Friday, October 19, 2012

‎ጥቂት የ ‹ A › መሪዎችና በርካታ የ ‹ A › በሽታ ‎



እገሌ የ ‹ A › ተማሪ ነው ከተባለ ቀለሜዋ መሆኑን እንረዳለን ፡፡ ፕሬዝዳንት እንቶኔ የ ‹ A › መሪ ናቸው ከተባለ ደስ የሚሉና የተባረኩ ናቸው ብሎ ማለፍ ያስቸግራል ፡፡  ‹ A › ማለት ምንድነው ?  የተከበረው ‹ A › እንዴት ይገኛል ?  የሚለውን ሀሳብ ማጦዝ ያስፈልጋልና፡፡


የ ‹ A › መሪነት በሽምደዳና በችከላ ብቻ አይገኝም ፡፡ አንድ የሀገር መሪ እዚህ ማዕቀፍ ውስጥ በክብር ሊቀመጥ የሚችለው ዴሞክራሲ የተባለውን መጠነ ሰፊ ባህር ዋኝቶ ባይጨርሰውም ውስጡ ምን እንዳለ ሲያውቅ ፣ የፕሬስ ነጻነት የተባለውን ጎምዛዛ ፣ አኞና ሆድ አጥጋቢ ማዕድ ቀምሶ ለብዙሃኑ ሲባርክ ፣ ሙስና በተባለው ‹ አሻፋጅ › ገላ ራሱም ሆነ ሌሎች ከመውደቃቸው በፊት ለሃጫቸውን እንዲቆጣጠሩ ሲሰራ ፣ የሰው ልማት የተባለውን መሰረታዊ የሰው ልጅ ፍላጎት ለሟሟላት ቀን ከሌሊት ሲተጋ ነው ፡፡


የተማሪነት ዘመናቸውን በቀለሜዋነት አሳልፈው የህዝብ አስተዳደሩ ግዜም በዚሁ ካባ ደምቀው የታዩ የአፍሪካ መሪዎች ካሉ እንደመታደል  ይቆጠራል ፡፡ አንዳንድ ጎበዝ ተማሪ የነበሩ የአፍሪካ መሪዎች ሲጎለምሱ ጎበዝ ገዳይና ጀግና ፈላጭ ቆራጭ ሆነዋል ፡፡ አንዳንዶች በትምህርት ብዙም ያልተጓዙ ቢሆንም ትንሽ ከራርመው ባለብዙ ዲግሪ መሆናቸውን ያስነግራሉ ፡፡ ብዙዎቹ አዋቂና ዘመናዊ እንዲባሉ ስለሚፈልጉ የቀለም ቦሃቃ ውስጥ ገብተው አያውቁም የሚለው ወሬ እንዲነገርባቸው አይፈልጉም ፡፡

ባለኝ የንባብ መረጃ መሰረት ስለ ትምህርቱ ሳይደባብቅ ለጋዜጠኞች በይፋ የተናገረው አረመኔው ኢዲያሚንን ዳዳ ነበር ፡፡
እንዲህም አለ ፡፡ ‹‹ እኔ ምንም ዓይነት የመደበኛ ትምህርት የለኝም ፡፡ ሌላው ቢቀር የነርስ ትምህርት ቤት ሰርተፍኬት የለኝም ፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ግዜ ፒኤችዲ ካለው በላይ ነው የማውቀው !! ›› መቼም ይህ ደፋር ሰው አነስተኛ የትምህርት ዝግጅቴ ለመሪነት አያበቃኝም የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ፈልጎ እንዳልተናገረ ግልጽ ነው ፡፡

ዞሮ ዞሮ የ ‹ A › መሪነት በሽምደዳ አይገኝም ። በባዮሎጂ ትምህርታችን መረጃ መሰረት
የቫይታሚን  B  እጥረት - ቤሪ ቤሪ
የቫይታሚን  C  እጥረት - አስኮርቢክ አሲድ
የቫይታሚን  D  እጥረት - ሪኬት

ከጉዳያችን ጋር ግንኙነት ያለው የቫይታሚን  A እጥረት - በደብዛዛ ብርሃን የማየት በሽታ / Night Blindness / ያስከትላሉ ፡፡
የአፍሪካ መሪዎች ባህርያት አመቱ በጨመረ ቁጥር የሚለያይ ነው ። ወደ ስልጣን ሊመጡ አካባቢና ስልጣንን እንደያዙ ተቆርቋሪነታቸው ፣ የበዛ አዳማጭነታቸውና የተንዠረገገው ቃልኪዳናቸው ብዙዎችን የሚያማልል ነው ፡፡ ምነው ይህን ሰው አባቴ ፣ አጎቴ ፣ ወንድሜ ፣ ውሽማዬ ባደረገው ባዩ ቀላል አይደለም ፡፡ የዚህ ሰው ተወዳጅ አበባ ግን ዕድሜውን ጨርሶ ሳይሆን በትዕቢትና ጥጋብ ከወዲሁ ይረግፋል ፡፡ ቀጥ ያለውና የተከበረውም ‹ A › በጉዳትና በመከራ እንደ ‹ C › እና ‹ D › መጣመም ይጀምራል ፡፡

የ2011 መረጃዎች እንደሚያስረዱት ከሆነ ከ 54 የአፍሪካ ሀገሮች የ A › ን ቦታ ያገኙት የቦትስዋናው / jeretse jan khama / ፣ የኬፕቨርዱ / Jorge carlos fonseca / ፣ የሞሪሽየስ / Navin Chandra Ragoolan / እና የጋና / John Evans Atta mills / መሪዎች ናቸው ፡፡ ተስፋ ከሚጣልባቸው የ ‹ B › መሪዎች ውስጥ ናሚቢያ፣ ደቡብ አፍሪካና ማሊን መጥቀስ ይቻላል ፡፡ ኬኒያ ፣ ታንዛኒያ ፣ ላይቤሪያና ዛምቢያ ለክፉ አይሰጥም በሚባለው የ ‹ C › ማዕቀፍ ውስጥ ናቸው ፡፡ ናይጄሪያ ፣ ሩዋንዳና ኒጀር ‹ D › ን ታቅፈዋል ፡፡ ኡጋንዳ ፣ ጊኒ ፣ ኮሞሮስ ባንዲራ የሚባለውን ‹ F › እያውለበለቡ ይገኛሉ ፡፡ ሊቢያ ፣ አልጄሪያ ፣ ካሜሮንና ኢትዮጽያ ለየት ያለ ስያሜ ተሰጥቷቸዋል ፡፡ ICU የሚል ፡፡ ይህን ምህጻረ ቃል ስናፍታታው Health Service Intensive Care Unit የሚል ሆኖ እናገኘዋለን ፡፡ ጥሬ ትርጉሙስ ከተባለ እዚህ ክፍል የሚመደብ በሽተኛ ፤ በሽታው ለህይወቱ በጣም አስጊ በመሆኑ በዘመናዊ የህክምና መሳሪያና ሙያተኞች ርዳታ መደገፍ እንደሚገባው እንረዳለን ፡፡ ይህን ርዳታ ባግባቡ ካላገኘ ግን መሞቱ ነው ፡፡ ኤርትራ ፣ ሱዳንና ዙምባብዌ ደግሞ < MORGUE > ተብለዋል ፡፡ የሞተ ሰው የሚቀመጥበት ክፍል መሆኑ ነው ፡፡ 

በሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽንና በምስራቅ አፍሪካ መጽሄት ዝግጅት ክፍል ይህን የመሰለ የአፍሪካ መሪዎች ስኮር ካርድ ማዘጋጀት ከተለመደ ሰነባብቷል ፡፡ 75.2 አስመዝግባ ‹ A › ባገኘቸው ቦትስዋናና 32.05 አግኝታ ICU በምትገኘው ኢትዮጽያ መካከል የ43 ነጥብ ልዩነት አለ ፡፡ የነጥቡን ስፋት ያንቦረቀቀው የዴሞክራሲ ፣ የፕሬስ ነጻነት ፣ የሙስናና የሰብዓዊ ልማት መሰረታዊ አጀንዳዎች ናቸው ፡፡ ርግጥ ነው የሞህ ኢብራሂም ኢንዴክስና የጋዜጠኞች ቡድን ነጥብ አሰጣጥ ስርዓትም ይካተታል ፡፡

አሜሪካ በአንድ ወቅት ተስፋ የሚጣልባቸው የአፍሪካ ዴሞክራት መሪዎች በሚል ስያሜ የሩዋንዳውን ፓውል ካጋሜ ፣ የኡጋንዳውን ዩዌሪ ሙሴቬኒ ፣ የኢትዮጽያዊውን መለስ ዜናዊ እንዲሁም ኤርትራዊውን ኢሳያስ አፈወርቂ የላቀ ዕውቅና እንዲያገኙ አድርጋ ነበር ፡፡ የነዚህ መሪዋች ስኮርድ ካርድ ግን ስያሜያቸውን መምሰል አልቻለም ፡፡ ካጋሜ 47.6 በማግኘት D ፣ ሙሴቬኒ 42.7 በማግኘት F ፣ መለስ 32.05 በማግኘት ICU ፣ ኢሳያስ 22.23 በማግኘት MORGUE ውስጥ ተመድበዋል ፡፡ አንዳቸው እንኳን የማለፊያውን ወገብ አለመንካታቸው በእጅጉ ያስገርማል ፤ ተግባራውም ሲታወቅ ያስደነግጣል ። 

ይህን የቤት ስራ በአግባቡ ለመከወን የ ‹ A › መሪዎችን ተሞክሮ መጠቀም ያስፈልጋል ፡፡ በነገራችን ላይ የ ሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን ዘንድሮን ብቁ መሪ አላገኘሁም በሚል ሂሳብ ይዝለለው እንጂ እስካሁን ለሶስት መሪዎች የ 5 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት በመስጠት ዕውቅና አጎናጽፏል ፡፡ 
መሪዎቹ ፣
የኬፕቨርዱ - ፔድሮ ቬሮና ፓይረስ
የቦትስዋናው - ፌስተስ ጎንተባይ
የሞዛምቢኩ - ጃኪም ቺሳኖ ናቸው ፡፡
ህገ መንግስትንና ህጎችን በተፈለገ ግዜ በልክ መቅደድና መስፋት በጣም የተለመደ ፣ ቀላልና የማያሳፍር ተግባር በሆነባት አፍሪካ እነዚህ መሪዎች ከሁለት ግዜ በላይ ሀገር አንመራም በማለት በፈቃዳቸው በመልቀቅና የተሻለ መልካም አስተዳደር በመፍጠር ይመሳሰላሉ ፡፡ ሞዴል መሪዎች የተባሉትም በነዚህና በመሳሰለው የላቀ የአመራር ጥበባቸው ነው ፡፡ እንግዲህ ይህን የመሰለ ቅዱስ ተግባር በአፍሪካ በተለይም በኢትዮጽያ እንዴት ይመጣል ? የሚለው ጥያቄ ነው የሚያስጨንቀው ፡፡ ምክንያቱም የነ ሙጋቤና ሙሴቬኒን መንገድ አጥብቀው የሚከተሉት አምባገነን የአፍሪካ መሪዎች የሚከተለውን ያልተበረዘና ያልተከለሰ ፖሊሲ እያቀነቀኑ ነውና

 ‹‹ እኛ መሪዎች ለህዝብ ጥቅም ሲባል በተወለድንበት አልጋ ላይ እስክንገነዝ ድረስ መቆየት እንፈልጋለን !! ››
ለማንኛውም  መሪዎቻችን ዳፍንት ገደልን መንገድ የሚያስመስል ክፉ በሽታ ስለሆነ ዘወትር በጠራ ሳሙና ፣ ውሃና ፎጣ ፊታቸውንና ጭንቅላታችሁን  ቢታጠቡ መልካም  ሳይሆን አይቀርም ፡፡ 

No comments:

Post a Comment