Sunday, April 21, 2013

‎‹‹ በዓሉ ግርማ በባህርዳር ››‎




ሰሞኑን ለስራ ወደ ሰሜን ስጓዝ በውስጤ ግዘፍ ነስቶ የቆየው የበዓሉ ግርማ ጉዳይ ነበር ፡፡ በቂ ግዜ ካገኘሁ ‹ የፌስ ቡክ ሰራዊት › ሲወያይበትና ሲከራከርበት ለከረመው አጀንዳ ቢቻል የተጠጋጋ ካልሆነም እንደነገሩ የቆመ መረጃ አሰባስቤ እመለሳለሁ ስል አሰብኩ ፡፡

የዜናው መነሻ ፤

‹‹ ከወደ ባህር ዳር አካባቢ የተሰማው ወሬ በርካቶችን እያስገረመና እያስደነገጠ ይገኛል … ደራሲ በዓሉ ግርማ በዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም ውስጥ አለም በቃኝ ብሎ ሞንኩሶ እግዚአብሄርን እያገለገለ መሆኑ ታውቋል … በይስማዕከ ወርቁ ደራሲነት የምናውቃቸው ዴርቶጋዳ ፣ ራማቶሃራ ፣ ዣንዣራ እና ተልሚድ የተሰኙ ስራዎች የደራሲ በዓሉ መሆናቸው ተረጋግጧል … ይህ ወሬ ከተሰማ በኃላ በርካታ የባህር ዳር ነዋሪዎች የዳጋ ደሴትን ያጨናነቁ ሲሆን የአዲስ አበባና ሌሎች ከተሞች ነዋሪዎችም በአስገራሚ መልኩ ወደ ስፍራው እየተመሙ ናቸው … ››

ይህን ዜና ያለማመንታት ‹‹ የማይታመን ›› ያሉ የመኖራቸውን ያህል ‹‹ ትክክለኛ ነው ›› እንዲሁም ‹‹ ትክክል ሊሆን ይችላል ›› የሚሉ ግምቶችን ያስቀመጡ ጥቂቶች አልነበሩም ፡፡ እኔም ‹‹ የደራሲዎች እየሱስ ! ›› የምለውን የበዓሉን ብዕር ከአድማስ ባሻገር እስከ ኦሮማይ እንደ ማስቲካ እያላመጥኩ ፣ ድዴ ሲደክም ደግሞ ወሬውን ለስራ ባልደረቦቼ በማካፈል መቋጫ የሌላው ክርክር እንዲነሳ ማድረጌ አልቀረም ፡፡

ከዚህ ቀደም ባለው አነጋገር ለመሞቱ ፣ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ደግሞ ለመጥፋቱ ምክንያት የሆነው ኦሮማይ የተባለውን መጽሀፍ … የማላቀውን የዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም … እንደ አብርሃም ቤት የለኝ እንደ ሙሴ መቃብሬ አይታወቅ የሚለውን የደራሲው ገጸ ባህሪ… ጽሁፍ ህይወት ነው ከዚያ ውጪ ሌላ የህይወት ምኞት የለኝም የሚለውን በዓሉንና በሰበቡ የተነሱትን እነ ዴርቶጋዳ …  ወደ ገዳም ለመጓዝ ሁከትና ጉጉት የሚታይበትን የባህርዳር ህዝብ… ተራ በተራ እየሳልኩ ነበር ባህርዳር የደረስኩት ፡፡

የማጣሪያ ወሬ ፤

በበዓሉ ግርማ ዙሪያ የተነሳውን ዜና ወይም ወሬ ለማጣራትና ወደ አንድ አቅጣጫ ለማምጣት በጉዳዩ ዙሪያ የሚወዳደሩ ክፍሎችን ወይም የሊግ አባላትን ማብዛት ያስፈልጋል ፡፡ ጋዜጠኛም ጸሀፊም በመሆኔ ነው መሰል አስቀድሜ የጨዋታውን ንድፍና ህግጋት / sketch / ለመሳል ያልቦዘንኩት ፡፡ በዚህ ፍትጊያ መሃል ነው ለእውነት የተጠጋ መረጃ ሊገኝ የሚችለው ወይም የተሰወረ መንገድን ማወቅ የሚቻለው ፡፡

እናም የባህርዳር ነዋሪዎች ፣ የተለያዩ የመንግስት መዋቅሮች / ፖሊስ ፣ ባህልና ቱሪዝም ፣ ጋዜጠኞች / ፣ ቀሳውስት ፣ መጽሀፍት ሻጮች ፣ አንባቢዎች ፣ የጀልባ አከራዮችና የዳጋ እስጢፋኖስ አስተዳደሮች በማጣሪያው እንዲሰለፉ አቀድኩ ፡፡ የትኛው ቡድን ወይም የትኛውም መንገድ ለፍጻሜ እንደሚደርስ ለመተንበይ ግን አልሞከርኩም  ፡፡

በጉዳዩ በጣም ተጨናንቋል የተባለውን የባህር ዳር ነዋሪ እኔ ያገኘሁት በሁለት መልኩ ነው ፡፡ አንደኛውና በጣም የሚበዛው ጭራሽ ስለ ርዕሰ ጉዳዩ ያልሰማና ምንም መረጃ የሌለው ነው ፡፡ ሁለተኛው ክፍል ስለ ጉዳዩ የሚያውቅ ነገር ግን የተለያዩ መላምቶችን ደርዝ በሌለው መልኩ ያዘለ ነው ፡፡ አንዳንዶች ‹‹ እስካሁን ይወራል እንጂ የታመነ ዜና አልተገኘም ›› ይላሉ ፡፡ ሌሎች ‹‹ ተጨባጭ መረጃ ባይገኝም በዓሉ ግርማ ገዳሙ ውስጥ ሊኖር እንደሚችል ይሰማናል ›› ብለዋል ፡፡ ወሬው ሀሰት ነው ከሚሉት ውስጥ ዜናው ተቀነባብሮ የተፈጠረው በጀልባ አከራዮች ነው ያሉት ጥቂቶች አይደሉም ፡፡ ለምን ለተባለው ጥያቄ ደግሞ ‹‹ ገበያ ለመፍጠር ›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ደራሲው ገዳም ውስጥ ሊኖር ይችላል የሚሉ ወገኖች ዋነኛ መከራከሪያ ደግሞ በዓሉ በደርግ ተይዞ ተሰወረ ተባለ እንጂ ስለመሞቱ ማረጋገጫ ያለመገኘቱን ጉዳይ ነው ፡፡

በርግጥ የበዓሉ ግርማ ወሬ በፌስ ቡክ ከተለቀቀ በኃላ በባህርዳር የሚገኙ የመንግስት አካላት ጉጉትና ውጥረት ገኖ ቆይቷል ፡፡ አንድ ስሙ እንዳይገለጽ የፈለገ የመንግስት ሰራተኛ የተለያዩ ከፍተኛ ኃላፊዎች ወሬው እውነት ይሁን ሀሰት እንዲጣራ በተለያዩ መንገዶች በገዳሙ ውስጥ ፍለጋ እንዲከናወን አድርገዋል ፡፡ ይህም ጥረት የገዳሙን ነዋሪ ከማጨናነቅ የዘለለ ተጨባጭ ፋይዳ ያስገኘ አልነበረም ፡፡ አንዳንድ የፖሊስ ሰራዊት አባላትም ወሬውን ሊያረጋግጥ የሚችል መረጃ ባለመገኘቱ እውነት ነው የሚል እምነት የለንም ብለዋል ፡፡

ርዕሰ ጉዳዩ ጋዜጠኞችም ሰፈር ደርሷል ፡፡ ጋዜጠኞችም ወሬው ህብረተሰቡ ምርጫውን በአግባቡ እንዳያከናውን ለማደናቀፍ ወይም ለማዘናጋት የሚደረግ ጥረት እንደሆነ ገለጻ ተደርጎላቸዋል ፡፡

በባህርዳር ከተማ ጥቂት የማይባሉ መጽሀፍት መሸጫ መደብሮች ይገኛሉ ፡፡ በዚህ ወሬ ምክንያት የበዓሉ ግርማ መጽሀፍት ከወትሮው በተለየ መልኩ ሊሸጡ እንደሚችሉ ገምቼ ነበር ፡፡ ይህን ግምት ይዤ አራት ከሚደርሱ ነጋዴዎች ጋር ተወያየሁ ፡፡ ሁሉም ስለ ወቅታዊው ወሬ ከበቂ በላይ መረጃ ቢኖራቸውም በዚሁ ሰበብ የበዓሉ ግርማ መጽሀፍት እንዳልተሸጡ ተናግረዋል ፡፡ ሁለቱ ሚያዚያ ውስጥ የተሰማው ወሬ ‹ የአፕሪል ዘ ፉል › ውጤት መሆኑን ሲናገሩ ሁለቱ ደግሞ ማንኛውም ወሬ ውስጥ ጥቂት የእውነት ፍሬ ሊገኝ እንደሚችል ጠቋቁመዋል፡፡ በየግዜው ለገዳሙ በርካታ መጽሀፍት እየተገዙ መግባታቸው የትላልቅ ሰዎች መናኀሪያ መሆኑን ለማስረዳት በመሞከር ፡፡

ሰው በሰው ያገኘኃቸው ቀሳውስት ወሬው ከተማው ውስጥ እንጂ በገዳሙ እንደማይሰማ ተናግረዋል ፡፡ ለብዙ ዓመታት በገዳም ውስጥ ህይወታቸውን ያቆዩ አባቶችን የትናንት ማንነት ለማወቅ ከባድ መሆኑን ብቻ ሳይሆን ብዙም ጠቃሚ እንዳልሆነም አስረድተዋል ፡፡ አለም በቃኝ ብሎ ከፈጣሪ ጋር ለመገኛኘት የሚተጋ ህብረተሰብ የቀደመውን ማንነት ማስታወስ ምን ይረባዋል በማለትም ጫጫታውን ለማርገብ የሞከሩም ይመስላሉ ፡፡

ይህ የጥቂት ቀናት አሰሳ ከጥሩ አንባቢያን ጋርም አገናኝቶኛል ፡፡ በተለይ አንድ አንባቢ ‹ ጥሩ ቀልድ ናት › ነው ያለኝ ፡፡ ይህ ሰው ወሬው ሆን ተብሎ ተቀነባብሮ የተፈበረከው የመቀበል ጸጋ በተሳናቸው ጠማማ ሰዎች ምክንያት እንደሆነ ነው የሚያምነው ፡፡ እሱ ጠማማ ሰዎች የሚላቸው የይስማዕከ ወርቁን ችሎታ ለመቀበል የተናነቃቸውን ነው ፡፡ ወጣቱ ደራሲ ያልተጠበቁ ስራዎች መስራቱ የቅናትና የመበለጥ ስሜታቸው እንዲቆጣ ምክንያት ፈጥሯል ፡፡ እናም ህያው ውብ እጅን ከማድነቅ ይልቅ ለሰበብነት የሞተ ማንነትን እንደ ምክንያት መጠቀም ተመርጧል ፡፡

ወሬውን መንግስት ራሱ ሆን ብሎ ያሰራጨው  መሆኑን በልበ ሙሉነት የሚናገሩም አጋጥመውኛል ፡፡ ይህ ዓይነት አከራካሪና በቀላሉ እልባት ሊያገኝ የማይችል መረጃ የሚለቀቀው ወቅታዊ ጉዳዮችን ወይም ውጥረቶችን ለማርገብ ሲፈለግ ነው ፡፡ መንግስት ከሙስሊሙ ህብረተሰብ ጋር መጋጨቱ ፣ ከተለያዩ ክልሎች የተፈናቀለው የአማራ ብሄረሰብ ጉዳይ መነጋገሪያ መሆኑን እንደ ምክንያት ያነሳሉ ፡፡ በተቃራኒው የበዓሉ ግርማ በዳጋ እስጢፋኖስ የመታየት ጉዳይ ለገዢው ክፍል የሚመች ዜና ያለመሆኑን ያስረዱ አሉ ፡፡ እንዴት ሲባሉ የበዓሉ በህይወት መገኘት የደርግን ገዳይነትና ጨካኝነት እንዲለዝብ ስለሚያደርግ በኢህአዴግ አይን መታየት ያለበት ጉዳይ አያደርገውም ፡፡ በመሆኑም ለገዳሙም ሆነ ለደራሲው ቀጣይ ስጋት እንዲፈጠር ሊያደርግ ይችላል ፡፡

መንገዶች ሁሉ ወደ ጣና ይወስዳሉ ፤

ከሰማኃቸው መረጃዎች መካከል ዳጋ እስጢፋኖስ የዶክተሮች ፣ የምሁራኖችና በንባብ የመጠቁ በርካታ ሰዎች ስብስብ ገዳም ነው የሚለው አስተያየት ከፍ ብሎ ይሰማኛል ፡፡ በገዳሙ ለሚገኙ ሰዎች አንዳንድ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገራት በጎ አድራጊዎች መጽሀፍና ቁሳቁስ የሚረዷቸው ከምን አንጻር ነው ? የሚለውም ጥያቄ የጥርጣሬ ሚዛን ወደታች ዝቅ ብሎ እንዲመዝን የሆነ አስተዎጽኦ ሊያደርግ ይችላል ፡፡ በርግጥ ዳጋ እስጢፋኖስ ጥቅጥቅ ባለ ደን የተሸፈነና ከሌሎቹ ገዳማትም ልዩ ገጽታ እንዳለው ይታወቃል ፡፡ የገዳሙ ህንጻ የጀልባ ቅርጽ ያለው ሲሆን የዚህ ተምሳሌትም የኖህ ጀልባ የሰው ዘርን ከጎርፍ ጥቃት የማዳኑን ምስጢር ይጠቁማል ፡፡

በዓሉ ግርማ በዚህ ደንና ዋሻ ውስጥ ተደብቆ ይሆን ? ‹ ተፈጸመ › ን ለንባብ አበርክቶ የፍጻሜው ማረፊያ ትሆን ዘንድ በኖህ ጀልባ ተሳፍሮ ይሆን ? ሽቅርቅሩና ታጋዩ ደራሲ በርግጥ ጭምተኛና ገዳማዊ መሆንን መርጧል ? ከሆነ እንዴት ከባድ ምርጫ ነው ፡፡ ምክንያቱም አንድ ገዳማዊ ጤዛ ልሶ ፣ ድንጋይ ተንተርሶ ፤ ድምጸ አራዊትን ግርማ ሌሊትን ታግሶ ነው የሚኖረው ፡፡ አንድ ገዳማዊ ከዓለማዊ ኑሮ ርቆ ፣ ራሱን በራሱ እየረዳ ዘወትር በጾምና ጸሎት ፣ በገድልና ትሩፋት ተጠምዶ የሚኖር የእግዚአብሄር ሰው ነውና ፡፡

እንደ ጣና ማዕበል ግራና ቀኝ የሚላተመውን ሀሳብ ይዤ ወደ ጣና ኃይቅ የግል ጀልባ ማህበር አመራሁ ፡፡ እዚህ ወደ ዳጋ እስጢፋኖስ የሚቀዝፉ ጀልባዎች ይገኛሉ ፡፡ እዚህ ወደተለያዩ ገዳማት የሚጓዙ ሰዎችን ሀሳብና ፍላጎት እንዳልሰሙ ሆነው የሚሰሙ የጀልባው ካፕቴኖች ይገኛሉ ፡፡ እዚህ ስለገዳማቱ የቀረበ መረጃ ያላቸው ሰዎች አይጠፉም ፡፡ እዚህ የሀሰት ፈጠራ ሊፈበረኩ ይችላሉ ተብለው የሚታሙ ሰራተኞችም አሉ ፡፡

ሰላምታ ሰጥቼ ወደቢሮው ከዘለቅኩ በኃላ ስለ ስራ ጉዳይ ማውራት ጀመርኩ ፡፡ የማህበሩ ኃላፊ የሞቀ አቀባበል አደረገልኝ ፡፡ ሞተሬን ካሞቅኩ በኃላ ስለ ርዕሰ ጉዳዩ መጠየቅ ጀመርኩ ፡፡

‹‹ በዓሉ ግርማ በዳጋ እስጢፋኖስ ሊኖርም ላይኖርም ይችላል ›› በማለት ማጋደል ያቃተው ምላሽ ወረወረልኝ
‹‹ እንዴት ነው ሊኖር የሚችለው ? ››
‹‹ ገዳሙ የምሁራን አምባ ስለሆነ ››
‹‹ እንዴት ነው የማይኖረውስ ? ››
‹‹ ምክንያቱም እስካሁን እኔ አይቸዋለሁ የሚል ሰው ስላልተገኘ ››
‹‹ ወሬው ከተሰማ በኃላ ወደ ዳጋ የሚሄደው ጎብኚ ቁጥር በዝቷል ? ››
‹‹ እንግዶች ይሄዳሉ ፡፡ ግን ደራሲውን ፍለጋ ነው ብለው አይናገሩም ››
‹‹ ይህ ወሬ ታዲያ ከየት መጣ ? ››
‹‹ ከፌስ ቡክ ነው ! ››
‹‹ ከእናንተ ነው የሚሉም አሉ ፡፡ ማለትም ገበያ ለመፍጠር ››
‹‹ ዉሸት ነው ! እኛ ያልተረጋገጠ ወሬ ለደንበኞች አንናገርም ፡፡ ይኀው እንዳንተ በርካታ ሰዎች እየመጡ በዓሉ ካለ ልሄድ ነው መረጃ ንገረኝ ይሉኛል ፡፡ እኔ ገንዘብ ብፈልግ አደርገዋለሁ ፡፡ በግልጽ የምነግራቸው ምንም መረጃ እንደሌለኝ ነው ፡፡ የምመክራቸውም መሄድ ያለባቸው ገዳሙን የመጎብኘት ፍላጎት ካላቸው ብቻ መሆኑን ነው ››
‹‹ እውነት ስለ በዓሉ ምንም አላውቅም ነው የምትለኝ ? ››

ኃላፊው የሚያውቀውን በትክክል እንደገለጸልኝ ደጋግሞ ነገረኝ ፡፡ ትንሽ ቆይቶ ግን የአንድ ሰው ስም ጠራና የተሻለ መረጃ ሊገኝ እንደሚችል ጠቆመኝ ፡፡ ወጣቱ የሚሰራው በዳጋ እስጢፋኖስ ጀልባ ላይ ነው ፡፡ ጀልባዋ ሁለት ጥቅም ትሰጣለች ፡፡ አንደኛው የገዳሙን አባላት ካሉበት ወደ ከተማ ፣ ከከተማ ወደ ገዳም ማመላለስ ሲሆን ሁለተኛው ጎን ለጎን ወደ ገዳሙ የሚጓዙ ሰዎችን በተለመደው ታሪፍ ታጓጉዛለች ፡፡ የጀልባዋ ካፕቴን አንተሁን ጥበቡ በገዳሙ የሚኖር ሲሆን የማስጎብኘትም አገልግሎት ይሰጣል ፡፡

ቀጠሮ ለመያዝ ስደውልለት ወደ ክብራን ገብርኤል እንግዶችን ይዞ እንደሄደ ገለጸልኝ ፡፡ ሌላ እድል ስላልነበር የስልክ ቃለ መጠይቁን ማድረግ አንደሚገባኝ ወዲያው ወሰንኩ ፡፡ ዳጋ ውስጥ ከመቶ በላይ መነኮሳት እንደሚገኙ የገለጸው አንተሁን ወደ ገዳሙ የገባ ሰው ራሱን ደብቆ የሚኖር በመሆኑ ተፈላጊውን ለይቶ ለማወቅ ያስቸግራል ባይ ነው ፡፡ በዓሉ ግርማን በፎቶ እንኳ እንደማያውቀው ፣ በቦታው ኖሮ ቢያየው እንኳ ትርጉም እንደሌለው አስረድቷል ፡፡ ብዙዎቹ የበሰሉና ምሁራን ሆነውም ራሳቸውን ምንም እንደማያውቅ መሃይም አድርገው ለመኖር የሚያደርጉት ጥረት ምስጢራዊው ህይወት ምን ያህል ከባድ መሆኑን የሚያስረዳ ነው ፡፡ በዚህም ምክንያት እስካሁን ለጠየቁኝ ሰዎች የሰጠሁት ምላሽ አላውቅም የሚል ነው ብሏል ፡፡ ደራሲውን በአካል የሚያውቀው ሰው ለአዳር መጥቶ መፈለግ እንደሚኖርበትም ሃሳብ ሰጥቷል ፡፡

የገዳሙን ሰው አመስግኜ ወደ ጣና ዳር ተጠጋሁ ፡፡ አያሌ ጀልባዎች ወታደራዊ ሰልፍ ይዘው እንግዶቻቸውን ይጠባበቃሉ ፡፡ ጀልባዎቹ ከተደገፉበት ግንብ አናት ላይ ጉዞን የተመለከተ መረጃ የሚሰጥ ታፔላ ቆሟል ፡፡ የአጭርና ረጅም ጉዞ ታሪፍ ነው ፡፡ ዳጋ እስጢፋኖስ የአጭር ጉዞ ዝርዝር ውስጥ የለም ፡፡ በረጅሙ ጉዞ ውስጥ በሁለተኛ ረድፍ ላይ ግን ጎልቶ ይታያል ፡፡ በብረት ጀልባ ለመሄድ 1700 ብር ፣ በፋይበር ጀልባ ከሆነ ደግሞ 2200 ብር ያስጠይቃል ይላል መልዕክቱ ፡፡



ካፒቴኑ እንደነገረኝ ዳጋ ለመድረስ አራት ሰዓት ይፈጃል ፡፡ ማደር ካለ ደግሞ ክፍያው ከፍ ይላል ፡፡ የቀረኝ እንጥፍጣፊ መረጃ ቢኖር ገዳሙ ራሱ የሚነግረኝ ነው ፡፡ በሁለት ምክንያት ግን ወደ ምሁራኑ አምባ ለማቅናት አልችልም ፡፡ የመጀመሪያው ወደ ደባርቅና ሁመራ ቀሪ መንገድ ስለሚጠብቀኝ የሚያወላዳ ግዜ የሌለኝ መሆኑ ነው  ፡፡ ሁለተኛው ገንዘብ ነው ፡፡ ግዜን ከመንግስት ስራ ቀነጫጭቤ ማትረፍ ብችል እንኳ ገንዘብን ከራሴ ኪስ ለመስረቅ አልቸልም - ከባዶ ኪስ ፡፡

ባዶነት ተሰማኝ ፡፡ ውጤቱ ምንም ሆነ ምን ገዳም ላይ የሚደረገውን የመጨረሻ ፍለጋዊ ውድድር መመልከት ነበረብኝ ፡፡ እንደ ሀገሬ ብሄራዊ ቡድን እያለቃቀስኩም ሆነ እየዘፋፈንኩ ስፖንሰር ለመጠየቅ ዕድል አልነበረኝም ፡፡ ለብሄር ብሄረሰቦች በዓል የተገዛችውን ህብር የተባለች የክት መሳይ ጀልባ እየቃኘሁ ሀይቅ ላይ ወደቆመው ጣይቱ መዝናኛ በዝግታ አመራሁ ፡፡ የኔ አሰሳ በዚሁ ተፈጸመ ፡፡ ‹ ተፈጸመ › የሚባለው የበዓሉ ግርማ ጀግና ወይም ‹ ጦሰኛ › መጽሀፍ ግን እንዲህ ይላል ‹‹ ህይወት አንድ ቦታ ላይ አትቆምም … ትቀጥላለች ያንዱን ህይወት ከሌላው ጋር ድርና ማግ እያደረገች …  ››

ኦሮማይ !!!

Friday, April 19, 2013

‎በመተካካት የተጎዳው ጢስ አባይ ! ‎




የአማራ ባህል፣ ቱሪዝምና ፓርክ ልማት ቢሮ ለቱሪስቶች በሚያሰራጨው ብሮሸር ላይ ስለ ጢስ አባይ ፏፏቴ ግሩም ጽሁፍ አስፍሯል ፡፡ በየቀኑ ጢስ አባይን ለመመልከት የሚሄደው ደቀመዛምርም መምህሩ የጻፈውን ቅኔ በልቡ እያጠና ወደ ቦታው ይጓዛል ፡፡ በነገራችን ላይ ወደ ፏፏቴው ለመሄድ ሁለት አማራጮች አሉ ፡፡ አንደኛው የአባይን ወንዝ በጀልባ ተሻግሮ 15 ደቂቃ የእግር መንገድ መጓዝ ነው ፡፡ በጎዞዬ ላይ ምን አያለሁ ካሉ በመስኖ የሚበቅሉ አትክልትና ፍራፍሬዎችን ፣ ጋሽዬ ልከተሎት ላስጎበኝዎትም ካሜራ ካልያዙ እንኳ በፌስ ቡክ ላይ የሚለቁትን ምርጥ ፎቶ በሞባይልዎ ላነሳዎት እችላለሁ የሚሉ በርካታ ማቲዎችን ፣ ሻርፕና ጌጣጌጦችን ካልገዙኝ በማለት እስከመዳረሻዎ ሳይታክቱ የሚሸኝዎትን ሰዎች እንዲሁም ‹  የሰው ነገር › የሚል ስም የተሰጠውን ቅጠል ይመለከታሉ ፡፡ ይህ ቅጠል በእጅ ሲነካ ሽምቅቅ ብሎ መጠኑን ይቀንሳል ፡፡ በሌላ አነጋገር የቅጠል ኤሊ መሆኑ ነው ፡፡ ድንጋይ ውስጥ ባይሆንም ሁለመናውን ግንዱ ላይ ይለጥፋል - ከሶስት ደቂቃ ቆይታ በኃላ ደግሞ ወደቀድሞው ይዞታው ይለጠጣል ፡፡

 ሁለተኛው መንገድ መኪናዋን እስከተወሰነ ርቀት ከነዱ በኃላ ከ 30 እስከ 40 ደቂቃ በእግር ሊጓዙ ግድ የሚልዋት ነው ፡፡ ይህኛውን በዳገት የታጀበ አድካሚ መንገድ ቱሪስቶች ይመርጡታል ፡፡ ምክንያቱም አካባቢውን በአግባቡ ለመቃኘት ፣ በ 17ኛው ክፍለ ዘመን የተሰራውን ጥንታዊ የአላታ ድልድይና ሸለቆ ለመመልከት ስለሚረዳ ነው ፡፡ እኔ ሁለተኛውን አማራጭ ስለማውቀው አንደኛውን ምርጫ በመጠቀም ቦታው ተገኝቻለሁ ፡፡ እናም የብሮሸሩ ምንባብ ከጉብኝት በኃላ የሆነ አጭር መልመጃ ቢኖር እንኳ በአግባቡ አስታውሶ ለመመለስ ስለሚረዳ ጎብኚው ደጋግሞ ከኪሱ እያወጣ ያያታል ፡፡ እንዲህ ትላላች ፡፡

The Falls are found at 30 km to south of Bahir Dar near Tis Abay town. Here there is a spectacular basalt cliff Where the Nile form an incredible falls of 45 meters high, known as the Blue Nile Falls. The noise, the force and the smoke created by this fall is really worth discovering. The Blue Nile Falls is locally called the Tis Isat , meant water that smokes .

ቱሪስቱ ከጉብኝት በኃላ ወደ መረጃ ክፍል ተመልሶ ቢገባ ግን መምህሩ ሊፈትነው አይሞክርም ፤ ምናልባትም ትምህርትም ሆነ መረጃ ሰጪዎችን ላያገኝ ይችላል ፡፡ ግን በትምህርቱና በብሮሸሩ ንባብ መሰረት ራሱን መፈተኑ ይጠበቃል - እንዲህ እያለ ፡፡ ‹ በንባቡ መሰረት ትክክለኛ የሆነውንና ያልሆነውን ለይተህ አውጣ ! ትክክለኛ ባልሆኑ ጉዳዮች ዙሪያ አብሮህ ከጎበኘው ሰው ጋር በድፍረት ተወያይበት ፡፡ የመፍትሄ ሀሳቦችህንም ሀሳብ መስጫ ሳጥን ውስጥ ጨምር ! ›

ሀ . ትክክለኛ የሆነው ፤

1 . ጢስ አባይ ከባህር ዳር 30 ኪሜ ርቀት ላይ ይገኛል
2 . 45 ሜትር ቁልቁል ይወረወራል

ለ . ትክክለኛ ያልሆነው ፤

1 . የሚገርም ፏፏቴ ሊባል አይችልም
2 . ድምጹና ሁካታው እንደተባለው የተጋነነ አይደለም
3 . ታች ሲወርድ የሚፈጠር ልዩ ጢስ የለም
4 . የሚፈጠር ቀስተ ዳመና የለም
5 . ግርማ ሞገሳም ሳይሆን ቆሌ የራቀው መሆኑ ይታያል ፡፡

የመፍትሄ ሀሳብ ፤

. የሰው ነገር የተባለው ቅጠል አባባል አሁን ገና በአግባቡ ገብቶናል

በርግጥም ቱሪስቶች ብዙ ተወርቶላቸው ግዜ ፣ ገንዘብ እና ጉልበታቸውን መስዋዕት አድርገው ጢስ አባይ ዳገት ላይ ሲደርሱ ‹‹ እንግዲህ ጢስ አባይ ፏፏቴ ማለት ይህ ነው ! ›› ይላቸዋል ወጣት አስጎብኚው

‹‹ የቱ ? ››
‹‹ ይኀው ፊት ለፊት የምታዩት ! ››
‹‹ መቼም እየቀለድክ አይደለም ! ››
‹‹ እረ በስራ አንቀልድም ››
‹‹ ካልቀለድክ ታዲያ የታለ  የፏፏቴው ግዝፍና ? የቱ ነው ግርማ ሞገሱ ? የታለ ዳገት ላይ የሚደርሰው የውሃ ፍንጥቅጣቂ ? ቀስተ ዳመና የተባለውስ ? የታለ አስደማሚው ጢሱ ? ››

አስጎብኚው ያለው ብቸኛ እድል የሰው ነገር እንደተባለቸው ቅጠል ቀስ እያለ መሸማቀቅ ብቻ ነው ፡፡ ሳር እንዳጣ ከብት እንዲህ የገረጣውን ጢስ አባይ ለሃይል ማመንጫ ስለተገደበ ወዘተ … እያለ ማሳበቡ ለቱሪስቱ በቂ ምላሽ እንደማይፈጥርለት እሙን ነው ፡፡ ምክንያቱም የኃይል ጥያቄ ለሀገሬው እንጂ ለቱሪስቱ ጉዳዩ አይደለምና ፡፡ የእሱ መሰረታዊ ጉዳይ ብዙ ያወጣበትና የለፋበትን መስህብ አይቶ መርካት ነው ፤ እርካታው ከሞላ ደግሞ ወደ ሀገሩ ሲሄድ ያየውን በማውራት እግረ መንገዱን ማስታወቂያ መስራት ነው ፡፡ ዛሬ ግን አያሌ አስጎብኚዎች እንግዳቸውን ለማሳመን ሳይችሉ በርካታ ጎብኚዎች በሚሰጣቸው ምክንያት ሳይረኩ እየተበሳጩ መመለስ ግዴታቸው ሆኗል ፡፡

የፏፏቴው ጉዳይ አሳሳቢ ነው ፡፡ 75 ከመቶ ያህሉ ለሃይል ጥቅም ስለተገደበ ወደ ፏፏቴው የሚወርደው የውሃ መጠን የወፍራም ሰው ሽንት አክሏል ፡፡ ይህን ኢምንት ውሃ ደግሞ በሌላ ቦታ ማየት ይቻላል ፡፡ ወይ ያለቅጥ የሚሰማውን የተንዠረገገ ማስታወቂያ እንደ ጎጃም ልጅ ቁንጮ አስቀርቶ መከርከም አሊያም በድንጋይ ፋንታ ሙሉ ዉሃ የሚታይበትን ፕሮግራም ነድፎ መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ፡፡ ለምሳሌ ያህል ቅዳሜና እሁድ በርከት ያለ የውሃ መጠን ከግድቡ ቢለቀቅ ጎብኚው ሳምንቱን እየጠበቀ እየረካ ሊመለስ ይችላል ፡፡ የማይቻል ከሆነ ግን በቴሌቪዥን የሚታየውና በቃል የሚነገርለትን ጢስ አባይ ለሁለት ከፍሎ ማየት ሊገባ ነው ፡፡ የሚያስጎመጀውን ‹ የቀድሞው ጢስ አባይ › በማለት የአሁኗን ‹ በመተካካት የተገኘች › ማለት ይሻላል ፡፡ 
ምክንያቱም ዉሸት ስለሚያሳፍር ፡፡ ባይሆን እቺ የተተካቸው ‹ አቅም እየፈጠረች ስትሄድ መፈርጠሟና ማስደመሟ አይቀርም › እያሉ መስበክ ይሻላል ፡፡ የቱሪዝሙም ገቢ አይቅርብኝ ፣ የሃይል ጉዳይም የግድ ነው ብሎ ውሃ ውሃ የሚል ወጥ መስራት ግን መጨረሻው የበሰለውን ማበላሸት ይሆናል ፡፡ 

Tuesday, April 9, 2013

‎ሰላማዊ ሰልፍ በየዓይነቱ !‎


mexico
.


ሰላማዊ ሰልፍ ዴሞክራሲ ከወለዳቸው የነጻነት ልጆች አንደኛው ነው ፡፡ በርግጥ እንደ ልጅና እንጀራ ልጅ የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰልፎች መኖራቸው ይታወቃል ፡፡ እንደ ልጅ የሚቆጠረው የደገፈውም ሆነ የተቃወመው ሰልፋዊ ጥያቄ ይፈታለታል ወይም ባይፈታለት እንኳ በጥሞና ይደመጥለታል ፡፡ የእንጀራ ልጅ ዓይነቱ ግን ሶስት ዓይነት መንገድ የሚከተል ይመስላል ፡፡

. ትንሽ በሚራራ ወላጅ ያለው - ያለ ምንም አዳማጭ አደባባይ ተንጫጭቶ እንዲመጣ ይፈቀድለታል ፡፡
. በተረገመ ወላጅ ስር ያለው - ሰላማዊ ሰልፍ የሚሰማ እንጂ የሚነካ አይደለም እየተባለ ያድጋል ፡፡
. በብልጣ ብልጥ ወላጅ መዳፍ ስር ያለው - አባቱ ሲፈቅድና ደስ ሲለው ብቻ ለድጋፍ የሚወጣበት ምርጥ መሳሪያ መሆኑን ጸጉሩ እየተደባበሰ በተመስጦ ይነገረዋል ፣ ይማራል ፡፡

በዚህና በመሳሰሉ ስሌቶች የዓለማችን ህዝቦች ሰላማዊ ሰልፍ አከናውነዋል ፤ እያከናወኑም ይገኛሉ ፡፡ የሰልፎቹ መነሻም ሆነ የሚንጸባረቁበት መንገድ ጠንካራ ፣ ረጅም ግዜ የሚቆይ ፣ ልዩና ገራሚ እንዲሁም ለውጥ አምጪ ሊሆን ይችላል ፡፡ በዚህ ረገድ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአንዳንድ ሀገሮች የሚታየውን ተጠቃሽ ሰላማዊ ሰልፍ ገጽታ በስሱ እንቃኝ ፡፡

. ደቡብ አፍሪካ  - ከአፓርታይድ ትግል ወዲህ በዚች ሀገር የጠንካራ ሰላማዊ ሰልፍ ምንጮች የማዕድን ሰራተኞች ናቸው ፡፡ ጉልበታችን አላግባብ እየተበዘበዘ ስለሆነ የላባችን ውጤት ይከፈል በማለት ሞትን ያስከተለና መንግስትን ያጨናነቀ ሰልፍ አድርገዋል ፡፡

. ቻይና  - ገባ ወጣ ቢሆንም በዚች አፋኝ ሀገር የሰላማዊ ሰልፉ መሰረታዊ ጥያቄ ቅድመ ምርመራና አፈናን መቃወም ነው ፡፡

. ሶሪያ ፣ ቱኒዝያ ፣ ግብጽ ፣ ሊቢያ፣  አልጀሪያ ፣ ሞሮኮ ፣ የመን ፣ ባህሪን  - መንግስትና የሚከተለው ፓለቲካዊ ስርዓት ቤተሰባዊ እንጂ ህዝባዊ ጥቅም የሌለው በመሆኑ መንግስትም አሰራሩ ይቀየርልን በሚል በብዙ ሰልፍና ተቃውሞ ደክመዋል ፡፡ የተሳካላቸው እንዳሉ ሁሉ ገና በመንገድ ላይም ያሉ ብዙ ናቸው ፡፡

. አሜሪካ  - በተለይም ዋል ስትሬት በተባለው ተቃውሞ እኛ 90 ከመቶ ነን ያሉ ሰልፈኞች የድሃውን እኩል አኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ይረጋገጥ በሚል ሰፊ ድምጽ አሰምተዋል ፡፡

. ፍልስጤም  - አሷፊዎች ለተቃውሞና ሰልፍ የተፈጠሩ ይሏቸዋል - ተገራሚዎች የመብትና የነጻነት ታጋዮች ይሏቸዋል ፡፡ ሰው በጥይት ሲሞት ይሰለፋሉ፣ ሞት ለእስራኤልና አሜሪካ በማለት ባንዲራ ለማቃጠል ይሰባሰባሉ ፣ ለመሬትና ድንበር ጥያቄ ያልተሰለፉበትና ያልተጋጩበት ቀን ኢምንት ነው ፡፡

. ቤልጂየም  - የወተት ሽያጭ ዋጋ አሽቆለቀለ በማለት የአውሮፓን ገበሬዎች በሙሉ አስተባብረው የተቃውሞ ሰልፍ ያከናውናሉ ፡፡ በሰልፉ ላይ አንድ ሺህ የሚደርስ ትራክተር ሊያሰልፉ ይችላሉ ፡፡

. ስፔን  - ሀገሪቱ ከቅርብ ግዜ ወዲህ የገጠማትን የኢኮኖሚ መላሸቅ ተከትሎ በርካታ እንጀራ ነክ ኡኡታዎችን ብታስተናግድም እቺ ሀገር ለየት ባለ ሰልፍም ትታወቃለች ፡፡ ይኅውም እጅግ ተስፋፍቶ የሚታየውን የ ‹ ቡል ፋይት › ከእንስሳት መብት አንጻር በመቃወም ሴቶች ራቁታቸውን አስፓልት ላይ የመተኛታቸው ጉዳይ ነው ፡፡

. ህንድ  - በሀገሪቱ ፍጹም እየተስፋፋ የሚገኘው የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ይቁም ! አጥፊዎች አስተማሪ ቅጣት ይሰጣቸው  ! በሚል በየግዜው ታላላቅ ሰልፎች ይደረጋሉ ፡፡

ሩሲያ  - የሩሲያ ተቃዋሚ ሰልፈኞች ትልቁ ጥያቄ ልክ እንደ ጣሊያናዊው ቤርለስኮኒ / Basta Berlusconi እንደተባሉት / የፑቲንም ስርዓት ማብቂያ ይበጅለት ፣ የመንግስት ስርዓት እንደፈለጉ የሚገቡበትና የሚወጡበት የግል ቤት አያድርጉት ! ፍትህ ይስፈን ! የሚል ነው ፡፡ የፑሲ ተቃውሞ / pussy Riot / በሚል አዲስና ልዩ ስልት ሴቶች ብልታቸውን በዘግናናኝ መልኩ ቆልፈው በየአደባባዩና ቤተ እምነት ሳይቀር የተቃወሙበት ሂደት ነው ፡፡

. ቺሊ - ልጆቻችን ጥራት ያለው ትምህርት እያገኙ አይደለም በሚል ጥንዶች ተቃውሞያዊ ሰልፋቸውን ያቀርባሉ ፡፡ በምን መንገድ ከተባለ ግን በመሳሳም ይሆናል ምላሹ ፡፡

. ኢትዮጽያ  - ኢትዮጽያኖች ሁልግዜም ጠዋትና ማታ ትላልቅና በሰው የተጨናነቀ ሰላማዊ ሰልፍ ያደርጋሉ ፡፡ ሰልፋቸው መስቀል አደባባይን ንቆ በየሰፈሩ ሆኗል ፡፡ የሰላማዊ ሰልፉ ምክንያት ታክሲ አጣን ፣ በትራንሰፖርት እጦትና ኢ ፍትሃዊ ታሪፍ ተንገላተን  በማለት አይደለም - በቃ ታክሲ ጥበቃ ነው ፡፡

Sunday, April 7, 2013

‎የወላጅ አልባ አንበሶች ያልተነገረ ታሪክ‎


ስለ ወላጅ አልባ ህጻናት እንጂ ስለ ወላጅ አልባ እንስሳት ብዙዎች ብዙ እንዳልሰሙ ግልጽ ነው ፡፡ ብይኑ እነዚህን እንስሳት ወላጅ የሌላቸው እንስሳት ሆነው ራሳቸውን ማስተዳደር የማይችሉ ይላቸዋል ፡፡ ለሀገራችን ወላጅ አልባ ህጻናት መፈረጃ ትልቁ ምክንያት ድህነትና ኤችአይቪውን ጥቂት ከጎናቸው በማራቅ በምትኩ በሽታን ይወስዳሉ ፡፡ በመኪናና በተፈጥሮ አደጋ በተለይም ደግሞ በአዳኞች ርጉም ጥይት መሞት አብይ መንስኤያቸው ሆኗል ፡፡

ትልቅ ሆነው ፍርሃት ከሚያነግሱ እንስሳት አንበሳን በዋናነት መጥቀስ እንችላለን ፡፡ ይህ የስልጣን ፣ የኃይል ፣ የድፍረትና የዝና ምልክት የሆነው እንስሳም ክፉ ቀን ከመጣበት ወላጅ አልባ መጠለያ ውስጥ ፊቱን ጥሎ ሊታይ ይችላል ፡፡ መቼም እነ ጎሽ ፣ የሜዳ አህያ ፣ ሚዳቆ ፣ አጋዘን የመሳሰሉት በአጋጣሚ በሽቦ አጥር የተከለለ መጠለያ ውስጥ ቢያዩት መቶ ፐርሰንት ተስማምቶም ሆነ ተገዶ እዚህ መገኘቱን አያምኑም ፡፡

‹ ወይ ጋሽ አንበሶ ? እንዲህ ዓይነት ማዘናጊያ ጀመረ ደግሞ ! › ልትል ትችላለች ሚዳቆ
‹ ቆይ ግን ምን ለማለት ነው ? በመላመድ ከሌሎች ጋ በሰላም መኖርም እችላለሁ እያለን ነው ? › አጋዘን እየበሸቀ መናገሩ ይጠበቃል ፡፡
‹ ሌባ በለው አጭበርባሪ ! › ከጎሽ ኃይለ ቃል አይጠፋም ፡፡

ሌሎቹም ቢሆኑ በጣም እየፈሩና እይተጠነቀቁም ቢሆን የበዛ ስልቂያ እንደሚያሰሙ አያጠራጥርም ፡፡ ምክንያቱም የደኑ ንጉስ ከፈለገ አጥሩን በጣጥሶ አሊያም ብዙም ሳይንደረደር ከለላውን እንደሚዘላት ይገባቸዋልና ፡፡ እንኳን እነሱ ‹ ከኔ በላይ ላሳር › የሚለው የሰው ልጅ ከእሱ በላይ መኖሩን የሚያስመሰክር ዘፈን ዘወትር እንደሚከተለው እንደሚያሰማ የወሬ ወሬ ሰምተዋል ፡፡

          ‹‹ አንበሳው አንበሳው አንበሳው ልጅሽ
                              ይኅው መጣልሽ !!! ››

ይህን የሚዘምረው በጣባብ የጎል ልዩነት ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈ ብሄራዊ ቡድን ብቻ አይደለም ፡፡ ይህን የሚዘምረው ወገቡ በዝናር ጥይትና በእጅ ቦንብ ፤ እጁ አውቶማቲክ ጠመንጃና ጸረ ታንክ የተሸከመ ስልጡን ወታደር ጭምር እንጂ ፡፡ ዓለምን የሚያደባይ መሳሪያ የጨበጠ ሰው እንኳ ከመሳሪያው ይልቅ ለአንበሳ ትልቅ ክብር እንደሚሰጥ ይረዳሉ ፡፡
ታዲያ የነጎሽና አጋዘን መላምት እንዴት ትክክል ላይሆን ይችላል ? እረ ለቁጥር የሚታክቱ ማሳያዋችና ማስረጃዋችንም አንድ ሁለት እያሉ መዘርዘር አይከብድም ፡፡ ምን ዘፈን ፣ ሙገሳና ቀረርቶ ብቻ ?

ማነው የአንበሳው ክፍለጦር እያለ ስያሜ የሚሰጠው ?
አንበሳ ግቢ ?
አንበሳ አውቶብስ ?
አንበሳ ጫማ ?
አንበሳ ባንክ ?
አንበሳ ኢንሹራንስ ?
ጥቁር አንበሳ ?
አቶ አንበሴ ?

የአውጉስታ ሸሚዝ ፋብሪካ ምልክት የሆነው የሜዳ አህያም ሆነ የፈጣንና ዘመናዊ መኪናዋች ምስል የሆነው አቦሸማኔ አንበሳ በአፍሪካ በተለይም በኢትዮጽያ የብዙ ነገሮች ምልክት መሆኑን የሚያውቁት ገና ጥርስ ከማውጣታቸው በፊት ነው ፡፡
አንበሳ በቀድሞዎቹ የኢትዮጽያ ባንዲራ ላይ
በአሁኑ ፍራንክ ላይ
በቀድሞ ጽሁፎች ላይ
በኢትዮጽያ ንግድ መርከብ
በቀድሞው አየር መንገድ
በኢትዮጽያ መንገዶች ባለስልጣን
በቴሌኮሙኒኬሽን

ባልጠቀስናቸው መ/ቤቶች እንደ ሎጎ አገልግሏል ፤ ዛሬም በገሃድ እያገለገለ ይገኛል ፡፡ በሚንሊክ ዘመነ መንግስት መስቀል በእግሩ የያዘና ዘውድ የደፋ አንበሳ ባንዲራ ላይ ይታይ ነበር ፡፡ ይህ ምልክት በንጉስ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስትም ሰርቷል ፡፡ የይሁዳ አንበሳ ይሉታል ፡፡ ደርግ ስልጣን ሲይዝ አናቱ ላይ የደፋውን ዘውድ በሞርታር ጥይት አሽቀንጥሮ በዚያው ይቀጥላል ቢባልም አንበሳው የያዘው መስቀልና እሱ የሚከተለው ርዕዮት ሊዛመድለት አልቻለም ፡፡ በአጠቃላይ ‹ አንበሳ አያስፈልገኝም › በማለት ገፈተረው ፡፡ ብዙም ሳይቆይ ግን አንበሳው ክፍለጦርን አቋቁሞ አንበሳውን ደጋግሞ ማሞገስ ተያያዘ ፡፡

አንበሳ ከዚህም በላይ ሊወራለት እንደሚችል ይታወቃል ፡፡ ከዚህ አንጻር አንበሳ በወላጅ አልባ እንስሳት ስም መጠለያ ገባ የሚለው ዜና የማይመስል ሊመስል ቢችል አያስገርምም ፡፡ ወይም የማይታወቅ ፡፡

ከአዲስ አበባ በ25 ኪሎ ሜትር ርቀት ማለትም ሆለታ አካባቢ የሚገኘው የእንስሳት መጠለያ ግን የስድስት አንበሶች ልዩ ታሪክ ይዟል ፡፡ ቦርን ፍሪ በሰዎች ተይዘው የሚሰቃዩ እንስሳትን ተግባር በማስቀደም ከችግር የሚላቀቁበትንና እንክብካቤ የሚያገኙበትን ሁኔታ የሚያመቻች አለማቀፍ ድርጅት ነው ፡፡ የዚህ ድርጅት የኢትዮጽያ ተጠሪ ሆለታ አካባቢ የሚገኘውን መጠለያ ‹‹ የእንስሳት ኮቴ ›› የሚል ስያሜ በመስጠት በሀገራችን የመጀመሪያውን የዱር እንስሳት ጥበቃ ፣ ልማትና ትምህርት ማዕከል በመሆን እየሰራ ይገኛል ፡፡

ግቢው 77 ሄክታር መሬት የሚያካልል ሲሆን በደን የተሸፈነ ነው ፡፡ በቀጣዮቹ አንቀጾች ከምንገልጻቸው ጥንድ - ጥንድ አንበሶች በተጨማሪ አቦሸማኔ ፣ ጉጉት ፣ ጦጣ ፣ ኤሊ ፣ ተራውና በሀገራችን ብቻ የሚገኘው ዝንጀሮዋችም ይገኙበታል ፡፡

ዶሎና ሶፍያ

ዶሎና ሶፍያ

ዶሎ የተባለው አንበሳ አንድ ሜትር ርዝመት ባለው ሰንሰለት በደቡብ ኢትዮጽያ በሶማሌ ድንበር አካባቢ በአንድ ሰው እጅ ነበር ፡፡ ይህ ሰው ለአራት ዓመታት ያህል በፍልጥ እንጨት በተሰራ ጠባብ ክፍል ውስጥ እንዲኖር አስገድዶታል ፡፡ የአካባቢው ሰዎች እንዳስረዱት አንበሳው ብቸኛ በመሆኑና አያያዙም ጥሩ ስላልነበር ዘወትር ጠዋት የሚያሰማው የሰቆቃ ጩኀት በከተማው ሙሉ  ይሰማ ነበር፡፡

ሰቆቃወ ወ ዶሎ ከአዛማጅ ትርጉም አንጻር እንደሚከተለው የሚገለጽ መስሎኛል . . .

‹ እረ የአንበሳ ያለህ ?! እረ የእንስሳት ያለህ ?! ዛሬስ ጠረናችሁ ናፈቀኝ !! ›
‹ አይ እናቴ ! ነጻ በሆነው ጫካ ተወልደሃል የምትይው መዝሙር እንዴት ተቀይሮ ከባርነት ጫማ ስር ተገኘሁ ?! ›
‹ እረ የነጻነት ያለህ ?! እረ የፍትህ ያለህ ?! በምን ጥፋቴ ነው ሰንሰለት የሚበላኝ ?! በምን ተፈጥሮ ነው በሰው ልጅ የምዳኝ ?! ›
ይህ ሁኔታ ብዙዎችን ስላሳሰበ ጉዳዩን ለሚመለከተው ክፍል አሳወቁ ፡፡

ዶሎ በዱር እንስሳትና በቦርን ፍሪ ትብብር መጀመሪያ የተወሰደው ወደ አዋሽ ብሄራዊ ፓርክ ነበር ፡፡ እዚያ የተሻለ እንክብካቤ አግኝቷል ፡፡ አንበሳ ያልነበረው የእንስሳት ኮቴ ዶሎን የመጀመሪያ እንግዳ አድርጎ ለመቀበል ብዙ ጥረት አድርጓል ፡፡ ደረጃውን የጠበቀ ግቢ ለመስራት ፣ የተሻለ ምግብ በቀጣይነት ለማቅረብና  ህክምናውን ለመከታተል የሚያስችሉ ዝግጅቶች ከተከናወኑ በኃላ ጉዞ ወደ ሆለታ ሆነ ፡፡ ዶሎን ለማጓጓዝ ሰባት ሰዓታትን ማሳለፍም ግድ ብሏል ፡፡

ዶሎ አሳድገዋለሁ ባለው ሰው እጅ እያለ ምን እንደሆነ ባይታወቅም አይኖቹ ተጎድተዋል ፡፡ ሩቅ የማየት ችግር እንዳለበትም ተረጋግጧል ፡፡ ሀኪሞች በልጅነቱ በምግብ እጥረት በመጎዳቱ ለአይን በሽታ ሳይጋለጥ አይቀርም የሚል ሀሳብ አላቸው ፡፡ በሰንሰለቱ ምክንያትም ግርማ ሞገስ ሊፈጥርለት የሚገባው የጋማው ጸጉር ሊረግፍ ችሏል ፡፡

ዶሎ በሰፊው ግቢ፣ በምግቡና በተፈጠረለት አንጻራዊ ነጻነት ቢረካም ‹  አንድ ውሃ አጣጪ ባገኝ ምን አለበት ? › እያለ እንደሚያስብ ይገመታል ፡፡ የአጋጣሚ ጉዳይ ሆኖ ኡደት በተባለ ቦታ የሚገኙ ልጆች ሴት አንበሳ ይዘው በአነስተኛ እንጨት ውስጥ መቀመጧ ሪፓርት ይደረጋል ፡፡ አንበሳዋ ስትገኝ እድሜዋ ገና ሰባት ወር ብቻ ነበር ፡፡ እናትየው ልጆቿ ወንዶች ከሆኑ ትልቁ አንበሳ በመቅናትና የነገ ባላንጣዬ ነው በማለት እንደሚገድላቸው ስለምታውቅ ከአጠገቧ እንዲርቁ አታደርግም ፡፡ አንበሶች ልጃቸውን ለመንከባከብ ግድ የማይኖራቸው የምግብ ችግር ባለበት ግዜ ነው ፡፡ ምናልባትም በኃላ ላይ ‹‹ ሶፍያ ›› የሚል ስም የተሰጣት አንበሳ በህጻናቱ እጅ የወደቀችው ይህን በመሰለ ችግር ሊሆን ይችላል ፡፡

ዞሮ ዞሮ ዶሎ ከሶፍያ ጋር መጣመር መቻሉን እንደ ሁለተኛ ዕድልም ድልም ነው የሚመለከተው ፡፡ የመጀመሪያው ሰንሰለቱን የማስቆረጡ ተግባር ነው ፡፡ ሰንሰለት በውሻ እንጂ በአንበሳ አንገት ላይ ቦታው አይደለምና ፡፡ ሁለተኛው ዕድል / ድል በረዶ የሰራበትን ብቸኝነት ብቻ ሳይሆን እንደ አለት የጠጠረውን የፍቅር ጥያቄ ቀስ በቀስ እያቀለጠች ምላሽ ልትሰጥ የምትችል ተቃራኒ ጾታ የማግኘቱ ሚስጢር ነው ፡፡ በርግጥ ጾታዊ ግንኙነቱ ‹ ብዙ ተባዙ ! › እስከማለት የሚያደርስ አይደለም ፡፡ ምክንያቱም የግቢው ህግ የተጎዱ እንስሳትን ለመንከባከብ እንጂ ለማራባት የሚፈቅድ አይደለምና ፡፡ ለምን ከተባለ የዱር እንስሳትን በተወሰነ አጥር ውስጥ ከልሎ ማራባት ከተፈጥሯዊ የኑሮ ዘይቤያቸው አንጻር ስለማይቻል ፡፡ አደኑ ፣ መሯሯጡ ፣ ምግብ ፍለጋው ፣ መደበቂያው ፣ መራቢያው እና ሌላውንም ጉዳይ የሽቦው ቤታቸው አይመልስምና ፡፡ በዚያ ላይ የተራቡትን ሁሉ ለማሳደግ የኢኮኖሚ አቅም አይፈቅድም ፡፡ ይህን ሳይንሳዊ የተባለ የሰው ልጅ ምክንያት እነ አንበሶ አይቀበሉትም ፡፡ አንዳንዶች ስለ ሙሉ ነጻነት ነው የሚያስቡት ፤ ሰዎች ደግሞ እነዚህ አንበሶች ወደ ጫካው ቢለቀቁ የመገለልና የመጠቃት ዕጣ ስለሚያጋጥማቸው ጉዳቱ ይብስባቸዋል ነው የሚሉት ፡፡ አንበሶቹ ግን የፈለገ ቢሆን ማን እንደ ቤት … ማን እንደ ዘር ባይ ናቸው ፡፡ አንዳንዶቹ ተቃውሟቸውን በጩኃት ይገልጻሉ ፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ የማንዴላን መጽሀፍ ያነበቡ ይመስል ‹‹ LONG ROAR TO FREEDOM ›› የሚል ድርሰት ለመጻፍ በዝምታ ያደፈጡ ይመስላል ፡፡

ሜጀርና ጄኔራል


ሜጀርና ጄኔራል

በወታደራዊ አጠራር ሜጀር ጄኔራል ትልቅ ስልጣን ነው ፡፡ በሀረር የሚገኝ አንድ የጦር ካምፕ ለ13 አመታት ሲያሳድጋቸው ለቆየው ሁለት አንበሶች ወታደራዊ መጠሪያ ለመስጠት ባያመነታም ትልቁን ወታደራዊ ማዕረግ ለሁለት መሰንጠቁ ግን ግራ አጋቢ መስሏል ፡፡ አንዱን ሜጀር ሌላውን ጄኔራል በማለት ፡፡

እነዚህን ጀርባ ጥቁር አንበሶች የተመለከተ በግርማ ሞገሳቸው ይማረካል ፡፡ ከነዶሎና ሶፍያ ግቢ በተወሰነ ርቀት ላይ በሌላ የሽቦ አፓርታማ ውስጥ ነው የሚኖሩት ፡፡ በርግጥም እንደ ወንድማማችነታቸው ተሳስበው በሰላም የሚኖሩ ይመስላሉ ፡፡ አልፎ አልፎ ግን ከአንዱ ጥግ ወደ ሌላው እየተንጎማለሉ የሚያሰሙት ልዩና አሳዛኝ ድምጽ አላቸው ፡፡ ባለሙያዎቹ የተለመደና ተፈጥሯዊ ጉዳይ ነው ቢሉም እኔ ግን ምናልባትም ስለ ሶፍያ የሚያሰሙት የፍቅር መወድስ ሊሆን ይችላል ባይ ነኝ ፡፡ የአንበሳ የፍቅር ዘለቄታነት እስከመጨረሻው ቢሆንም ሴት እጅግ ብርቅ በሆነበት በዚህ ጫካ መንግስት እንደሚለው ወጪን ብቻ ሳይሆን ሁሉን ነገር ተጋርቶ መኖር እንደ ስርዓት አልበኝነት አያስቆጥርም ፡፡ እናም ዶሎ ቢከፋው እንኳ … ሜጀርና ጄኔራል እንደሚከተለው  እያሉ መስሎኛል …

                  ኦ ! ሶፍያ . . .
                  መች ይሆን የፍቅርሽ ገበያ
                  የሚውለው ከጠረንሽ አልፎ
                  ልፍያና ጉንተላን አሰልፎ
                  ከኛም ግቢ … ከኛ መንደር
                  የሚወደስ  … የሚከበር
                  ኦ ! ሶፍያ . . .
                  ከለለን አጥሩ
                  አነቀን ድንበሩ
                  እንዲህ ነበር እንዴ ወጉ ?!
                  የባህል ልምዳችን ማእረጉ
                  ታዲያ መች ይጸድቃል ቀኑ ?
                  ‹ ፓሪ › መጨፈሪያችን ‹ ዩኒየኑ ›
                   ኦ ! ሶፍያ . . .                           

የዛሬን አያድርገው እንጂ ወንድማማቾቹ የተፈጠሩት ሶስት ሆነው ነበር ፡፡ በአንድ ክፉ ቀን ሶስት የአንበሳ ግልገሎች በባሌ አካባቢ በወታደሮች ተገኙ ፡፡ ወይም በወታደራዊ ቋንቋ ተማረኩ ፡፡ የግልገሎቹ ወላጆች የት ጥለዋቸው እንደሄዱ ፣ ወይም ምን እንደሆኑ አይታወቅም ፡፡ አንደኛዋ ግልገል ሴት ነበረች ፡፡ ይሁን እንጂ ማራኪዎቹ ወደ ካምፓቸው ባደረጉት ጉዞ ሴቷ በፋቲክ ለባሾች እጅ ከመውደቅ በሚል ነው መሰለኝ ከመኪና በመዝለሏ ወዲያው ሞተች ፡፡ ሁለቱ ወንድማማቾች ከመሞት መሰንበትን መርጠው ካምፕ ውስጥ በአነስተኛ መጠለያ ለመቀመጥ በቁ ፡፡

ግልገሎቹ እያደጉ ሲመጡ ማራኪዋቻቸው የየዕለት ተግባራቸውን መቆጣጠር አልቻሉም ፡፡ በመሆኑም የዱር እንስሳት ባለስልጣን እንዲታደጋቸው ጥሪ አቀረቡ ፡፡  ቦርን ፍሪ በበኩሉ የአንበሶቹን መኖሪያ በመገንባት የሶስት ወራት ግዜ ወሰደ ፡፡ ትላልቆችን አንበሶች በትልቅ የጭነት መኪና የእንስሳት ኮቴ ግቢ ለማድረስ 16 ሰዓታት መንዳት አስፈልጓል ፡፡ ዛሬ የሜጀርና ጄኔራልነት ተክለ ሰውነት ብቻ ሳይሆን ስለ ፍቅር ፣ ወንድማማችነትና ስለ ህይወት የሚያቀነቅኑትን ፉከራዎችንና አርምሞዎችን መስማት የሆነ ስሜት ይፈጥራል ፡፡

አንድሪያና ጃኑ


አንድሪያና ጃኑ

ስማቸው እንደሚጠቁመው እነዚህ ሁለት አንበሶች ዜግነታቸው ከጣሊያን ነው ፡፡ አስተዳደጋቸው ደግሞ ኢትዮጽያ ፡፡ አንበሶቹ በሆነ ወቅት አነጋጋሪ ጉዳይ መፍጠር ችለው ነበር ፡፡

ነገሩ እንዲህ ነው ፡፡

እአአ በ2006 ሁለቱ ቤተሰብ አልባ ግልገል አንበሶች ጣሊያን ኤምባሲ ውስጥ ተገኙ ፡፡ የመጡት የአንድ ልዑክ ቡድን ምክትል ኃላፊ በሆኑ ሰውና ሚስታቸው አማካኝነት ነበር ፡፡

ሁለቱ ወንድማማች አንበሶች እያደጉ ሲመጡ ጣሊያኖቹ አንበሶቹ ማግኘት ስለሚገባቸው ትክክለኛ ቤትና የወደፊት ዕጣ ፈንታ በተመለከተ ቦርን ፍሪን ማነጋገር ጀመሩ ፡፡ አንደኛው ሀሳብ አንበሶቹ ወደተወለዱበት ጣሊያን መመለስ ይኖርባቸዋል የሚል ነበር ፡፡ጣሊያን መቼም የራሷን ንብረት አይደለም የወረረችውንም ሀገር ሃውልት ሳይቀር ተሸክማ ሄዳለች ፡፡ በነገራችን ላይ ወራሪዎች የከበሩ ማዕድናትንና ውድ ቅርሶችን በመዝረፍ አልሆን ካላቸውም አውድመው በመሄድ ይታወቃሉ ፡፡ ጣሊያን ግን ያን ትልቅ ሃውልት ስንት ባህር አቋርጣ ተሸክማ መሄድዋ ይገርመኛል ፡፡ እንደውም አንዳንዴ እኛ በተረት የምናውቀው አህያ ተሸክሞ የሚሄደውን ማሞ ቂሎ ሁሉ የሆነች ይመስለኛል ፡፡ እያደር ግን ድንጋይና ኃውልት ላይ ሃይለኛ ፍቅር እንዳላቸው ተገንዝቤያለሁ ፡፡

መቼም ፍትሃዊ ህዝብና መንግስት ሀገር ላወገዘው ወንጀለኛ / ግራዚያኒ / የጀግና ሃውልት ያቆማል ተብሎ አይታሰብም - ልክ ብልጥ መንግስት የሰማይ ስባሪ የሚያህል ሃውልት ተሸክሞ እንደማይሄደው ሁሉ ፡፡ ጣሊያን ግን ከነዚህ እውነት ጀርባ በኩራት ቆማለች ፡፡ እናም አንበሶቻችን ይመለሱ ብለው መጠየቃቸው የኃላ ታሪካቸውን ለሚያውቅ አያስገርምም ፡፡

የኢትዮጽያ መንግስት ግን ከብዙ ሁኔታዎች አንጻር ይህን ሀሳብ ለመቀበል ተቸገረ ፡፡ ይሄኔ ቦርን ፍሪ ከፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መነጋገር ጀመረ ፡፡ ይህ ውይይትም ትውልደ ጣሊያን አንበሶቹ ለግዜው በፕሬዝዳንቱ ቤ/መንግስት ይቀመጡ የሚል ውሳኔ ሀሳብ እንዲመነጭ አስቻለ ፡፡

ቤተ መንግስቱ ግን የተሻለና የመጨረሻ አማራጭ ባለመሆኑ ዘለቄታዊ ማረፊያ ወደሆነው የእንስሳት ኮቴ በህዳር 2011 እንዲጓዙ ተደረገ ፡፡

አንድርያና ጃኑ እንደ ሜጀርና ጄኔራል የመቅበጥበጥም ሆነ እረ ጎራው የማለት ባህሪ አይታይባቸውም ፡፡ ምናልባት እንደ ጌቶቻቸው አድፋጭነት ተጋብቶባቸው ይሆናል ፡፡ ምናልባት ጸብ አጫሪነት ፋይዳ ቢስ መሆኑን በመረዳት በነጭ ባንዲራ ስር ለመኖር ቆርጠው ይሆናል ፡፡ ምናልባትም መወለድ ቋንቋ ነው እንዲሉ ላደጉበት ሀገር ሰላምና ፍቅር በመመኘት ቋሚ ‹ አርምሞ › ውስጥ ገብተው ይሆናል ፡፡ ምናልባትም በቅርቡ  ይፋ የሆነውን ሰበር ዜና አስቀድመው ስለሚያውቁት በራስ የመተማመን ስሜታቸው ተሰብሮ ይሆናል ፡፡

የቅርቡ ዜና  የኢትዮጽያ አንበሶች ዝርያ ከመላው አፍሪካ አንበሶች ይለያል የሚል ነው ፡፡ ከ 20 አንበሶች ውስጥ የዲ ኤን ኤ ምርመራ የተደረገላቸው 15ቱ ልዩነት ማሳየታቸው ታውቋል ፡፡ ይህ ማለት እንግዲህ አንበሳ ‹ አንበሳ › ከሚለው አስፈሪና ሞገሳም ዝናው በተጨማሪ ‹‹ በኢትዮጽያ ብቻ የሚገኝ ! ›› የሚለው ማዕረግ በሰዎች ክብር ሊጨመርለት ነው ማለት ነው ፡፡ ለነገሩ ነገሩ ቀድሞ የተገለጠላቸው የሚመስሉት አንዳንድ የሀገራችን መሪዎች ለአንበሳ የሚገርም ፍቅርና አክብሮት ነበራቸው ፡፡ አጼ ቴዎድሮስ መቅደላ ተራራ ላይ በአንበሳ ተከበው ይውሉ ነበር ፡፡ ንጉስ ሃይለስላሴ አንበሳ እያረቡ መሳጭ ወዳጅነት መፍጠር ችለዋል ፡፡ የሀገራችን አርበኞች በህቡዕ ሲደራጁ ስማቸውን  ‹ የጥቁር አንበሳ አርበኞች እንቅስቃሴ › ማለት ነው የወደዱት ፡፡ አንበሳ ብቻ አይደለም - ጥቁር አንበሳ ፡፡  አንበሳ ወደ ዳለቻና ቡኒ ቀለም መጠጋቱ እየታወቀ በሀገራችን ብዙ ነገሮች ‹ ጥቁር አንበሳ › የሚል ስያሜ እንዴት ሊያገኙ ቻሉ ? የሚሉትን ጥያቄዎች ጆሮውን መጠምዘዝ ከተፈቀደ ቀደም ያሉትን አባቶቻችንን ምናባዊ ዕውቀት ልናድቅ ግድ ይለናል ፡፡ የመገለጥ ብቃት ፡፡

ርዕሰ ዜናውን አንድ ግዜ ላስታውስና ልቀጥል ፡፡ ይህ ማለት እንግዲህ አንበሳ ‹ አንበሳ › ከሚለው አስፈሪና ሞገሳም ዝናው በተጨማሪ ‹‹ በኢትዮጽያ ብቻ የሚገኝ ! ›› የሚለው ማዕረግ በሰዎች ክብር ሊጨመርለት ነው ማለት ነው ፡፡ በሌላ አነጋገር ዶሎ ፣ ሶፍያ ፣ ሜጀርና ጄኔራል እንደ ሳሞራ የኑስ ብቸኛውን ማዕረግ ትከሻቸው ላይ ሊጭኑ ነው  - ሙሉ ጄኔራል ወይም ልዩና ብርቅዬ አንበሳ ፡፡ አንድርያና ጃኑ ደግሞ ባለ ሌላ ማዕረግተኛ  - ወይም ተራው አንበሳ ፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጽያዊ ደም ስለሌላቸው ሳይንሳዊው እርከን አይመለከታቸውም ፡፡ ይህ ኮምፕሌክስ በጫካው ሰፈር አይኖርም ለማለት ማረጋገጫ አይኖርም ፡፡ 
ተመራማሪዋቹ በነካ እጃቸው ይህ ኮምፕሌክስ እየቆየ ሲሄድ ‹ አንበሳዊ ፍርሃት › ይፈጥራል የሚል ጥናት ያሰሙን ይሆናል ፡፡

ለማንኛውም  ተሷሚዎቹንም ሆነ ባለ ሌላ ማዕረግተኞቹን  ወላጅ አልባ አንበሶች በእንሰሳት ኮቴ ተገኝቶ መጎብኘት ስለሚቻል አንድ እሁድ ጎራ ብለው ይዝናኑ ፡፡

ማስታወሻ፡ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ቅፅ 12 ቁጥር 149 ላይ የወጣ ፅሑፍ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡ 

Wednesday, April 3, 2013

ፓራdox







ኮሌጅ ገብተው ስነ ጽሁፍ የሚማሩ ተማሪዎች ለ ‹‹ PARADOX ›› ‹‹ አያዎ ›› የሚል ትርጉም ይሰጡታል ፡፡ ‹ አይ › እና ‹ አዎ › እንደማለት ፡፡ መዝገበ ቃላታችን ደግሞ እንደወረደ ‹‹ ርስ በርሱ የሚጋጭ ›› በማለት ይበይነዋል ፡፡

የስነ ጽሁፍ ጉዳይ በእግረ መንገዱ ከተነሳ የሶስት ምርጥ ደራሲያንን ‹‹ አያዎ ›› ሀረጎች ማስታወስ ለርዕሰ ጉዳያችን ቅመምነት ሳይጠቅም አይቀርም ፡፡ አየርላንዳዊ ጸሀፊና ገጣሚ ኦስካር ዋይልድ ‹‹ I can resist anything but temptation ›› የሚላት ነገር አለችው  ፡፡ ዊሊያም ሼክስፒር በሃምሌት ላይ ‹‹ Be cruel to be kind ›› ሲል እናገኘዋለን ፡፡ ጆርጅ ኦርዌል በአኒማል ፋርም ላይ ‹‹ All animals are equal, but some are more equal than others ›› ሲል ይቀኛል ፡፡

የሶስቱንም ታዋቂ ብዕረኞች አባባል ስንመረምር ጥልቅ ትርጉም የያዙ መሆናቸውን እንረዳለን ፡፡ ሶስቱም ብዕረኞች በአሽሟጣጭና ግራ ገብ በሆነ ስራዎቻቸው የተጠቃና የቆሰለ አንጀትን በቅቤ ለማራስ የገዘፈ አቅም አላቸው ፡፡

ጥናት ቢያስፈልገውም ‹ paradox › በድሃና የሶሻሊዝምን ስርዓት በሚከተሉ ሀገሮች / ምስኪን ህዝቦች / ይበልጥ የሚበዛ ይመስለኛል ፡፡ በኛ ሀገር ተጨባጭ ሁኔታ ደግሞ ፓራዶክስ ‹‹ በየዓይነቱ ›› እንደማለት ነው ፡፡ በውዴታ ግዴታችን የምንመርጠው ፡፡

ወጋችንን  በአንድ ሁለት ቆጠራ ለማሳመር  ወደ ጉሮሮ የሚወረወር ነገር እንያዝ ፡፡ ብሂሉም ነገር በምሳሌ ጠጅ በብርሌ አይደል የሚለው ፡፡

አንድ  .

በቅርቡ በሚከናወነው የወረዳና የክልል ምክር ቤቶች ምርጫ በርካታ ተቃዋሚ ድርጅቶች ‹‹ የምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አሰራር አልተመቸንም ›› በሚል ምክንያት ለራሳቸው ቀይ ካርድ አሳይተዋል ፡፡ ምርጫ ቦርድ በየሰፈሩ ግድግዳ ላይ የለጠፈው የተወዳዳሪዎች ስምም የሚጠቁመው  ከ90 እስከ 95 ፐርሰንት የሚሸፍኑት ዕጩዎች የተገኙት በኢህአዴግ አቅራቢነት ነው ፡፡ 

በኢህአዴግ በኩል የሚታየው የምረጡኝ ቅስቀሳ መጠን ሰማይ ጥግ መድረሱ ግን ሳያስገርም አይቀርም ፡፡
መቼም እንደ ዘንድሮ  በተወዳዳሪዎች ማነስ በእጅጉ ኮስምኖና ገርጥቶ የታየ ምርጫ መኖሩ ያጠራጥራል ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ መልካም ፍቃድ እንደ ዘንድሮ ምርጫ ለተቃዋሚ ድርጅቶች መቀስቀሻ የሚውል ሰፊ የአየርና የህትመት ግዜ ተሰጥቶ አያውቅም ፡፡ 50 ከመቶ ፡፡ ይህን ቁጥር የሰሙ የተወሰኑ ተቃዋሚዎችም ቋንቋ እየቀያየሩ ‹ አስገራሚ ነው › ‹ fair ነው › ሁሉ ብለውታል ፡፡

ሁለት .

ህንጻና መንገድ እያበዛች የምትገኘው አዲስ አበባ አስጸያፊ ቆሻሻዋንም እንደ ኩይሳ ከመቆለል ወደ ኃላ አላለችም ፡፡ በአዲስ አበባ መንደሮች ውስጥ ስታልፉ ለቆሻሻ ማስወገጃ የተሰሩት ፍሳሾች የሚሰቀጥጥ ክርፋት ይመግቧችኃል ፡፡ በየሰፈሩና አስፋልት ዳር የተሰየሙት ገንዳዎች እንደ ከተማው ታክሲዎች ከጭነት በላይ የሚሸከሙ በመሆናቸው የቅርናታቸው ከበሮ ከሩቅ ለአፍንጫ ይሰማል ፡፡ 

አይነምድሩ ፣ አተላውና የፋብሪካው ተረፈ ምርት ምንም ሳይሳቀቅ ወደ ተገኘው ወንዝ በዝግታ እየገማ ሲቀላቀል ይመለከታሉ ፡፡ ህግ የለም እንጂ ህግ አስከባሪ ‹‹ እጅ ወደላይ ! ›› ብሎ ቢጠይቃቸው ከጤና ቢሮና ከአካባቢ ጥበቃ የተሰጣቸውን ፍቃዶች በኩራት የሚያሳዩ ነው የሚመስሉት ፡፡

የከተማችን ቆሻሻ ፣ ግማትና ክርፋት የጥጋቡ ጥጋብ ጨረቃ ቤት ሰርቶ ያለምንም ፍርሃት እየኖረ የሚገኘው በማዘጋጃ አጥር ዙሪያ በሙሉ መሆኑ ነው ፡፡ ግቢያቸውን እንኳ ማጽዳት ያልቻሉት የከተማው አስተዳደሮች በየዕለቱ ስለ ሩቁ ይሰብካሉ ፡፡ ጽዳትና ውበት ፣ ደረቅና ፍሳሽ ፣ ጸረ ቆሻሻ ማህበራት ወዘተ በማለት ሪፖርት ላይ ይደንሳሉ ፡፡

እንግዲህ እያኖረችን የምትገኘውና ከ ሀ እስከ ፐ የምናውቃት አዲስ አበባ ይቺ ናት ፡፡ አንድ  ቡድን ግን በ 2013 ሊጎበኙ ከሚገባቸው አስር ምርጥ ከተሞች አንዷ አዲስ አበባ ናት በማለት ገራሚ ወሬ አሰማን ፡፡ ለ ‹ ቀባሪው አረዱት › ን ከጠቀሱ ላይቀር በዚህ መልኩ ነው ፡፡


ሶስት  .

የሳኡዲ አረቢያ ምክትል መከላከያ ሚ/ር የሆኑት ካሊድ ቢን ሱልጣን በሶስተኛው የአረብ ውሃ ካውንስል ስብሰባ ላይ ‹‹ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ውሃ የመያዝ አቅሙ 70 ቢሊየን ኪዩቢክ ሜትር ይደርሳል ፤ ይህን ውሃ ለመያዝ ደግሞ የግድቡ ከፍታ ወደ ላይ እስከ 700 ሜትር ሊረዝም ይችላል ፡፡ ይህ ግድብ የሚደረመስ ከሆነ ካርቱም በሙሉ በውሃ ትጥለቀለቃለች ፡፡ ጦሱም ለአስዋን ግድብ ይተርፋል ›› በማለት አስተያየት ሰጡ ፡፡

የኢትዮጽያ መንግስት ብዙ ግዜ የሚናገራት ‹‹ ትዕግስት ›› አሁን በፍጹም አልሰራችም ፡፡ በአምባሰደሩ ፣ በውጭ ጉዳይ ሚ/ርና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሳይቀር አስተያየቱ ጸብ አጫሪና ያልተገባ በመሆኑ ማብራሪያ እንዲሰጥ የሳዑዲ አረቢያ መንግስትን ማጨናነቅ ያዘ ፡፡ ቢፒአርና ቢኤስሲ ላይ የሚታወቀው ‹‹ ፈጣን ምላሽ ›› እንደዚህ ተግባራዊ ሆኖ ማወቁ ያጠራጥራል ፡፡

በሌላ በኩል የ30 ሺህ ኢትዮጽያዊያንን ደም ያፈሰሰውና አያሌ ቤቶችን ያቃጠለው የሮዶልፎ ግራዚያኒ ወንጀለኝነቱ ተፍቆ የጀግና አክሊል ሊደፋ አይገባም በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ በኛም ሆነ በምድረ ጣሊያን ተነስቶ ነበር ፡፡ ጉዳዩ ያሳሰባቸው ሸገሬዎችም  የተቃውሞ ሰልፍ በ የካቲት 12 መታሰቢያ ሃውልት አደባባይ ለማድረግ ሞክረዋል ፡፡

የግራዚያኒን አረመኔነትና ጭካኔ በሰብዓዊነት ሚዛን መለካት ያልፈለጉ የአፊሌ መንደር ነዋሪዎች ናቸው 127 ሺ ዩሮ በማውጣት ሃውልት ያሰሩለት ፡፡ ሃውልቱ ላይም ‹‹ Father land ›› እና ‹‹ Honour ›› የሚሉ ቃላቶችን  አጽፈዋል ፡፡ ይህ መቼም ለኢትጽያ መንግስትም ሆነ ህዝብ ከፍተኛ ንቀትና ውርደት ነው ፡፡ ለነጻነት የታገሉ ሰማዕታትን ክብር  የተለየ ግምት ያለመስጠትም ያስመስላል ፡፡ መንግስት የወንጀለኛና ጨፍጫፊ ኃውልት በምድረ ጣሊያን ሲቆም የዝምታ ዲፕሎማሲ ተጠቀመ  ፡፡ 

እንዳቅማቸው በጉዳዩ ላይ ያገባናል ያሉትን ደግሞ ያልተፈቀደ ሰልፍ አድርገዋል በማለት በተነ ወይም አሰረ አሉ ፡፡ የአራዳ ልጆች ‹‹ ፈጣን ምላሽ ›› አሁን የት ገባች እያሉ ነው  ፡፡

አራት  .

የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን በኢህአዴግ ስብሰባ ላይ አቶ መለስ 4 ሺህ እና 6 ሺህ ብር በፔሮል የሚከፈላቸው ብቸኛ ድሃ መሪ መሆናቸውን ይፋ አድርገዋል ፡፡ የእሳቸውን ዜና ስሰማ በቅርቡ ቢቢሲ ይፋ ያደረገው ፣ እረ እኔም አርቲክል ከጻፍኩባቸው የዓለማችን ድሃ ፕሬዝዳንት ወሬ ጋር ተጋጨብኝ ፡፡ ቢቢሲ የዓለማችን ድሃ ፕሬዝዳንት ብሎ ይፋ ያደረጋቸው የ 77 ዓመቱን የኡራጋይ ፕሬዝዳንት ጆሴ ሙጂካን / José Mujica / ነው ፡፡ በወር የሚያገኙት እውነተኛ ደመወዝ 7 ሺ 500 ፓውንድ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 7 ሺህ 15 ፓውንዱን ማለትም 90 ከመቶውን ለድሃዎች መቋቋሚያ ነው የሚሰጡት ፡፡ ይበቃኛል ብለው ወደ ቤታቸው ይዘውት የሚገቡት ገንዘብ 485 ፓውንድ ወይም 10 ከመቶውን ብቻ ነው ፡፡

ወ/ሮ አዜብ የነገሩን እውነት ከሆነ የቢቢሲውን ዜና አስተባብለው ስለ አቶ መለስ ድሃነት እንዲዘገብ ማድረግ ነበረባቸው ፡፡ ይህን የመሰለ ወርቅ መረጃ ይዞ ፍጆታውን ለሀገር ውስጥ ብቻ ማድረግ ተገቢ አይመስልም ፡፡ የአራዳ ልጆች የጊነስ ወርልድ ሪከርድንም ጉሮሮ ማሰብ ያስፈልጋል ባይ ናቸው ፡፡ ‹‹ እሱስ እኛ ካልደረስንለት ምን ይሆናል ? ››