Saturday, July 7, 2012

‎እውነት ድንጋዩ ማነው ?‎


አመክንዮ ተኮር ዳሰሳ


‹‹ ድንጋይ ራስ ! ›› ያስባል ተብሎ ለሚታሰበው ፍጡር ክፉ ስድብ ነው ፡፡ ለነገሩ ህይወት ካላቸውም ሆነ ከሌላቸው መካከል የማያስቡ በርካታ ቢሆኑም የድንጋይ ክፉ ተምሳሌትነት ግራ ያጋባል፡፡ በግ ራስ ! … ዛፍ ራስ ! … ለምን አልተባለ ይሆን ? በድንጋዮች ወገን ሆነን ብናስብ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው የሚሆንብን ፡፡

ከድንጋይ ስር የማይለየው ሰው ድንጋይን ማንቋሸሹ ለድንጋዮች አይዋጥም፡፡ ድንጋይ በመሬት፣ በጨረቃ፣ በባህር፣ ሌላው ቢቀር በሰው ሆድ ዕቃ ውስጥ አለ፡፡ መኖሩ ብቻ ሳይሆን መገለጫው በርካታ ነው፡፡ ድንጋይ ! እያለ የሚያንቋሽሸው ዘመናዊው ሰው የድንጋይ ቤት ውስጥ ለመቀመጥ ዕድሜ ልኩን ይለፋል፡፡ የአንድ መኪና ድንጋይ ዋጋ ጣራ ነካ እያለ እዬዬውን ያቀልጠዋል፡፡ የከበረ ድንጋይ በመሻት እርስ በርሱ ይጨራረሳል፡፡ ካባ ውስጥ ወዛም ድንጋይ ለመፈለግ አካባቢውን በፈንጂ ያሸብራል፡፡ በኮብል ስቶን ስራ ሲሰማራ ድንጋይ ዳቦ ሆነ በማለት ይፈላሰፋል ፡፡ ለአጥር፣ ለመንገድ፣ ለመጸዳጃ ቤት ወዘተ ውበት መፍጠሪያ ያለ ድንጋይ አይታሰብም ፡፡ ሲሞት ድንጋይ መሃል መቀበሩ አላረካው ብሎት የድንጋይ ህንጻ ይገነባል፡፡ ድንጋዩም ላይ እነሆ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ ሲል በድንጋይ ፊውቸር ቴንስ ጥቅሶችን ይጠቃቅሳል ፡፡

ይህን ሁሉ ድርጊት አርቀው የሚያስቡ ድንጋዮች በሰው አላዋቂነት …. ትንሽ ዕውቀት አደገኛ ነው እያሉ ማሽሟጠጣቸው ይጠበቃል፡፡ በተለይ እሱ ራሱ አፈር ከሆነ በኃላ ወደ ድንጋይ የመለወጥ ዕድሉ የሰፋ መሆኑን አለመገንዘቡ ያበሽቃቸዋል፡፡ እናም የመሰዳደቢያ ፈሊጣቸው ሰው ነው፡፡ ‹‹ ሰው ራስ ! ››… የተባለ ድንጋይ ራሱን ከመፈረካከስ ወደ ኃላ እንደማይል አይታያችሁም ?

በርግጥ ለድንጋይ ክብር የነሳው ዘመናዊው ሰው እንጂ የጥንቱ አይደለም፡፡ የጥንቱማ ቤቱ፣ ጠመንጃው፣ ክብሪቱ፣ ምጣዱ፣ ወረቀቱ… ድንጋይ ነበር ፡፡ ለድንጋይ ክብር የማይፋቅ ተዓምራትን አበርክቷል፡፡ የግብጹ ፒራሚድ፣ የሮሙ ላተርንና የአክሱሙ ሀውልቶች ሌሎችም ዛሬም ድረስ የሰውና የድንጋይ ጥምረትን ያሳብቃሉ፡፡ ድንጋይ ራስ ! እያለ የሚሳደበው ዘመናዊው ሰው በጥንቶቹ ሰዋች ተአምር ዛሬም እየተደመመ ነው፡፡ ተዓምራቶቹን ፈልቅቆ መነሻቸውንና ውበታቸውን ለማወቅ ቢፍጨረጨርም እንቆቅልሹ ባሰበው መልኩ አልተፈታለትም፡፡ ታዲያ ሰው ድንጋይን በቅጡ ሳያውቅ እንዴት የስድብ መጠሪያ አደረገው ? እስኪ እስካሁን አጥንቶ ምላሽ ያላገኘባቸውን ጥቂት የድንጋይ ጉዳዮች እያነሳን እንጫወት፡፡

ኮስታሪካ

በ16ኛው መቶ ክ/ዘመን በደቡብ ምዕራብ ኮስታሪካ ልዩ ልዩ መጠን ያላቸው ድንጋዮች ነበሩ፡፡ ድንጋዮቹ ትሪያንግል፣ ሬክታንግልና ክብ ቅርጽ ያላቸው ነበሩ፡፡ አብዛኛዋቹ ድንጋዮች የተገኙት በድኩዊስ ወንዝ አካባቢ ሲሆን የተፈጠሩት በ400 CE እንደሚሆን አርኪዋሎጂስቶች ገምተዋል፡፡ ይሁን እንጂ የኮስታሪካ ሙዚየም እስካሁን በሀብትነት የመዘገባቸው 130 ያህሉን ነው፡፡ ሌሎችማ በዘመናዊው ሰው ግልብ ፍላጎት ተፈረካክሰዋል -  ድንጋዮቹ መሃል ጌጣጌጥ ይገኛል በሚል፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ለጌጥነት በመኖሪያ ቤት፣ በአትክልት ቦታዋችና በየቤተክርስትያናት ተበታትነዋል፡፡

የዛሬውን ሰው እያነጋገረ ያለው ጉዳይ ድንጋዮቹ እንዴት ተፈጠሩ ? የሚለው ነው ፡፡ የአንዱ ድንጋይ ክብደት 16 ቶን ሲደርስ ፍጹማዊ ክብነቱ ጂኦሜትሪን ያሳጣል፡፡ ያኔ ደግሞ ስርዓት ያለው የሂሳብ ትምህርት አይታሰብም፡፡ አንዳንድ ተመራማሪዋች ቀራጺዋች ለዝናና ለጌጥ የሰሯቸው ናቸው በማለት ገምተዋል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በወቅቱ የነበሩ ሰዋች በከፍተኛ ደረጃ የማቅለጥ ግንዛቤ ነበራቸው ? የሚል ጥያቄ ያስከትላል፡፡ ምናልባት ድንጋዩን በአሸዋና በቆዳ አቅልጠው በማለስለስ ከበረደ በኃላ ክብ ገጽታ ለፈጥር ይችላል ይላሉ፡፡ የግራናይቱ ድንጋይ ከዲኪዋስ ወንዝ 40 እና 50 ኪሎ ሜትር ርቆ በሚገኝ ተራራ ላይ እንደነበር ታውቋል፡፡ እና ቀራጮቹ ድንጋዩን ሰርተው እንዴት ወደሌላ ቦታ አዘዋወሯቸው ? የሚለውም ጥያቄ ምላሽ አላገኘም፡፡ ምክንያቱም አንዱ ድንጋ|ይ ከ16 ቶን በላይ ስለሚከብድና በወቅቱ ዘመናዊ በሆነ መንገድ መጠቀም ስለማይታሰብ ነው፡፡

ኢትዮጽያ

ከ7 እሰከ 9 የሚገመቱት የአክሱም ሀውልቶችም ከጥበባቸው በላይ ርዝመታቸውና ግዝፈታቸው እስካሁንም እያጠያየቀ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እንዴት ተጓጓዙ ? እንዴትና በየትኛው መሳሪያ ደጋፊነት እንዲቆሙ ተደረገ ? በአበሾች ወይስ በሌሎች ? ለሚሉት ጥያቄዋች የሚሰጠው ምላሽ ያው አንጀት የማያርስና የግምት ትራስን የተደገፈ ነው፡፡ የጢያ ትክል ድንጋይ በቅርስነት የተመዘገበ ሃብት ነው፡፡ አካባቢው የመቃብር ቦታ እንደነበር ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ በሀውልቱ ላይ የተቀረጹት ምስሎች ግን ያው በፈረደበት ግምት እየተመተሩ ነው፡፡ የሳርና የዘንባባ ምልክቶች ልምላሜና ሀብትን… በወንድ ብልት መሰል የተቀረጹት ሀውልቶች የጀግንነትና የዘር መራባትን ሊጠቁሙ ይችላሉ በሚል፡፡ 

ኔዘርላንድ

በደች ግዛት በሆነቸው ድሬንዝ በፐ ቅርጽ የተሰሩ ድንጋዮች በብዛት ይታያሉ - ዶሊሚን ይሏቸዋል፡፡ ድንጋዮቹ ቀብር አካባቢ የሚገኙ ሲሆን ቱሪስቶች በብዛት ይጎበኙዋቸዋል፡፡ 53 ዶሊሚን የተመዘገቡ ሲሆን 52ቱ በድሬንዝ ይገኛሉ፡፡ ትልቁ ድንጋይ 22 ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን የ47 ድንጋዮች ቅንጅት ነው፡፡ አንዱ ድንጋይ 3 ሜትር ቁመትና 20 ቶን ክብደት አለው፡፡ ይህ ሁሉ ሁኔታ እነዚህን ድንጋዮች ማን ሰራ ? መቼ ? ለምንና እንዴት ? የሚሉ ጥያቄዋችን ያጭራል፡፡ ሳይንቲስቶች ዶሊሚን የተገነቡት በበረዶ እየተንሸራተቱ ነው ብለው ያስባሉ - በበረዶ ዘመን፡፡ የሚገነቡትም ገበሬዋች ሲሆኑ የባህላቸው አካል ስለሆኑ ነው፡፡ ሌላው ወገን በእንጨት እየተንከባለለ እንደሚጓዝ ይናገራል፡፡ ነገር ግን የሞቱ ሰዋች ለምን በተለመደው መልኩ ሊቀበሩ አልተፈለገም የሚለውን ጥያቄ መመለስ አልተቻለም፡፡

ዘመናዊው ሰው ስለ ድንጋዮች በቂ መረጃ ባያገኝም የጥንቱ ሰው በተግባር ተኮር እንቅስቃሴ የተከበበ ይመስላል፡፡ ጥናት፣ ምርምር ፣ኮንፈረንስ በሚሉ መሰረተ ሃሳቦች ግዜውን ከመግደል ይልቅ ያሰበውን ለመስራት ይተጋል፡፡ የበጀት፣ የአቅም፣ የግዜ ፣ የተነሳሽነት ጥያቄዋችን አካብዶ ሳያነሳ ድርሻውን ተወጥቷል፡፡ በዚህ እውነታ ስር የፈበረካቸው ምርጥ ተግባራት ለዘመናዊው ሰው ፈተና ፈጥረዋል፡፡ ዳናውን ለማግኘት ሌት ተቀን ቢያጠና ተጨባጭ እውነት አልያዘም፡፡ ጠብ ያለው ውጤት የግምት መልሱ ብቻ ነው፡፡ ለዚህ ዓላማ… ለዚህ ጥቅም… ለዚህ ተልዕኮ በዚህ ዓይነት ሰዋች ተሰርተው ይሆናል ይለናል፡፡ ከዚሁ ጎን የጥንት ሰዋችን የአሰራርና የእምነት ፍልስፍና በእሱ መነጽር ብቻ እየተመለከተ ኃላቀርነታቸውን ይነግረናል፡፡ ስለ ድንጋይ ክብር ሳይገነዘብ ወይም ምኞቱን ከሟላ በኃላ እየረሳ ድንጋይ ራስ ! እያለ ይሳደባል፡፡ ይህ ደግሞ ድንጋይ ራስ ! የሚለው ስድብም ግምታዊ ሊሆን እንደሚችል ጠቋሚ ነው፡፡

ዘመናዊው ሰው ትልቁ ድንጋይ  ውስጥ ወርቅ ይገኛል እያለ መፈረካከሱ ግለኝነቱንና አላዋቂነቱን ያቃጥራል፡፡ የቱሪስት መስህብ እያለ ገንዘብ ይሰበስብባቸዋል፡፡ ለዚህ ሁሉ የሃብት፣ የሞራልና የታሪክ ፍላጎቶች መሰረቱ የጥንት ሰው ነው፡፡ የጥንት ሰው ደግሞ ለድንጋይ ታላቅ ክብር አለው፡፡ በዚህ እሳቤ ድንጋይ ራስ ! የሚል ስድብ አይጠቀምም፡፡ ይህን ሁሉ ሃሳብ / logic / ብናገጣጥመው አንድ ስዕል እናገኛለን፡፡ ሊሳደብ የሚችለው አፍ ያለው ሰው ወይስ አንደበቱ የማይታየው ድንጋይ ? የትኛውስ ነው ትክክል ?…. ድንጋይ ራስ ! የሚለው ሰው ወይስ ሰው ራስ ! የሚለው ድንጋይ ?….

No comments:

Post a Comment