Monday, May 27, 2013

‹‹ ጉድ በል ቢሊየን ዶላር !! ››




አቶ መለስ ዜናዊ በፔሮል የሚከፈላቸው ብቸኛ የአለማችን መሪ መሆናቸውና ክፍያቸውም ከ 4 እስከ 6 ሺህ እንደማይበልጥ በባለቤታው በወ/ሮ አዜብ መስፍን ተነግሮን ነበር ፡፡

በዚሁ መሰረት የወ/ሮ አዜብ ጡረታ ቢያንስ በግማሽ ካነሰ በቀጣዩ ህይወታቸው ላይ እክል እንዳያጋጥም እየሰጋን ነበር ፡፡ ለነገሩ መንግስት ያደረጉትን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ግምት ውስጥ በማስገባት ሙሉ ደመወዛቸው ሳይሸራረፍ እንደሚሰጣቸው የብዙዎቻችን እምነት ነው ፡፡ ቀጣዩን ኑሮ ለመደጎም ከታሰበ ብዙ አማራጮችን መጠቀምም ይቻላል ፡፡ ለምሳሌ ያህል በተለያዩ ቦታዎች የቦርድ ሰብሳቢ ማድረግ ፣ ከቅርብ ሰዎችና ከልማታዊ ባለሀብቶች ሚኒ ቴሌ ቶን ማሰባሰብ ወዘተ ይቻላል ፡፡

በዚህ ስጋት ውስጥ እያለን The Richest የተባለ ዌብ ሳይት / www.the richest. org / የዓለማችን ሀብታም ጠ/ሚኒስትሮች በሚል ለእኛ አስገራሚ ለቤተሰቦቸቸው ደግሞ አስደሳች ዜና ለቀቀ ፡፡ አቶ መለስ ዜናዊን ከሀብታሞቹ ጎራ አሰልፏቸው የተጣራ 3 ቢሊየን ዶላር በዉጭ ሀገር እንዳላቸው ነገረን ፡፡

‹ ጉድ በል ጎንደር! ›  አለ የጎንደር ሰው የአማርኛ መምህር ከደቡብ ክልል መጥቶልሃል ሲባል ፡፡ እኛ ስንት እየተጨነቅን …  እረ ይህን ሁሉ ሃብት ከወዴት አመጡት ? አቶ መለስ ቀደም ሲል ደጋግመው ስለ ቁጠባ ባህል ጠቃሚነት ብዙ ይነግሩን የነበረው ከራሳው ተሞክሮ ተነስተው ነበር ማለት ነው ? ይህ ወሬ እውነት ከሆነ ‹‹ ጉድ በል የሀገሬ ፓርላማ  የድሮውን የሀገሪቷን ዓመታዊ በጀት አንድ ሰው ላይ ስታገኝ ! ›› መባሉ ነው ።

እኔማ ቢቸግረኝ … የገንዘባውን አመጣጥ ለማወቅ የማያልቅና የማይደረስበት የሂሳብ ስሌት ውስጥ ገባሁ ። እስኪ ሳይቆራረጥ 6 ሺ ብራቸውን በፔሮል ይወሰዱ እንበል ፡፡ ለ 21 ዓመታት በዚሁ ብር አገለገሉ እንበል ፡፡ በ21 ዓመታት ውስጥ 252 ወሮች አሉ፡፡ ለ ጠ/ሚ/ር ጻጉሜም ሊከፈለው ይችል ይሆን በሚል እሳቤ 21 ዓመቱን በ13 ወራት አባዛሁት - 273 ወራቶች መጡልኝ ፡፡ እነዚህን ወራቶች በ 6 ሺህ ደመወዝ አባዛዋቸው ፡፡ ቁልጭ ያለ 1 ሚሊየን 638 ሺህ የኢትዮጽያ ብር ሰጡኝ ፡፡ መቼም የሀገር መሪ ከፍተኛ ኃይልም ክብርም አለውና ለቤት ኪራይ ፣ ለምግብ ፣ ለትራንስፖርት፣ ለሻይ ቡና ፣ ለውስኪ ፣ ለልጆች የትምህርት ወጪ ፣ ለእሱና ለቤተሰቦቹ አልባሳት ፣ ደስ ላለው ቁሳቁስ ወዘተ እንደማይከፍል ገመትኩ ፡፡ ስለዚህ 6 ሺውን ብር ሳይሸራርፉ እንዳለ መቆጠብ ችለዋል  ፡፡ ብሩ ግን ሁለት ሚሊየን እንኳን መሙላት አልቻለም ፡፡

ታዲያ ከየት አመጡት ? ሌላ የገቢ ምንጭ ማፈላለግ ያዝኩ ፡፡ እ… አበል ተገኘ ፡፡ አበል ለአንዳንድ ኃላፊዎች ወር ማዳረሻ ሳይሆን ራሱን የቻለ ደመወዝ መሆኑ ትዝ አለኝ ፡፡ ስለዚህ አቶ መለስ ለሀገራዊ ጉዳይ በዓመት 12 / አይበዛም ? / ግዜ ወደ ዉጭ ቢመላለሱ በ21 ዓመታት ውስጥ 252 ግዜ ወጥተዋል ማለት ነው ፡፡ ለአንድ ግዜ ጉዞ በሀብታም ሀገር እይታ 3 ሺህ ዶላር ቢከፈላቸው ለ252 ግዜ 756 ሺህ ዶላር አግኝተዋል ፡፡ ይህን ዶላር ለመዘርዘር በአማካኝ በ 17 ብር ሳባዛው / ጥቁር ገበያን መቼም አይሞክሩትም በሚል ነው / 12 ሚሊየን 852 ሺህ ብር መቆጠብ ችለዋል ማለት ነው ፡፡ አሁን የብራቸው መጠን 14 ሚሊየን 490 ሺህ ደረሰ ፡፡ ቢሆንም ገና ብዙ ይቀራል ። እስካሁን እየቆጠቡ እንጂ ብር እያወጡ አለመሆኑንም ልብ በሉ ፡፡

ሌላ የገቢ ምንጭ ትዝ አለኝ ፡፡ የቦርድ ሰብሳቢ የሆኑ ባለስልጣናት ከደመወዛቸው በላይ ከፍተኛ ጥቅማጥቅም ያገኛሉ ይባላል ፡፡ አቶ መለስ ምንም እንኳ በስራ የተጨናነቁ መሪ ቢሆኑም ከእንቅልፋቸው ሰዓት ቀንሰው  40 የሚደርሱ  ቁልፍ መ/ቤቶችንና ድርጅቶችን በቦርድ ሰብሳቢነት ያገለግላሉ እንበል ፡፡ ከአንዱ መ/ቤት በዓመት 20 ሺህ ብር ብር ያገኛሉ ቢባል ከአርባው 8 መቶ ሺህ ብር አላቸው ማለት ነው ፡፡ ይህን ብር ላገለገሉበት 21 ዓመታት ስናባዛው 16 ሚሊየን 8 መቶ ሺህ ብር ይሆናል ፡፡ አሁን ደግሞ አጠቃላይ ገንዘባቸው 31 ሚሊየን 290 ሺህ ብር ደርሷል ፡፡

በተለያዩ ግዜያት ከሚያገኙት የእውቅና ክብር ጋር የ 100 ሚሊየን ብር ስጦታም አግኝተዋል ቢባል / የተወሰነ ብር ለሆነ ደርጅት የለገሱ ቢሆንም / የብሩ መጠን 131 ሚሊየን 290 ሺህ ብር ነው ፡፡ ሌላ ገንዘብ የሚያገኙበት ምን ምንጭ አለ ?

አንዳንድ መ/ቤቶች በተለይ አትራፊ ድርጅቶች ዓመቱ መጨረሻ ላይ ለሰራተኛ ቦነስ ይሰጣሉ ፡፡ ታዲያ አትራፊ ያልሆነው ቤ/መንግስት ለሚያፈሰው የቤቱ ጣሪያ እንኴን ማደሻ ጥሪት አልነበረውም ፡፡ ‹ ቦነስ በቤተመንግስት › እያልን ብናወራ አሪፍ የሲኒማ ርዕስ ካልሆነ በስተቀር እንዴት ይታመናል ?  ለነገሩ ስፖንሰር በመጠየቅም የአትራፊነት የበጀት ርዕስ መትከል ይቻላል ፡፡ በቃ ! እንዲህ ሊሆን ይችላል ብለን ኦዲታችንን እንቀጥል ፡፡ ቦነስ ያው ደመወዝን ስለሚያክል 273 ወራቶችን በ6 ሺህ ብር ማባዛት ይጠበቃል ፡፡ 1 ሚሊየን 638 ሺህ ብር መጣ ፡፡ አጠቃላይ ሃብታቸው ስንት ሆነ መሰላችሁ 132 ሚሊየን 928 ሺህ ብር ፡፡

ታዲያ The Richest የተባለው ዌብ ሳይት ምንድነው የሚነግረን ? የሳቸውን ገንዘብ በጣም አብዝተነው እንኴ በዶላር ቢታሰብ ከ 8 ሚሊየን አይዘልም ፡፡ አላቸው የሚለው ግን 3 በሊየን ዶላር ነው ፡፡ ወይ አቶ መለስ ጨዋ ናቸው እያልን እንደ አፍሪካ መሪዎ ድርሻውን ወስደዋል ማለት ነው ? አያደርጉትም  ይህን ሂሳብ ለማምጣት ርግጠኛ ነኝ 24 ሰዓት ብደምርና ባካፍል አላገኘውም ፡፡ ታዲያ ማነው የዋሸን ? ዌብ ሳይቱ ወይስ ወ/ሮ አዜብ ፡፡ በርግጥ በሁለቱም በኩል አነጋጋሪ ክፍተቶች አሉ ፡፡ ዌብ ሳይቱ መረጃውን ያገኘበት ምንጭ አልጠቀሰም  ፡፡ ወ/ሮ አዜብም ምንም እንደሌላቸው ሲነግሩን ግድ የለም እንመናው በማለት እንጂ ያጡ የነጡ ለመሆናቸው ምን መረጃ ያቀርባሉ ? ታዲያ የወሬው አመጣጥ የአቶ መለስን ስም ለማጥፋት ነው ወይስ እሳውንም  እንደሌሎ ባለስልጣናት በሙስና ተጠያቂ ለማድረግ ? ያም ሆነ ይህ ወደፊት የሚታይ ይሆናል ። 

ደግሞ እኮ አሳምሮ ነው ያስቀመጠው ፤

የተጣራ ገቢ - 3 ቢሊየን ዶላር
የሀብት ምንጭ - ፖለቲካ
የመለስ ዜናዊ ዕድሜ - 58
የመለስ ዜናዊ የትውልድ ቦታ - አድዋ
የጋብቻ ሁኔታ - ያገባ / አዜብ መስፍን/ ን ይላል ፡፡

‹‹ ጉድ በል ቢሊየን ዶላር !! ›› አለ የሀገሬ ሰው ፡፡

1 comment:

  1. Hey before you jump to right this crap please check your source credibility ? did you ever know this website before ? you don't ,just like you i was amazed , but checked who the website is ? it's not forbs right it's a n individual called sammy s , who created website and posted wrong informatio some of them are available on google,

    ReplyDelete