Monday, July 13, 2020

መንግስት ለእውነተኛ ፍትህ ይቁም !



በኦሮሚያ በተለያዩ ከተሞች የደረሰውን አሰቃቂና ዘግናኝ ድርጊት ስመለከት እንደወንድ ልጅ አዘንኩ ። በድንጋይ ፣ በዱላ፣ በሜንጫ ፣ በእሳት …  የሰው ልጅ የሰው ልጅን አጠፋው ። ይህን መሰል የመንጋ ፍጅት በቡራዩ ከተማ ሲጀመር ‹ እንዴት ወንድም በወንድሙ ላይ ይጨክናል ? › ነበር ያልኩት ። በአዲስ አበባና በደቡብ ክልሎች ተመሳሳይ ጥፋት ሲፈጸም ‹ እንዴት ወገን በወገኑ ላይ ይጨክናል ? › ነበር ያልኩት ። የአሁኖቹን ገዳዮች ግን ወንድምም ሆነ ወገን ለማለት ድፍረት አጣሁ ። ቄሮ ነን ለሚሉ ወገኖች / ከደሙ ንጽህ የሆናችሁትን አይመለከትም /  የክፋታቸውን ልክ የሚመጥን ስያሜ ለመፈለግ ብዙ ባዘንኩ ። ገዳይ ፣ ጨፍጫፊ ፣ አረመኔ ፣ ዘረኛ ፣ አሸባሪ፣ ርጉም ፣ አውሬ … ብዙ መገለጫዎችን ብደረድርም ልካቸውን ያገኘሁላቸው አልመሰለኝም ።

እነዚህ አውሬዎች እኩይ ተግባራቸውን አንዴ ብቻ ሳይሆን ደጋግመው አሳይተውናል ። ሰላማዊውን የሰው ልጅ ከላይ በገለጽኩት መንገድ አጥፍተዋል ። አሁንም ራሴን ጠይቄ መልስ ያጣሁለት ነገር ከዚህ በላይ ምን ቀርቷቸው ይሆን ? የሚል ነው ። በሚቃጠል ሬሳ እየጨፈሩ ተደስተዋል ። የሞተ አስከሬን መንገድ ለመንገድ በመጎተት ፌሽታ አድርገዋል ። እናትን እናከብራለን እያሉ እናቶችን ልጆቻቸው ፊት ገድለዋል ። እህቶች አለን እያሉ ሴቶችን በጭካኔ ደፍረዋል ። አባት ዘውድ ነው እያሉ በእርጅና የተጎዱ አረጋዊያንን ጨፍጭፈዋል ። ሰላሳና አርባ አመታት በስንት ላብና ድካም የተገነቡ ተቋማትን አቃጥለዋል ። የሚጠራጠሩትን መታወቂያ ካርዱን በማየት ፣ የሚለዩትን ደግሞ ከአማራና ጉራጌ ወገን ነው በማለት ቤታቸውን አንድደው እንደ ዳመራ ሞቀዋል ። ነገ የተሻለ ዜጎች እንዲሆኑ መሰረት የሚጥልላቸውን የራሳቸውን ትምህርት ቤቶች አውድመዋል ።

ይሄን ሁሉ አድርገው ግን ገና አልረኩም ። አሁንም ይፎክራሉ … አሁንም ያስፈራራሉ ። ታዲያ ምን ቀራቸው ? እንደ ህንዶች ያቃጠሉትን የሬሳ አመድ ተራራ አናት ላይ ወጥተው መበተን ? … የገደሏቸውን ህፃናትና ሴቶች ደም እንደ ቫምፓየር መመጠጥ ?… በሚጎትቱት የወጣቶች ሬሳ እግር ኳስ መጫወት ? … ዱላና ሜንጫቸውን በእሳት አግለው የንጽሃን ገላ ላይ ቄሮ የሚል ንቅሳት መጻፍ ?…
ነው ከዚህ የላቀ ሌላ የርካታ ጣራ አላቸው ? እንዴትስ ከሰው ተፈጥረው በተለይ መከላከል የማይችለውን ሰላማዊ ዜጋ ያጠፋሉ ? ይህስ በባህላቸው ‹ ጀግና ወይም አንበሳ ገዳይ › የሚያስብል ነው ? ኦሮሞ አቃፊ ነው የሚባለው ነገር ለተወሰኑ ቡድኖች ብቻ ነው የሚሰራው ? ይህ አባባል መፈክር ካልሆነ በስተቀር ትንች ኮሽ ባለ ቁጥር ‹ ነፍጠኛና መጤ › በሚል ታርጋ እንዴት ወገንን ለማረድ መጣደፍ ይኖራል ? ድርጊቱ የአንድ ሰሞን ወይም የአንድ ግዜ አጋጣሚ ቢሆን ጥሩ ፤ ካልሆነ እንዴትስ በተደጋጋሚ የሰው ጎርፍ ሲፈስ ተመለክትን ? ለዚህ ወሳኝ ጥያቄዬ ወሳኝ መልስ የሚሰጠኝ አለ ?

አንዳንዶች በመጥፎ ትርክት ስላደጉ … ሌሎች ደግሞ የግብረገብና የፖለቲካ ብስለት ስለሌላቸው ነው የተቀባበለ ጠመንጃ ሆነው የሚኖሩት ይላቸዋል ። ለዚህም ነው የሆነ ቡድን ተነስ ! በለው ! ካላቸው ለምን እና እንዴት የሚሰኙ ህሊናዊ ጥያቄዋችን ሳይመረምሩ ዱላና ገጀራቸውን ይዘው የሚሮጡት በማለት ። አንዳንዶች ከሃይማኖት የራቁና ፈሪሃ እግዚአብሄር ስለሌላቸው የጭካኔን ዜማ ለማንጎራጎር ተገደዋል ባይ ነው ። ብዙ ብዙ ይባላሉ ። ነገር ግን በቅርቡ ከአርሲ በተለቀቀ አንድ ቪዲዮ ላይ የንጽሃንን ቤት እያቃጠሉ ‹ አላሁ አክበር › የሚሉ ቄሮዎችንም ታዝበናል ። ይህን ቪዲዮ ያየሁ ግዜ ይበልጥ ነው የተሸማቀቅኩት ። መጥፎ ተግባር እየተከናወነ እንዴት የፈጣሪ ስም ይጠራል ? ለሃይማኖታቸው የቆሙ ቀናኢ ሙስሊም ወገኖች ይህን ተግባር የግድ ሲያወግዙ መስማት ያስፈልጋል ። አሊያ የቄሮን ክፉ ተግባር እንደመጋራት ነው የሚያስቆጥረው ።

አረመኔው ቡድን በተድጋጋሚ ንጽሃንን ሲገድልና ንብረት ሲያውድም እንዴት መከላከል አልተቻለም ? ወይም ለምን መከላከል አልተፈለገም ? የሚለው ጥያቄ አብሮ ይመጣል ። የኛ ሀገር የፖለቲካ ዘውግ ከቧልት ቦሃቃ የሚቀዳ ነው ። በኦሮሚያ ክልል ለበርካታ ዙሮች በርካታ ፖሊሶች ተመርቀው ሲወጡ አይተናል ። አንዳንዶች እንደውም ‹ ወደ አጎራባች ክልሎች ዘመቻ ሳይኖር አይቀርም › በማለት ሲያሸሟጥጡ ነበር ። ሰልጥኖ የወጣው የፓሊስ ቁጥር የኦርሚያን ሰላምና ድህንነት ለማስጠበቅ የሚያንስ አልነበረም ። ይሁንና በአዳማ ፣ በዝዋይ ፣ በአርሲ ፣ በሻሸመኔ ፣ በጅማና በሌሎች ከተሞች ስፍር ቁጥር የሌላቸው ህንጻዋችና ቤቶች ሲነዱ ይህ ‹ የሰለጠነ › ሃይል ተደብቆ ነበር ። ወይም ልብሱን አውልቆ ለአውዳሚዎቹ ክብሪት እየጫረ ነበር ። ወይም ደግሞ ዱላ የያዘውን መንጋ ከያዘው ጠመንጃ ጋር ሲያነጻጽረው አንሶበት ጥሎ ለመሄድ ተገዶ ይሆናል ። በእውነት ሌላው አሳፋሪና አሸማቃቂ ጉዳይ ይሄ ነበር ። ሰላምን ለማስጠበቅ ሰልጥኖ ከተማው ጦር ሜዳ ስትሆን እያየ እጅን አጣጥፎ በ‹ ሰላም › መቀመጥ በአለም ያልተመዘገበ ቧልት ነው ። ከተማውን ሊጠብቅ የነበረው ኦሮምኛ ተናጋሪ ያልሆኑ አካላት ከተማውን ሊያወድሙ ሲመጡ ብቻ ነበር እንዴ ? ኦሮምኛ ተናጋሪዎች እሳት ሲለኩሱና ንጽሃንን እያጋደሙ ሲያርዱ የሰላም መናጋት አይደለም እንዴ ? ነው በክልሉ ህገመንግስት ኦሮምኛ ተናጋሪ ወንጀለኛና አሸባሪ እንዳይቀጣ ተደንግጓል ?

ከፖሊሶቹ አጥፊ ተግባር ጎን ለጎንም የየከተሞቹ አስተዳዳሪዎችና ባለስልጣናት የፈጸሙት ሀገራዊ ክህደት በቀላሉ የሚታይ አይደለም ። የጭፍጨፋው ተግባር ክስድስት ሰዓታት በላይ በግልጽ ሲከናወን የራሳቸውን ፖሊሶች አስተባብረው ለመከላከል ያደረጉት ጥረት የይስሙላ ነው ወይም የለም ። አቅም ቢያንሳቸው እንኳ ለሚመለከተው አካል ሪፖርት አድርገው የጥፋቱን መጠን ለመቀነስ ሲተጉ አልታየም ። እንደማንኛውም ነዋሪ ከሳቱ ዳር ቆመው ‹ ወይ ጉድ › ማለት አሊያም ሬሳ ሲጎተት ክንፈር መምጠጥ ህዝብን እናስተዳድራለን ብለው ሃላፊነት ከወሰዱ ዜጎች የሚጠብቅ አልነበረም ። እንዳልኩት የኢትዮጽያ በተለይ የኦሮሚያ ፖለቲካ ከቧልትም የዘለለ ነው ። ራስንና ህዝብን መከላከያ ጠመንጃ ይዞ ለዱላ የሚማረክ ወይም በግልባጩ ጠመንጃውን ተደግፎ አጥፊዎች ሲያጠፉ ጥርሱን እየፋቀ የሚታዘብ ፖሊስ ነው ያለን ። ይህን አይነቱን ፖሊስ ነው እንግዲህ ‹ ህዝባዊ › እያልን ማእረግ የምንሰጠው ። ይህንኑ ፖሊስ ወይም መከላከያን ጠርቶ ወንጀልን መከላከል ሲገባው ያላደረገን ባለስልጣናት ነው እንግዲህ  የ ‹ ለውጥ አቀንቃኝ › እያልን የምንጠራው ።

ነገሩ በእንቁላሉ ግዜ በቀጣሽኝ አይነት ነው ። መንግስት ገና በማለዳው የጃዋርና የኦነግ ቡድን የሚፈጽማቸውን ወንጀሎች እያየ እንዳላየ ይክድ ነበር ። ህግ ይከበር … የህግ አለመከበር ንጽሃንን ብቻ ሳይሆን መንግስትን ያጠፋል እያልን ስንጮህ ምህዳሩን እናስፋ… ሆደ ስፊ እንሁን … ትእግስት ይኑረን እያለ ሲመልስ ነበር ። ምህዳር የሚሰፋው ህጉ በሚያዘው ህጋዊ ሜዳ ላይ እንጂ ህገወጥነትን እሹሩሩ በማለት አልነበረም ። በአንድ ሰው ሰበብ 86 ንጽሃን ሲገደሉ የህጋዊነት ጥያቄ እየተካደ ቆይቷል ። ማንም ክህግ በላይ አይደለም እያሉ የተወሰኑ ቡድኖች ሲገድሉ ፣ ሲዘርፉ ፣ ህዝብን በህዝብ ላይ ሲያነሳሱ ‹ እንታገሳቸው › የሚል ቀልድ እንሰማ ነበር ። ይህ ደግሞ ህግን አለማክበር ብቻ ሳይሆን ሚዛናዊነትን ማንሻፈፍ ለተለዩ ቡድኖች የተለይ ጥቅም የመስጠት ያህል ነበር ። ለዚያም ነው በግሌ ዶክተር አብይ ብዙ በጎነቶች ያሉት ቢሆንም ብዙ ድክመቶችም አሉበት ስል የነበረው ። ብዙ ድክመት ያልኩት በቁጥር ብዙ ሆነው ሳይሆን ‹ ህግ ማስከበር ያለመቻል › ጽንሰ ሀሳብ እንደ ብዙ ችግሮች ሊመነዘር በመቻሉ ነው ።

የዶ/ር አብይ መንግስት ለሀገር የሚያስፈልጉ ሶስት ማእዘኖችን ደጋግሞ ሲጠራ ይሰማል ። ሰላም ፣ ልማትና ዴሞክራሲ ። ልማትና ዴሞክራሲ እውን ሊሆኑ የሚችሉት ሰላም ሲረጋገጥ ብቻ ነው ። ሰላም የሚረጋገጠው ደግሞ በመፀለይ ብቻ አይደለም ፤ ይልቁንም ህግን በአስተማማኝ መልኩ አክብሮ ማስከበር ሲቻል ነው ። ሀገር የሚቆመው ቁጥር አንድ በሚባለው ህግ የማስከበር ተልእኮ ነው ። ወንጀልና ስርዓት አልበኝነት ልማትና ዴሞክራሲን እያረደ ሲመጣ እያየህ ልታገሰው ማለት አራጁ የቤትህን በር እስኪያንኳኳ መጠበቅ ማለት ነው ። አራጁ የኦሮምኛ ተናጋሪ ስለሆነ አራት ኪሎ አይደርስም የሚል ፌዛዊ የገበጣ ጨዋታም መንግስት ሲጫወት ታዝበናል ። በዚች ገበጣ የታቆሩት ጠጠሮች ግን የጥይትን ሚና ተክተው የመንግስት ባለስልጣናትን ለመግደል ወይም የመንግስትን ህልውና ለማፈራረስ መወንጨፍ ደረጃ ደርሰዋል ። መንግስት ህዝብ የሚሰጠውን አስተያየት ቀድሞ ቢሰማ ፣ መስማት ብቻ ሳይሆን ተግባራዊ ቢያደርግ ኖሮ ዛሬ የደረስንበት ወዳሚ ምእራፍ ላይ ባልደረስን ነበር ። መንግስት ከሆንክ ህግንና ስርዓትን እንጂ ይሉኝታን ፖሊሲ ወይም መመሪያ ማድረግ የለብህም ። አሁንም ቢሆን ከልብ የመነጨ ህጋዊ አሰራር እንዲሰፍን መጠየቅ ግድ ይላል ። የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ገዳዮች በማይታመን ፍጥነት አድኖ ለፍርድ ማቅረብ ቢገርምም  ያስደስታል ። ይህ ሙሉ የሚሆነው ግን በየከተማው ህይወታቸውን ላጡ ንጽህ ነፍሶች ፍትህ ሲገኝ ነው ። ንብረታቸውን ላጡ በርካታ ዜጎች የፍትህ ስርዓቱ ተደራሽ መሆን ሲችል ነው ። አጥፊዎች በፍትህ አደባባይ ‹ አጥፊ › ፣ ገዳዮች በፍትህ አደባባይ ‹ ነፍሰ ገዳይ › ተብለው ህጋዊውን ቅጣት ሲከናነቡ ነው ።

ይህን አለማድረግስ አልከኝ ? … ይህን አለማድረግማ ፖለቲካዊ ሽፍጥና ብቻ ሳይሆን ልማታዊ አስተሳሰብን መቅበር ነው ። ይህን አለማድረግ ዜጎች በተለይም ባለሃብቶች ከኦሮሚያ ክልል ጋ እንዲቆራረጡ ማድረግ ነው ። ይህን አለማድረግ በክልሉ የሚኖሩ ሌሎች ብሄሮች ነገንም ጭራቅ  አድርገው እንዲስሉና ለስነልቦና ቀውስ እንዲጋለጡ በር መክፈት ነው ። መንግስት በተደጋጋሚ ሊታደጋቸው አለመቻላቸውን ከተረዱ ራሳቸውን አስታጥቀው ለመከላከል ይገደዳሉ - ይህ ደግሞ የምናዜምለትን ሰላም የማናጋት አቅም አለው ። ይህን አለማድረግ የነገ ውጤቱን አደገኛ ማድረግ ነው ። ክልሉ ፍትህን ባለማረጋገጡ ‹ ገዳዩ ወይም አስገዳዩ ክልል › የሚል መጥፎ ስያሜ እንዲያገኝ ይለፍ መስጠት ነው  ። የአዲስ አበባ ነዋሪም  ከክፉ የማያድነውን አስተዳደር ወደጎን ትቶ በራሱ ጎበዞች አማካኝነት ሌላኛው ቄሮ እንዲሆን ማበረታታት ነው  በመሆኑም ከእንግዲህ ሁላችንንም መዝኖ መዳኘት ያለበት ህግ ብቻ እንዲሆን እንፍቀድለት - ሆደ ሰፊነት የሚል ዲስኩር ይቁም ! የብልጽግና መንገዳችንን ብሩህ ለማድረግ ለእውነተኛ ፍትህ እንቁም !