Thursday, November 22, 2012

የአምባገነኖች ቀልድ



ለተለያዩ ስራዎች የተለያዩ መረጃዎችን ሳገላብጥ ካሰባሰብኳቸው አምባገነናዊ ቀልዶች የተወሰኑትን እነሆ ብያለሁ ፡፡ ካዝናኗችሁ ዘና በሉባቸው ፡፡

ሂትለር በገነት

አዶልፍ ሂትለር  እንደሞተ ራሱን ከሲኦል በር ጋ አገኘው ፡፡ ሲያንኳኳ በሩን ከፍቶ የወጣው ሰይጣን ‹‹ ስምህ ማነው ? ›› ሲል ጠየቀው
‹‹ አዶልፍ ሂትለር ››
 ሰይጣን በጣም እየተገረመ  ‹‹ በምድር ላይ ምን እንደሰራህ አውቃለሁ ፤ ወደ ውስጥ እንዳላስገባህ ቦታ የለም ፡፡ በርግጥ ሲኦል ቢሆንም ለሁሉም ነገር ወሰን አለው፡፡ ለምን ወደ ገነት አትሄድም  ?››
‹‹ አላውቀውም ! ››
‹‹ ይህን መንገድ ተከተል ፡፡ በስተቀኝ በኩል ትልቅ በር ታገኛለህ ፡፡ አታጣውም ››
ሂትለር ባልጠበቀው ጥሩ እድል እየተደሰተ ወደ ገነት ተጓዘ ፡፡ በቀጣዩ ቀን የሲኦል በር ተንኳክቶ ሰይጣን በሩን ሲከፍት እየሱስን ቆሞ ተመለከተ
‹‹ እየሱስ ! እዚህ ምን ታደርጋለህ ?! ›› በግርምት ጠየቀው
‹‹ ከካምፕ ጠፍቼ ነው የመጣሁት ! አመጣጤም የፖለቲካ ጥገኝነት ለመጠየቅ ነው ›› ሲል እየሱስም መለሰ

የስታሊን ግርፍ

            ከጆርጂያ የመጡ የልዑካን ቡድን አባላት ለረጅም ሰዓታት ከስታሊን ጋር ስለ ልማትና እርዳታ ከተወያዩ በኃላ በሚደረግላቸው ትብብር  በመርካት ቢሮውን ለቀው ወጡ ፡፡ ስታሊን ሲጋራ የሚያጨስበትን ትቦ መሳይ ነገር በማጣቱ  ወዲያው አንድ ስራውን ጠንቅቆ የሚያውቅ ደህንነት  ሰው ጋ ደውሎ ሲጋራ ማጨሻውን ነጥቆ እንዲያመጣ ያዘዋል ፡፡ ነገር ግን  ከ30 ደቂቃ በኃላ ዕቃውን ጠረጼዛ ስር በማግኘቱ የላከው ሰው ጋ በመደወል ትዕዛዙን ትቶ እንዲመጣ ይነግረዋል ፡፡
‹‹ አዝናለሁ ጓድ ስታሊን ! ››
‹‹ምን ተፈጠረ ?! ››
‹‹ ከልዑካን ቡድኑ ግማሽ ያህሉ እኮ ዕቃውን መውሰዳቸውን አምነዋል ፡፡ የተቀሩት ደግሞ ጥያቄው  በሚከናወንበት ወቅት አልፈዋል ›› በማለት ምላሹን በስልክ አሰማ

የመሪዎች ፉክክር

           ንግስት ኤልሳቤጥ፣ ቢል ክሊንተንና ሮበርቱ ሙጋቤ እንደሞቱ ቀጥታ ወደ ሲኦል አመሩ ፡፡ ወዲያው ንግስት ኤልሳቤጥ ‹‹ እንግሊዝ በጣም ናፍቃኛለች፣ መደወል እፈልጋለሁ፡፡ ሁሉም ሰው ምን እያደረገ መሆኑን ማወቅ እፈልጋለሁ ›› በማለት ለ 5 ደቂቃ ያህል አወራች፡፡ ከዚያም ‹‹ ሰይጣን ስንት ነው የምከፍለው ? ›› ስትል ጠየቀች
‹‹ አምስት ሚሊዮን ዶላር ›› አላት ፡፡ ቼክ ጽፋ ሰጠቸውና ወደ ቦታዋ ተመለሰች፡፡ ክሊንተን በኤልሳቤጥ ተግባር በመቅናቱ ‹‹ እኔም ወደ አሜሪካ መደወል እፈልጋለሁ ›› አለ፡፡ ለሁለት ደቂቃም አውርቶ ሂሳብ ሲጠይቅ 10 ሚሊዮን ዶላር ተጠየቀ፡፡ እሱም ቼክ ጽፎ ሰጠ፡፡
ሮበርቱ ሙጋቤም ከማን አንሳለሁ በሚል ስሜት ተነሳስቶ ‹‹ እኔም ወደ ዙምባብዌ መደወል እፈልጋለሁ ፣ ከቤተሰቤና ሚንስትሮቼ ጋር ማውራት እፈልጋለሁ ›› አለ ፡፡ ሙጋቤ ወሬውን ማቋረጥ ባለመቻሉ ለ10 ሰዓታት ያህል አወራ፡፡ ኤልሳቤጥና ክሊንተን ከየት አባቱ አምጥቶ ሊከፍል ነው በማለት መጨረሻውን ለማየት ቋመጡ ፡፡ ሙጋቤ እንደጨረሰ ሂሳብ ሲጠይቅ
‹‹ አንድ ዶላር ! ›› ሲል ሰይጣን መለሰለት
‹‹ ሂሳብ አትችልም እንዴ ?  ይህን ሁሉ አውርቼ  አንድ ዶላር ትለኛለህ ?! ››
‹‹ ባክህ እችላለሁ ! ሂሳቡ ይሔው ስለሆነ ወዲህ በል ! ››
‹‹አዝናለሁ አትችልም ! ››
‹‹ ሰውዬ ምን ነካህ ! ከሲኦል ወደ ሲኦል  እኮ ነው የደወልከው ! ይህ ደግሞ የሀገር ውስጥ ጥሪ ነው ! ›› ሲል አምባረቀበት

የቴይለር ርህራሄ

ቻርልስ ቴይለር እና ሾፌራቸው በመኪና ወደ ዋና መንገድ ሲያመሩ አንድ አሳማ ገጩ ፡፡ አሳውም ወዲያው ሞተ ፡፡ ቴይለርም ለሾፌራቸው ‹‹ እዛ ወዲያ ወዳለው የእርሻ ቦታ ሂድና አሳማው ምን እንዳጋጠመው አስረዳ›› አሉት
ከአንድ ሰዓት በኃላ ሾፌራቸው ከእርሻው ቦታ ከሴቶች ጋር ሲመለስ ተመለከቱ ፡፡ በአንድ እጁ የወይን ጠርሙስ ፣ በሌላ እጁ ሲጋራ ጨብጧል
‹‹ ምን ሆንክ አንተ ;! ››
‹‹ ገበሬው ጠርሙስ ወይን፣ ሚስቱን፣ ሲጋራና ከእኔ ጋር ፍቅር የያዛትን የ 19 ዓመት ልጁን ሰጠኝ ››
‹‹ እንዴት ? ምን ብለህ ነግረሃቸው ነው ? ›› ቴይለር አፈጠጡ
‹‹ እንደምን አመሻቸሁ ! እኔ የቴይለር ሾፌር ነኝ ፣ እናም አንድ አሳማ ገድያለሁ ! ››

የፑቲን ስጋ

የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን መጥፎ ህልም በሌሊት ቀሰቀሳቸውና እየተጨናበሱ ወደ ፍሪጅ አመሩ፡፡ ልክ ፍሪጁን እንደከፈቱ በመልክ በመልክ ተደርድረው የተቀመጡ ስጋዎች መንቀጥቀጥ ጀመሩ፡፡ በድርጊታቸው በመናደዳቸውም እንደሚከተለው ገሰጽዋቸው
‹‹ አትንቦቅቦቁ !! እኔ የመጣሁት ቢራ ለመጠጣት ብቻ ነው !! ››


የመለስ የጾታ ፍቃድ

አንድ ዝነኛ አርቲስት ክስ ተመስርቶበት ከታሰረ ትንሽ ቆየት ብሎ ነበር ። በዚህን ወቅት አንድ ታዋቂ አትሌት በውጭ ሀገር አስደናቂ ድል ተቀዳጅቶ ወደ አገሩ ሲገባ ጠ/ሚኒስትር መለስ አድናቆታቸውን ለመግለጽ ኤርፖርት ድረስ ሄደው ይቀበሉታል ። አትሌቱም አጋጣሚውን በመጠቀም አንድ አንገብጋቢ ጥያቄ እንዳለው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ይናገራል ።
« ምን ችግር አለ ጠይቃ » አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቀለል አድርገው
« ቴዲ አፍሮ የተባለው አርቲስት ካልተፈታ በመጣሁበት አውሮፕላን እመለሳለሁ »
« ወዴት ? »
« ወደ ሌላ ሀገር ፣ ጥያቄዬ ምላሽ ካላገኘ ዜግነቴንም ለመቀየር እገደዳለሁ »
« ወንድም ፣ እንኴን ዜግነትህንም ጾታህንም መቀየር ትችላለህ » አሉት ቆምጨጭ ብለው

የሙሻራፍ ፈተና

ፔርፔዝ ሙሻራፍ ወደ ደልሂ ለስብሰባ ሲያመራ ከህንዱ ጠቅላይ ሚንስትር ቫጅፔይ ጋር አጭር ቆይታ አደረገ ፡፡ ቫጅፔይ ‹‹ ስለ ካቢኔ አባላትህ እውቀት ምን እንደምታስብ አላውቅም፡፡ የኔ ሰዎች ግን በእጅጉ ጎበዞች ናቸው ›› ይለዋል
‹‹ እንዴት አወቅክ ? ›› ሙሻራፍ ይጠይቃል
‹‹ ቀላል ነው፡፡ ሁሉም ሚንስትር ከመሆናቸው በፊት ልዩ ፈተናዎችን ይወሰዳሉ ፡፡ ቆይ አንድ ግዜ ›› ይልና አድቫኒ የተባለውን ሚኒስትር ጠርቶ ይጠይቀዋል
‹‹  ያንተ ወንድም አይደለም፣ ያንተ እህት አይደለችም ፣ የአባትህ ልጅና  የእናትህ ልጅ ማነው ? ››
‹‹ ይህማ ቀላል ነው፡፡ እኔ ነኛ ! ›› ሲል አድቫኒ ይመልሳል
‹‹ ጎበዝ አድቫኒ ! ›› ቫደፓዬና ሙሻራፍ ተገረሙ
ሙሻራፍ ወደ ኢስላማባድ ሲመለስ ስለ ሚንስትሮቹ አዋቂነት በጣም እየተገረመ ነበር ፡፡ በመጀመሪያ ስብሰባውም በጣም የሚወደውን የካቢኔ አባል ጠርቶ ‹‹ የአባትህ ልጅና የእናትህ ልጅ ማነው ? ያንተ ወንድም አይደለም ፣ ያንተ እህት አይደለችም.፣ እሱ ማነው ? ›› ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ሰውየው ቢያስብ መልሱ ለመጣለት አልቻለም፡፡
‹‹ ትንሽ አስቤ ነገ መልሱን ባመጣስ ? ›› ሲል ያስፈቅዳል
‹‹ እንዴታ ! 24 የማሰቢያ ሰዓታት ተሰጥቶሃል ! ›› ሙሻራፍ መለሰ
ባለስልጣኑ ሚኒስትሮች፣ የካቢኔ ጸሃፊዎችና ትላልቅ ሰዎች ጋ እየደወለ ቢጠይቅ መልሱን ማግኘት አልቻለም ፡፡ ባለቀ ሰዓት ቤናዚር ቡቶ ብልህ ስለሆነች ታውቃለች በሚል ስልኩን መታና ‹‹ የአባትሽና የእናትሽ ልጅ የሆነ፤ ወንድምሽና እህትሽ ያልሆነ ማነው ?›› ሲል ጠየቃት
‹‹ በጣም ቀላል እኮ ነው ፡፡ እኔ ነኛ !! ›› ስትል መለሰችለት ፡፡ የካቢኔው አባል ደስ ብሎት ወደ ሙሻራፍ ደወለ ፡፡
‹‹ ጌታዬ መልሱን አግኝቼዋለሁ ፤ ቤናዘር ቡቶ ናት ›› አለ
‹‹ አንተ ደደብ ! አይደለም ›› አሉ ሙሻራፍ በቁጣ ‹‹ መልሱ አድቫኒ ነው !! ››
አይ ሙሻራፍ ???

የአህመዲንጃድ ቆምጫጫ ምላሽ

የኢራኑ ፕሬዝዳንት መሀመድ አህመዲንጃድ በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ተጋብዘው ስለ ሀገራቸው ወቅታዊ ሁኔታ ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ከንግግራቸው በኃላ የተለያዩ ጥያቄዎችን ማስተናገድ ጀመሩ ፡፡
‹‹ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ ችግር እንዳለባችሁ ምእራባዊያን ይናገራሉ፡፡ እውነት ነው ; ››
‹‹ ወረኛ በላቸው ! ዛሬ የተሻለ መብትም ሆነ ዴሞክራሲ ያለው ኢራን ውስጥ ነው ››
‹‹ እሺ እዛጋ ጆሮህን እንደ ሴት የተበሳሐው ! ›› ፕሬዝዳንቱ ለሌላ ጠያቂ ዕድል ሰጡ
‹‹ አመሰግናለሁ ፡፡ በሀገራችሁ ምን ያህል ግብረ ሶዶማዊያን ይገኛሉ ; ››
‹‹ በታላቋ አራን ይህን የሚፈጽሙ ሰዎች የሉም ! ››
‹‹ መረጃዎች የሚጠቁሙት ግን በግብረሶዶማዊያን ላይ ኢ- ሰብዓዊ ድርጊት እንደምትፈጽሙ ነው ›› ሌላ ጠያቂ
‹‹ ወንድሜ ጥያቄ መደጋገም ለምን ያስፈልጋል! በሀገራችን የሉም አልኩህ እኮ ! ምክንያቱም ሁሉንም ጨርሰናቸዋል ! ››

የአሳድ ትዕዛዝ

በሀገሪቱ ከተደረገ አጠቃላይ ምርጫ በኃላ አንድ ሚንስትር እየተቻኮለ ወደ ሶርያው ፕሬዝዳንት ሃፌስ አሳድ ቢሮ ይገባል
‹‹ እሺ ! ›› አለ አሳድ ካቀረቀረበት ቀና ሳይል
‹‹ የተከበሩ ፕሬዝዳንት! እጅግ በጣም ደስ የሚል ዜና ይዤ መጥቻለሁ ፡፡ በምርጫው 98.6 ከመቶ አሸንፈዋል፡፡ እርስዎን ያልመረጡት ከ 2 በመቶ በታች የሚያንሱ ሰዎች ናቸው ፤ ከዚህ በላይ ምንም የሚፈልጉ አይመስለኝም ጌታዬ ;! ››
‹‹ እፈልጋለሁ ! እፈልጋለሁ እንጂ አንተ !! ›› አለ አሳድ ካቀረቀረበት ቀና ብሎ እያፈጠጠ ‹‹ በአስቸኳይ ያልመረጡኝን ሰዎች ስም ዝርዝር ለቅመህ አምጣ !!! ››

የማኦ ፈስ

አንድ ቀን የቻይናው ሊቀ መንበር ማኦ የግል ሀኪማቸውን ዶ/ር ዣንግን ጠርተው የሚከተለውን አዘዙት
‹‹ ሆዴን በሚገባ መርምር! ካለፉት ጥቂት ሳምንታት ጀምሮ በጣም እንግዳ ነገር እየገጠመኝ ነው ፡፡ በተደጋጋሚ ያስፈሳኛል ፤ ማለትም በየአምስት ደቂቃው ልዩነት… ይህ ከይሲ ነገር ሊቆም አልቻለም፡፡ እንግዳው ነገር ደግሞ ፈሱ ድምጽ የሌለው እንዲሁም ሽታው የማይታወቅ መሆኑ ነው ››
ማኦ ንግግራቸውን ከጨረሱም በኃላ ፈሱ ፡፡ ዶ/ር ዣንግን ከመድሃኒት ማስቀመጫ ሳጥናቸው ውስጥ የሆነች ጠርሙስ አወጡና
‹‹ ሊቀመንበር ማኦ ይህን መድሃኒት ለአምስት ቀናት በየአራት ሰዓቱ ልዩነት አንድ- አንድ በመውሰድ ተጠቀሙ ›› ብሎ ተሰናብቶ ወጣ
ከአምስት ቀናት በኃላ ማኦ ዶክተሩን አስጠርተው ይጮሁበት ጀመር ፡፡
‹‹አንተ የተረገምክ !! ምን ዓይነት መድሃኒት ነው የሰጠኀኝ ? አሁን ደግሞ በጣም ነው የባሰብኝ ፡፡ ትናንት በወጣቶች ስብሰባ ላይ ንግግር ሳደርግ ያለማቋረጥ እየፈሳሁ ነበር ፡፡ ድምጹ በጣም የሚጮህ ስለነበር አሳፍሮኛል ! ››
‹‹ ሊቀመንበር ማኦ አሁን የመስማትዎ ችግር ተቀረፈ ማለት ነው ›› አለ ዶክተሩ ኮስተር ብሎ ‹‹ አሁን የሚቀረኝ እንደምንም ብዬ የአፍንጫዎን ችግር ማስተካከል ይሆናል !! ››

Monday, November 12, 2012

የላቀ ክብር - ለሚገባው መሪ



ደቡብ አፍሪካዊያን የቀድሞ ጀግና መሪያቸውን አልፎ አልፎ ብቻ በሚፈጠሩ አጋጣሚዎች ማስታወስ አላረካቸውም ፡፡ በርግጥ በርካታ ኀውልቶችን ቀርጸውላቸዋል ፣ የመናፈሻ ቦታዎችን ገንብተውላቸዋል ፣ ሌላም ሌላ ፡፡ ይህም ለዓለም ምርጡ ሰው በቂ አይደለም ፡፡ ምግባሩ እንደ ኤቨረስት ተራራ የገዘፈ ሰው ሁሌም የስስትና የአድናቆት አይን ሊርቀው አይገባምና እንደ ሌሎች ሀገሮች በቁልፍ ማንጠልጠያ ወይም በፖስት ካርድ ላይ ማስተዋወቅም ከሰሞነኛ ጉዳይነት የሚራመድ አልመሰላቸውም ፡፡

በጥልቀት አሰቡበት ፡፡
አንድ ሁነኛ ዘዴም አገኙ ፡፡

ዓለም የሚወደውን መሪ ዘወትር እየተመለከተ ማድነቅ የሚገባው በቅርበት ኪሱ ውስጥ ሲያገኛቸው ነው ፡፡ እናም የሀገራቸውን የብር ኖት / rand / መቀየር ወደዱ ፡፡ አዲሶቹ የብር ኖቶች ባለ 10፣ 20፣ 50፣ 100 እና 200 ራንዶች ሲሆኑ በሁሉም የመጀመሪያ ገጽ ላይ የታላቁ መሪ የኔልሰን ማንዴላ የፊት ገጽታ እንዲታይ ተደረገ ፡፡ ደቡብ አፍሪካዊያን ብልሆች ናቸውና ትልቅ ገቢ ከሚያስገኙበት ዘርፍ አንደኛ የሆነውን ቱሪዝም ይበልጥ ለማስተዋወቅ በገንዘቡ የኃላ ገጽ ላይ ትላልቆቹ አምስቶች / Big Fives / የሚሏቸውን የዱር እንስሳት ማለትም አንበሳ፣ ነብር፣ አውራሪስ፣ ጎሽ እና ዝሆንን አተሙበት ፡፡ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ እንዲሉ ፡፡

የሀገር መሪን በገንዘብ ላይ ማተም ለዓለማችን አዲስ አይደለም የሚል አስተሳሰብ ሊነሳ እንደሚችል አስባለሁ ፡፡ በርግጥ ሀሳቡ የሸመገለ ነው ፡፡ የማያረጀው ጥያቄ የማስተዋወቁ ሂደት ወይም የተሰጠው ዕውቅና የተከናወነው በዲሞክራት መንገድ ወይስ በኩዴታ የሚለው ይሆናል ፡፡ ሁሉንም መመዘዎች ብንጨፈልቅ ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮችን እናገኛለን ፡፡

አንደኛው አምባገነን መሪዎች የራሳቸውን ግለሰባዊ አምልኮ / Personality Cult / ለመገንባትና ህዝቡን ጸጥ ለጥ አድርገው ለመግዛት በማቀድ ወይ በራሳቸው ሙሉ ፍቃድ አሊያም በከበቧቸው ጥቅም ፈላጊዎችና ሆዳም ካድሬዎችና አጫፋሪዎች ጎትጓችነት የሚከናወን ነው ፡፡ ሁለተኛው ለሀገራቸው ነጻነት፣ ልማት፣ ዴሞክራሲና ፍትህ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት አምጥተው እውነተኛው ህዝብ / fake ያልሆነው / መሪውን ለማክበርና ለማስታወስ ሲል ያመነጨው መንገድ ነው ፡፡

እንግዲህ በብር ላይ የምናየው የፊት ገጽታ የሚፈጠረው በዚህ መሰል አግባብ ነው ፡፡ በጣም የሚገርመው ግን በሀገራቸው ገንዘብ ላይ ከወጡ መሪዎች 90 ከመቶው ያህል አምባገነኖችና የማይገባቸው መሆኑ ነው ፡፡ አንድ ከሩቅ አንድ ከቅርብ ላንሳ ፡፡

የሩቁ ፤

በርማን ከ1962 እስከ 1981 የገዟት ኒ ሊዊን በገዳይነታቸውና በአምባገነንነታቸው ይታወቃሉ ፡፡ በአንድ ወቅት ብድግ ብለው የሀገራቸውን ገንዘብ ባለ 15፣ 35፣ 45፣ 75 እና 90 ኖቶች በማድረግ ከምስላቸው ጋር አተሙት፡፡ ዓለም እንዲህ ለየት ያለ ባለ ጎዶሎ የብር ቁጥሮች ስለማትታወቅ የተለየ አትኩሮት መፍጠር መፈለጋቸው አንድ ጉዳይ ነበር ፡፡ ዋናው ጉዳይ ግን ባለ ‹‹ 90 ›› ብር ኖቱን የሚመለከተው ነበር ፡፡ ይህን ብር ያሳተሙት የሚያማክሯቸው ‹‹ ጠንቋዮች ›› ዘጠና ዓመት ይነግሳሉ ብለው ሹክ ስላሏቸው ነበር ፡፡

የቅርቡ ፤

በኮንጎ ነብር የሚመሰለው እንደ አዋቂ፣ ጠንካራና ተመላኪ ነገር ነው ፡፡ ይህን የሚያውቁት ሞቡቱ ሴሴኮ በነብር ቆዳ የተሰራች ኮፍያ አትለያቸውም ነበር ፡፡ በዚህ ብቻ መታወቅ ግን አላረካቸውም ፡፡ እናም የሀገራቸውን ብር በመቀየር በአንደኛው ገጽ ላይ የነብር ኮፍያና ነብራማ ፊት አሳይተው፣ ይህም አልበቃ ስላላቸው ከአጠገቸው የሚወረወር የነብር ስዕል አስለው ገጭ አሉ ፡፡ ላለማስፎገር ደግሞ ከብሩ ጀርባ ለኮንጎ የሃይል ምንጭ ቁልፍ ሚና የሚጫወተውን የኢንጋ ግድብ በሰፊው አዘረጉት ፡፡ ከዚያም ይህንን የግለሰብ ገጽታ ግንባታ ‹‹ ዛየርናይዜሽን ›› ብለው ለሚጠሩት አሰልቺና አደንቋሪ ፕሮፓጋንዳ ከ30 ዓመት በላይ ማቀጣጠያ አደረጉት ፡፡

ከሀገራችን ተነስተን ሩቅ እስከሚገኙት ዋልታዎች  ድረስ ብናስስ አያሌ ገዳይ፣ የህዝብ ፍቅር የሌላቸው፣ ሙሰኞችና አምባገነን መሪዎች በጉልበት  የህዝብ ሃብት የሆነው ገንዘብ ላይ ለፕሮፓጋንዳ መጠቀሚያ በጉርድ፣ በቁመት፣ በፈገግታ፣ በቁጣ፣ በስላቅ፣ ፎቶ በመነሳት የፈነጩበት መሆኑን እንረዳለን ፡፡

ርግጥ ነው አፓርታይድ የተባለውን አስከፊ ስርዓት ለማስወገድ ብጥብጥ አልባ የተባለ ሰላማዊ ትግል እንዲሁም የሲቪል አለመታዘዝ እንቅስቃሴን በመፍጠር ሀገራቸውን ነጻ ያወጡት ማህተመ ጋንዲም በብር ኖት ላይ ደምቀው ታይተዋል ፡፡ እኚህ መንፈሳዊና ፖለቲካዊ መሪ ፍጹም በሆነ የሰው ልጆች ፍቅር የሚታወቁ፣ ንብረትና ሃብት ለህዝቤ እንጂ ለእኔ ወይም ለዘመዶቼ በተለየ መልኩ አይገባም ብለው በማይታመን ኑሮ ውስጥ ያለፉ፣ የታገልኩት ራሴን ለማሳበጥ ሳይሆን የህዝቤን ነጻነት ለማጎናጸፍ ነው በሚል በህንድ የማይታመን የዴሞክራሲ ስርዓት እንዲዘረጋ፣ ዛሬም ሀገሪቱ ተጠቃሽ እንድትሆን ያደረጉ በመሆናቸው ህዝቡ የሰጣቸው ዕውቅና የሚበዛባቸው አልነበረም ፡፡

ማህተመ ጋንዲን የሚተኩ የዓለም መሪዎች ግን በቀላሉ እየተገኙ አይደለም ፡፡ በርግጥ በአሁኑ ዘመን ከአፍሪካ ብቸኛው ተኪ መሪ ኔልሰን ማንዴላ ናቸው ፡፡ እኚህ ሰው ‹‹ የዚህ ትውልድ ታላቁና ጀግና መሪ ›› መሆናቸውን ዓለም በተመሳሳይ ቋንቋ መስክሯል ፡፡ 27 ዓመታት በእስር ያማቀቃቸውን ስርዓት በይቅርታ አስተማሩት እንጂ አልተበቀሉትም ፡፡ እንደ ብዙ የአፍሪካ መሪዎች ግዜንና አጋጣሚን እየተጠቀሙ የበደላቸውን ወይም በዳይ የመሰላቸውን አልገደሉም ፣ አላሰሩም ፣ ሰበብ እየፈለጉ አላስጨፈጨፉም ፡፡ በዚሁ ሰበብ ህዝቦችን አልከፋፈሉም ፣ የማይዋጥ ወይም የማይፈለግ ርዕዮት አላሸከሙም ፡፡ አንዱን እውነተኛ  ሌላውን ጸረ ህዝብ በማለት አላሸማቀቁም ፡፡ አንዱ ባማረ ቪላ ሌላውን በየመንገዱ እንዲተኛ አላስፈረዱም ፣ አንዱን ባለ ሃብት ሌላውን ለምኖ አዳሪ እንዲሆን ክፉ መንገድ አላሳዩም ፡፡ ህዝቦችን በፍቅር አቅፈው ሳሙ እንጂ አልተዛበቱም ፣ አልተሳደቡም ፡፡ ስለደማሁና ስለቆሰልኩ ስልጣን ሁሉ ለእኔና በእኔ ፍላጎት ላይ ብቻ ይመሰረታል በማለት ‹‹ ወንበሩ ›› ላይ አልተሰፉም ፡፡ ስልጣን ገደብ ይኑረው የሚል ጠቃሚ ምክር ለለገሱ  ‹‹ ስልጣን ናፋቂ… ስልጣን የሚሻ ብረት አንስቶ መድማት ይኖርበታል ›› በማለት የደደበ አስተምህሮ አላሰሙም ፡፡ በርግጥ እሳቸው ያደረጉት ፍጹም የሚያስገርመውንና ተቃራኒውን ነበር ፡፡ ለሁለተኛ ግዜ እንኳን ሳይወዳደሩ ስልጣናቸውን ለተተኪው ትውልድ ማሰረከብ ፡፡

እንደ እንክርዳድ የበዙ አምባገነን መሪዎች በየግዜው በሚፈሉባት አፍሪካ የዚህ ዓይነት ስብዓና የተላበሰ መሪ ይበቅላል እንዴ ? የዚህ ምርጥ ዘር ምንጭ እውነት አፍሪካ ነው ? ይህ ጥያቄ ነበር በወቅቱ ለዓለም ራስ ምታትና ጭንቀት የሆነው ፡፡ ወዲያው ግን ከጭንቀቱ ጥላ እየወጣ ማክበር፣ ማድነቅና በደስታ ማንባት ጀመረ ፡፡ አያሌ ውርደት የተሸከመቸው አፍሪካ በማንዴላ ተግባር መጽናናት ብቻ ሳይሆን እንደ ዔሊ የሸጎጠቸውን አንገት አውጥታ ዙሪያ ገባውን በልበ ሙሉነት መቃኘት ቻለች ፡፡ አለም ደስታ መግለጫ ቃላት ተቸገረ ፡፡ ባለፉት 40 ዓመታት 250 የሚደርሱ ልዩ ልዩ ሽልማቶች ለማንዴላ የተሰጡትም በዚሁ አግባብ ነበር ፡፡ በ1993 ደግሞ የኖቤል ተሸላሚ ሆኑ ፡፡ ህዳር 2009 በተመድ ውሳኔ ሀምሌ 18 ቀን የማንዴላ የልደት በዓል ‹‹ የማንዴላ ቀን ›› ተብሎ እንዲከበር ተደረገ ፡፡

ጎበዝ ማንዴላና የዛሬ የክብር ሽልማታቸው የመነጨው እንግዲህ በሳቸው ፍላጎት ወይም በካድሬዎቻቸው ብልጣ ብልጥ የፖሊሲ ቀረጻ ምክንያት ሳይሆን ባገጠጠውና በማይካደው ተግባራቸው መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል ፡፡  በሌላ አነጋገር የተወሰኑ ቲፎዞዎች ተጽዕኖ ፈጥረው ባስገኙት ወፍራም ጭብጨባ ብቻ አይደለም ፡፡ አኩሪ ስራ ለሰሩ የሀገር መሪዎች ተገቢውን ዕውቅናና ክብር መስጠት ግድ ይላል ፡፡

የሰው ልጆች ፍቅር፣ እኩልነት፣ ነጻነት፣ ፍትህና ዴሞክራሲን ከምንም በላይ አብልጠው ይፈልጋሉ ፡፡ አፍሪካም ለገዳይና አምባገነን መሪዎች የሚሰጠው ፕሮፓጋንዳዊ እውቅና ይቆም ዘንድ መታገል ይኖርባታል ፡፡

ረጅም ዕድሜ ለማንዴላ ዓይነቶች !!!

Thursday, November 1, 2012

እውነት ሱዳን እያሴረችብን ነው ?



አባይ በካርቱም

የጉዳዩ መነሻ ፤

በአባይ ወንዝ ላይ ‹‹ ቬቶ ፓወር ›› አለኝ የምትለው ግብጽ ኢትዪጽያ የጀመረቸውን ግድብ ለመደብደብ እቅድ መንደፏን ዊክሊክስ መዘገቡ ይታወሳል ፡፡ ከዚህ ዘገባ ይፋ መሆን በኃላ በኢትዮጽያና ግብጽ መካከል ያለው ግንኙነት መወጣጠሩ እንደቀጠለ ነው ፡፡

ግብጽ ‹ ወዳጄን › ኢትዪጽያን ለመተናኮል አላሰብኩም በማለት ማስተባበያ ብትሰጥም በ1929 በጸደቀው ስምምነት መሰረት በናይል ወንዝ ላይ ችግር ሲፈጠር የምንፈታበት ስምምነት ላይ ነው ከሱዳን ጋር የመከርነው ብላለች ፡፡ ነገሩ አልሸሹም ዞር አሉ ዓይነት መሆኑ ነው ፡፡ በወራሪዋ እንግሊዝ የጸደቀው የ1929ኙ ስምምነት ለግብጽ 55፣ ለሱዳን ደግሞ 18.5 ቢሊዮን ኩዩቢክ ሜትር ውሃ በዓመት እንዲያገኙ ፈቅዶላቸዋል ፡፡ በዚሁ መሰረትም ላለፉት 84 ዓመታት ሁለቱ ሀገራት ያለማንም ተቀናቃኝ ተጠቅመውበታል ፡፡

እነሆ ቤንች ላይ ተቀምጠው የውሃ ላይ ቦሊቦል ፣ የጀልባ ውድድር፣ የጠብታ መስኖ የመሳሰሉትን ጨዋታዋችና ስራዎችን  ሲመለከቱ የነበሩ ሀገሮች አጉራ ጠናኝ በማለት የአባይ ተፋሰስ ሀገሮችን ጥምረት አቋቁመው የእኩል ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ስምምነት እስከመፈረም ደርሰዋል ፡፡ ሞኝ ካመረረ በግ ከበረረ መመለሻ የለውም እንዲሉ የስምምነቱን የመጀመሪያ ምዕራፍ የሚያበስረውን ስራ  በተግባር ለማስደገፍ ይመስላል ኢትዮጽያ 5250 ሜጋዋት የኤትሪክ ኃይል የሚያመነጭ ግድብ በመስራት ለኩሳለች ፡፡ ሌሎቹም የሌላውን ጥቅም በማይጎዳ መልኩ ቀጣይ ስራቸውን ያከናውናሉ ተብሎ ይጠበቃል ፡፡

ግብጽ እስካሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የውሃው ከፍተኛ ተጠቃሚ በመሆኔና ትልቁ ስልጣንም በእኔ እጅ ያለ በመሆኑ ኢትዪጽያ የምትሰራውን ግድብ መመርመርና መረዳት አለብኝ ብትልም ኢትዪጽያ ይህን ለማድረግ መጀመሪያ ስድስቱ ሀገራት የተስማሙበት ሰነድ ላይ ፊርማሽን  አስቀምጪ በማለት ጀርባዋን ሰጥታታለች ፡፡

የግብጽ ስጋቶች ጥቂት አይደሉም ፡፡ ግድቡ በወንዙ ፍሰት ላይ ተጽዕኖ ይፈጥራል … ወደ ግብጽ ከሚፈሰው የውሃ መጠን በ 25 ከመቶ ያህል ይቀንሳል … ኢትዪጽያ ግድቡን ለሃይል ማመንጫ አለች እንጂ ለመስኖ መጠቀሟ አይቀርም የሚሉት ዋነኛዎቹ ናቸው ፡፡ በተለይም የግድቡ ጥልቀት ከ90 ሜትር ወደ 150 እንዲያድግ መደረጉ ከኃላ የመስኖ ስራ ለማከናወን የሚደረግ መደላድል  ነው በማለት ትጨምርበታለች ፡፡ ይህ ሁሉ ነገር ተደማምሮ ነው እንግዲህ ‹ የኢትዪጽያ ግድብ የብሄራዊ ደህንነቴ ስጋት ነው › እስከማለት የደረሰቸው ፡፡

በዚህ ስዕል መሰረት የዊክሊክስ ዘገባ ሀሰት ነው ለማለት ይከብዳል ፡፡ እናም የዲፕሎማሲያዊ ጥረት የማይሳካ ከሆነ ጉልበትን ለመጠቀም አቅዳለች ፡፡ ለዚህ ደግሞ በሁለተኛ ደረጃ ‹ የቬቶ ፓወር › ያላትን ሱዳን ፈረስ ታደርጋለች ፡፡ ለጀት መንደርደሪያም በምዕራብ ሱዳን ዳርፉር የምትገኘው ‹ ኩርሲ › ናት የተመረጠችው ፡፡ አስገራሚውና አጠያያቂው ጉዳይ ሱዳን በጭብጡ ዙሪያ ትንፍሽ አለማለቷ ነው ፡፡ መቸም ግብጽ ብዙ ሴራ ብትሸርብ ከማንነቷ አንጻር አይገርምም ፡፡ በርግጥ ሱዳን ‹ ከማንም አቀርባታለሁ › የምትላትን ኢትዪጽያ ለመውጋትም ሆነ ለማስወጋት ፍላጎት አላት ? ከምን አንጻር ?  ብዙ ተጽዕኖና በደል ፈጽማብኛለች የምትላትን ግብጽ መርዳቷ ከኪሳራና ትርፍ ስሌት አኳያ እንደምን ይታያል ? ሱዳን ካላት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ አንጻር በኢትዪጽያ የምትታመን ሀገር ናት ? የሚሉትን ጉዳዮች በአግባቡ መፈተሽ ተገቢ ይሆናል ፡፡

 የህዳሴው ግድብ በሱዳን ዓይን ፤

ኢትዪጽያ ግድቡን በራሷ አቅም እንደምትሰራ ይፋ ስታደርግ በማሾፍ፣ በመገረምና በመደንገጥ ውሰጥ ከነበረው ዓለም ቀድማ አስተያየት የሰጠችው ሱዳን ነበረች ፡፡ ግድቡ ከኢትዪጽያ ይልቅ ሱዳንን ይበልጥ ተጠቃሚ ያደርጋል በማለት ፡፡ የመስኖና ውሃ ሃብት ሚንስትሩ ፕሮፌሰር ሰይፍ አዲን ሃመድ አብደላ ‹‹ የአባይ ውሃ ሲገደብ ወደ እኛ የሚመጣውን ደለል እንዲቀንስ ያደርጋል ፡፡ ደለሉን ለማስጠረግ ደግሞ በየዓመቱ ብዙ ሚሊዮን ዶላሮችን ወጪ እናደርግ ነበር ፡፡ ለመስኖ እርሻና ለኃይል አቅርቦትም ያግዘናል ፡፡ በአጠቃላይም ለሱዳንም ሆነ ለግብጽ የሚጠቅም ዕቅድ በመሆኑ ሊበረታታ ይገባል ›› ብለው ነበር ፡፡

ይህ አስተያየት የመነጨው የባለሙያዎችን ጥናት  መሰረት ከማድረግ አንጻር በመሆኑ በጤናማ አይን የታየ ነው ማለት ይቻላል ፡፡  እያደር የተንሸዋረረው መረጃው ነው ወይስ የፖለቲከኞቹ አይንና ጭንቅላት የሚለው አጠያያቂ ጉዳይ ነው ፡፡ እውነቱ በውሸት የሚታይበት ወይም የሚቀለበስበት አካሄድ ግር ሲያሰኝ ‹ የሱዳን አይን እንደ ቆዳ ስፋቷ ትልቅ ነው እንዴ ? › የሚል ጥያቄ ያጭራል ፡፡ የአህያ ትልቅ ዓይን ትልቅ የማየት ችግር አለበትና ፡፡

የመሆን አለመሆን ጉዳይ ፤

 አሸባሪዎችን በገንዘብና በቁሳቁስ በመርዳት፣ ስልጠና በመስጠት በአጠቃላይ በማስጠለል ምክንያት ‹ አሸባሪ ሀገር › በሚለው ጥቁር መዝገብ ውስጥ የሰፈሩት ኩባ፣ ኢራን፣ ሶርያና ሱዳን ናቸው ፡፡ በዚህም ፍረጃ ምክንያት ሀገሪቱ ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስተጋብሮቿ ተናግተው ቆይተዋል ፡፡ ከደረሰባት መገለልና እቀባ በተጨማሪ ምዕራባዊያን ለሀገሪቱ ጥሩ ምስል እንዳይኖራቸውና ግንኙነታቸውን እንዳያጠናክሩ ተጽዕኖ አሳድሯል ፡፡

ይህን መጥፎ ገጽታ ለማስወገድ ብዙ ሰርቼያለሁ በማለት ከተመዘገበችበት የአሸባሪነት ዝርዝር ውስጥ እንድትፋቅ ጥያቄም አቅርባ ነበር ፡፡ ይሁን እንጂ የለም የተባለው ሀማስ  በሀገሪቱ ውስጥ በግልጽ  የገንዘብ ማሰባሰቢያ መድረክ  ሲያዘጋጅ ታይቷል ፡፡ አሸባሪዎችን ከሀገሬ አስወጥቻለሁ ብትልም አልቃይዳና ሌሎች ድርጅቶች በሱዳን ስላለው እንቅስቃሴያቸው የሚያደርጉት የንግግር መረጃዎች ተይዘዋል ፡፡ ይህም ሀገሪቱ ያቀረበቸው ማመልከቻ እንዲዘገይ አድርጓል ፡፡ ከዚህ ምስል ሱዳን የምትናገረውን የማታደርግ ሀገር ናት እንዴ ? የሚል ጥያቄ ማመንጨት ከባድ አይደለም ፡፡

በአሸባሪዎች የምታደርገው ጨዋታ ፤

እንደ ሱዳን ለበርካታ አሸባሪዎች ድጋፍም ሆነ መጠለያ በመስጠት የሚታወቅ ሀገር መኖሩ ያጠራጥራል ፡፡ ለአልቃይዳ፣ ሂዝቦላ፣ የፍልስጤም እስላሚክ ጂሃድ፣ የግብጽ እስላሚክ ጂሃድ፣ የአልጄሪያ አርመዲ እስላማዊ ቡድን፣ እንዲሁም እስላማዊ ያልሆኑ የኢትዮጽያ፣ የኤርትራ፣ የኡጋንዳና ታንዛኒያ ሸማቂ ቡድኖችን ስልጠና በመስጠትና ቦታዎችን በማመቻቸት ትረዳለች ፡፡ በመላው ዓለም እንዲደረጉ በሚታቀዱ የሽብር ጥፋቶች ላይ ፍላጎቷን እግረ መንገድ ትወጣበታለች ይሏታል ፡፡ ለምሳሌ ያህል ሎርድ ረሲስታንስ አርሚ በሚባለው የኡጋንዳ አማጺ ቡድን ጥቃት 25 ሺህ የሚደርሱ የደቡብ ሱዳን ዜጎች እንዲፈናቀሉ መደረጉን የተመድ ሪፖርት ያመለክታል ፡፡ ሱዳን ባላንጣዎን ለማጥቃት ሌላ ረጅም እጅ አላት ማለት ነው ፡፡

በሌላ በኩል ዩዌሪ ሙሴቪኒ ‹ ሱዳን ፍቃድ ብትሰጠኝ ይህን አማጺ ቡድን በሰላሳ ደቂቃ ውስጥ አጠፋዋለሁ › ብለው ነበር ፡፡ አልበሽር ይህ አማጺ ቡድን ለክፉ ቀን ስለሚጠቅማቸው የረጅም ግዜ ጓደኛቸውን ጥያቄ መቀበል አልፈለጉም ፡፡ ከራስ በላይ ንፋስ በማለት ፡፡ የአፍሪካ ህብረት በአንድ ወቅት ይህን አማጺ ቡድን ለማንበርከክ ሱዳንን ጨምሮ ከአፍሪካ የተውጣጣ ብርጌድ አቋቁሞ መላክ ሲፈልግ አሪፍ ስልት ነው ተብሎ ነበር ፤ እያደር ግን አልበሽር ለሀሳቡ ከአንገት በላይ ሆኑ ፡፡ የሱዳን የዳማ ጨዋታ በነጩም በጥቁሩም ሜዳ ላይ በመሆኑ ፋውልም ሆነ ኦፕሳይት አይታወቅም ፡፡ ይህም ግድየለሽነትን ወይም አደገኛነትን ሳይጠቁም ይቀራል ?

ሚሳይልን እንደ ሚዝል የምትቅም ሀገር ፤

በቅርቡ ያርሙክ የተባለው የጦር መሳሪያ ፈብሪካዋ ከራዳር እይታ መሰወር በሚችሉ አራት የእስራኤል ጀቶች ወድሟል ፡፡ ይህ ፋብሪካ ሮኬትና ሌሎች ከባድ መሳሪያዋችን የሚያመርት ሲሆን በኢራን፣ ግብጽና ሱዳን ሽርካነት የሚንቀሳቀስ ነበር ፡፡ የፋብሪሳው ዓላማ ሀማስና ሌሎች ተዋጊ / አሸባሪ ድርጅቶችን ማጠናከር ነው ፡፡

ሱዳን ለዚህ መሰሉ ጥቃት አዲስ አይደለችም ፡፡ በሚያዚያ 2011 ፖርት ሱዳን አካባቢ መኪና ውስጥ የነበሩ ተጠርጣሪ አሸባሪዎች ተገድለዋል ፡፡ በ2009 ሰሜን ምስራቅ ሱዳን ውስጥ ወታደራዊ ኮንቮይ ተደብድቦ 119 ሰዎች አልቀዋል ፡፡ ብዙዎቹም ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ አጓጓዦች ነበሩ ፡፡ በ1998 አል ሺፋ የተባለ መድሃኒት ፋብሪካ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ያመርታል ተብሎ የአሜሪካ ሚሳይል ሰለባ ሆኗል ፡፡ እስራኤል በጥቃቱ ዙሪያ ቀጥተኛ አስተያየት ሰጥታ ባታውቅም ጮክ ብላ  ‹‹ ሱዳን አደገኛ የአሸባሪዎች ሀገር ናት ! ›› ከማለት ግን ወደ ኃላ ብላ አታውቅም ፡፡ ሱዳንም ጠብ አጫሪዋንና ህገ ወጧን እስራኤል  እከሳለሁ እያለች ከመፎከር የዘለለ የተጨበጠ እንቅስቃሴ አታደርግም ፡፡ ይህም ‹ መድሃኒቱ › የተስማማት ወይም የታዘዘላት አስመስሎባታል ፡፡ ለነገሩ በ ‹ ICC › የሚፈለጉት አልበሽር ሌላውን ለመክሰስ ምን ሞራል አላቸው ?

ዞሮ ዞሮ ሱዳን አሸባሪነትንም ሆነ የአሸባሪዎችን ዓላማ መሾፈር የምትፈልግ ሀገር ከሆነች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በኢትየጽያ ጥቅሞች ላይ እጆቿን ትዘረጋለች ለማለት የሚያስችል መነሻ አይኖርም ?

ጉርብትና ለመቼ ነው ?

ሁለቱ ሀገሮች ተራ ጎረቤታሞች አይደሉም ፡፡ ከናይል ወንዝ ተመሳሳይ ውሃ ጠጥተዋል ፡፡ በአረብ ሊግ ስብሰባ ላይ በተመሳሳይ ቋንቋ አንድ አይነት ሀሳብ ያስተጋባሉ ፡፡ ሁለቱም የሮምን ስምምነት/ ICC / አልፈረሙም ፡፡ ፕሬዝዳንት አልበሽር የሙስሊም ብራዘር ሁድ አባል ናቸው ፡፡ የሙባረክ መንግስት ከወደቀ በኃላ ግብጽን የጎበኙ የመጀመሪያው መሪ ናቸው ፡፡ ሁለቱም ሀገሮች ዕድሜ ለቅኝ ገዢዎች ውል በናይል ውሃ ላይ ‹ Veto power › አላቸው ፡፡ ስድስቱ ሀገራት የፈረሙትን የእንቴቤ ስምምነት አይመለከተንም ብለዋል ፡፡ ሱዳን ለሁለት በመከፈሏ ሁለቱም ደስተኞች አይደሉም ፡፡

ሱዳን ለሁለት መከፈሏን ደግሞ ሀገራችን ትደግፋለች ፡፡ ይህ በራሱ ለመቃቃር አይነተኛ ጥንስስ ይፈጥራል ፡፡ የሁለቱን ሀገሮች የዘመናት የ ‹ Veto power › እንዲናድ የሰራቸው ኢትዮጽያ ገና ከጠዋቱ ትልቁን የስልጣን ካፖርት እያጠለቀች በመሆኑ አይሰማትም ማለት አይቻልም ፡፡ በ 25 ከመቶው የውሃ ድርሻዋ ደስተኛ ባትሆንም ዛሬ ትክክለኛ ድርሻሽ መቶ ሲካፈል ለአስር ሀገሮች ነው እየተባለች ነው ፡፡ የምክትል ሰብሳቢ ፈላጭ ቆራጭነት ሚናም አይኖራትም ፡፡ ይህ የመውረድና የመወራረድ ፖለቲካ የሚፈጥረው ግዜያዊ ራስ ምታትም ሚዛናዊ ብይኗን አያስትም ማለት አይቻልም ፡፡ እናም በተመሳሳይ ቀለም ከግብጽ ጋር ለመብረር ‹‹ ኩርሲ ›› ላይ መንደርደሪያ ሰርታ ጀባ ለማለት አቅዳ ከሆነስ ?

ከማያውቁት መልዓክ … ፤

የሱዳንን ግብጽ ግንኙነት እድሜ ጠገብ ቢሆንም የተመሰረተው በአሸናፊና ተሸናፊ፣ በአለቃና ምንዝር ምህዳር ላይ ነው ፡፡ 790 ማይልስ ርዝመት ያለው የድንበር ወሰን አጨቃጭቋቸዋል ፡፡ ሃይላንድ ትሪያንግል የተባለው ቦታ የሱዳን ነው ቢባልም ግብጽ በጡንቻዋ የራሷ አድርገዋለች ነው የሚባለው ፡፡ በዚህ የሚበሽቁት አልበሽር -  ሙባረክ አዲስ አበባ ለስብሰባ ሲመጡ በእጃቸው መዳፍ ውስጥ ካሉት አሸባሪዎች ጋር መክረው ሊያስገድሏቸው እንደነበር ተጠርጥሯል  ፤ እረ ተዘግቧል ፡፡

 ትንሽ ቆይቶ ደግሞ አልበሽር ‹ ግብጽ መንግስቴን ልትገለብጥ እያሴረች ነው › በማለት መጮህ ጀመሩ ፡፡ ይህን የሰሙት ሙባረክ ‹ ግብጽ የአንተን መንግስት መገልበጥ ብትፈልግ አስር ቀናት ብቻ ይበቃታል ! › ሲሉ አናዳጅና የበላይነታቸውን የሚያስረግጥ ምላሽ ሰጡ ፡፡ በነገራችን ላይ ግብጾች ይህን የመሰለ ጉራ በማምረት የሚተካከላቸው የለም ፡፡ በሀገራችን ግድብ ዙሪያም ማስተባበያ ሲሰጡ   ‹‹  የዲፕሎማሲያዊው ጥረት የማይሳካ ከሆነ ጀቶቻችን ግድቡን ደብድበው በአንድ ቀን ይመለሳሉ ! ›› ብለው ነበር ፡፡ እንዴት ነው ነገሩ እንደ እስራኤልም ያደርጋቸዋል ልበል ? እኛ የምናውቀው በስድስቱ ቀን ጦርነት እነሱ ፣ ሶርያና ጆርዳን በእስራኤል ታስረው መገረፋቸውን ነው ፡፡ ታዲያ ይህን በስድስት ቀን ፣ በአስር ቀን የሚባለውን ተሞክሮ ከየት አመጡት ?  ‹ ወገኛ ! › የሚባለው ሀገር የዚህ ዓይነቱ መሆን አለበት ፡፡ ያም ሆነ ይህ ሱዳን ከነጭቆናዬ የማውቃትን ግብጽ መደገፍ ስትራቴጂያዊ ርምጃ ነው ብትል ከልካይ የላትም ፡፡ ኢትዮጽያን ደግፋ ጀግና ከምትባል ለግብጽ አድራ ተቀምቻለው የምትለው መሬት እንዲሰጣት አሳዛኝ ማመልከቻ ብታስገባ ሊጠቅማት ይችላል ፡፡

የጉዳዩ መድረሻ ፤

ሱዳንና ኢትዮጽያ ከማህበራዊና ባህላዊ ትስስር አንጻር በተለይም የህዝብ ለህዝብ ግንኙነታቸው ጠንካራ ነው ማለት ይቻላል ፡፡ ከዘላቂ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥቅም አንጻርም ሱዳን ከኢትዮጽያ የኤሌትሪክ ኃይል እና ሰላማዊ የድንበር ደህንነት ትፈልጋለች፡፡ ኢትዮጽያ የሱዳንን ነዳጅ፣ ወደብና ገበያዋ በአማራጭነት ያስፈልጋታል ፡፡

በርካታ ኢትዮጽያዊያን በፖለቲካም ሆነ በኑሮ ሲንገፈገፉ ወደዚች ሀገር ማምራታቸውም ይታወቃል ፡፡ ሁለቱ ሀገሮች በቀለም፣ በቋንቋና ስነ ጥበብ ይመሳሰላሉ ፡፡ በተለይም የስዕል፣ ዳንስ፣ ቅርጻ ቅርጽና ሙዚቃ ስራዎቻቸው  የተቀራረቡ ናቸው ፡፡ ታዋቂዎቹ ሳኢድ ከሊፋና መሃመድ ዋርዴ ሀገራችንን እንደ ቤታቸው በመቁጠር ጣፋጭ ስራቸውን አስኮሙኩመውናል ፡፡ በተለይም ሳኢድ ከሊፋ

‹‹ ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ከሱዳን መጣን ልናያችሁ … ›› በማለት ውስጣችንን ኮርኩሮታል ፤ እኛንም መስሏል፡፡ በብዙዎቻችንም ክብርና ሞገስ አግኝቷል ፡፡ ታዲያ ይቺ ቅርብ የመሰለች ሀገር እውነት ዛሬ ፊቷን እያዞረችብን ፣ በፖለቲካም ቋንቋ እያሴረችብን ነው ? ነው ወይስ የጠላት ወሬ ነው ? እውነት ከሆነማ የቀጣዩ ‹ ሲንግል › ግጥም ቁልጭ ብሎ ይታየኛል ፡፡ ….

‹‹ ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ከግብጽ ጋር አበርንባችሁ
  ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ‹ ኩርሲ › ላይ መሸግንባችሁ
   ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
   በናይል ጉዳይ ከዳናችሁ
   ጤና ይስጥልኝ ….

 እነሆ ሱዳን የምንሰማው ሁሉ እውነት ከሆነ ትጣሊናለሽ ፤ ማርያምን አንለቅሽም !! ከዚያ በኃላ ለቁጥር የሚታክተውን የሽለላና የቀረርቶ ዜማችንን ምንጭ እየጠቀስሽ እንደሚከተለው ታዜሚልን ይሆናል
1.
ደሞ፣ደሞ፣ደሞ ግለሌ
ገስግሶ ገዳይ በሰው ቀበሌ
ግለሌ ምሳው ግለሌ እራቱ
መለቃለቂያው ደም ራጨቱ
ገለል በሉለት አንድ ግዜ ለእሱ
ግልግል ያውቃል ከነፈረሱ
2.
የፍየል ወጠጤ ትከሻው ያበጠ ልቡ ያበጠበት
እንዋጋ ብሎ ለነብር ላከበት
የማትረባ ፍየል ዘጠኝ ትወልዳለች
ልጆቿም ያልቃሉ እሷም ትሞታለች
እረ ጎራው - ጎራው እረ ደኑ - ደኑ ...



Friday, October 19, 2012

‎ጥቂት የ ‹ A › መሪዎችና በርካታ የ ‹ A › በሽታ ‎



እገሌ የ ‹ A › ተማሪ ነው ከተባለ ቀለሜዋ መሆኑን እንረዳለን ፡፡ ፕሬዝዳንት እንቶኔ የ ‹ A › መሪ ናቸው ከተባለ ደስ የሚሉና የተባረኩ ናቸው ብሎ ማለፍ ያስቸግራል ፡፡  ‹ A › ማለት ምንድነው ?  የተከበረው ‹ A › እንዴት ይገኛል ?  የሚለውን ሀሳብ ማጦዝ ያስፈልጋልና፡፡


የ ‹ A › መሪነት በሽምደዳና በችከላ ብቻ አይገኝም ፡፡ አንድ የሀገር መሪ እዚህ ማዕቀፍ ውስጥ በክብር ሊቀመጥ የሚችለው ዴሞክራሲ የተባለውን መጠነ ሰፊ ባህር ዋኝቶ ባይጨርሰውም ውስጡ ምን እንዳለ ሲያውቅ ፣ የፕሬስ ነጻነት የተባለውን ጎምዛዛ ፣ አኞና ሆድ አጥጋቢ ማዕድ ቀምሶ ለብዙሃኑ ሲባርክ ፣ ሙስና በተባለው ‹ አሻፋጅ › ገላ ራሱም ሆነ ሌሎች ከመውደቃቸው በፊት ለሃጫቸውን እንዲቆጣጠሩ ሲሰራ ፣ የሰው ልማት የተባለውን መሰረታዊ የሰው ልጅ ፍላጎት ለሟሟላት ቀን ከሌሊት ሲተጋ ነው ፡፡


የተማሪነት ዘመናቸውን በቀለሜዋነት አሳልፈው የህዝብ አስተዳደሩ ግዜም በዚሁ ካባ ደምቀው የታዩ የአፍሪካ መሪዎች ካሉ እንደመታደል  ይቆጠራል ፡፡ አንዳንድ ጎበዝ ተማሪ የነበሩ የአፍሪካ መሪዎች ሲጎለምሱ ጎበዝ ገዳይና ጀግና ፈላጭ ቆራጭ ሆነዋል ፡፡ አንዳንዶች በትምህርት ብዙም ያልተጓዙ ቢሆንም ትንሽ ከራርመው ባለብዙ ዲግሪ መሆናቸውን ያስነግራሉ ፡፡ ብዙዎቹ አዋቂና ዘመናዊ እንዲባሉ ስለሚፈልጉ የቀለም ቦሃቃ ውስጥ ገብተው አያውቁም የሚለው ወሬ እንዲነገርባቸው አይፈልጉም ፡፡

ባለኝ የንባብ መረጃ መሰረት ስለ ትምህርቱ ሳይደባብቅ ለጋዜጠኞች በይፋ የተናገረው አረመኔው ኢዲያሚንን ዳዳ ነበር ፡፡
እንዲህም አለ ፡፡ ‹‹ እኔ ምንም ዓይነት የመደበኛ ትምህርት የለኝም ፡፡ ሌላው ቢቀር የነርስ ትምህርት ቤት ሰርተፍኬት የለኝም ፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ግዜ ፒኤችዲ ካለው በላይ ነው የማውቀው !! ›› መቼም ይህ ደፋር ሰው አነስተኛ የትምህርት ዝግጅቴ ለመሪነት አያበቃኝም የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ፈልጎ እንዳልተናገረ ግልጽ ነው ፡፡

ዞሮ ዞሮ የ ‹ A › መሪነት በሽምደዳ አይገኝም ። በባዮሎጂ ትምህርታችን መረጃ መሰረት
የቫይታሚን  B  እጥረት - ቤሪ ቤሪ
የቫይታሚን  C  እጥረት - አስኮርቢክ አሲድ
የቫይታሚን  D  እጥረት - ሪኬት

ከጉዳያችን ጋር ግንኙነት ያለው የቫይታሚን  A እጥረት - በደብዛዛ ብርሃን የማየት በሽታ / Night Blindness / ያስከትላሉ ፡፡
የአፍሪካ መሪዎች ባህርያት አመቱ በጨመረ ቁጥር የሚለያይ ነው ። ወደ ስልጣን ሊመጡ አካባቢና ስልጣንን እንደያዙ ተቆርቋሪነታቸው ፣ የበዛ አዳማጭነታቸውና የተንዠረገገው ቃልኪዳናቸው ብዙዎችን የሚያማልል ነው ፡፡ ምነው ይህን ሰው አባቴ ፣ አጎቴ ፣ ወንድሜ ፣ ውሽማዬ ባደረገው ባዩ ቀላል አይደለም ፡፡ የዚህ ሰው ተወዳጅ አበባ ግን ዕድሜውን ጨርሶ ሳይሆን በትዕቢትና ጥጋብ ከወዲሁ ይረግፋል ፡፡ ቀጥ ያለውና የተከበረውም ‹ A › በጉዳትና በመከራ እንደ ‹ C › እና ‹ D › መጣመም ይጀምራል ፡፡

የ2011 መረጃዎች እንደሚያስረዱት ከሆነ ከ 54 የአፍሪካ ሀገሮች የ A › ን ቦታ ያገኙት የቦትስዋናው / jeretse jan khama / ፣ የኬፕቨርዱ / Jorge carlos fonseca / ፣ የሞሪሽየስ / Navin Chandra Ragoolan / እና የጋና / John Evans Atta mills / መሪዎች ናቸው ፡፡ ተስፋ ከሚጣልባቸው የ ‹ B › መሪዎች ውስጥ ናሚቢያ፣ ደቡብ አፍሪካና ማሊን መጥቀስ ይቻላል ፡፡ ኬኒያ ፣ ታንዛኒያ ፣ ላይቤሪያና ዛምቢያ ለክፉ አይሰጥም በሚባለው የ ‹ C › ማዕቀፍ ውስጥ ናቸው ፡፡ ናይጄሪያ ፣ ሩዋንዳና ኒጀር ‹ D › ን ታቅፈዋል ፡፡ ኡጋንዳ ፣ ጊኒ ፣ ኮሞሮስ ባንዲራ የሚባለውን ‹ F › እያውለበለቡ ይገኛሉ ፡፡ ሊቢያ ፣ አልጄሪያ ፣ ካሜሮንና ኢትዮጽያ ለየት ያለ ስያሜ ተሰጥቷቸዋል ፡፡ ICU የሚል ፡፡ ይህን ምህጻረ ቃል ስናፍታታው Health Service Intensive Care Unit የሚል ሆኖ እናገኘዋለን ፡፡ ጥሬ ትርጉሙስ ከተባለ እዚህ ክፍል የሚመደብ በሽተኛ ፤ በሽታው ለህይወቱ በጣም አስጊ በመሆኑ በዘመናዊ የህክምና መሳሪያና ሙያተኞች ርዳታ መደገፍ እንደሚገባው እንረዳለን ፡፡ ይህን ርዳታ ባግባቡ ካላገኘ ግን መሞቱ ነው ፡፡ ኤርትራ ፣ ሱዳንና ዙምባብዌ ደግሞ < MORGUE > ተብለዋል ፡፡ የሞተ ሰው የሚቀመጥበት ክፍል መሆኑ ነው ፡፡ 

በሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽንና በምስራቅ አፍሪካ መጽሄት ዝግጅት ክፍል ይህን የመሰለ የአፍሪካ መሪዎች ስኮር ካርድ ማዘጋጀት ከተለመደ ሰነባብቷል ፡፡ 75.2 አስመዝግባ ‹ A › ባገኘቸው ቦትስዋናና 32.05 አግኝታ ICU በምትገኘው ኢትዮጽያ መካከል የ43 ነጥብ ልዩነት አለ ፡፡ የነጥቡን ስፋት ያንቦረቀቀው የዴሞክራሲ ፣ የፕሬስ ነጻነት ፣ የሙስናና የሰብዓዊ ልማት መሰረታዊ አጀንዳዎች ናቸው ፡፡ ርግጥ ነው የሞህ ኢብራሂም ኢንዴክስና የጋዜጠኞች ቡድን ነጥብ አሰጣጥ ስርዓትም ይካተታል ፡፡

አሜሪካ በአንድ ወቅት ተስፋ የሚጣልባቸው የአፍሪካ ዴሞክራት መሪዎች በሚል ስያሜ የሩዋንዳውን ፓውል ካጋሜ ፣ የኡጋንዳውን ዩዌሪ ሙሴቬኒ ፣ የኢትዮጽያዊውን መለስ ዜናዊ እንዲሁም ኤርትራዊውን ኢሳያስ አፈወርቂ የላቀ ዕውቅና እንዲያገኙ አድርጋ ነበር ፡፡ የነዚህ መሪዋች ስኮርድ ካርድ ግን ስያሜያቸውን መምሰል አልቻለም ፡፡ ካጋሜ 47.6 በማግኘት D ፣ ሙሴቬኒ 42.7 በማግኘት F ፣ መለስ 32.05 በማግኘት ICU ፣ ኢሳያስ 22.23 በማግኘት MORGUE ውስጥ ተመድበዋል ፡፡ አንዳቸው እንኳን የማለፊያውን ወገብ አለመንካታቸው በእጅጉ ያስገርማል ፤ ተግባራውም ሲታወቅ ያስደነግጣል ። 

ይህን የቤት ስራ በአግባቡ ለመከወን የ ‹ A › መሪዎችን ተሞክሮ መጠቀም ያስፈልጋል ፡፡ በነገራችን ላይ የ ሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን ዘንድሮን ብቁ መሪ አላገኘሁም በሚል ሂሳብ ይዝለለው እንጂ እስካሁን ለሶስት መሪዎች የ 5 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት በመስጠት ዕውቅና አጎናጽፏል ፡፡ 
መሪዎቹ ፣
የኬፕቨርዱ - ፔድሮ ቬሮና ፓይረስ
የቦትስዋናው - ፌስተስ ጎንተባይ
የሞዛምቢኩ - ጃኪም ቺሳኖ ናቸው ፡፡
ህገ መንግስትንና ህጎችን በተፈለገ ግዜ በልክ መቅደድና መስፋት በጣም የተለመደ ፣ ቀላልና የማያሳፍር ተግባር በሆነባት አፍሪካ እነዚህ መሪዎች ከሁለት ግዜ በላይ ሀገር አንመራም በማለት በፈቃዳቸው በመልቀቅና የተሻለ መልካም አስተዳደር በመፍጠር ይመሳሰላሉ ፡፡ ሞዴል መሪዎች የተባሉትም በነዚህና በመሳሰለው የላቀ የአመራር ጥበባቸው ነው ፡፡ እንግዲህ ይህን የመሰለ ቅዱስ ተግባር በአፍሪካ በተለይም በኢትዮጽያ እንዴት ይመጣል ? የሚለው ጥያቄ ነው የሚያስጨንቀው ፡፡ ምክንያቱም የነ ሙጋቤና ሙሴቬኒን መንገድ አጥብቀው የሚከተሉት አምባገነን የአፍሪካ መሪዎች የሚከተለውን ያልተበረዘና ያልተከለሰ ፖሊሲ እያቀነቀኑ ነውና

 ‹‹ እኛ መሪዎች ለህዝብ ጥቅም ሲባል በተወለድንበት አልጋ ላይ እስክንገነዝ ድረስ መቆየት እንፈልጋለን !! ››
ለማንኛውም  መሪዎቻችን ዳፍንት ገደልን መንገድ የሚያስመስል ክፉ በሽታ ስለሆነ ዘወትር በጠራ ሳሙና ፣ ውሃና ፎጣ ፊታቸውንና ጭንቅላታችሁን  ቢታጠቡ መልካም  ሳይሆን አይቀርም ፡፡ 

Sunday, October 14, 2012

‎ዋሊያዎቹ ከተራራ ወረዱ‎




‹‹ የቆየ ከሚስቱ ይወልዳል ይሉሃል ይሄ ነው ›› ብሄራዊ ቡድናችን ዋሊያዎቹ ከ 31 ዓመታት ቆይታ በኃላ ለአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ አለፉ ፡፡ ይህን አባባል በሌላ ቅርጽ መድገም ያስፈልጋል  ‹‹ ዋሊያዎቹ ከ31 ዓመታት ቆይታ በኃላ የአፍሪካን ዋንጫ አሸነፉ ሳይሆን መከራ የሆነባቸውን የማጣሪያ ግንብ ደርምሰው አለፉት !! ›› ማጣሪያን የደፈረ ቡድን ማለት እንችላለን ፡፡

ኩሩው፣ አይናፋሩና ግርማ ሞገስ የተቸረው ዋሊያ በኢትዮጽያ ለዛውም በሰሜን ተራራዋች  ብቻ የሚገኝ አጥቢ እንስሳ ነው ፡፡ ይህን ብርቅ እንሰሳ ለመጎብኘት ከመላው ዓለም ወደ ሀገራችን የሚያቀናው ቱሪስት ቁጥር ቀላል አይደለም ፡፡ ግና ቱሪስቶቹ እንደ ጅብ፣ የሜዳ አህያና ሌሎቹም እንስሳት በቀላሉ በቅርበት ስለማያገኙት ትንፋሽ የሚያሳጥረውን የሰሜን ተራራዋች መውጣት ይጠበቅባቸዋል ፡፡ ዋልያዋች በአብዛኛው የሚኖሩት ከ 2500 ሜትር በላይ፣ ከ 4000 ሜትር በታች በሆኑ አካባቢዎች መሆኑ ይታወቃል ፡፡

ዋሊያ በዚህ ባህሪው እሱ ተራ ወደሚለው ‹ ሜዳማ ስፍራ › ለመውረድ ፍቃደኛ ሳይሆን ህይወቱን ይገፋል ፡፡

የብሄራዊ ቡድናችን ‹ ዋሊያም › ለ31 ዓመታት የአፍሪካም ሆነ የዓለም ዋንጫ አይመቸኝም የሚል የመሰለ አስተሳሰብ ወዶም ይሁን ተገዶ በማዳበሩ ‹‹ ብርቅና በኢትዮጽያ ብቻ የሚገኝ ብሄራዊ ቡድን ›› የሚል ቅጽል እስከማግኘት ደርሶ ነበር ፡፡ በርግጥ እንደ ቀንዳሙ ዋሊያ የሚጎበኙት ነጫጭ ሰዎች አልነበሩም ፡፡ በዚህ የተደፋፈሩት እነ ሶማሊያና ትናንሽ ቡድኖች ሁሉ ባገኙት ቁጥር የሚያቃጥል ጥፊና የሚያሳክክ ኩርኩም ሲያቀምሱት ቆይተዋል ፡፡ ህመሙ ቢጋባብንም ላለው ይጨመራል እንዲሉ ‹‹ ይሄ ውሽልሽል ! አሰዳቢ ! ወኔ ቢስ ! ቡድን ›› እያልን በጎን አገጩን ስናጣምም ነበር ፡፡

ዛሬ ተመስገን ሆነ ፡፡

‹ ቀንዳሙ ዋሊያ ታች ወርዶ የማይታየው ከስነ ፍጥረታዊ ግዴታው አኳያ ነው ፡፡ ታዲያ የኔ ተራራ ላይ መቆለል ምን ሊረባኝ ነው ? ተራራ ላይ ከመኖር አስተሳሰብን ተራራ ማሳከል ይሻላል › የሚል ጥሞና ውስጥ ቆየ ፡፡ ይኀው ስድቡን፣ ኩርኩሙን፣ ቁጭቱን በጉያው ይዞ የምሽት ድል አበሰረ ፡፡

በዚህም ምክንያት የአበሻ ምድር ቀውጢ ሆኖ አመሸ ፡፡ ህዝቡ አበደ ፡፡ ከመናገር ይልቅ መጮህ መረጠ ፡፡ መንገድ ሞልቶ እንዳለቀሰ ሁሉ መንገድ አጣቦ ጨፈረ ፡፡ ብርጭቆ እያጋጨ ዘመረ ፡፡ ከመተቃቀፍ  ይበልጥ አስፋልት ላይ ተንከባለለ ፡፡ ቀሪው ዓለም ‹ የኢትዮጽያ ህዝብ ምን ዓይነት ወገኛ ቢሆን ነው ለማጣሪያ እንዲህ መጠን የሚያልፈው ? › ቢል ‹ በሰው ቁስል እንጨት አይሰደደም ! › ብሎ ለመመለስ ግዜ ያጣረው መስሏል ፡፡  ‹ እረ እንደ አሪፎቹ ዋንጫ ቢያነሳ ምን ሊያሳየን ነው ? › የሚል አሽሙር ንፋሱ ቢያደርሰው የፍቅሩን፣ የአንድነቱን፣ የደስታውን፣ የድል ናፍቆቱን፣ የጥቃቱን ልክ በሀገርኛው ቀመር ለማስረዳት እንደሚያስቸግረው ይገመታል ፡፡

ሀገሬው ግን እንደ ዉጩ አይደለምና ራሱን ‹ ቃሉን የደፈረ ተመልካች ! › ብሎ የሳሳ ትከሻውን በኒሻን ሊያጥለቀልቀው ይችላል ፡፡ አምስት ጎል የገባበትን ቡድን ‹ ታሸንፋለህ ! › ብሎ ያነቃውና ያበረታታው እሱ ነውና ፡፡

እነሆ ዋሊያዎቹ ከተራራ ወረዱ ፡፡

አዲስ ታሪክ ሰሩ ፡፡

ለካስ ዋሊያ ሜዳ ላይም ሮጦ ማሸነፍ ይችላል ፡፡

ነገና ከነገ ወዲያ ደግሞ በነጮች ብቻ ሳይሆን በጥቁሮችም ቱሪስቶች ይታያሉ ፡፡

Wednesday, October 10, 2012

የተረሳው ባህል ትንሳኤ ያገኝ ይሆን ?




ኪነ ጥበብ ያዝናናል፡፡ የህብረተሰቡን አስተሳሰብ በአስደሳች መልኩ ቀርጾ መልሶ ለህብረተሰቡ ሲያቀርብ  ‹‹ ወቸው ጉድ ?! ›› ያሰኛል    ፡፡ ታዲያ ልንሰንቅ በምንችለው ግርምት ውስጥ  የመምህርነት ሚና አለው ፡፡ ባልተሰላቸ መልኩ የሚሰጠው ዕውቀት እንደኛ ባሉ ድሃ ሀገሮች ውስጥ ተጠናክሮ መቀጠሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ባህላዊ ዕድገታችንን ዕውን ለማድረግ ይጠቅማል ፡፡

በተረት ፣ በወግ፣ በስነቃልና በስነግጥም ሀብታም በሆነቸው ኢትዮጽያ ‹‹ ኪነ ጥበብ ›› ሲጫወት የቆየው ሚና ቀላል አለመሆኑ ርግጥ ነው ፡፡ ቅድመ አያቶቻችን  በማህበራዊ ትስስራቸው ውስጥ በጉልህ ሲያንጸባርቁት ቆይተዋል ፡፡ በዚህ ረገድ የ ‹‹ በልሐ - ልበልሃ ›› ስርዓት በዋናነት ሊጠቀስ ይችላል ፡፡

በታሪክ የመጀመሪያዎቹ ጠበቆች ካህናት፣ የህግ ምንጭ ደግሞ ብሉይ ኪዳን እንደነበሩ ይነገራል ፡፡ በሀገራችንም ተሟጋቾች የህግ ዕውቀት ያገኙ የነበረው በገዳማትና በሌሎች መንፈሳዊ ተቋማት ፍትሐ ነገስትን በማጥናት እንደነበር ‹‹ ጠበቃና ስነ ምግባሩ ›› የሚለው መጽሀፍ ያስረዳል ፡፡ በርግጥ የድሮ ጠበቆች እንደዛሬው ህግ የሚማሩበት ትምህርት ቤት አልነበራቸውም ፡፡ ትምህርት ቤታቸው አደባባይ ነው ፡፡ ጥብቅናን የሚማሩት ተረት፣ ወግ፣ ሰምና ወርቅ፣ ባህልና ስነ ግጥም በማጥናትና በመለማመድ ነበር ፡፡
የሚከተለው ክርክር ልጅነትን ለማሳወቅ የተደረገ ነው ፡፡ ተከራካሪዎቹ ምን ያህል የስነ ግጥም ብቃት እንዳላቸው እንመልከት ፡፡
ከቤት ክፉ ሰቀላ
ከልብስ ክፉ ነጠላ
ከእህል ክፉ ባቄላ
ከልጅ ክፉ ዲቃላ
መልኩ የእናሪያ / ጥቁር /
እግሩ መታረሪያ
እየው ፊቱን የተገዛበቱን
እናም አላውቅም ልጅነቱን ብሎ ይቃወማል ፡፡

መላሽም በተቃራኒው ወገን የተነሳውን እያንዳንዱ መሰረታዊ ነጥብ በመልቀም የማፍረሻ ወይም የመቃወሚያ ሀሳቦችን ይሰነዝራል ፡፡

ክረምት ያወጣል ሰቀላ
ከብርድ ያድናል ነጠላ
ቀን ያሰልፋል ባቄላ
ጠላት ይገፋል ዲቃላ
መልክም ቢጠቁር የዘር ነው
እግሩም ቢቀጥን ዘምቶ ነው
ስለዚህ ያለብህ ማወቅ ነው በማለት ጠንካራ የአጸፋ መልስ ይሰጣል ፡፡

የታወቁ ጠበቆች አደባባይ ሲሟገቱ ነጭ ልብስ ለብሰው፣ አደግድገው፣ አንዳንዴም ጎራዴ ታጥቀው፣ በቀጭን ዘንግ ወደፊት እየተወረወሩ ሲናገሩም እየጮሁ ነበር ይባላል ፡፡ ይህ እንግዲህ በክርክሩ ውስጥ ከስነ ግጥም ሌላ የትወና ጥበብም እንደሚንጸባረቅ ጠቋሚ ነው ፡፡

በአንድ ወቅት አባትና ልጅ ተጣልተው ተካሰሱ አሉ ፡፡ ይህ በሀገራችን ባህላዊ ልማድ ያልተለመደ ቢመስልም አንዳንዴ ወጣ ያለ አመለካከትና አተያይ  ያላቸው ልጆች አይፈጠሩም ማለት ግን አይቻልም ፡፡ እናም ልጅ ጉዳዩን ባህላዊው ፍርድ ቤት እንዲያይለት አመለከተ ፡፡ አባት ይህን የመሰለ ድፍረት ባይዋጥለትም ልጅ ተጠየቅ ማለቱ አልቀረም ፡፡ በህግ አምላክ ተጠየቅ !! አለ ልጅ  ወግድ !! እያለ አንገራገረ አባት ፡፡ በወቅቱ ለታዳሚው ያሰሙት ሙግትም የምጥቃታቸውን ደረጃ እንዴት አንጸባርቆ እንደነበር በቅንጭብታ እንመልከተው ፡፡

ልጅ ፤  ተጠየቅ ልጠይቅህ ?!
አባት ፤  አልጠየቅም
          ሰማይ አይታረስም
          ውሃ አይታፈስም
         መሬት አይተኮስም
         አባት አይከሰስም !!
ልጅ ፤  ሰማይ በመብረቅ ይታረሳል
         ውሃም በእንስራ ይታፈሳል
         መሬትም በማረሻ ይተኮሳል
         አባትም በጥፋቱ ይከሰሳል !!
አባት ፤ ፍረዱኝ ሰማይ ያለ መዓት ነጎድጓድ አያወርድ
         ፈጣሪ ያለ ክህደት ገሃነም አያወርድ
         ያለ እርሻ በመሬት ላይ እሳት አይነድ
         ሴትም ያለ እንስራ ውሃ አትወርድ
         አባትም ያለ ጥፋት ልጁን አይክድ
         አባት ለልጁ ዳኛ
         አትሞግተኝም ዳግመኛ !!

ልጅም በዋናነት የአባቱን የምላሽ ሰበዝ እየመዘዘ የማጣመም ወይም ሀሳቡን የማክሽፍ ተልዕኮውን ይቀጥላል ፡፡ ለምሳሌ ያህል አባት ልጄን የካድኩት ስላጠፋ ነው የሚል ሀሳብ ፈንጥቋል ፡፡ ልጅም ጥፋት የተባለውን ነገር በመዘርዘር ንጹህ መሆኑን ለማስረዳት እስከ መጨረሻው ይተጋል ማለት ነው ፡፡ ሌላው አስገራሚ ገጽታ ሁልግዜም ቢሆን ተከራካሪዎች ጥፋተኛ መሆናቸውን ልባቸው ቢነግራቸው እንኳን ከፍተኛ የራስ መተማመን እንዳላቸው የሚያሳዩበት መንገድ ነው ፡፡ ባላጋራቸውን በማስደንገጥ ከክርክሩ እንዲወጡ ከፍ ያለ ቃል ይገባሉ ፡፡ ለምሳሌ ያህል አንደኛው ፤

በልሀ ልበልሃ ልንዛብህ
የሙግት ዠሃ
ሀሰት ቢገኝብኝ በቃሌ
ቅቤ አምጥቼ በብርሌ
እሰጣለሁ ለሽማግሌ ሊል ይችላል ፡፡ ሌላኛውም

በላ ልበልሃ
ልንዛብህ የሙግት ዠሃ
ብትወነጅለኝ በሀሰቱ
ይበረታብሃል ቅጣቱ
የረታህኝ እንደሁ ተሟግቼ
ቀንጃ በሬዬን አምጥቼ
ለዕለት ጉርሴ እንኳን ሳልሳሳ
አገባታለሁ እምቦሳ


በማለት የጠነከረ ምላሽ ይሰጣል ፡፡ ከዚህ በኃላ ክርክሩን ራሳቸው ስላጦዙት ሰሚውም ሆነ ፍርድ ሰጪዎች ዳኞች ቀጣዩን ለመስማት ያቆበቅባሉ ፡፡

እስቲ ሌላ ዘወር ያለ አብነት ደግሞ እንመልከት ፡፡ አንድ በሬ የጠፋበት አርሶአደር በፍለጋ ረጅም ሰዓት ቢያሳልፍም በቀላሉ ማግኘት አልቻለም ፡፡ ሁኔታው አበሳጨው ፡፡ ጉዳዩን ዝም ብሎ መተው የለበትምና በፍለጋ ሰዓታት ያያቸውን ጥቃቅን ፍንጮች በማገጣጠም የሰፈሩን ሰው ጠረጠረ ፡፡ እናም ሊሞግተው አደባባይ አቆመው ፡፡ 

ከሳሽ ፤ የአጤ ስርዓቱን የመሰረቱን
         አልናገርም ሀሰቱን
         ሁልግዜ እውነት እውነቱን
         መጣሁ እንደ ውሃ ስፈስ
         እንደ ጋዣ ስነፍስ
         በቅሎዬ ሰጋሪ
         ሚስቴ ነጭ ጋጋሪ
         ለወታደር የለው ምሳ
         ለቀበሮ የላት ገሳ
         በሬዬ ጠፍቶ ከደጋ
         ስከተል  መጣሁ በደም ፍለጋ
         ብደርስ በፍለጋው ከደጅህ
         ሙዳ ስጋ ይዟል ልጅህ
        ስለዚህ በሬዬን ትከፍላለህ በግድህ !!

ተከሳሽ ፤ ፍየል መንታ ትወልዳለች አንዱ ለመጣፍ
           አንዱ ለወናፍ
           መጣፉ እኔ መናፉ አንተ
           እንደ ውሃ ብትፈስ በቦይ ትመለስ
           እንደ ጋዣ ብትነፍስ አጭዶ ለፈረስ
           ሚስትህ ነጭ ብትጋግር  አንድ እንግዳ አታሳድር
           በቅሎህ ብትሰግር እመሸበት ታድር
            እንዴት ለወታደር የለውም ምሳ
            እራት ጋግሮ ለራት ለምሳ
            እንዴት ለቀበሮ የላት ገሳ
            ትገባለች አርባ ክንድ ምሳ
            በሬህ ቢጠፋ ከደጋ
            አንተም ብትመጣ በደም ፍለጋ
            ከቤቴ በላይ አለ ተራራ
            መዘዋወሪያው የጅብ ያሞራ
            አሞራና ጅብ ሲጋፉ
            ሙዳ ስጋ ስጋ ስለተፉ
            ያላወቀ ልጅ ቢያነሳ
            አያስከፍለኝም ነገርህን አንሳ !!  ይለዋል ፡፡ 

ተሟጋቾቹ በግለት ሲከራከሩ ከየጎጡ መጥተው የታደሙ ሰዎች በክርክሩ መሃል    ‹‹ እውነት ነው !! በደንብ አርገህ ንገረው !! ይገባዋል !! ›› በማለት ደጋፊ ሀሳብ በማቅረብ አጋርነታቸውን ይገልጻሉ ፡፡

ይህን በመሰለ መልኩ የሚደረግ ክርክር ላይ መገኘት መንፈስን እንደሚያስደስት አያጠራጥርም ፡፡ ከዘመናዊ ህግ አሰራር አኳያ ‹‹ በልሀ ልበልሃ ›› አንዳንድ ክፍተቶች ሊኖሩበት ቢችልም ይህ ድንቅ ባህል እየተረሳና እየጠፋ መሄዱ በተለይም ኪነ ጥበብን የሚጎዳ ይመስለኛል ፡፡ ሰዎች ሀሳባቸውን በግጥምና ስነ ቃል መግለጻቸው ፣ በግጥም የሚቀርቡ ሀሳቦችን ደግሞ ያለ ምንም ችግር ማጣጣም መቻላቸው ለደራሲዎች ቀጣይና የጠነከረ ፈጠራ ምርኩዝ ይሆናል ፡፡ ጥሩ ልቦና ያላቸው ደራሲያን በበዙ ቁጥር ብዙ እንዲጽፉ ይገፋፋቸዋልና ፡፡

በልሀ ልበልሃ በአሁኑ ወቅት ለዘመናዊ ህግ አያስፈልግ ይሆናል ፡፡ ወይም አባት ነኝ ባዩ ህግ ያንተ ነገር በቃኝ በማለት ክዶት ይሆናል ፡፡ ግን በልሃውንና ዘመናዊውን ህግ እንደ ሀገራችንና እንደ ሌሎች ሀገሮች ፕሬዝዳንትና ጠቅላይ ሚኒስትር በንጽጽር ማየት ጠቃሚ ይመስለኛል ፡፡ በልሃውና ንጉሱ የመወሰን ስልጣናቸው አነስተኛ ቢሆንም ክብርና ሞገሳቸው ትልቅ ነው ፡፡ ፕሬዝዳንታችን ህጎችን በነጋሪት ጋዜጣ ያውጃል ፤ በልሃው የቀድሞው ማንነታችን አለመሞቱን ያውጃል ፡፡ ፕሬዝዳንታችን የሹመት ደብዳቤ ይቀበላል ፤ በልሃው ከገጠር ቅኔ ዘራፊዎችም ሆነ ከከተሜው ገጣሚዎች የተሳትፎ ጥያቄዎችን እየተቀበለ የተቀናጀ ተሳትፎ እንዲደረግ ሀሳብ ሊያመነጭ ይችላል ፡፡ ፕሬዝዳንታችን ኒሻኖችንና ሽልማቶችን ይሰጣል ፤ በልሃው በት/ቤት፣ በትያትር ቤት፣ በዩኒቨርስቲዎችና በኮንሰርቶች ውድድር እየተካሄደ ለሚያሸንፉት ሽልማት ይሰጣል ፡፡ ፕሬዝዳንታችን ይቅርታ ያደርጋል ፤ በልሃው ተሸናፊዎች በተጋነነ ቅጣት እንዳይጎዱ ይቅርታ ያደርጋል ፡፡

ታዲያ ማነው ይህ ጠቃሚ ባህል ተጠብቆ እንዲቆይ መስራት ያለበት ? እንደ እኔ እምነት ቢያንስ ይህን የህግ የበኩር ልጅ በጉዲፈቻነት ለማሳደግ የባህል መዋቅሮችና በደምሳሳው ከያኔዎች ግንባር ቀደም ሚና መጫወት ይኖርባቸዋል ፡፡


Monday, September 24, 2012

የጉራጌ ቁጥሮች



እየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል በተአምራዊነቱና በክርስቲያኖች ዘንድ ከፍተኛ ክብር የተሰጠው በመሆኑ፣ አይሁድ በቅናት ተነሣሥተው ለ300 ዓመታት ያህል በቆሻሻ መጣያ ጥለውት ነበር። ይሁንና በ326ዓ/ የቄሳር ቆስጠንጢኖስ እናት ንግስት እሌኒ ኪራቆስ በተባለ አንድ የታሪክ አዋቂና ሽማግሌ ጠቋሚነት፣ መስቀሉ የተጣለበትን አካባቢ ወቀች ። ከዚያም በኋላ ደመራ ደምራ በእሳት አቀጣጥላ ዕጣን ባጨሰች ጊዜ ፣ የዕጣኑ ጢስ ወደ ላይ ከወጣ በኋላ ተመልሶ ያረፈበትን ሥፍራ አስቆፍራ መስቀሉን አወጣች።
ንግሥተ እሌኒ በጭሱ ምልክትነት፣ መስቀሉን ለማውጣት ለሰባት ወራት ያህል ማስቆፈሯን ማለትም መስከረም 17 ቀን አስጀምራ መጋቢት 10 ቀን እንዳስወጣቸው ይነገራል። ዛሬ በኦርቶዶክስ ምዕመናን ዘንድ ደመራ የሚደመረውም ይህንን ታሪክ ተከትሎ እንደሆነ ሊቃውንቶች ይናገራሉ ፡፡
መስቀል ብዙ ነገር ነው ፡፡ ክርስትያኖች በግጥም ሲገልጹት እንደሚከተሉት ይደረደራል ፡፡

ዕፀ መስቀሉን ያዙ ጋሻ
ሰይጣን እንዲጠፋ እንዲያጣ መድረሻ ፡፡
ዕፀ መስቀለን ተሳለሙ
የአምላክ ቃል አለበት ደመ ማህተሙ ፡፡
መስቀል ኃይል ነው ለክርስቲያን
እሱን የያዘ ሰው አይደፍረውም ሰይጣን ፡፡
መመኪያችን ነው መስቀል
ተቀድሷልና በመለኮት ኃይል ፡፡

መሰቀል በዓል ብዙ ገራሚ ትውፊቶችን በየክልሉ አቅፎ የያዘ ነው ፡፡ የአዲስ አበባው በከተሜው፣ በመዘምራን፣ በሃይማኖት አባቶችና በቱሪስቶች ድብልቅ መንፈስ ተዋህዶ ልዩ ለዛና መስህብ ይፈጥራል ፡፡ በተለይም በደቡብ ክልሎች ያለው የመስቀል ስርዓት ባህላዊ ትውፊቱ እንደ ተራራ የገዘፈ ሀሴትን የሚያጭር ነው ፡፡ ይህ ባህላዊ እሴት በዓመት አንዴ የሚነገርለት እንጂ ሰፊ ምርምር ተካሂዶበት እንደሚታይ ድንቅ ቅርስ በውስጣችን የምንተክለው አልሆነም ፡፡ ዞሮ ዞሮ የጉራጌ ብሄረሰብ የበዓል አከባበርም ዩኔስኮ  እንዲመረምረውና ዕውቅና እንዲሰጠው ከወዲሁ መጠየቅ አስፈላጊ ሳይሆን አይቀርም ፡፡
አነዚህ በመስቀል ሰሞን የሚደምቁት የጉራጌ 13 ቁጥሮች ማለትም 12፣ 13 ፣ 14.፣ ……. 23፣ 24 …. የማይዳሰሱ ሃብቶች እየመሰሉኝ ነው ፡፡  በበዓል አይን ስናያቸው እያንዳንዳቸው የሚያምር የተግባር ዝናር  ታጥቀዋል ፤ ይህን ወረድ ብለን እናየዋለን ፡፡ በሌላ በኩል ግን በዓላዊ  ምሳሌያቸውን በማስፋት ለሌላ የትግል ግዳጅ ማዝመት ይቻላል ፡፡ ለምሳሌ ነው - የብሄራዊ ቡድናችን ተጫዋቾች አነዚህን ቁጥሮች ለምን ለጀርባቸው መጠሪያ አያደርጓቸውም ? ቀንደኛ ግብ አዳኝ ካለን የማሊያ ቁጥሩ ዳመራው በሚቀጣጠልበት ቀን ይሆናል ፡፡ የራቀንን ውጤት በዚህ መልክ ማምጣት ይቻላል ወይስ ለምን ጥቅም አትበሉኝ ፡፡ ለምሳሌ ነው - መስከረምን 12ኛ ወር ብለነው ጻጉሜን 24ኛ ማድረግ ይቻላል ፡፡ እንደ ጻጉሜ ሁሉንም ልዩ ለማድረግ ወይስ ለምን ጥቅም አትበሉኝ ፡፡ ለምሳሌ ነው - ....
መስቀል ለጉራጌ ብሄረሰብም ብዙ ነገር ነው ፡፡
መስቀል ደስታ ነው
መስቀል ትዳር ነው
መስቀል ምርቃት ነው
መስቀል መዝናኛ ነው
መስቀል የቁጥሮች ውበት ነው ፡፡
መስቀል በጉራጌ ሲታሰብ ከ12 እስከ 24 ያሉ ቁጥሮች ምን ያህል የተለቀ ሚና እንደሚጫወቱ ማሰብ ይቻላል ፡፡  ለመሆኑ በነዚህ ሁሉ እንደ ባቡር ፉርጎ የተቀጣጠሉ ቀናት ምን ይደረጋል መባሉ አይቀርም፡፡ እያንዳንዱ ቀን በራሱ በዓል ወይም የበዓል ድጋፍ ሰጪ ነው ፡፡ እስኪ ቀናቱን እየተረጎምን እንውረድ፡፡
መስከረም 12 ፤  የጃፎር መስቀል ይባላል ፡፡
ይህ በዓል በቡድን በመሆን በዛፍ ስር ይከበራል ፡፡ የቡድኑ አባላት መስዋዕት የሚያደርጉትን ከብት ይዘው ዛፉ ስር  የሚገናኙት ከቀኑ አስር ሰአት ላይ ነው ፡፡ የተዘጋጀው በሬ ታርዶ ደሙ ዛፍ ላይ ሲረጭ ሞራውም በእሳት ይቃጠላል ፡፡ የዚህም ምክንያት የሞራው ሽታ አካባቢውን ከበሽታ ነጻ ያደርገዋል የሚል ነው ፡፡ አባላቱ የቻሉትን ያህል ጥሬ ስጋ በልተው ቀሪውን ተከፋፍለው ወደ ቤት ሲያመሩ ዞረው እንዲያዩ አይፈቀድም፡፡ ቦታውን ከለቀቁ በኃላ ይተካል ተብሎ በሚገመተው ኃይል ችግር እንዳይደርስባቸው በመስጋት ፡፡

መስከረም 13 ፤  ወሬት ያህና ወይም እንቅልፍ ነሺ ቀን ይሉታል ፡፡
 በዚህ ቀን እንቅልፍ የሚታጣው ሁሉም ቤተሰብ መስቀልን ‹‹ እንዴት አሳልፈው ይሆን ; ›› ብሎ ስለሚያስብ ነው ፡፡ አንዳንድ     ሰዋች ቀኑን የበዓሉ መክፈቻ ይሉታል ፡፡
መስከረም 14 ፤ ይፍት ወይም የዕርድ ዋዜማ የሚል መጠሪያ አለው ፡፡
ቀን ሴቶቹ የቤቱን ጣራና ግድግዳ ካጸዱ በኃላ መሸት ሲል ለቤቱ ወለል የተሰሩት ምንጣፎች ይነጠፋሉ ፡፡ የቤት ዕቃዋችና        ጌጣጌጦች ግድግዳ ላይ ይሰቀላሉ ፡፡ ቆጮው በተለየ መልኩ በእንፋሎት ብቻ እንዲበስል ይደረጋል ፡፡ ይህም ‹‹ ዳቡዬ ›› በሚል ይታወቃል ፡፡ ይህ አይነት የቆጮ ጋገራ የተመረጠው አማልክት በምግብ ስነ ስርዓት ላይ የሚሳተፉ ባለመሆናቸው ቢያንስ ሽታው እንዲደርሳቸው በማሰብ ነው ፡፡

መስከረም 15 ፤  ወኀምያ ወይም የእርድ በዓል ተብሎ ይጠራል ፡፡
ወኀምያ ደስታና ሰላም ማለት ነው ፡፡ እለቱ በአንዳንድ አካባቢዋች ‹‹ የጨርቆስ ማይ ›› በመባል ይታወቃል ፡፡ ይህ እለት ጨርቆስን ያመለክታል ፡፡ በዚህ ቀን ለእርድ የተዘጋጁ ከብቶች በየቤቱ በራፍ ይታረዳሉ ፡፡ ከበሬው የሚፈሰው ደም በቃጫ ተነክሮ የቤቱ ደጃፍ መቃንና ምሶሶ ይቀባል ፡፡ ከበሬው የተገፈፈው ሞራም እስከ መጪው ዓመት ድረስ የቤት ምሶሶ ላይ ይሰቀላል ፡፡ የማረድ ግዴታ ያለባቸውና የሌለባቸው ሰዋች እንዳሉም መታወቅ አለበት ፡፡  የማረድ ልምድ ያለባቸው ሰዋች የወሸምያ ዕለት ካላረዱ ወሸምያ ይገድላቸዋል ተብሎ ይታመናል ፡፡ በየዓመቱ ከሚያርዱበት የተወሰነ ቦታ ፈቀቅ ለማለት እንኳን አይሞክሩም ፡፡ ልማድ የሌላቸው ሰዋች ግን ስጋም ገዝተው በዓሉን ማክበር ይችላሉ ፡፡

የማረድ ልማድ ያለባቸው ልምዱን ለመሰረዝ ከፈለጉ የሚከተለውን ህግጋት ተግባራዊ ማድረግ አለባቸው ፡፡ በየአመቱ በሬ የሚያርድ ሰው በቀጣዩ ዓመት ጥጃ ያርዳል፡፡ በሁለተኛው ዓመት ፍየል ያርዳል ፡፡ በሶስተኛው ዓመትም ፍየል ያርዳል ፡፡ በአራተኛው ዓመት ዶሮ አርዶ በአምስተኛው ዓመት ምንም ባያርድ ወሽምያ ስለሚረሳ ችግር አይመጣበትም ፡፡ አሪፍ የማካካሻ ስልት ናት ፡፡

መስከረም 16፤   ምግይር ወይም ደመራ ነው ፡፡
ደመራው በየቤቱ ደጃፍ የሚተከለው የልጆች ደመራና የአባቶች ደመራ ተብሎ ይታወቃል ፡፡ በየበራፉ የሚተከለውን ደመራ ጠዋት ወይም ማታ ማቀጣጠል ይቻላል ፡፡ የአባቶች ደመራ የሚለኮሰው ግን ከምሽቱ አንድ ሰዓት ጀምሮ ነው ፡፡ በዚሁ ግዜ አባ ተዘር / ክረምትና በጋ / የተባለውን ጨዋታ ልጆች ይጫወታሉ ፡፡ በደመራ እለትም ሆነ በሌሎች የመስቀል ቀናት ከብቶች ውጪ አይወጡም ፡፡ የተዘጋጀላቸውን ምግብ ከቤት ይበላሉ ፤ አይታለቡም ፡፡

መስከረም 17፤    ንቅባር ወይም ትልቁ በዓል ይባላል ፡፡
በዚህ ቀን ቤተዘመዶች ፣ በቡና የሚገናኙ ጎረቤቶች ተሰብስበው ደስታቸውን ይገልጻሉ ፡፡ አዛውንቶች አናታቸው ላይ ቅቤ ይደረግላቸዋል ፡፡  የከብቱ ሻኛም የሚበላው በዚህ ቀን ነው ፡፡ አንድ ሰው እናት ፣ አባት፣ ታላቅ ወንድም ወይም አያቱ እያለ የመስቀል ሻኛን ለብቻ አይበላም ፡፡ ዘመድ ከሌለው እንኳን በእድሜ የገፉ አዛውንቶች ጋ ይዞ በመሄድ ማስመረቅ ይኖርበታል ፡፡ ይሄ ሁሉ ለሻኛ  ; ካላችሁ ሻኛ በሰባት ቤት ጉራጌ የበስር ንጉስ ወይም የስጋ ንጉስ መባሉን ማወቅ ያስፈልጋል ፡፡

መስከረም 19- 23 ፤   የጀወጀ ወይም የመተያያ ቀን ይባላል ፡፡ ከመስከረም 18 በኃላ ያሉትን ቀናት የሚያመለክት ሲሆን ለአንድ
ሳምንት ያህል ባሉት ቀናት ባልና ሚስት ወገኖቻቸውን በተለይም እናት አባቶቻቸውን ስጦታ በመያዝ የሚጠይቁበት ነው ፡፡    የሙየቶቸም ጭፈራ ይከናወናል ፡፡ ሙየት ማለት በእናቶችና ሴቶች የሚዘፈን ባህላዊ ጨዋታ ነው ፡፡
ዘመዳሞች ይጠያየቃሉ፣ ይመራረቃሉ ፡፡

መስከረም 24 ፤   አዳብና ወይም መሰነባበቻ በሚል መጠሪያ ይታወቃል ፡፡ በአንዳንድ በተ ጉራጌዋች ዘንድ ከጀወጀ በተለየ መልኩ አሁንም
                   ድረስ በድምቀቱ  የሚታወቅ ሲሆን ለወጣቶችና ልጃገረዶች የተለየ የጭፈራ አጋጣሚ ነው ፡፡ ጭፈራው ከመስከረም
                    አጋማሽ ጀምሮ  ጥቅምት ድረስ ይዘልቃል ፡፡ የአዳብና ጭፈራ በገበያዋች ላይ የሚከወን ሲሆን ድንቅ ባህላዊ አልባሳትና
                   የውዝዋዜ  ትዕይንቶች ይታዩበታል ፡፡ በነገራችን ላይ ‹ መንጠየ › የቋንጣ ክትፎ የሚበላበት የመጨረሻ ስነ ስርዓት ማሳረጊያ
                    ነው ፡፡ ይህ በዓል በአንዳንድ አካባቢዋች እስከ ጥቅምት 5 ሊቆይ ይችላል ፡፡