Sunday, July 28, 2013

‎የኃይሌ ገብረስላሴ መንገድ የት ያደርሳል ?‎



የአትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የህይወት ቅደም ተከተል ባልተጠበቀ መልኩ መጓዝ በመጀመሩ ይመስላል ሰሞኑን በህዝቡ ውስጥ ትልቅ የመወያያ አጀንዳ ሊሆን የበቃው ፡፡ ለመሆኑ የሚጠበቀው ቅደም ተከተል ምን ነበር ? የሚል መሰረታዊ ጥያቄ እንደሚነሳ እንጠብቅ ፡፡

በአሰላ አንድ ተራራማ መንደር የተወለደው ኃይሌ ወደ ት/ቤት ለመጓዝ ረጅም ርቀት መጓዝ ይጠበቅበት ነበር ፡፡ የህይወት አርጩሜ ዘወትር እንዲሮጥ ብታስገድደውም እሱ ባያውቀውም በጥንካሬ ለሌላ ዕድል እያዘጋጀችው ቆይታለች፡፡ እናም ፤
. በ15 ዓመቱ ውድድር ጀመረ ፡፡
. ከአራት ዓመት ቆይታ በኃላ ደቡብ ኮሪያ በተካሄደው ጁኒየር ሻምፒዮን በ 5 ሺህ እና 10 ሺህ ሜትር ሩጫ አሸነፈ ፡፡
. ከዛማ ምኑ ቅጡ ? ሁለት ግዜ በኦሎምፒክ ፣ አራት ግዜ በአለም ሻምፒዮንሺፕ ፣ ለአራት ተከታታይ ግዜ በበርሊን ማራቶን ማሸነፍ ችሏል ፡፡ አያሌ የብሄራዊና ዓለማቀፍ ውድድሮችን የሩጫ ሪከርድ ሰባብሯል ፡፡
. በውድድር መፈተን ብቻ ሳይሆን በዕድሜ መግፋት ሲጀምር ደረጃውን ቀየረ ፡፡ በ2006 ግማሽ ማራቶን አሸነፈ ፡፡
. በ 2007 አዲስ የማራቶን ሪከርድ ማስመዝገብ ችሏል ፡፡

በ 43 ዓመቱ በሞስኮ ኦሎምፒክ በማራቶን ለመሳተፍ ይፈልጋል ፡፡ ከወጪ ቀሪ ስናወራርድ ኃይሌ በ 28 ዓመታት ውስጥ በስፖርት መድረክ በተለይም በረጅም ርቀት ውስጥ ነግሶ ቆይቷል ፡፡ ከዚህ በኃላ ይህን የሩጫ ንጉስ አብዛኛው ህዝብ ይጠብቅ የነበረው / የንግድና ኢንቨስትመት ስራው እንደጠበቀ ሆኖ / በዚሁ መደዳ እንደሚገኝ ነበር ፡፡ ማለትም ፤

. በሩጫ አስልጣኝነት
. በአትሌትክስ አማካሪነት
. በስፖርት ጥናትና ምርምር
. እንደ አቶ ይድነቃቸው ተሰማ በአፍሪካ የስፖርት ተወካይነት
የሩጫው ንጉስ ግን ለ cctv ቴሌቪዥን እንዲህ አለ ‹‹ የአጭር ግዜ እቅዴ ለፓርላማ አባልነት መወዳደር ነው ፡፡ አንድ ቀን ደግሞ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት መሆን እፈልጋለሁ ››

የንጉሱ መሰረታዊ ምክንያት ?
 
አጃንስ ፕሬስ እንደዘገበው ኃይሌ ወደ ፖለቲካው መቀላቀል የሚፈልገው በፖለቲካው አማካኝነት ወደ ህብረተሰቡ ለመቅረብና ህብተረሰቡን ለመርዳት ነው ፡፡ ለፓርላማ የሚወዳደረው በግል ውክልና ነው ፡፡ ባለቤቱና ቤተሰቦቹ በኢትዮጽያ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፉን ባይወዱለትም እሱ ግን ራስን ከፖለቲካ ማራቅ ‹‹ ትልቅ ስህተት ›› ነው ባይ ነው ፡፡ ‹‹ እዚህ እስካለንና እዚህ እስከኖርን ድረስ በርካታ ችግሮቻችንን በመለየት በመፍትሄው ዙሪያ የራሳችንን ድርሻ መወጣት አለብን ›› በማለት ጽኑ እምነቱን ለማጠናከር ሞክሯል ፡፡

ውሃ የሚቋጥረው ምክንያት የማነው ?
 
ኃይሌ እንደ ሩጫው ሁሉ በተሰማራባቸው የንግድ መስኮች ውጤታማ ነው ፡፡ በሆቴል ፣ በመኪና ንግድ ፣ በህንጻ ኪራይ ፣ በሲኒማ ቤትና በታላቁ ሩጫ ዝግጅት  እያደረጋቸው ያሉት ዘርፈ ብዙ እንቅስቃሴዎችን መጠቃቀስ ይቻላል ፡፡ በቅርቡ በ 70 ሚሊየን ብር ካፒታል ወደ ቡና አምራችነት ጎራ የተቀላቀለ ሲሆን ማርን የመላክ ስራ ውስጥም ለመሳተፍ ዕቅድ እንዳለው ተመልክቷል ፡፡

የእነዚህ የተሳኩ ድምር ውጤቶች ግን በፖለቲካው መስክም ይደገማሉ ማለት ይከብዳል ፡፡ በርግጥ በኛ ሀገር ፖለቲከኛ ለመሆን የፖለቲካ ዲግሪ የግድ አለመሆኑ ያለፉት መንገዶቻችን ይጠቁማሉ ፡፡ አቶ መለስ ዜናዊም በአንድ ወቅት ለሹመት ከትምህርት ይልቅ ታማኝነት ሚዛን እንደሚደፋ አስረግጠው ተናግረዋል ፡፡ በርግጥ በእጅጉ የሚታወቀው ጆርጅ ዊሃ በርግጠኝነት አሸንፋለሁ በሚል ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውስጥ ገብቶ ያልተማረ አይመራንም … ዊሃን ያደነቅነው እግሩን እንጂ ጭንቅላቱን አይደለም በሚል የላይቤሪያ ህዝብ ካርዱን በሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ለተከታተሉትና በዓለም ባንክ ላገለገሉት ኤለን ጆንሰን ሰጥቷል ፡፡ ዊሀም ከዛ በኃላ ሚያሚ በሚገኘው ዴሪ ዩኒቨርስቲ የቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ትምህርት መከታተል ጀምሯል ተብሏል - ዛሬ ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ባይታወቅም ፡፡ እናም ለኃይሌ ስጋት የሚሆነው የትምህርት ዲግሪና / የክብር ያልሆነ / ፖለቲካዊ ዕውቀት አይሆንም ማለት ነው ፡፡ የሚከብደው ፖለቲካዊ  ተደራሽነቱን ለማረጋገጥ የመረጠበት መንገድ በእጅጉ አጠያያቂ ከመሆኑ ላይ ነው ፡፡

ኃይሌ በርካታ የመልካም አስተዳደር ህጸጾች ፣ የተንጠለጠሉ የዴሞክራሲ ጥያቄዎች ፣ የሰብዓዊ መብት ጉደለቶች ፣ የድህነት ማነቆዎች ያሉበት ህብረተሰብ ጋ ደርሶ መፍትሄ ለማምጣት የመረጠበት መንገድ የግል እንደራሴ በመሆን ነው ፡፡ በሀገራችን የፖለቲካ ታሪክ በግለሰብ ከተወከሉት ውስጥ ሻለቃ አድማሴ ዘለቀ ፣ አቶ በድሩ አደም እና ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንዲሁም የተቃዋሚው ብቸኛ ተወካይ አቶ ግርማ ስይፉ ትላልቅ ሀሳቦችን ሲያሰሙ ቢቆዩም ‹ አንድ እንጨት አይነድም › የሚለውን ብሂል እውነተኛነት ከማረጋገጥ ውጪ የፈጠሩት ነገር በጉልህ የተጻፈ አይደለም ፡፡ በርግጥ በደማቅ ሙሉ ቀለም በተቀባው ፓርላማ ውስጥ ሌላ ቀጭን ሰረዝ እንዲታይ መፍጠራቸው ለተቃራኒው ወገን ሊጠቅም ይችላል ፡፡

ችግሮችን በመጠቆም ለህብረተሰቡ የድልድይነት ፣ ለመንግስት ደግሞ የመስታውነት ሚና ይጫወታሉ ቢባል እንኳ መንግስት በግል ተወካዮች የቀረቡትንና የተጠኑትን ትላልቅ ሀሳቦችና ውጥኖች ዕውቅና በመስጠት አይደለም ለተግባራዊነቱ የሚንቀሳቀሰው ፡፡ ጉዳዩ ለድርጅቱ አንድ የድጋፍ ካፖርት የሚደርብ ከሆነ በድርጅቱ ልዩ ታፔላ ዳር እንዲደርስ ይደረጋል ፡፡ እናም የትኛውም ድርጅት ቢሆን መነሻ ሀሳቡና ግጥሙ ‹‹ የተከበሩ የም/ቤት አባል የአቶ እገሌ ነው … ›› ብሎ እንደ ነጠላ ሙዚቃ እንደለቀቀ ድምጻዊ እውቅና ለመስጠት አይጨናነቅም ፡፡ ካልፈለገም ገና ከመጀመሪያው እንዳልሰማ ሆኖ የማለፍ መብቱ የተጠበቀ ነው ፡፡ በዚህ የአጣብቂኝ አካሄድ የግል ተመራጭ ህብረተሰቡን ከመስማትና ከንፈሩን ከመምጠጥ ውጪ ምን የሚያመጣው ተጽዕኖ አለ ለሚለው ጥያቄ ደፋር ምላሽ ለማምጣት ይቸግራል ፡፡ ለዚህም ነው ይህ አይነቱ የፓርላማ ውክልና እና ተፈላጊው ራዕይ ምን ያህል ውሃ የሚቋጥር ነው የሚያሰኘውም ?

የኃይሌ ሌላኛው ራዕይ ‹‹ ፕሬዝዳንት ›› መሆን ነው ፡፡ ፕሬዝዳንት በመሆንስ ህብረተሰቡን ቀርቦ ካለበት ህመም መፈወስ ይቻላል ? ፕሬዝዳንቱ ዘወትር ሩህሩህና አዛኝ ድምጾች ቢኖራቸው በገዢው ፓርቲ ፖሊሲ ፣ ስትራቴጂና ይሁንታ ላይ ተጽዕኖ የመፍጠር አቅም አላቸው ? የእነዚህ ጥያቄዎች ትክክለኛ ምላሽ የሀገሪቱን የፖለቲካ ስርዓት በአግባቡ ከማወቅና ካለማወቅ የሚመነጭ ነው የሚሆነው ፡፡

የፕሬዝዳንትነት በትረ መኮንን

የኢፌዴሪ ህገመንግስት የሀገሪቱን ፕሬዝዳንት ‹‹ ርዕሰ ብሄር ›› ብሎ ቢጠራም ትልቁን ስልጣን የሰጠው ለጠ/ሚ/ሩ ነው ፡፡ ጠ/ሚ/ሩን የሚሰይመው ደግሞ አብላጫ የፓርላማ ወንበር ያለው የፖለቲካ ድርጅት ነው ፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 71 መሰረት ፕሬዝዳንቱ የተሰጡት ስራዎች ሰባት ናቸው ፡፡ ከነዚህም መካከል የሁለቱ ምክር ቤቶች ዓመታዊ ስብሰባን መክፈት … ያለቀላቸውን ህጎችና ስምምነቶችን በነጋሪት ጋዜጣ እንዲወጡ ማወጅ … በጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚቀርብለትን አምባሰደሮችና ሌሎች መልዕክተኞች ሹመት ማጽደቅ … እንግዶችን ቢሮ ቁጭ ብሎ መቀበል … ሜዳሊያና ሽልማት መስጠት እና ይቅርታ ማድረግ ይገኙበታል ፡፡

እነዚህን ስራዎች ጣጣው እንዳለቀለት የአምባሳደር ሙሉ ልብስ ወይም ተፈትፍቶ ጉርሻን በጉጉት እንደሚጠብቅ የአድአ እንጀራ ልትቆጥሩት ትችላላችሁ ፡፡ የመጀመሪያው መሰረታዊ ጉዳይ ፕሬዝዳንቱ በወሳኝ ሁነቶች ውስጥ ራሱን ሊያሳትፍና እኔም ነጥብ ሊያዝለት የሚገባ ልዩ ድምጽ አለኝ ለማለት የሚያስችለው መፈናፈኛ የሌለው መሆኑ ሲሆን ሁለተኛውና ዋነኛው ግን እነዚህንም በህግ የተቀመጡ ስራዎች ለመስራት የመረጠው ፓርቲ ይሁንታ ማስፈለጉ ነው ፡፡ በህገመንግስቱ ድንጋጌ መሰረት አንድ ሰው ፕሬዝዳንት ሆኖ የሚሾመው በሁለቱ ፓርላማዎች የጋራ ስብሰባ ሁለት ሶስተኛ እጅ ካገኘ ብቻ ነው ፡፡

አንድ በምርጫም በቁንጥጫም ስልጣን የጨበጠ ፓርቲ ደግሞ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት እንዲሆንለት የሚፈልገውን ግለሰብ የሚመርጠው የአይኑ ቀለም ስላማረው ወይም ታዋቂ ስለሆነ ብቻ አይደለም ፡፡ ፖሊሲውን የሚያስፈጽም ፣ ፓርቲውን የሚያሞግስ ያለፈውን ስርዓት በጥፊ የሚያቀምስ … በክፉ ቀን ዎሽቶም ቢሆን የሚደግፈው እንዲሆን ይፈልጋል ፡፡ ከዚህ ውጪ ትላልቅ ህጸጾችን ቢመለከት እንኳ በየሄደበትና በአጋጣሚው ሁሉ ‹ ዘራፍ ! አጉራ ጠናኝ - አሁንስ መንግስቱን መሰልከኝ ! › ምናምን የሚሉ ጉርምርምታዎቹን በደረቅ ውስኪ ተጉመጥሙጦ መዋጥ ይጠበቅበታል ፡፡ ወይም ዝቅ ባለ ድምጽ የችግሩን አሳሳቢነት በትህትና መጠቆም ይኖርበታል ፡፡ ልክ እንደ ቢሮክራቱ የቢሮ ደብዳቤ - ከሰላምታ ጋር ! መባሉንም ሳይዘነጋ፡፡ለነገሩ ፕሬዝዳንቱ በተቃራነው እየተንጋደደ የሜሄድ ከሆነ ፓርቲው ለምንስ በዕጩነት ያቀርበዋል ? አጉል ባህሪው እያደር የተገለጠም ከሆነ ጸጥ እንዲል የሚያስችሉ መፍትሄዎች 1001 ያህል ስለሆኑ ብዙም አያስጨንቅም ፡፡ ስለዚህ ለፓርቲው ታማኝነቱ ወይም በውስጠ ታዋቂነት ደጋፊነቱ የግድ ይመስላል ፡፡

እንግዲህ ፕሬዝዳንትነት የገባ የወጣውን ስቆ ከመቀበል ፣ ዋንጫ ከመስጠትና የተሰፋ የመክፈቻ ንግግር ከማድረግ ፣ ውጭ ሀገር ከመጎብኘትና ከምግባረ ሰናይ ድርጅቶች የክብር ኒሻን ከመጠበቅ ዉጪ ምን የተረፈ ውጤት አለው ? በርግጥ ኃይሌ ፕሬዝዳንት ከሆነ ሊሻሻሉ ወይም ሊለወጡ የሚችሉ ጥቃቅን አሰራሮች ይጠፋሉ ማለት አይደለም ፡፡

የ First Lady ጉዳይ አንዱ ይመስለኛል ፡፡ First Lady መባል ያለበት የፕሬዝዳንቱ ወይስ የጠቅላይ ሚንስትሩ ባለቤት ? ስልጣኑን ሁሉ ጠቅልሎ የያዘው የሀገራችን ጠ/ሚ/ር ይህንን የክብር ስያሜ ቢያንስ ሚስት ላለው ፕሬዝዳንት መልቀቅ ይኖርበታል ፡፡ በዶ/ር ነጋሶ ዘመን ሚስታቸው የውጭ ዜጋ በመሆኗ ፣ ፕሬዝዳንት ግርማ ደግሞ ሚስት የሌላቸው መሆኑ እንጂ ቦታው ተቀምቶ አይደለም የሚል ያልተረጋገጠ ሀሳብም ስላለ ይህንን ዕቅድ የተሳካ ማድረግ የሚቻል ይመስላል ፡፡ እና ሚስትንና ልጆችን ይዞ በየሀገሩ መዝናናት ፣ በተከበረ የራት ግብዣ ላይ መናገርና ከአቻ ጋር መፎጋገር ፣ በማርሽ ባንድ መታጀብ ፣ በክብር ዘብ መሃል መንጎማለል ፣ የክብር መድፍ ማስተኮስ … ግዴላችሁም እቺኛው ክፍል የምታስመረቅን ሳትሆን አትቀርም ፡፡ በአጠቃላይ ግን ፕሬዝዳንት በመሆን ትርጉም ያለው ለውጥ ሊፈጠር የሚችለው ለህብረተሰቡ ነው ወይስ ለራሱ ለፕሬዝዳንቱ ክብርና ዝና ? የሚል ጥያቄ ያስከትላል ፡፡

ስውር ተጽዕኖዎች
   
                                                  
ከሁሉ አስቀድሞ እያንዳንዱ ሰው በፈለገው መስክ የመሰማራትና ህልሙን የመፈለግ መብት ያለው በመሆኑ የኃይሌን የፖለቲካ ተሳትፎ ማንም መቃወም የማይችል መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል ፡፡ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነው እውነታ የኃይሌ የፖለቲካ ተሳትፎ ሳይሆን ያስቀመጣቸው ሀሳቦች ናቸው ፡፡ እንደራሴ ወይም ፕሬዝዳንት በመሆን ህብረተሰቡን ይበልጥ እጠቀማለሁ የሚሉት ፡፡ የሙግቱ ባቡሩም እንዴት ይቻላል ? በሚለው ሃዲድ ላይ የሚያተኩር ይሆናል ማለት ነው ፡

አሁን ባለው የፖለቲካ መዋቅር እንደሌሎች ሀገሮች በግል ተወዳድሮ ፕሬዝዳንት መሆን አይቻልም ፡፡ በጣም የሚከበርና የሚደመጥ ሴናተር ለመሆንም መንገድ የለም ፡፡ ይህ ቢቻል በርግጥም ታዋቂ ግለሰቦች ለውጥ ለመፍጠር ቅርብ ይሆኑ ነበር ፡፡ ኃይሌ እኛ በምንከተለው የፖለቲካ ስርዓት ፍላጎቱን ዕውን ለማድረግ የማይቻለው ከሆነ ቢያንስ በአንደኛው ውጤት ለመጽናናት የፈለገ ይመስላል ፡፡ ፕሬዝዳንት በመሆን ክብርና ዝና ለመጎናጸፍ ፡፡

ይህ ክብር ለአንዳንድ ታዊቂዎች ካላቸው ሀብት በላይ ነው ፡፡ ለምሳሌ ያህል የሰውነት ቅርጽ ተወዳዳሪና የፊልም አክተር የሆነው አርኖልድ ሸዋዚንገር የካሊፎርንያ ገዢ ሆኖ በየዓመቱ የተፈቀደለትን 175 ሺህ ዶላር አይቀበልም ነበር ፡፡ በሀብት ጫፍ የደረሱ አንዳንድ አትሌቶችና ስፖርተኞች ከሙያቸው ወደ ፖለቲካ ሲዞሩ ከፍተኛ ክብርና ርካታ አግኝተዋል ፡፡ ጋዜጠኛ ሲያረጅ ጸሀፊ ይሆናል እንዲሉ አትሌቶች ሩጫ በማቆሚያቸው ወቅትም ዝናቸው የሚቀጥልበትን ሰንሰለት ቢጠግኑ አይገርምም ፡፡

ለሁለት አስር ዓመታት አለማቀፍ የክሪኬት ተጫዋች ሆኖ ያገለገለው ፓኪስታናዊው ኢምራን ካህን ወደ መጨረሻው Movement For Justice የተባለ ድርጅት እስከማቋቋም ደርሶ ነበር ፡፡ በግንቦት 2013 ፓርቲው 35 መቀመጫ ሲያገኝ አንዱ ተመራጭ ሆኗል ፡፡ PEW የተባለ የምርምር ማዕከል በሰራው የ 2012 ጥናት ከአስር ፓኪስታናዊ ሰባቱ ለካህን ጥሩ አስተያየት አላቸው ፡፡

የእንግሊዙ መካከለኛ ርቀት ሯጭ ስባስቲያን ኮ አራት የኦሎምፒክ ሜዳሊያዎችን አሸንፏል ፡፡ በ1979 ሶስት የዓለም ሪኮርዶችን በ 41 ቀናት ልዩነት ውስጥ ማሻሻል ችሏል ፡፡ ኮ ራሱን ከሩጫው ዓለም ሲያገል ወግ አጥባቂውን ፓርቲ በመወከል ከ 1992 እስከ 1997 ድረስ የፓርላማ አባል ሆኖ አገልግሏል ፡፡ እንግሊዞች ይህን ድንቅ ሯጭ የህይወት ዘመን የም/ቤት አባል አድርገው ሾመዋል ፡፡ እንግሊዝ በ 2012 ለማግኘት የቋመጠችውን የኦሎምፒክ አዘጋጅነት ፉክክር በብቃት የመራ ሲሆን የኦሎምፒክ ጨዋታ ኮሚቴን እንዲመራም ኃላፊነቱን አግኝቶ ነበር ፡፡ የቢቢሲ ስፖርት ዝግጅትም በታህሳስ 2012 የዓመቱ ምርጥ ሰው በማለት ሸልሞታል ፡፡

ታዋቂው የብራዚል ተጫዋች ዚኮ በ 1990ዎቹ የስፖርት ሚንስትር እስከመሆን ደርሷል ፡፡ የቶተንሃም ተጫዋች ሮማን ፓብሊቼንኮ የፑቲንን ‹‹ United Russia  ›› ን በመወከል በ 2007 ተወዳድሮ ለከተማ ም/ቤትነት ተመርጧል ፡፡ በ 1995 የዓለማችን ምርጥ ተጫዎች የሚል ክብር ያገኘው ጆርጅ ዊሃ ለፕሬዝዳንትነት ተወዳድሮ ህልሙ በኤለን ጆንሰን ጨንግፏል ፡፡ ስለ አሉሚናቲ ማህበረሰብ በርካታ ሚስጥራዊ መጻህፍትን የደረሰው ዴቪድ አይክ ተስፋ የተጣለበት የኮቨንተሪ ሲቲ በረኛ ነበር ፡፡ 38ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጌራርልድ ፎርድ የሁለት ግዜ የአሜሪካ እግር ኳስ ሻምፒዮን ነበሩ ፡፡
ወደ ፖለቲካው ጎራ የተቀላቀሉ ሌሎች ታዋቂ አትሌቶችን መጠቃቀስ ይቻላል ፡፡ ምሩጽን አይቼ ነው ወደ ሩጫው የተገፋፋሁት የሚለው ኃይሌ አውቆም ሆኖ ሳያውቀው እነ ስባስቲያን ኮ ተጽዕኖ ቢያደርጉበት አይገርምም ፡፡

የድርጅት ጥላ
 
ከፓርላማ መራቅ ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› ነው የሚለው ኃይሌ ከግል ተወዳዳሪነት ዉጪ የድርጅት አባልነትን የማይታሰብ መሆኑን ተናግሯል ፡፡ ምናልባት እዚህ ላይ ራሱ የተናገረው ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› ለራሱም የሚሰራ መስሏል ፡፡
በሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ በግል መወዳደር የግል ታዋቂነትንና ዝናን ከመጨመር ዉጪ ፖለቲካዊ ፋይዳ እንደሌለው ከላይ አይተናል ፡፡ ኃይሌ በግሉ ከሚወዳደር ይልቅ እንደ ፓኪስታናዊው ኢምራን ካህን የራሱን ድርጅት ማቋቋም አሊያም ከገዢው ወይም ከተቃዋሚ ድርጅቶች ሰፈር ጎራ ቢል ይመረጣል ፡፡ እንደዚያ ሲሆን ነው የእውነት ህብረተሰቡን ሊቀርብና ለውጥ ሊያመጣለት የሚችለው ፡፡

ለምሳሌ ያህል ኢህአዴግ ውስጥ ታቀፈ እንበል ፡፡ የድርጅት ጥላ ካገኘ በጣም ቢያንስ ባካባተው ሰፊ ልምድ መሰረት አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ወይም ስፖርት ኮሚሽን ውስጥ በኃላፊነት ለመሾም ምቹ ሁኔታ ይፈጠራል ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ያደፈውን አሰራር ለማጥራት እንዲሁም በህልሙ የያዛቸውን አዳዲስ አሰራሮች እውን ለማድረግ ይመቻል ፡፡ ይህም ለውጥ ስለሚያስገኝ የስንት ዓመት የውጤት ጥማት ያለበትን ህብረተሰብ ታደገ ማለት ይሆናል ፡፡ ስለዚህ እውነተኛ ፖለቲከኛ ለመሆን ከቆረጠ አካሄዱ ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› እንዳይፈጥር መመርመር ይኖርበታል ፡፡

የትኛው መስመር ?

በርግጥ ኃይሌ የትኛውን መስመር ቢከተል ነው ህብረተሰቡን ይበልጥ መቅረብና መርዳት የሚችለው ?
. ኢንቨስትመንቱን በማስፋፋት
. የበጎ አድራጎት ስራን በማጠናከር
. ሙያዊ ልምዱን በመመንዘር
. የፕሬዝዳንትነት ካባን በመላበስ …  ????????


ማስታወሻ፡- ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ቅፅ 12 ቁጥር 157 ላይ የወጣ ፅሑፍ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡


Tuesday, July 16, 2013

ጥርስ የሚፍቁ መስሪያ ቤቶች



1 . ‹‹ እንደ ተቋም ጥፋት ስላጠፋን ይቅርታ እንጠይቃለን ›› የሚለው መግለጫ የሚጠበቅ ስለነበር የሚያስገርም አልሆነም ፡፡ አስገራሚ የሆነው የሚጠበቀው መፍትሄ ሊፈታ ያልቻለ እንቆቅልሽ መሆኑ ነው ፡፡ የተጎዳውን ህዝባዊ ስሜት ለመጠበቅ ከሞራልና ህግ አንጻርም ሊሰራበት ያልተቻለን ስልጣንን ለሚሰራ አካል ማስረከብ ግድ ነውና አመራሩ ለራሱ ቀይ ካርድ እንደሚያሳይ ተጠብቋል ፡፡
ግን አልሆነም ፡፡

‹‹ ሁለት ቢጫ ማየት በምንያህል ተሾመ ይብቃ ! ›› ሲል የአቋም መግለጫውን አሰማ ፡፡ ይህ መግለጫ ደረቅ አይሆን ዘንድም ጥቂት የእግር ኳሱና የአመራሩ አባላት በጥፋተኝነት ቅባት እንዲዋዙ ተደረገ ፡፡ የፌዴሬሽኑ አመራር አካላት በህዝብ ለቀረበላቸው የልቀቁ ጥያቄ ‹‹ በክረምት ቤት አይገኝም ! ›› በሚል ሰበብ ለራሳቸው የወራት እድሜን ጨምረዋል ፡፡ በውስጣቸው  ግን  ‹ ይህ ስልጣን በመልቀቅ ሀብታም የሆነው የአውሮፓ ፌዴሬሽን አይደለም ! › ማለታቸው ይገመታል ፡፡

መቼም ይህ ፌዴሬሽን እንደ ሁላችንም ጨዋታ ተመልካች እንጂ መንገድ አመላካች አልሆነም ፡፡ ምንም ስራ እንደሌለበት ፊውዳል ክቡር ትሪቡን ላይ ቁጭ ብሎ ጥርሱን እየፋቀ ይባስ ብሎ ግራና ቀኝ ሰው መኖሩን በመዘንጋት የቆሸሸ ምራቁን ጢቅጢቅ .. በማድረጉ ስንቱን የዋህ ህዝብ ለማዲያትና ለጨጓራ በሽታ ዳረገ ?

2 . አንድ ሰሞን ከነዳጅ መውጣትና መውረድ ጋር ተያይዞ የትራንስፖርት ታሪፍን ለህዝቡ ይገልጽ ነበር ፡፡ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን ድሃዋ አዲስ አበባ በሚያስገርም ሁኔታ ሀብታም ፎቆችን ሳይቀር ማፈራረስ ይዛለችእግረ ጠባቦቹም ሆኑ ሰፋፊዎቹ መንገዶቿ አዲሱን ሰርገኛ ለማስተናገድ በመፈራረስ ሽርጉድ አብዝተዋል ፡፡

ይህ ያልተጠበቀ ግርግር የአዲስ አበባ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮን ያደናገረው ይመስላል ፡፡ አምስትና አስር ሳንቲም መጨመር የሚቻለው በእኔ እውቅና ነው ይል የነበረው ይኀው ተቋም ዛሬ ታክሲዎች 1 . 35 መንገድን 2 . 70 2 .70 መንገድን 3 . 70 በገዛ ፍቃዳቸው ሲያስገቡ ስልጣኑን ማስጠበቅ አልቻለም ፡፡ ለአብነት ያህል ከጦር ኃይሎች /ፍርድ ቤት በልደታ አድርጎ ሜክሲኮ በመድረሱ ብቻ ዋጋው መቶ ፐርሰንት መድረሱ በእጅጉ የሚያስገርም ሆኗል ፡፡

በዚህ ሁሉ የህግ ጥሰትና ዘረፋ መካከል ቢሮው ጋቢ ደርቦ ቁጭ ብሏል ፡፡ ከሶማሌ ባስመጣው ረጅም መፋቂያ ጥርሱን ደጋግሞ እየፈተገ ከራሱ ጋር እሰጥ አገባ ይዟል  ‹‹ ምን ይደረግ ታዲያ ! የልማት ጉዳይ ነው ፡፡ መንገድ በሌለበትስ ታሪፍን እንዴት ከፍና ዝቅ ማድረግ እችላለሁ ? ››
ከደረበው ጋቢ ይሁን ከግድየለሽነቱ ከመብራት ኃይል ቀጥሎ የላቀ የቸልተኝነት ኃይል እያመነጨ ይገኛል ፡፡ ይኀው ቸልታው ግን  ‹ እንኳን እናቴ ሞታ ድሮም አልቅስ አልቅስ ይለኛልየሚለውን የከተማ ነዋሪ ለጉዳት እየዳረገው ነው ፡፡ አዲሱ ሰርገኛ የሚመጣው ከሁለትና ሶስት ዓመታት በኃላ በመሆኑ ይህ ቢሮም እስከዛ ድረስ የአፉን መደገፊያ ላይጥል ነው ማለት ነው :: እስከዛ ድረስ ለሚደርሰው ብዝበዛ ማን እንደሚጠየቅ ለጸረ ሙስና ወይም ለእንባ ጠባቂ ግልባጭ ማድረግ ሳያስፈልግ አይቀርም ፡፡

3 .ገንዘብ በመቆጠባችሁ ብቻ እሸልማለሁ ማለት ከጀመረ አመታት አሳለፈ ፡፡ ስልቱም የልማት አጋር ብቻ ሳይሆን የአዲስ አሰራር መንገድ መሆኑን
ነግሮናል ፡፡

ኬር ! ብለናል ፡፡

አዲስና ዘመናዊ መንገድ ብሎ ካስተዋወቀን አሰራር ውስጥ ኤቲኤም ይገኝበታል ፡፡ ይህ ካርድ የተሰጠን ግዜ ላላፊው አግዳሚው ብቻ ሳይሆን ለራሳችንም አስር ግዜ ከኪሳችን መዥለጥ እያደረግን አስኮምኩመነው ነበር ፡፡

መሰለፍ ድሮ ቀረ ብለናል ፡፡
ብር እንደ አበሻ ጎመን ከቅርባችን ሊቀነጠስ ነው ብለናል ፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህ ማሽኖች በአጭር ግዜ ውስጥ በበሽታ ማስነጠስ ጀመሩ ፡፡ ቀስ በቀስም የሚከበሩ ዋንጫዎች ሳይሆኑ ባዶ ቆርቆሮ መሆናቸውን አስመሰከሩ ፡፡ እንደ ወንድማቸው የመንገድ ስልክ የነሱንም ወገብ በፍልጥ የሚነርት በዛ ፡፡ የአራዳ ልጆች አናታቸውን ከፈት አድርገው ቆሻሻ ይጥሉበት ነበር ፡፡ ይህ ከመሆን ለጥቂት የተረፈው ቆርቆሮዎቹ የቆሙት ጥበቃ ያለበት አካባቢ መሆኑ ነው ፡፡ አልፎ አልፎ የሚሰሩት ደግሞ ሰው ብር በሚፈልግበት ቅዳሜና እሁድ ለጥቂቶች አገልግለው ጎተራቸው ባዶ መሆኑን ያውጃሉ ፡፡
የታመመውን ዘመናዊነት መታደግ የደከመው የኢትዮጽያ ንግድ ባንክ ነው እንግዲህ በአናቱ ላይ ስለ ቁጠባ ሳያሰልስ የሚጨቀጭቀን ፡፡ አንዳንዶች ዘወትር ለስራ የሚጠቀሙትን አንዳንዶች ወር ጠብቀው የሚያገኙትን ደመወዝ ለመቀበል ሲሄዱ ‹‹ እንኳን ደህና መጣችሁ ! ›› የሚለው ትሁት ቃል አይጠብቃቸውም ፡፡ ደንበኛን የማያስቀይመው ንግድ ባንክ ግን ተመሳሳይ ቃል አመንጭንቷል ፡፡

‹‹ ኮንኬሽን የለም ! ›› የሚል
‹‹ ዛሬም ?! ››
‹‹ ምን እናድርግ ? ቴሌ እኮ ነው ?! እጀ ሰባራ አደረገን ! ››
‹‹ ታዲያ ሌላ አማራጭ የለም ? ››
‹‹ ምን ይምጣ ? የለም ! ››
‹‹ ወይ ጌታዬ ምን ይሻል ይሆን ? ››
‹‹ ሌላ ቀን ብቅ ማለት ወይ እስኪመጣ መጠበቅ ነዋ ! ››
‹‹ መቼ ይመጣ ይሆን ? ››
‹‹ እንጃ ! ቴሌም አያውቀው ! ››

ስለ ዘመናዊነት የሚያወራው ባንክ ስራውን ከቴሌ ጋር በጋራ ተስማምቶና ተነጋግሮ እንደጀመረ ይገመታል ፡፡ ግን ጉልቤው በየቀኑ ሲቆነጥጠውና ሲያሸው ሊታገለው ሊቃወመው ሊገስጸው አልደፈረም ፡፡ ስለዚህ ብር አስቀማጩ ባንክ አስር አለቃ የአየሩ አክሮባቲክስ ቴሌ ኮሎኔል መሆናቸውን ለመገመት እንገደዳለን ፡፡ ጂኔራሎቹን ያው መገመት ይቻላል ፡፡
በዚህም ምክንያት አዳራሽ የሞሉት ባለከራባት ሰራተኞች ወንበር ላይ ተለጥጠው ጣራ የነካ ብር ተደግፈው ጥርሳቸውን መፋቅ ይጀምራሉ ፡፡ ትዕግስተኛው ህዝባችን ደግሞ ከመስታውቱ ጀርባ እጅብ ብሎ አፋፋቃቸውን በጥብቅ ይመለከታል ፡፡

‹‹ አለ መፋቂያ ! መፋቂያ  ! … የክትክታየቀረሮየዋንዛ
  የሚያሳምር  … የሚያወዛ ››

የሚል ድምጽ ስማ ስማ አለው ጆሮዬን ::