Thursday, May 4, 2017

የቴዲ አፍሮ ትሪያንግል


አዲሱን የቴዲ አፍሮ አልበም አጣጣምኩት ። ከላይ ወደታች ፣ ከታች ወደላይ ተመላላሰኩበት ። ከአንዱ ጫፍ ወደ ሌላው ስዘል ውበቱን ፣ ስልቱን ፣ ስሜቱንና መልእክቱን ለመለካት እየሞከርኩ ነበር ። በዚህ የወዲህ - ወዲያ ቅኝቴ የፈጠርኩት ስእል ትሪያንግል ሆነ ።

እኩል ሶስት ማእዘን ባለው ቅርጽ ላይ ሶሰት ሙዚቃዎች ከፍ ብለው ተመለከትኩ ። በአንደኛው ጫፍ ‹ ኢትዮጽያ › ፣ በሁለቱ ጎኖች ደግሞ አጼ ቴዎድሮስ እና ማር እስከ ጧፍ ። የእነዚህ ሶስት ሙዚቃዎች ተምሳሌትነት ከፍ ያለ ነው ። የሶስቱም ዘፈኖች ግጥማዊ ክህሎት ምጡቅ ነው ። ትሪያንግሉ በራሱ ለመቆም ምሉዕ ቢሆንም አንዳንዴ ሀገር ከሚያምሰው የነገርና ምቀኝነት ሱናሜ ለመትረፍ የሚያስችልም ስንቅ አንግቧል ። ኢትዮጵያ ውስጥ / ሀገር/ ፣ አጼ ቴዎድሮስ  ውስጥ / ጀግንነት /  ማር እስከ ፍ ውስጥ ደግሞ / ፍቅር / ተወከሎ ይገኛልና ።
                                                                                                       ኢትዮጽያ
                  አጼ ቴዎድሮስ                                                                               ማር እስከ ጧፍ              

        
‹ ኢትዮጵያ › ቀደም ብሎ የተለቀቀ ነጠላ ዜማ ቢሆንም ከሙሉ አልበሙ ጋር ሳየውም መጠሪያ መሆኑ አያንስበትም ። ሙዚቃው የትልቅ አጀንዳ ባለቤት ነው ። የሞት- ሽረት ጠርዝ ላይ የሚገኘውን ኢትዮጵያነት ይሞግታል ። ኢትዮጵያነት ከዘጠና ሚሊየን ህዝቦች ውህደት በላይ መሆኑን ለማሳየት ባንዲራው ያለውን ክብርና ጸጋ ይዘክራል ።

              « እንኳን ሰማይ ላይ ባንዲራሽን አይቶ
                ኢትዮጵያ ሲባል ማን ዝም ይላል ሰምቶ »

ቴዲ የፖለቲካ ኩርፊያና በደል ማንነትን ለመካድ መሰረት ሊሆን አይችልም ባይ ነው  « ቢጎል እንጀራው ከመሶቡ ላይ ፣ እናት በሌላ ይቀየራል ወይ » በርግጥም ዓለም የሉሲ ልጆች ፣ የነጻነት ምሳሌዎች እያለ የሚጠራቸው አበሾች በየአደባባዩ በርካታ ትናንሽ ባንዲራዎች ተሸክመው ሲያያቸው ያዝናል ። በትልቁ ባንዲራችን ፍቅር ወድቀው የራሳቸውን ለመቅረጽ መነሻ ያደረጉ አፍሪካዊያንም ከንፈራቸውን መምጠጥ ከጀመሩ ቆይተዋል ። እናም የሰንደቅ እና ሀገር ጉዳይ ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ እንደሆነ ቀጥሏል ።

  « ተዉኝ ይውጣልኝ ልጥራት ደጋግሜ
    ኢትዮጵያ ማለት ለኔ አይደል ወይ ስሜ » ያስብላል

ይህ ሙዚቃ ብቻውን የተለቀቀ ሰሞን እንካሰላንቲያ ያማዘዘውም የትሪያንግሉ አንደኛው ማእዘን ሰለሆነ ነው ። ኢትዮጵያነት ግን ያው የነብር ቆዳነት ነው ። ብዙ ሂትለሮች በለስ ቀንቷቸው ኢትዮጵያዊያንን ማጥፋት ቢችሉ እንኳ ኢትዮጵያ የተሰራችበትን ታሪካዊ ፣ ሃይማኖታዊ እና ሳይንሳዊ አሻራዎች መደለዝ አይችሉም ።

በርግጥ አንዳንዶችም ሙዚቃውን አሰታከው የዋህ አስተያየት ሲሰጡ ተሰምተዋል ። አንደኛውና ዋነኛው ወቅትን እየጠበቁ እንዲሁም ሰዎችና ክስተቶች ላይ መዝፈን የጥበብ ሰው ባህሪ አይደለም የሚል ነው ። ይህ አባባል የጥበብ ምንነትን ካለማወቅ ይነሳል ። የጥበብ ግብ የገሃዱን ዓለም ጥሬ እውነት ጥበባዊ በሆነ ኩታ አስውቦ መገኘት ነው ። ስለዚህ ሰዎች እና ክስተቶች ከብዙ በጥቂት የሚቀዱ ምንጮች ናቸው ማለት ነው ።

ሌላው የቴዲ አፍሮን የጥበብ መንገድና ስልት አለመገንዘብ ነው ። ይህ ድምጻዊ በአጭር ግዜ ውስጥ የማይታመን ተቀባይነት ያገኘው  ለምንድነው ? የሚለውን ጥያቄ ስንመልስ  መስመሩን እናገኛለን ። ቴዲ የድፍረት ፣ የፈጣንና ሰፊ ምናብ ባለቤት ነው ። ማንም አቀንቃኝ የሚፈራውን የአንድነትና የመገንጠል ጉዳይ ሲፈልግ አስውቦ ያዜማል ። በፈጣን ምናቡ ወቅታዊና ትኩስ እውነቶችን የውበትና ተዝናኖት ክንፍ ሰርቶላቸው አድማጩ ቤት ድረስ እንዲያንዣብቡ ያደርጋቸዋል ። 

ፖለቲካ ያስፈራራቸውን ወይም ሀገር የረሳቸውን ጀግኖች በፈጠራ ሃውልት ያንጻቸዋል ። እነዚህ ሃውልቶች እንደምናውቃችው አይነቶች የተመረቁ እለት ብቻ የሚነገርላቸው አይደሉም ። ሃውልቶቹን በፍቅር ይተክላቸዋል ፤ እኔና እናንተ ደግሞ ደምና ስጋ ሞልተን ስለነፍሳቸው ዘወትር እናዜማቸዋለን ። በግጥም ዘርፍ « የጸጋዬ ቤት » እንደምንለው ሁሉ ይህን የዜማ አተያይም « የቴዲ አፍሮ ስልት » ማለት ይቻላል ። ታዲያ ይህን በእሱ ፍቃድ ብቻ የሚገኝ ሃያል ስልት እንዳይቀጥል የሚፈልግ ጅላጅል ተደራሲ ማነው ?

የትሪያንግሉ ሁለተኛው ማእዘን « አጼ ቴዎድሮስ » ነው ። በዚህ ዜማ የጀግንነት ከፍታ ታይቶበታል ። የታሪኩ ባለቤት አጼ ቴዎድሮስ ለሀገራቸው ክብር በመቅደላ ተራራ ያደረጉት ተጋድሎ ተዘርዝሯል ። ቴዎድሮስ የተከፋፈለችውን ኢትዮጽያ አንድ ለማድረግ በተደረገው ትግል የአንድነት ምልክት ናቸው ። ለዛም ነው ድምጻዊው
 « ጎንደር ጎንደር የቴዎድሮስ ሀገር
   የአንዲት ኢትዮጽያ ዋልታና ማገር » የሚለው

ቴዎድሮስ በኢትዮጽያ የመሪዎች ታሪክ ልዩ ቦታ ያገኙትም የተከፋፈለች ወይም የተሸነፈች ሀገርን ላለማየት መስዋዐት በመሆናቸው ነው ። ከራስ በላይ ንፋስ የሚል መሪ በችግር ግዜ እጁን ይሰጣል ወይም ይሰደዳል እንጂ ራሱን አያጠፋም ። ድምጻዊው ይህን መስዋእትነት ያስተሳሰረው ከሰንደቅ ዓላማ እና ከቀጣይ መልዕክት ጋር ነው ።
   « ጨክኖ ካሳ ጋተና ኮሶ
     ሞተ ለአንድ ሀገር ባንዲራ ለብሶ »           
      
ቀጣዩ መልዕክትም የተላለፈው በባንዲራው ድልድይነት ነው ። ይህን ባንዲራ ማንሳት ብቻ ሳይሆን የተዳፈነውንም ጀግንነት በብዙሃኑ ላይ እንዲጋባ ይፈለጋል ። ሀገር ለመስራት ጀግኖች ያስፈልጋሉ ። የግኖችን ራእይ ተግባራዊ ለማድረግ የወራሾች ሚና ወሳኝ ይሆናል ። ወራሾች የሞተውን ጀግና በማሰብ ከማለቃቀስ ይልቅ የአሟሟቱን ሚና በመረዳት ላይ እንዲተጉ ይጠበቃል ። ይህን ግን እውን ለማድረግ ቀላል አይደለም ።
 « ግመሌን ላጠጣት ቀይ ባህር ተጉዤ

    አንድ ገመድ አጣው ልመልሳት ይዤ » የሚለው ስንኝ የአንድን ጠንካራ ወራሽ ስጋትና ተስፋ መቁረጥ በምሳሌ የሚያሳይ ነው ። የአጼ ቴዎድሮስን ህልም እውን ለማድረግ ወቅታዊው የፖለቲካ ምህዳር ጠባብ ቢሆንም መልእክት አደራሹ ከያኒ ግን የጋመ ፍላጎቱን ጾታ ሳይለይ ለማስተላለፍ ‹ ሹሩባ › የሚለው ቃል የተመቸው ይመስለኛል ።
  « አንጡ ቆርጣችሁ ከሹሩባው ላይ
    ኪታብ እንሰር እንዳንለያይ »

የትሪያንግሉ ሶስተኛው ማእዘን « ማር እስከ » ይሰኛል ። ሙዚቃው የተመሰረተው የፍቅር እስከ መቃብር ድርሰት ላይ ነው ። ይህ መጽሀፍ በእንግሊዘኛ የመተርጎም እድል ቢያጋጥመው ኖሮ ዓለም ‹ የድርሰት ሉሲ › በኢትዮጵያ ተገኘ ማለቱ ባልቀረ ነበር ።
ቴዲ ይህን ትልቅ መጽሀፍ እንደገዘፈ ለማቅረብ ሞክሯል ። ገጸባህሪያቱን አሳይቶናል ። በተለይ ተፈቃሪዋ ሰብለ ወንጌል መልከ ብዙ ሆና ተስላለች - ብራና ፣ ንብ እና ማር ። ብራና ሆና የፍቅር መወድስ እናነብባታለን ። ንብ ሆና በአንድ በኩል ትጋትዋን በሌላ በኩል የጥቂት አመታት እድሜዋን እንዲሁም ማር ሆና ጣፋጭነትዋን በተለዋጭ ዘይቤ እንመለከታለን ። ይህን ውብ ቋንቋ ቅኔያዊ በሆነ መስተጋብር እያስተሳሰረ አቅርቦታል ።

 « ላሳደገኝ ደብር የስለት ልጅ ሆኜ
   ካህን እንዴት ይፍታኝ ያንቺ እስረኛ ሆኜ
   ማር ጧፍ ሆኖ ገባ - ከመቅደስ
   ነዶ ለኔ ጸሎት ሊያደርስ  »

ቢጫ ለብሳ ገዳም የገባችውን ሴት መንጥቆ ለማውጣት የሚደረገው  ትግል ጠንካራ ነው ። ሆኖም የቱንም ያህል አዋቂ ቢኮን ፍቅር አንበርካኪ መሆኑን እንረዳለን ።

  « ለካ ሰው አይድንም በደገመው መጽሀፍ
    እንደ ሰም አቅልጦ ፍቅር ካደረገው ፍ »         
የቴዲን ትሪያንግል እንደ ጋሪ ለመግፋት ብንፈልግ አራት ጎማዎች ያስፈልጉናል ። ሰምበሬ ፣ አና ንያቱ ፣ ያምራል እና ኦላን ይዞ በአቀራረብ ስልታቸውና ሳቢነታቸው የእኔ ምርጫዎች ናቸው ።           
 ኦላን ይዤ አላፍርም ይህን አውቃለሁ
 ወደ ፍቅር ልሂድ ምን እጠብቃለሁ
 ወደ ፍቅር ጉዞ ተያይዞ
 ቂምን ከሆድ ሽሮ
 ኦላን ይዞ …