Sunday, October 29, 2017

« አውሮራ » - የጦርነት አረር ፣ የፍቅር ቀለሃ


ሪኩ የተገነባው ዙዎቻችን በምናውቀው እውነት ላይ ነው ። ጠላትህ ጠላቴ ነው ተባብለው የተማማሉ ሁለት ብሄርተኛ ቡድኖች ለረጅም አመታት ታግለው እንደ ሀገር የሚያስበውን ቡድን አሸንፈው ስልጣን ያዙ ።

በስልጣን ማግስት ሀገር የፈለገውን ይበል ብለው መስመር ባለፈ ፍቅር ከነፉ ። እንደ ደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ‹ ሁለት አፍ ያለው ወፍ › ሆኑ ። በፍቅር ተጎራረሱ ። ተቃቅፈው በረሩ ፣ አለም ጠበባቸው ... ተጣብቀው ዘመሩ ‹ አይበላንዶ  ...  › እያሉ ።ተያይዘው ፈከሩ ! ‹ ነፍጠኛ ሰመጠ ፣ ተራራ ተንቀጠቀጠ › በማለት ... አብረው ተዛበቱ ‹ ትግል ያጣመረውን ህዝብ አይለየውም › በሚል ስልቂያ ... ኪስህ ኪሴ ነው ፤ ሚስትህ ሚስቴ ናት ፤ ግዛትህ ግዛቴ ... ምን ያልተባባሉት አለ ?

 ከአይን ያውጣችሁ ያላቸው ግን አልነበረም ።

እየቆየ አይንና ናጫ ሆኑ ... በአጎራረስህ እየተጎዳው ነው በሚል አንደኛው አፍ የጫካ ውንድሙን ካደ ። የእህል ምርቱንም ሆነ የሚያጌጥበትን ማእድን ደበቀ ። የብር ኖቶችን ቀየረ ፣ የድንበር ንግድ ግብይት በዶላር እንዲሆን ድንገተኛ ህግ አረቀቀ ። ይህ ተግባር ለሁለተኛው አፍ የማይታመን ክህደት ነበር ። ባጎረስኩ እጄን ተነከስኩ አለ ። ጠፍጥፎ በሰራው ልጅ ተናቀ ... ሹካ አያያዝ አስተምሬው ? በኔ ደም ለወንበር በቅቶ እንዴት ክብሬን ያራክሳል በማለት ለጦርነት ተዘጋጀ ።

‹ አውሮራ › ይህን የምናውቀውን ታሪክ ይዞ ነው መዋቅሩን የገነባው ። የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት እንዴት ተጀምሮ እንደምን እንዳለቀ እናውቃለን ፣ ምን እንዳስከተለም የብዙ ወገኖች መረጃ አለን ። የመንግስት ሚዲያዎችን ጨምሮ የድርጅቶቹ ልሳኖች የአውደ ውጊያውን ታሪክና የታሪክ ሰሪ ሰዎችን ህይወት በመዳሰስ አታካች በሆነ መልኩ በተከታታይ አቅርበውልናል ። ታዲያ አውሮራ ምን የተለየ ነገር ሊነግረን ታሪክ ቀመስ ልቦለድ ሆነ ? ቢባል ትክክል ነው ።

ደራሲው ሀብታሙ አለባቸው ግን ብልህ ነው ፣ ገና በጠዋቱ ፣ ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ያስተዋወቀንን የታሪክ በከራ እንዴት ሳይሰለች እያጠነጠነ እስከ ምዕራፍ 43 መዝለቅ እንዳለበት በሚገባ ተረድቷል ። ስለተረዳም ሳቢና ተነባቢ አደረገው ።

ይህን ለማከናወን ከረዳው ስልት አንደኛው የትረካውን ኳስ ለመለጋት በመረጠው የመቼት አንግል የተወሰነ ይመስለኛል ። ደራሲው 80 ከመቶ የሚሆነውን ታሪክ የሚያቀብለን ከኤርትራ አንጻር ሆኖ ነው ። በትረካው የአስመራን ውበት ፣ የወታደራዊ ካምፖችን ሚስጢር ፣ የደህንነት ተቋማት ፕሮፓጋንዳ ፣ ሳዋ ስለተባለው የሰው ቄራ ፣ የፕሬዝዳንቱን ጽ/ቤት ከነተግባርና ግዴታቸው እንመለከታለን ። የህዝቡን አበሻዊ ጥላቻ ፣ ፖለቲካዊ ሹክሹክታ እና ስነልቦና እንመረምራለን ። የባለስልጣናቱን በተለይም የፕሬዝዳንቱን እምነት ፣ አስተሳሰብ እና ፍላጎት እንታዘባለን ። በአጠቃላይ ከአስመራ የምናገኘው አዲስ መረጃ ታሪኩ ሰቃይና አጓጊ እንዲሆን ትልቅ ሚና ተጫውቷል ። የታሪኩ ልጊያ ከአስመራ እየተነሳ ወደ ኢትዮጽያ ፣ ጅቡቲና ሌሎች አካባቢዎች ሲያመራ ደግሞ ተዝናኖት ብቻ ሳይሆን አማራጭ እሳቤ ይፈጥርልናል ። በመሆኑም የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት አዲስ ሆኖ እንዲሰማን አድርጓል ።
ሌላም አለ ። ታሪኩን የሚደግፉት የሴራ ቅንብሮች ባለሁለት አፍ ወፎቹ ይፋ በሆነ መልኩ በመድፍ እንዲቆራቆሱ ብቻ አይደለም የሚያደርገው - ወፎቹ በየሰፈራቸው በተዳፈነው ረመጥ እንዲለበለቡም ጭምር እንጂ ።

የአስመራው ወፍ / ኢሳያስ / ክብሩንና ጥቅሙን ለማስጠበቅ መጠነ ሰፊ ፣ የተደራጀና ህቡዕ ተኮር እንቅስቃሴ ያደርጋል ። ኢትዮጽያዊው ወፍ / መለስ / አንድም አናት አናቱን ከሚጠቀጥቁት ወንድም ግንደ ቆርቁሮች በሌላ በኩል ከሩቅ አጎቱ የሚወረወርበትን ሞርታር ለመከላከል መከራውን ሲበላ እንመለከታለን ።

በነገራችን ላይ ከአስመራ ወደ ኢትዮጽያ የሚጋልበው የታሪክ ጅረት ሁለት መቆጣጠሪያ ቤተመንግስቶች አሉት ። የአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ እና የአቶ ሃይላይ ሃለፎም ። በፍትህ ሚ/ሩ አቶ ሃይላይ ቤት አራት የታሪኩ ቁልፍ ሰዎች ይገኛሉ ። ቤተሰቦች ናቸው ። ሳህል በረሃ የተወለደችው ፍልይቲ ፣ ወንድሟ ሰለሞን እና ባለስልጣን እናታቸው አኅበረት ። ሃይላይ በርግጥም ለሰላምና ፍትህ የቆመ ብቸኛ ሚኒስትር ነው ። ከኢትዮጽያ ጋር የሚደረገው ጦርነት መሰረት የሌለው የዜሮ ድምር ፖለቲካ በመሆኑ መቆም አለበት በሚለው አቋሙ ከዋናው ቤተመንግስት ሰውዪ ጋር ይጋጫል ።

በሌላ በኩል ኢሳያስ የሃይላን ልጅ ፍልይቲን እንደ ጆከር ሲጠቀምባት እናያለን ። ኢ/ያ ውስጥ የሚከናወነውን የዶላር ዘረፋ ፣ የስለላ ስራና ህቡዕ ግድያ ትመራለች ። በጅቡቲ ወደብ ወደ ኢ/ያ የሚገባውን ስትራቴጂካዊ ንብረት ለማውደም ተመራጭዋ ሰው እሷ ናት ። ባድመ በመዝመት ለሌሎች ያስቸገሩ የመረጃና የተመሰጠሩ መልእክቶችን የመፍታት ስራ ትሰራለች ። ፍልይቲ የፕሬዝዳንቱ ቀኝ እጅ ፣ ብሩህ አእምሮ ያላት ፣ ደፋር ፣ አፍቃሪ እና ጨካኝ ገጸባህሪ ናት ።

ከኤርትራ ህዝብ አንጻር / አማራ ጠላት ነው የሚል ቆሻሻ ሀሳብ / ግን አንድ ይቅር የማይባል ክህደት ትፈጽማለች ። ክህደቱ ለኤርትራ የቴሌ እና ኤሌክትሮኒክስ ግንባታ ትልቅ ድርሻ ያከናወነውን ኢትዮጽያዊ ሰው በማፍቀሯ ነው ። አስራደ ሙሉጌታ ይባላል ። ሻእቢያ ጉልበቱንና እውቀቱን እንደ ሽንኮራ ከመጠጠው በኋላ ሊያስወግደው ቀነ ቀጠሮ ይዞለታል ። ለአስመራ ፖለቲካ ትልቅ አይን የሆነችው ፍልይቲ ከመንግስታዊው ተልዕኮ ጎን ለጎን ፍቅረኛዋን ለማዳን ህቡዕ ትግል ስታከናውን እንመለከታለን ። የሃይላይ ወንድ ልጅ ሰለሞን ‹ ናጽነት › በሚለው ነጠላ ዜማው በከተማው የታወቀ ዘፋኝ ሆኗል ። ሙዚቃው ማዝናኛ ብቻ ሳይሆን የዘመቻ መቀስቀሻም ነው ። ናጽነት ብሎ የዘፈነው ግን በኢሳያስና በአባቱ ለተመራው ትግል ማስታወሻ ለመስራት ብቻ አይደለም ። እንደውም በዋናነት የዘፈነው ነጻነት የተባለች ቆንጆ ወጣት በማፍቀሩ ነው ። ነጻነት ለኤርትራ ወጣት የእግር እሳት ወደሆነበት ሳዋ ስትገባ እሱም እንዳላጣት ብሎ ፈለግዋን ይከተላል ። እሷን ፍለጋ ላይ ታች ሲል ነጻነት በሁለት የባደመ ጦር ጄነራሎች አይን ውስጥ ትወድቃለች ። ልክ እንደ ባድመ መሬት ሊቆጣጠሯት ሌት ተቀን ስትራቴጂክ ይነድፋሉ ።

እናም የአንደኛው ቤተመንግስት ሰውዪ ከኢ/ያ ድል ለማግኘት ሲራራጥ ፣ የሁለተኛው ቤተመንግስት አባላት ደግሞ ከራሱ ከኢሳያስ ጭቆና ለመላቀቅ እንዲሁም ፍቅረኛዎቻቸውን ለመታደግ ላይ ታች ሲሉ በታሪኩ ተወጥረን እንያዛለን ።

መጽሐፉ ጥቃቅን ቴክኒካል ችግሮች የሉበትም ማለት አይቻልም ፣ ለአቅመ ግነት የሚበቁ ስላልመሰለኝ ዘልያቸዋለሁ ። ይልቁንስ ደራሲው የራሱ እምነት የሚመስል ጉዳይ መጀመሪያ ምዕራፍ ላይ ቆስቁሶ እንዲረሳ ወይም እንዲጨነግፍ ማድረጉ የሚቆጭ ይመስለኛል ። ያነሳቸው ጥያቄዎች የአንባቢም መሰረታዊ ጥያቄዎች ሊሆኑ የሚችሉ ናቸው ። የባርካ ማተሚያ ቤት ባለቤት የሆኑ ግለሰብ አቶ ሃይላይ ሊጽፉ ባሰቡት መጽሐፍ ውስጥ አራት መሰረታዊ ጥያቄዎችን አዳብረው አንዲሰሩ ሀሳብ ያቀርባሉ ። ከቀረቡት ሃሳብ ውስጥ ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው ፣

1 . የኤርትራ ነጻነት ትግል ለምን በ 1885 ምጽዋ በኢጣሊያ መያዝን በመቃወም አልተጀመረም ?
2 . ከኤርትራ ልዩ ማንነት የተፀነሰ ትግል ከሆነ ለምን 30 አመታት ፈጀ ?

ደራሲው ስራውን ከሰሩት 285 ሺህ ናቅፋ እንደሚያገኙም ውል ታስሮ ነበር ። ሆኖም የማተሚያ ቤቱ ባለቤት ሲያዙ ፣ አቶ ሃይላይም ሲገደሉ ሃሳቡ ይመክናል ። እንደ ስነጽሁፍ ሃያሲ የሁለቱ ሰዋች መጥፋትን በአስመራ ወስጥ የመጻፍ ፣ የመናገር ፣ የማሰብ እና የዴሞክራሲ መሞትን ለመተርጎም ያስረዳን ይሆናል ። ከዚህ በላይ ግን ታሪኩ ባይጨነግፍ የበለጠ ጠቃሚ ያደርገን ነበር ብሎ መከራከር ያስኬዳል ። አቶ ሃይላይ ለእውነት የቆሙ ገጸባህሪ በመሆናቸው እየመረራቸውም ቢሆን ከኤርትራ ጀርባ የተደበቁ ጉዳዮችን ያነሱ ነበር ። ይሄን አንስተው ቢሞቱ ደግሞ ሞታቸውንም ይመጥን ነበር ። የበለጠ ጀግና መስዎዕት እናደርጋቸው ነበር ።

‹ አውሮራ › ጦርነት ላይ መሰረት አድርገው እንደተሰሩት ልቦለዶቻችን ማለትም ኦሮማይ እና ጣምራጦር የተሳካ ስራ ነው ። ድንበር ያቆራርጣል ፤ እዚህና አዚያ እንደ ቴኒስ ኳስ ሲያንቀረቅበን ጨዋታው ሰለቸኝ ብለን ከሜዳው ዞር ማለት አንችልም ። ፈጣን ነው ፤ በድርጊት የተሞላና በመረጃ የደነደነ ። መንቶ ነው ፤ ፍቅርና ጦርነትን በእኩል ጥፍጥና ከሽኖ ማቅረብ የቻለ ። ሰባኪ ነው - ፍቅር ያሸንፋል የሚል አይነት ፤ ተዛምዶ ተጋብቶ ተዋልዶ የተካደ ትውልደን የሚያባብል ። የሆነውን ብቻ ሳይሆን  የሚሆነውን ቁልጭ አድርጎ የሚናገር ። በተለይም የአንድነት አሳቢዎችን ገድለን ቀብረናል ብለው ለሚመጻደቁ ጠባቦች « ውሸት ነው ! » ብሎ ጥበባዊ ምስክርነት የሚሰጥ ።

በታሪኩ ውስጥ ማንነቱን ደብቆ ስሙን አቦይ ግርማ አስብሎ ቀን ከለሊት በባድመ የልመና ተግባር የሚያከናውነው እንኮዶ /የደርግ ኮማንዶ የነበረ / አንድ እጁ ስለተቆረጠና አይኑ ስለተጎዳ ማንም ግምት ውስጥ ያሰገባው አልነበረም ። ሆኖም መጀመሪያ የባድመን መሬት ፈልፍለው የገቡ የሻእቢያ ወታደሮችን ፣ በመጨረሻም እጁን በመጋዝ ቆርጦ የጣለውን ጄኔራል ግዜ እየጠበቀ መበቀል ችሏል « ለገንጣይና ጡት ነካሽ ዋጋው ይሄ ነው » እያለ ። ይህ ትርክት በስነጽሁፍ ቋንቋ ፎርሻዶው ወይም ንግር የሚባለው ቴክኒክ ነው - ነገ እንዲህ መሆኑ አይቀርም ለማለት ።



Sunday, October 22, 2017

በአፍሪካ ጭንቅላት ዓለምን መምራት ?


« የማይቻለውን እንደሚቻል እናረጋግጥ » በሚል መሪ መፈክር ስር ተወዳድረው የአለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጄነራልነትን ያሸነፉት አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ፣ ሮበርቱ ሙጋቤን የበጎ ፍቃድ አምባሳደር አድርገው መሾማቸው አለማቀፍ ተቃውሞ አስከትሎባቸዋል ። እኔም ሰውየው የሚመለከቱበት መነጽር እንዴት ሸውራራ ሆነ ብዪ ጥያቄ አንስቼያለሁ ።

አንዳንዶች ነጮች ሙጋቤን ስለማይወዱት በተራ ጥላቻ የተደረገ ተቃውሞ እንደሆነ ያስባሉ ። እውነቱ ግን ይሄ አይደለም ። ሙጋቤ የፈለገ ያህል ለነጭ ተንበርካኪ አይሁኑ እንጂ በሀገራቸውም የሚመሰገን የፖለቲካ ስብእና የላቸውም ። ሀገሪቱን ላለፉት ሰላሳ አመታት የገዙት የተቃዋሚዎቻቸውን ድምጽ ብቻ ሳይሆን የህዝባቸውን የዴሞክራሲ ጥማት ጨፈላልቀው ነው ። ለስሙ ያህል ምርጫ ያካሄዳሉ እንጂ ‹ በህይወት እስካለሁ ድረስ ፕሬዝዳንት ነኝ › የሚሉትን መርህ አጥብቀው እየተገበሩ የሚገኙ ሰው ናቸው ። ምን ይሄ ብቻ በቅርቡም ባለቤታቸው ግሬስ ፣ ሙጋቤ ቢሞት እንኳ ሬሳው ይወዳደራል ማለታቸው የሚዘነጋ አይደለም ። የሰው ልጆች በተፈጥሮ ያገኙትን የዴሞክራሲ መብቶች የግል በማድረግ ነጻነት እንዲጠፋ ፣ ጭቆና እንዲስፋፋ የሚተጉ ባለስልጣናትን እውቅና ከሚሰጠው ጎዳና ገለል አለማለታችን ያሳዝናል ።

  ከአፍሪካ የተገኙት ቴዎድሮስ የሙጋቤ አምባገነን መሆን ጉዳያቸው ላይሆን ይችላል - ስልጣንን አለመልቀቅ የአፍሪካ ያልተጻፈ ህግ ስለሆነ ። አንድ የአፍሪካ ባለስልጣን ወደ አለማቀፉ ደረጃ ከፍ ሲል ግን በዚያው የአሰራር ስርዓት ውስጥ ሊጓዝ ግድ ይለዋል - ምክንያቱም ከአፍሪካ መጣ እንጂ አፍሪካን ብቻ ሊመራ አይደለም እዛ የተወከለውና ። እና አንድ መሪ አዎንታዊ  ቅቡልና የሚያገኘው ለሰው ልጆች ካለው ክብርም አኳያ ነው ። ሙጋቤ በሰብዓዊ መብት አያያዝ ረገድ የረባ ሰእል የላቸውም ። ተመድ በግልጽ ከሚመራባቸው መርሆዎች አንዱ ደግሞ ሰብዓዊ መብትን ማክበር ነው ። ታዲያ ሙጋቤ በምን አንጀታቸው ነው ርህራሄ የሚፈልገውን የጤና ተቋማት መደገፍ የሚችሉት ?

ሙጋቤ 93ተኛ አመታቸው ላይ ይገኛሉ ። አለመታደል ሆኖ እንጂ ይህ የማረፊያና የጥሞና ግዜ ነበር ። በየግዜው እንደምናያቸውም በአካልም ሆነ በአእምሮ ደክመዋል ። መራመድ ተስኗቸዋል ፣ ስብሰባ መቀመጥ ባለመቻላቸው በየሄዱበት ያንቀላፋሉ ። አንድ ሰው ንቁ ካልሆነ እንዴት ለሌላ ስራ ይታጫል ? አቶ ቴዎድሮስ ለዚህ ጥያቄ አሳማኝ ምላሽ የሚኖራቸው አይመስለኝም - በሙጋቤ ቃል አቀባይ ፎጋሪ አስተያየት ካልተስማሙ በስተቀር ። ፎጋሪው ሰውየ ምን አለ መሰላችሁ « ሮበርቱ ሙጋቤ በየስብሰባው የምታዩዋቸው እየተኙ አይደለም - አይናቸውን ስለሚያማቸው እያረፉ እንጂ »

አቶ ቴዎድሮስ ለዙምባቤ ጤና አገልግሎት አሰጣጥ አዎንታዊ ድጋፍ እንዳላቸውም ተናገረዋል ። ይህ አስተያየታቸው ግን ከነባራዊው እውነታ ጋር የሚጣረስ ነው ። በርካታ መረጃዎች የሚያመለክቱት የዙምባቤ የጤና ስርአት እጅግ አሳዛኝና አሳሳቢ ደረጃ ላይ የሚገኝ መሆኑ ነው ። ሰራተኞች ያለ ደመወዝ የሚሰሩበት ግዜ ጥቂት አይደለም ፣ በመንግስት ሆስፒታሎች መድሃኒት ባለመኖሩ ሰራተኞች በቂ ህክምና ለመስጠት ተቸግረዋል ።

አቶ ቴዎድሮስ ሙጋቤ በዓለማቀፉ ጤና ድርጅት ተመርጠው መስራታቸው የሀገራቸውንም ሆነ የአፍሪካን የጤና አያያዝ ሊያሻሽሉ ይችላሉ ባይ ናቸው ። እውነቱ ግን ሙጋቤ በሀገራቸው ጤና ስርአት ላይ እምነት የሌላቸው መሆኑ ነው ። እምነት በማጣታቸውም ሲታመሙ እንኳ በሆስፒታላቸው ሊታከሙባቸው አይፈልጉም ።  አቶ ቴዎድሮስ ‹ የህክምና ቱሪስት ፕሬዝዳንቶች ›  / Medical Tourist Presidents / ስለተባሉት የአፍሪካ መሪዎች አንበው ቢሆን ኖሮ ይህን ከመሰለ ስህተት ውስጥ ባልገቡ ነበር ።

ዓለም የሚሳለቅባቸው እነዚህ የህክምና ቱሪስቶች የናይጄሪያው ሙሃመድ ቡሃሬ ፣ የአንጎላው ጆሴ ኤድዋርዶ ፣ የቤኒኑ ፓትሪስ ታሎን ፣ የአልጄሪያው አብዱላዚዝ ቡተፍሊካ እና የዙምባቤው ሮበርቱ ሙጋቤ ናቸው ። እነዚህ መሪዎች በአመት ውስጥ ደጋግመው ውጭ ሀገር ለህክምና ስለሚመላለሱ በርካታ የሀገር ሃብት ያጠፋሉ ። ሙጋቤ ባለፈው አመት ብቻ ሶስት ግዜ ወደ ሲንጋፖር ለህክምና አቅንተዋል ፣ ለዚህም 50 ሚሊየን ዶላር ወጪ ያደረጉ ሲሆን ይህ ገንዘብ የሀገሪቱን ጤና ጣቢያዎች ለማስፋፋት ከተመደበው አመታዊ በጀት በሁለት እጥፍ ይበልጣል ። ሙጋቤ ሲንጋፖር ሄደው የሚታከሙትም በጥቁር ሀኪም ነው ። ነጭ ሁሉ ጠላት ነው የሚሉት ሙጋቤ በአለም አቀፍ የህክምና መድረክ ብቅ ቢሉ እንዴት ነው በፍቅር መስራት የሚችሉት የሚለውን ጥያቄ አቶ ቴዎድሮስ መመለስ ይኖርባቸው ነበር ።

ዞሮ ዞሮ የሙጋቤ አምባሳደርነት ተፍቋል ። አቶ ቴዎድሮስ ይህን በፍጥነት ማድረጋቸው መልካም ነው ፣ ነገር ግን በብዙ መልኩ ጥያቄና ጥርጣሬ ውስጥ ወድቀዋል ። ነገሮችን የሚያዩብት መነጽር ሸውራራ እንዳይሆን ተፈርቷል ። ስለ ተመድ ያላቸው እውቀትና አረዳድ አስጊ መስሏል ። በስሜት ሳይሆን በተጨባጭ መረጃ ውሳኔ ሰጪ አይሆኑ እንዴ አሰኝቷል ። የዴሞክራሲ ማእከል ውስጥ ገብተው ዴሞክራት ላልሆኑ ሰዎች መወገናቸው አስደንግጧል ። አቶ ቴዎድሮስ ከለመዱት ‹ አብዮታዊዊ › አሰራር በፍጥነት መላቀቅ ካልቻሉ ገና ከብዙ ጉዳዮች ጋር መላተማቸው አይቀርም ። በርግጥም በኢትዮጽያና አፍሪካ ባርኔጣ ዓለምን መምራት አይቻልም - ባርኔጣው ካልተስተካከለ ::


Saturday, October 14, 2017

የ « ማዕቀብ » መሳጭ ሀሳቦች


« ማዕቀብ » ከእንዳለጌታ ከበደ ግሩም ስራዎች አንደኛው ነው ። መጽሐፉ በዋናነት ‹ ዴሞክራት ገዢዎቻችን › በድርሰት ፣ ደራሲያንና ተደራሲያን ላይ ስላስከተሉት አሉታዊ ተጽዕኖ ይተርካል ። ከዚያ በመለስ የተመረጡ ደራሲያንና መጻህፍት ሻጮችን የህይወት ውጣ ውረድ ያመላክታል ።

በመጽሐፉ ከአዳዲስ መረጃዎችና ሀሳቦች ጋር እንተዋወቃለን ፤ ከመሳጭና ሞጋች ሀሳቦች ጋር እንፋጠጣለን ። በመሳጭ ሀሳቦች እየተብሰከሰክን ከሞጋቾቹ ጋር የከረረ ምናባዊ ምልልስ እናደርጋለን ።

ከተነሱት ሞጋች ሀሳቦች አንዱ የአቶ መለስ ዜናዊ ልቦለድ ደራሲነት ጉዳይ ነው ። አቶ መለስ በብዕር ስም ‹ መንኳኳት ያልተለየው በር › እና ‹ ገነቲና › የተሰኙ ሁለት መጻህፍትን ለንባብ አብቅተዋል ። እንዳለጌታ ተማሪ በነበረበት ወቅት አንድ ተጋባዥ መምህር ስለ ትግርኛው ስነጽሁፍ የማብራራት እድል ያገኛሉ ። እኚህ ምሁር « በአማርኛው ስነጽሁፍ በቋንቋ ፣ በጭብጥ ፣ በአጻጻፍ ቴክኒክ ታዋቂ የሆነው ዳኛቸው ወርቁ እንደሆነ ሁሉ የትግርኛው ዳኛቸው ደግሞ መለስ ዜናዊ ነው » በማለት ሃሳባቸውን ያጠቃልላሉ ።

ሲጀመር በዳኛቸው ላይ የተሰጠው ዳኝነት ትክክል አይመስለኝም ። እንዳለጌታ እንደሚለው ደግሞ መለስን እንደልቦለድ ደራሲነት ማወቅ እና ማሰብ ይከብዳል ። ደራሲ የደራሲን ህይወት ያውቃል ... ይረዳል ... ባይረዳ እንኳ ያበረታታል ... ጥበብ እንዲያድግ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል ። የነበሩ ቤተመጻህፍትን እንዲጨምሩ እንጂ እንዲጠፉ አያደርግም ። ሰውየው በስልጣን ዘመናቸው ለደራሲያን ሲቆረቆሩ አልታየም ። በአንድ ወቅት አስታዋሽ ስላጡ አንጋፋ ደራሲያን ሲጠየቁ ከአንድ አርሶአደር ለይተን አናያቸውም ነበር ያሉት - በርግጥ ከአድካሚ ስራ ጋር የሚተዋወቅ ደራሲ ደራሲነትን በዚህ መልኩ ብቻ ነው የሚረዳው ? እናም ሰውየው ስለጭብጥ እና ገጸባህሪያት ቀረጻ ይበሰለሰላሉ ብሎ ማሰብ ቁንጫ ቆሞ ሲቀድስ ፣ አህያ ሞቶ ጅብ ሲያለቅስ የመስማት ያህል ነው ይላል - እንዳለጌታ ።

በርግጥ ደራሲያን እሳቸው ‹ መንኳኳት ያልተለየው በር › እንዳሉት የድርሰት ስያሜ ሁሌም ሃሳብ እንዳንኳኳ የሚኖር ነው ። እሳቸው የቤተመንግስት በር ወለል ብሎ ከተከፈተላቸው በኋላ ሰለተዘጉ በሮች አለማሰብ ፍትሃዊ አይሆንም - በር የሚያንኳኳውን እንዳልሰማ መዘንጋት ፣ ባስ ካለም በውሻና በጥበቃ ማባርረ ከባለ ብዕረኛ አይጠበቅም ።

ሌላኛው ሞጋች ሀሳብ ሳንሱር ዛሬም ቢሆን የለም ማለት ይቻላል ወይ የሚለው ጉዳይ ነው ። ሳንሱር በአዋጅ በግልጽ ይደንገግ እንጂ በውስጥ ከሳንሱር የሚተካከሉ አሰራሮች አሉ ።

ሜጋ የመጻህፍት ማከፋፈያ ስራው መጽሐፍ በአደራ ተቀብሎ ማሰራጨት ቢሆንም ይዘታቸውን እየገመገመ የሚመልሳቸው ስራዎች አሉ ። ይህ ቁልጭ ያለ እውነት ነው ። ማተሚያ ቤቶች ህትመት ከጀመሩ በኋላ የሚቋረጡ ስራዎች አሉ ። ይህም እንዳይታተሙ የሚል ቀጭን የቃል መመሪያ ከነጌቶች ስለሚደርሳቸው ነው ። አንዳንድ ማተሚያ ቤቶች የመንግስትን ቅጣት በመፍራት ያተሙት መጽሐፍት ጀርባ ላይ ድርጅታቸውን ከመጻፍ ይቆጠባሉ ። 

ፓለቲካ ነክ ፊልሞች ከተሰሩ በኋላ እንዳይተላለፉ ታግደዋል ። የቴዲ አፍሮና የአንዳንድ ሙዚቀኞች ስራ በመገኛኛብዙሃን እንዳይተላለፉ ተደርጓል ። ዝግጅት አጠናቀው መድረክ የጀመሩ ቲአትሮች መጋረጃ ተዘግቶባቸዋል ። ጋዜጦች በጻፉት ጉዳይ መጠየቅ ሲገባቸው ገና ማተሚያ ቤት እንደደረሱ ቀኝ ኋላ ዙር ተብለዋል ።
ታዲያ ይህ ሁሉ ጉዳይ ክፍል ሁለት ሳንሱር ነው የሚባለው ወይስ የዚያኛው ሳንሱር ሁለተኛው ገጽታ ? ሀገሬው አጠናክሮ ሊወያይበት የሚገባ የቤት ስራ ይመስለኛል ።

አንዳንድ መሳጭ ሃሳቦችን ደግሞ እንመልከት ።

በርግጥ የዳኛቸው ወርቁ ‹ አደፍርስ › አከራካሪ ስራ ነው ። ለዚያም ነው አንባቢያን በብዙሃን ድምጽ ጥሩነቱን መመስከር የተሳናቸው ። ደራሲው ግን ጠመንጃ ባነገበው አንባቢ አንጻር ጦርና ጋሻ ይዞ ቆመ ። እጅና እግር ለሌለው መጽሐፍህ አምስት ብር አይገባውም እያለ በሚዘምተው ተደራሲ ፊት « ዋጋውን አስር ብር አድርጌብሃለሁ ! » ሲል የተሳለ ውሳኔውን እንደ ጦር እየነቀነቀ አሰማ ። ታዳሚውና ነጋዴው የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል አሉ ።

ቆይቶ ብቅ አለና ደግሞ አንባቢው ምን እንደሚል ጠየቀ ። ማንበብ ስላልቻለ ምን ሊል ይችላል ሲሉ ነጋዴዎች መለሱ ፤ ቅናሽ እንዲያደርግም ሃሳብ አቀረቡ ። ዳኛቸው ጦሩን ነቅንቆ እረ ጎራው አለ ፤ እረ ወንዱ አለ ። የጀግንነቱን ልክ ለማሳየትም ዋጋው ወደ 15 ብር ከፍ ማለቱን አበሰረ ። በአንባቢውና በደራሲው መሃል እንደ አሸማጋይ የቆሙት ነጋዴዎች ማሰራጨት አንደማይፈልጉ ነገሩት ። ዳኛቸው ከፉከራ በላይ ተቆጣ ። ጦሩን መሬት ላይ ቸንክሮ « ንሳ ! » ሲል ትዕዛዙን አሰማ « ከእንግዲህ መጽሃፍቶቼን ለማንም እንዳትሽጥ ! ያሰራጨሃቸውን በሙሉ ሰብስበህ አስረክበኝ ! »

ማንም ያልጠበቀው ሃሳብ ነበር ። የኢትዮጽያ ደራሲ ነጋዴ ዋጋ ቀንስ ሲለው የሚቀንስ ፣ ኮንሳይመንት ጨምሯል ሲሉት እሺ የሚል ፣ የወረቀት ክምርህ ስላልተሸጠ ይዘህ ጥፋ ሲባል ተሽክሞ የሚሮጥ ነው ። ይሄኛው ደራሲ ግን ነጋዴውን የሚያሽቆጠቁጥ ሆነ ፣ ይሄኛው ደራሲ አንባቢ ካልገባው መንገዱን ጨርቅ ያድርግለት የሚል ሆነ ። ይሄኛው ደራሲ ፍጹም አፈንጋጭ ነው ። ይሄኛው ደራሲ በክብሩም ሆነ በመንፈስ ልጁ ላይ የመጣን ጥቃት ለመመከት ቆርጦ የተነሳ ነው ። ይሄኛው ደራሲ የኢትዮጽያዊያንን ለንቋሳ አንባቢነት እና እውቀት የሚራገም ሆነ ። ምንም ሳይፈራና ሳይጠራጠር ቀጥታ ወደ ህዝቡ የሚተኩስ ሆነ « እኔን ለመረዳት 20 አመት ይቀርሃል ! » እያለ ። አደፍርስ የፈለገ ባይመች የዳኛቸው ልበ ሙሉነት ግን ይደላል ባይ ነኝ ።

በኢትዮጽያ ስነጽሑፍ ታሪክ ትልቅ  ቦታ ከሚሰጣቸው ደራሲያን መካከል አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ነው ። ይህ ደራሲ በርካታ ስራዎችን ቢያቀርብልንም  በርካታ ስራዎች መስራት በሚችልበት እድሜው ላይ ነበር /54 / ያለፈው ።

አሁን እኔ ማውራት የፈለኩት ሰለ ብርሃኑ ሳይሆን ብርሃን ስለፈጠረችለት ሚስቱ ነው ። ስለ ብርሃኑ ምርጥ ባለቤት ስለ ወ/ሮ የሺ ። ዘወትር የብርሃኑ አምሽቶ መምጣት ያሰጋት ሚስት አንድ ነገር እንዳይሆን በመፍራት መጠጡን እንዲተው ትጨቃጨቅ ነበር ። እሱ ግን በደሙ ስለተዋሃደ ያለጂን ብእር ማንሳት አልቻለም ። አልኮል እያጣጣሙ  ከ 10 በላይ ግሩም መጻሕፍትን መድረስ በራሱ ገራሚ ነው ። ምክንያቱም ለብዙዎች አልኮል እንቅልፍ መጥሪያ እንጂ ለስነጽሑፍ ከራማ መዘየጃ ሲሆን አልታየምና ።

ግራ ቢገባት ጂን እየገዛች ቤት ውስጥ ትቀዳለት ጀመር ፤ አላስደሰተውም ። ምነው ? ብትለው ብቻዪን እንዴት እጠጣለሁ ? የመጠጥ ቤት ድባብ ያስፈልገኛል አላት ። ፈተና ሆነባት ። ጎረቤት እየጠራች ቤቷን እንደ ቡናቤት አታሟሙቀው ነገር ሃብት ይፈልጋል ። ቡቡዋ ሚስት መንገድ ወድቆ ከሚቀር በሚል ‹ እኔ አጣጣሃለሁ › አለችው ። ለእሱ ብላ የጠላችውን ወደደች ። ቀስ በቀስ ጨዋታውን ለመደች :: ምን ያደርጋል ታዲያ ታላቁ ደራሲ በዚሁ ጦስ ከሞተ ጥቂት ቆይቶ የእሷም ጉበት መበላሸቱ ተነገራት ። በአንድ በኩል የባለቤቷ ሀዘን በሌላ በኩል የራሷ ህመም ተባብረው ገደሏት ።

ለባሏ ብላ መስዋዕት ሆነች ። በኢፍትሃዊ መንገድ ተቀጣች ። የደራሲ ሚስቶች ታይፕ በመምታትና በመናበብ ፣ ቡና በማፍላትና ጋቢ በመደራረብ ሲተጉ ነው የምናውቀው ። የሺ ግን ለእነዚያ ለሚያምሩ ድርሰቶች ሻማ ሆና ቀለጠች ። የዓለም አስደናቂ ስራዎች መመዝገቢያ መጽሐፍ ያላየው ታሪክ ።

ማዕቀብ ብዙ አዲስ መሳጭ ታሪኮችን ይዛለች ። ስብሃትና ባለቤቱ ዋሴ በተባለው ህመምተኛ ልጃቸው እንዴት እንደተሸነፉ ... አዲሱን መጽሐፌን አይቼውና ዳብሼው ልሙት እያሉ በጉጉት ስላለፉት ማሞ ውድነህ እና ስለሌሎችም ተረክ አላት ። ማዕቀብ የአዝናኝ መልኮችም ባለቤት ናት ። አድሃሪያን በህይወት ብቻ ሳይሆን በልቦለዱ አለምም መኖር አይፈቀድላቸውም ተብሎ በግድ ስለተገደሉት ገጸባህሪም ትሰማላችሁ ። ሰው ሲሞት ይናዘዛል ፤ ስብሃት ከመሞቱ በፊት እንደምንም ተነስቶ የተናገረው ምን ይመስላችኋል ?

« እኔ የምለው መለስ ዜናዊና ሰይፉ ፋንታሁን አሁንም በኢትዮጽያ ህዝብ ላይ እየቀለዱበት ነው ወይስ አዲስ ነገር አለ ? »
ሃሃሃሃሃሃሃሃ .... ‹ ማዕቀብ › የሌለው ንግግር ይልሃል ይሄ ነው !