር ተያይዞ ቀርቧል ማለት ያስደፍራል ። ለአብነት ያህል በሀዋርያት ስራ ላይ « የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጻጻሳት አድርጎ ለሾመበት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ » የሚለውን ጥቅስ እናነባለን ። በሌሎቹ ጥቅሶች ላይ ደግሞ መንጋውን ጠብቁ የሚላቸው ሽማግሌዎችንና አስተማሪዎችን ነው ።
ዞሮ ዞሮ በፈጣሪ ትልቅ ቦታ የተሰጣቸው ቄሶችም እንበላቸው ፓስተሮች የእግዚአብሄርን መንጋ እንዲጠብቁ ከፍተኛ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል ። በጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ 5 ላይ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ የሚለውን ሀረግም ለዚህ አባባላችን ማጠናከሪያ መጠቀም እንችላለን ። ታዲያ እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ? እያስተማሩም እየተመራመሩም ... እያገዱም እያንጋደዱም ይመስላል ። በተለይ በአንዳንዶቹ ላይ
አፈንጋጭነት ፣
ራስን ቅዱስ አድርጎ መሾም
እና ያልተገባ ተግባር መፈጸም በተደጋጋሚ እየታየ ነው ። የጥቂት ወራቶችን ጥቂት አስገራሚ አብነቶችን እየመዘዝን ለምን ቆይታ አናደርግም ? በጣም ጥሩ ...
ደቡብ አፍሪካዊያኑን ፓስተር ሌሴጎ ዳንኤልን እንመልከት ። በቅርቡ « እግዚአብሄርን መቅረብ ከፈለጋችሁ ሳር ብሉ » የሚል ትዕዛዝ በማስተላለፉ ጉባኤተኛው ሳሩን ሲያሻምደው ውሏል ። አንዳንዶቹ ታመው ወደ ሆስፒታል ቢሄዱም አንዳንዶቹ የፓስተሩን ተግባር ደግፈው ሲከራከሩ ነበር « የፈጣሪ ኃያልነትን ማሳያ በመሆኑ ሳር በመብላታችን እንኮራለን ፣ ማንኛውንም ነገር እናደርጋለን » ብላለች አንዲት የህግ ተማሪ
እንግዲህ ይህ ፓስተር ትዕዛዙን የፈጸመው መንፈስ ቅዱስ በራዕይ ተገልጦለት መሆኑ ነው ። በከፋ የረሃብ ዘመን የሰው ልጆች ህይወታቸውን ለማቆየት ርስ በርስ ከመበላላት አልፎ ተሞክረው የማያውቁ ስራስሮችን ለጠኔ ማስታገሻነት ሙከራ አድርገዋል ። በመጽሀፍ ቅዱስ ታሪክም እንደ በሬ ሳር እንዲበላ የተፈረደበት ንጉስ ናቡከደነጾር ነበር ። እሱም ለዚህ ቅጣት ያደረሰው ስልሳ ክንድ የሚያህል የወርቅ ምስል አሰርቶ ለምስሉ እንዲሰግዱ የታዘዘውን አዋጅ የተላለፉ ሰዎችን በግፍ በእሳት በማቃጠሉ ነው ። ስለዚህ < ሳር > የቅጣት ምልክት እንጂ የፈጣሪ መቅረቢያ ስጦታ አይደለም ። የሰው ልጅ አንጀት ሊፈጨው የማይችለውና መጠነኛ መርዛማ ባህሪ ያለውን ሳር መመገብ ሳይንስም አይቀበለውም ።
ባለሁለት እግራሙ የሰው ልጅ ቀሪውን ሁለት እግር ከእጁ ተበድሮ እንደ በግ ሳር ሲግጥ ማየት ሞራላዊና ተፈጥሯዊ ውድቀት ነው ። በዚህ ስሌት ባልታሰበ ሰዓት ሽንት እያሸተተ እንደ በግ ሲያገጥና አባሮሽ ሲጫወት ማየት ይቻላል ። የፓስተሩ የፈጣሪ መቅረብ እሳቤ ሳርን ለአንድ ቀን እንደ ስለት ጧፍ አብርቶ ለማምኖ መለያየትን ብቻ የሚያሳይ አይመስልም ። ምናልባትም ከጥቂት ወራቶች በኃላ ደፋር ነውና  « በግ » ስለሆናችሁ ቤዛነትንም እንለማመድ ብሎ ካራ ሊያስታጥቅ ይችላል ። ይህን የሚደግፍ አንቀጽ ደግሞ አያጣም ። ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 22 ፡ 1 – 2  እንዲህ ይላል « የምትወደውን አንድ ልጅህን ይስሀቅን ይዘህ ወደ ሞሪያም ምድር ሂድ ፣ እኔም በምነግረህ በአንድ ተራራ ላይ በዚያ መስዋዕት አድርገህ ሰዋው » ፓስተር ሌሶጎ እኔ የአብርሃም እናንተ ደግሞ የይስሀቅ ምሳሌ መሆናችሁን አትዘንጉ ካለ የህግ ተማሪዋን ጨምሮ ሌሎቹም ድጋፍ ከመስጠት ወደ ኃላ አይሉም ማለት ነው ።
የኬንያው ፓስተር ኖሂ « ሃይማኖታዊ » ግኝት ደግሞ የሴቶች አለባበስ ላይ ያተኮረ ነው ። ፓስተሩ አንድ ቀን በ « lord ‘s propeller redemption church » የሚታደሙ ሴቶች በሙሉ ፓንት ማድረግ የለባቸውም ሲል ትዕዛዝ ሰጠ ። ምክንያት ሲባል ቅዱስ መንፈስን ለማቅረብ ፣ በአጠቃላይ አምልኮ ከጭንቅላትና ከሰውነት ነጻ ሆኖ ማሰብን ስለሚፈልግ የውስጥ ቁምጣቸውን ቤት ትተው መምጣት ይኖርባቸዋል ።
የፓስተሩን ግኝት የመነሻና መድረሻ ክር ይዤ ለማገናኘት ሌት ተቀን ብማስን ውሉን ማግኘት አልቻልኩም ።
ምን ለማለት ፈልጎ ነው ?
ከምን አንጻር ተመልክቶት ይሆን ? መንፈስ ቅዱስ የህሊናችንን በር ሲያንኴኴ ቶሎ የማናዳምጠው ፓንት መጥፎ ጋርድ እየሆነ ነው ? የሚል አስመስሎበታል ። ይህ ቦታ ከነስሙ « ሃፍረተ » እንጂ « ቤተልሄም » ወይም « ጎለጎታ » አይደለም ።
ታዲያ እንዴት መረጠው ? በጣም የሚያስደንቀው ደግሞ የፓንት ማውለቁ ትዕዛዝ ወንዶችን የማይመለከት መሆኑ ነው ።
ለነገሩ የአሜሪካዊውን ፓስተር አለን ፓርከር ግኝት ብናዳምጥ የላይኛውን « እረ ይሻላል » ማለታችን ይጠበቃል ። በቨርጂኒያ የ « white tail chapel » መሪ የሆኑት ፓስተር ትዕዛዝ ደግሞ ጉባኤተኛው ስብሰባውን ራቁቱን ሆኖ እንዲከታተል መገፋፋት ነው ።
የጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ አምስት « ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ » ተፈጻሚ ይሆን ዘንድም ፓስተሩ ራቁታቸውን በመሆን ትምህርት ሰጥተዋል ። እረ ጥንዶችንም ለጋብቻ ራቁታቸውን  አማምለዋል ። ከተወለድን ከጥቂት ወራት በኃላ እረኞች ለክርስትናችን ውሃ ውስጥ ፣ እናቶች ለመጪው ህይወታችን ተድላ እንጀራ ላይ ሊያንከባልሉን እንደሚችሉ ነው መረጃው ያለን ። ይኀው ቃልኪዳንም የጸና ማህተም ይፈጥርልናል ብለን ነው ተስፋ የምናደርገው ። አድገን በውሃ የተረጨነውንም ሆነ እንጀራ ላይ « ግፍ » ሳይሆንብን የተንደባለልነውን ፎቶ ስንመለከት ያረካናል ። ራቁትነት የንጹህነት ፣ የፍጥረት መነሻነት ነው ብለን ልንወስደውም እንችላለን ። በትናንት ንጹህነትና በዛሬ ተጨባጭ ማንነታችን መሃል ያለውን አንድነትና ልዩነት ለማነጻጸርም ይረዳል ።
በጉርምስና እና በጉልምስና ወቅት ራቁታችንን የምንቀበለው ቃልኪዳን ልብስ ለብሰን ከምናደርገው ጋር በምን እንደሚለያይ ግልጽ አይደለም ። ተምሳሌትነቱም ስውር ወይም ድፍን ነው ። በራቁትነት ለመደናነቅ ከሆነ ባልና ሚስቱ በመኝታ ፣ በሻወር በወዘተ ግዜ የሚያገኙት ነው ። ይህን ለማድረግ ደግሞ አይተፋፈሩም ። ህግ የተላለፉት አዳምና ሄዋን የደረሰባቸውን የእፍረት መሸማቀቅ ይሄ ትውልድ ያካክሰዋል ነው የሚሉት - ፓስተሩ ? በጋብቻ ማግስት እየፈረሰ ያስቸገረውን ትዳር ለማጽናት ይሄኛውን ዘዴ እንሞክረው ነው የሚሉት - እረኛው ?
የኚህ ፓስተር ግኝት ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው ። የመጀመሪያው  ጉባኤተኛው ሁሉ ራቁቱን መማር ከቻለ ሁሉም የሰው ልጆች እኩል መሆናቸውን ያሳያል የሚል ነው ። ርግጥ ነው ሰዎች በሚለብሱት ፣ በሚያጌጡበትና በሚጠቀሙባቸው ዕለታዊ ቁሶች የኑሮ ደረጃቸው ሊገመት ይችላል ። ችግሩ ይኀው ጉዳይ የሰዎችን ውስጣዊ ማንነት ፣ ጥንካሬ ፣ ባህሪ ፣ አስተሳሰብ እና ፍልስፍና በፍጹም ሊያሳይ አለመቻሉን ፓስተሩ የተረዱ አለመምሰላቸው ነው ወይም ባላወቀ ተራምደው ማለፋቸውም ይሆናል ።
ሁለተኛው መነሻቸው ቤተክርስቲያን በምሳሌ ማስተማር ይኖርባታል ከሚል ሀሳብ ይመነጫል ። ክርስቶስ ሲወለድም ሲሰቀልም ራቁቱን ነበር ያሉት ፓስተሩ ፈጣሪ በዛ መልክ ካሳየን እኔ እንዴት ነው ስህተት የምሆነው በማለት ሲኤንኤንን ሞግተዋል ። በርግጥ እድሜ ለአዳምና ሄዋን እንጂ ዛሬ የሰው ዘር በሙሉ መላመላውን ነበር ታች ላይ የሚለው ። ሆኖም እንደ ፓስተር አለን በመምህርነቱ የሚታወቀው እየሱስ በገጠር ፣ በከተማ ፣ በመንደር ፣ በገበያ ስፍራና በመስበኪያ ቦታዎች ሁሉ እየተዘዋወረ ያስተማረው ራቁቱን ሆኖ አይደለም ።
ሌላው ችግር ራቁት ሆኖ ትምህርት መማርና ማስተማር ከባድ ፈተና ላይ በግድ የመውደቅ ያህል መቆጠሩ ነው ። አእምሮ ከምዕራፍና ቁጥሮች ይልቅ ቅርጽንና ከርቮችን ማጥናትና ማድነቅ ላይ ማተከሩ ሳይታለም የተፈታ ነው ። የአካል ንኪኪ ባይፈጠር እንኴ በሃሳብ መመኘትን ለማስቀረት ምን ዋስትና አለ ? እና ራቁትነት ከሌሎች ለመለየትና ጀብዱ ለመፍጠር ካልሆነ በስተቀር ዘለቄታዊ መፍትሄ ነው ብሎ መስበክ ወንዝ የሚያሻግር አይደለም ።
ናይጄሪያዊው ፓስተር ኬንዲ ቦሉዋጂ ያደረገው ምርምር ደግሞ ከፓንት ነጻ በሆነው የሴት ልጅ ብልት ላይ ነው ። ለምርምሩ የተጠቀመባቸው ቁሶች የተፈጨ ጨው ፣ መሃረብና ጸሎት / ድግምት / ናቸው ። የዚህ አይነቱ ፓሰተሮች የሚሰሩትን ውስብስብ ጥናት « pastorization » ብሎ መጥራት ሳይቻል አይቀርም ። ፓስቸራይዜሽን እና ፓስተራይዜሽን ይቀራረቡ እንጂ አይመሳሰሉም ። 
እንደሚታወቀው ፓስቸራይዜሽን ከፈረንሳዊው ቀማሚና ማይክሮ ባዮሎጂስት ሉዊስ ፓስተር ተግባር ጋር የተያያዘ ነው ። በክትባትና እርሾ ዙሪያ ትልቅ ስራ የፈጸመው ሉዊስ ወይን ፣ ቢራና ወትት እንዲቆመጥጥ በሚያደርገው ባክቴሪያ ላይም አንድ ግኝት አፍልቌል ። ባክቴሪያውን ለማጥፋት ፈሳሹን በጣም ማሞቅ ፣ ቀጥሎም በጣም ማቀዝቀዝ የሚለውን ሂደት ነበር ያበረከተው ። ይህም ሂደት « ፓስቸራይዜሽን » ለሚለው ሳይንሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ።
ፓስተር ኬንዲም እንግዳ በሆነ መንፈስ የሚሰቃዩ ሴቶች በተለይም አግብተው መውለድ ካልቻሉ ያለግዜያቸው እንደሚሞቱ አወቀ ወይም ተገለጠለት ። መንፈሱ ደግሞ ባል እንዳይገኝ ደንቃራ ይሆናል ። በዚህ ስሌት ተጎድታለች ብሎ ላሰባት አንዲት የ22 ዓመት ወጣት ሴት ጉዳዩን ያጫውታትና መፍትሄውም በእጄ ነው ይላታል ። < ከፈጣሪ በታች እናንተን ነው የምናምነው በእርሶ መጀን > ትላለች ልጅት በልቧ ። ወዲያው ፓስተሩ
 < ያዝ እጇን
  ዝጋ ደጇን >
የተባለውን ኢትዮጽያዊ ዘፈን ተተርጉሞ የሰማው ይመስል ወጣቷን አስገብቶ ክፍሉን ይጠረቅምና  ለምርምሩ ይዘጋጃል ። በገቢር አንድ ልብስዋን አውልቃ እርቃኗን ቁጭ እንድትል ተደረገች ። በገቢር ሁለት ጸሎት ይሁን ድግምት ለደቂቃዎች ማንበልበል ቀጠለ  ። በክፍል ሶስት በነጭ መሃረብ ጨው ካወጣ በኃላ ብልቷ ውስጥ እንድታስገባው ይነግራታል ። ያልተለመደ ነገር ነውና ይተናነቃታል ፣ የሷ ፈራ ተባ ማለት ሂደቱን ሊያጔትተው ስለሚችልና ተግባሩን ለማፋጠን ይቻል ዘንድ ጣቱን ብልቷ ውስጥ ይጨምራል ። በዚህ የሚያበቃ ግን አልሆነም ። ከግራ ወደ ቀኝ ፣ ከቀኝ ወደ ግራ ማማሰል ይጀምራል ። ምናልባት ይኀው ተግባር እንደ ሊዊስ ፓስተር ባክቴሪያ ፣ ክፉ መንፈሱንም ይገድለው ይሆን ? አነጋጋሪ ጉዳይ ነው ። ግራም ነፈሰ ቀኝ  ይህ ሂደት « pastorization » ለሚለው መንፈሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ብሎ መሳለቅ ይቻላል ። ዞሮ ዞሮ ፓስተር ኬንዲ ወደ ሌላ ምዕራፍ ከመሸጋገሩ በፊት በሩን ሲጠረቅም አይተው በተጠራጠሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋል ችሏል ።
አንዳንድ ፓስተሮችም ልክ እንደ እየሱስ ተዓምር መስራት እንችላለን በማለት አሳፋሪ ተግባር ከመስራት አይቆጠቡም ። በዚህ ረገድ ተጠቃሽ የሚሆነው ናይጄሪያዊው ፓስተር ፍራንክ ካቢሌ ነው ።
ራዕይ ስለታየኝ የተአምሩ ታዳሚ ሁኑ በማለት ደቀመዛምሩን ኮምቦ ሃይቅ ሰበሰበ ። ከዚያም ማቲዎስ ምዕራፍ 14ትን በመጠቃቀስ የሰው ልጅ በቂ እምነት ካለው እንደ እየሱስ በውሃ ላይ መራመድ እንደሚችል ማብራሪያ ሰጠ ። በተለምዶ ሃይቁን ለማቌረጥ የሃያ ደቂቃ የጀልባ ጉዞ ማድረግ አስፈላጊ ቢሆንም ፓስተሩ ርቀቱ አላሳሰበውም ።
መቼም በውሃ ላይ እንደባለሞተር ጀርባ እየነጠሩ መራመድ በእጅጉ አስደሳች ነገር መሆን አለበት ። ብዙዎቹ ቢሸበሩም አንዳንዶቹ መምህራቸው የውሃውን ጫፍ በጫማው ሶል እያነጠረ ብዙ ርቀት ሴሄድ ማለም ጀምረው ነበር ። ዞር እያለም እጁን ሲያውለበልብላቸው ለማጨብጨብ ፣ ለማፏጨትና እልልታቸውን ለማቅለጥ ተቁነጥነጥዋል ። ምናልባትም ጫፍ ደርሶ ከመጣ በኃላ ተሰብሳቢውን ለጉዞ ሲጋብዝ ፍርሃት በማየቱ « እናንተ እምነት የጎደላችሁ ስለምን ትጠራጠራላችሁ ? » እንደሚላቸውም ከማሰብ ወደ ኃላ አላሉም ።
እውነት ነው ፓሰተሩ ጉዞ ጀመረ ለማለት እንኴ ይከብዳል ። በሁለተኛው ርምጃ ሰውነቱ ሰመጠ - በፍጹም ወደ ደቀመዛምሩም አልተመለሰም ። ምዕመናኑ በድንጋጤ ተውጠው « RIP » ለማለት እንኴ አልታደሉም ነበር ። እኔ ግን አሁን ትዝ ያለኝ የእንግሊዛዊው ገጣሚ ዊሊያም ኮስሞ ሞንክሃውስ ግጥም ነበር ። ርዕሱ There was a young lady of niger ይሰኛል ። በአምስት ስንኞች ጣጣውን የጨረሰውን ግጥም እነሆ ብያለሁ
There was a young lady of niger
Who smiled as she rode on a tiger
They returned from the ride
With the lady inside ,
And the smile on the face of the tiger .
እውነት እረኞቹ ምን እየፈጸሙ ነው ? ወዴትስ እየተሄደ ነው ? ዮሀንስ ወንጌል 10 ፡ 11 ላይ እየሱስ መልካም እረኛ እኔ ነኝ ፣ መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል ይላል ። ይህ ምሳሌ በሌሎቹም ላይ እንዲጋባ ነበር የተፈለገው ። ግን የምናያቸውና የምንሰማቸው ነገሮች ተስፋ ከመስጠት ይልቅ የሚያስፈሩ እየሆኑ ነው ። ብዙ እረኞች ተኩላና ቀበሮ ለመሆን እየቸኮሉ ይመስላል ።

« መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት  ! » የሚለው ቃል የትኛው ትንቢት ላይ ነበር የሚገኘው ?

No comments:

Post a Comment