Thursday, May 29, 2014

ማቋረጥ

                                      

                   . ልቦለድ ቢጤ

መምህር ተሻለ አዲስ አበባ ውስጥ አለ በሚባለው ትምህርት ቤት ውስጥ የአማርኛ መምህር ነው ። ለሁለት ሰዓታት የነበረውን እረፍት ከጓደኞቹ ጋር ቼዝ ሲጫወት ቆይቶ ፔሬዱ ሲደርስ ወደሚያስተምርበት ክፍል እየተጣደፈ ሲጓዝ ነበር ድንገት ከኌላው በዳይሬክተሩ አቶ ዘሩ የተጠራው
<< የት ክፍል እየገባህ ነው ? >>
<< ስድስተኛ ቢ ነኝ - ምነው ፈለጉኝ እንዴ ? >>
<< እንግዶቹ ቤተመጻህፍቱንና ላቦራቶሪ ክፍሉን ጎብኝተው ጨርሰዋል >>
<< እንዴ እስካሁን ከዚህ ግቢ አልወጡም ? >> አለ ተሻለ በግርምት
<< አዎ አኔ ቢሮ ብዙ ስለቆዩ ነው ። ሪፖርቴን ጣፋጭ በሆነ መልኩ አቅርቤያለሁ ። ምቀኞች ደካማ ነው እያሉ የሚያሰወሩትን የትምህርት ጥራት መገምገም ስለፈለጉ ተግባራዊውን ነገርም ማየት ፈልገዋል ። ዛሬ ርዕሰ ጉዳይህ ምንድነው ? >> ዳይሬክተሩ እየተጣደፉ ነው የሚያወሩት ።
<< ቃላት ፣ የቃላት እርባታና የቃላት አረዳድ የሚል ነው ። በተጨማሪም ... >>
<< ኡ ? ... ምነው ተሻለ ? ምንድነው ዲሪቶ አደረከው እኮ ? >>
<< ተማሪዎች አንድን ተመሳሳይ ቃል እንዴት እንደሚተረጉሙትና በምሳሌም እንዴት እንደሚያስደግፉት የሚታይበት በመሆኑ የአረዳድ ማዕዘናቸውን የሚያሰፉበት ነው >>
<< ጥሩ ... ጥሩ ... ዘዴው ምንድነው ? ማለቴ የምታስተምርበት ? >> አሉ ግራና ቀኝ እየተገላመጡ
<< ተማሪዎች ቃሉን ከሶስት ቀናት በፊት ስለወሰዱ ያዩበትን መንገድ ሰምተን ወደ አጠቃላዩ ትምህርት ነው የምንደረደረው >>
<< አደራ እንግዲህ ? ... >> ዳይሬክተሩ ሀሳባቸውን ሳይቋጩ እንግዶቹን ወዳዩበት አቅጣጫ በሩጫ ተፈተለኩ ።
ሃላፊ ሆኖ የመርበትበትና ሃላፊ ሆኖ የመኮፈስ መንታ ገጽታዎች ሽንት ቤት ገብቶ አሜባን ማማጥና ከግልግል በኌላ ፈገግ ብሎ ቀበቶን ከማሰር ጋር እንዴት እንደተመሳሰለበት አላወቀም - ግን ያለቦታው ይህን ምሳሌ ነበር ሲያነጻጽር የነበረው ። ወደመሬት ወድቄ እምቦጭ እላለሁ የሚል የሚመስለውን ቦርጭ በአንድ እጅ ፣ ወዲህና ወዲያ የሚወራጨውን ካራቫት በሌላ እጃቸው ይዘው በዚህን ያህል ፍጥነት መሮጣቸውም በአስገራሚ መልኩ ፈገግታ ጭሮበታል ።
ለመምህር ተሻለ የማስተማር ስልት መሰረት የሆነው ቢቢሲ የተባለው መገናኛ ብዙሃን ነው ። ይህ ጣቢያ በቀጣዩ ሳምንታት የሚያቀርባቸውን አንኳር ጉዳዮች አስቀድሞ ነው የሚያስተዋውቀው ። ተማሪዎችም ቀጣዩን ምዕራፍ አስቀድመው ካወቁ መደናገርን አስወግደው ተሳታፊና እንደ ካራ ስል ይሆናሉ የሚል እምነት አለው ። ይህ ስልት ከፍተኛ ባለስልጣን ፣ ሀብታሞችና ታዋቂ ሰዎች ልጆቻቸውን በሚያስተምሩበት በዚህ ትምህርት ቤት በሁሉም መምህራን እንደ ቋሚ አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን በተለያዩ ግዜያት በተካሄዱ ስብሰባዎች ላይ እስከመናገር ደርሷል ። የማስተማሪያ መንገድንና የፈተና አወጣጥ ዘዴን ደብቅ እያደረግን የትምህርት ጥራትን ከፍ ለማድረግ መሞከር ከንቱ ምኞት ነው የሚል ሀሳብም አለው ።
የስድስተኛ ቢ በር ድንገት ተበርግዶ በርካታ የሀገሪቱ ባለስልጣናት ተግተልትለው ወደ ውስጥ ሲገቡ ተማሪዎቹ እንግዶቹን ቆመው ተቀበሏቸው ። እንግዶቹ ክፍት በተደረገው አንደኛው ጠርዝ ከተቀመጡ በኌላ መምህር ተሻለ ሞቅ ያለ ሰላምታ አቅርቦ ማስተማሩን ቀጠለ ።
<< እሺ ተማሪዎች ሁላችሁም እንደምታውቁት የዛሬው ክፍለ ግዜ የቃላት አረዳድ ላይ የተመሰረተ ነው ። እስኪ ዋነኛ ቃሉን የሚያስታውሰኝ ማነው ? >>
<< አቋረጠ >> አለ በላይ የተባለው የክፍሉ አለቃ ተሽቀዳድሞ ፤ እንደስሙ ሁሌም የበላይ መሆን አለብኝ ብሎ ስለሚያስብ ለብዙ ነገሮች ደንታ የለውም ።
<< ልክ ነው አቋረጠ ሲረባ ማቋረጥ ፣ ያቋርጣል ፣ አቋራጭ ፣ ያቆራርጣል ወዘተ እያለ ይቀጥላል ። ለመሆኑ አቋረጠ ምንድነው ? እንዴት ተረዳችሁት የሚል ነበር የቤት ስራው ? >>
<< እሺ መስፍን >> አለ መምህር ተሻለ እጅ ካወጡት ውስጥ ለአንደኛው እድል እየሰጠ
<< አቋረጠ ማለት የቀለበት መንገድ አጥርን ዘለለ ማለት ነው ። ሰዎች ብረቱን የሚያቋርጡት በቅርበት መሸጋገሪያ ድልድይ ስለማይሰራላቸው ነው ። ሆኖም ብዙ ሰዎች ቶሎ እንደርሳለን ብለው ሲዘሉ በመኪና አደጋ እስከመቼውም ሳይደርሱ ቀርተዋል ። የመኪና አደጋ አሰከፊ ነው >> አለ ተማሪው የሀዘን ገጽታ እያሳየ ።
<< የማን ልጅ ነህ መስፍን ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር በፈገግታ
<< የኢንጂነር ፈቃዱ >> ባለስልጣናቱ በአግርሞት ሳቅ አውካኩ
<< በመንፈስ ደግሞ የሳጅን አሰፋ ... >> አሉ ጥግ ላይ የተቀመጡት የፖሊስ ኮሚሽነሩ ፤ ቤቱ እንደገና በሳቅ ተንጫጫ ።
<< እሺ አያሌው ? >> ሳቁ እየሰከነ ሲመጣ መምህር ተሻለ ሁለተኛውን ተጠያቂ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የቀበሮ ማቋረጥ ነው ። ሰዎች ለውጊያ ሲሄዱ ቀበሮ መንገዱን ካቋረጠቻቸው ይሸነፋሉ ። አጼ ቴዎድሮስም ሆኑ አጼ ሚኒሊክ በዚህ እንደሚያምኑ አያቴ አጫውተውኛል >> አለና ቁጭ አለ ። መምህር ተሻለ ፊት ላይ መደናገጥ ቢታይም ባለስልጣናቱ ከመሳቅ የገደባቸው ነገር አልነበረም ።
<< አያሌው አያትህ ማናቸው ? >> አሉ አሁንም አንደኛው ሚኒስትር እንደዘበት
<< ቀኛዝማች ነቅአጥበብ ....  >>
ወደ መሃል ቁጭ ያለ አንድ ባለስልጣን የተማሪውን ሀሳብ አቋርጦ << እነ ፊታውራሪና ቀኛዝማች አሁንም ሄደው ሄደው አላለቁም እንዴ ? >> ከማለቱ ቤቱ በእንባ ቀረሽ ሳቅ ተበጠበጠ ። መምህር ተሻለ የውሸት ፈገግታ እየታየበት ቀጣዩን ተማሪ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የማራቶን ሩጫን ማቆም ማለት ነው ። ሩጫውን የሚያቆሙት ወንዶች ናቸው ። ወንዶች ሩጫውን የሚያቋርጡት በሴት ሰዓት ላለመግባት ነው ። የአባቴ ስም አሰልጣኝ ቶሎሳ ይባላል >>
የስድስተኛ ቢ ክፍል ኮርኒስ በሳቅ ወላፈን የእሳት ጢስ የፈጠረ መሰለ ። ሳቁን ያባባሰው ተማሪው አይቀርልኝም ብሎ ከወዲሁ  የአባቱን ስም ማስተዋወቁ ነበር ።
<< ማነህ ስምህ ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ወደተናጋሪው ተማሪ እየተመለከቱ
<< ዘላለም >>
<< ዘላለም  እኔ እንኳን የአባትህ ስም ቱርቦ ቱሞ ይሆናል ብዬ ጠብቄ ነበር >> አሉ ቀድመው እየሳቁ
<< እንዴ አያውቁም እንዴ ? እሱ እኮ ሞቷል - በጣም ጎበዝ አትሌት ነበር ። የሞተውም ተማሪ መስፍን እንዳለው በመኪና አደጋ ነው ። በመኪና አደጋ ላይ ብዙ መሰራት አለበት >> አለ ተማሪው ፈርጠም ብሎ
<< በእውነት የተማሪዎችህ የአመላለስ ስርዓት ጥሩ ነው ። በተለይ ጥሩ ነው ያልኩት በጣም ግልጽ ከመሆናቸው አንጻር ነው ። ይህ ባህሪ ነው እያደገ መውጣት ያለበት ። አንድን ጉዳይ የሚያዩበት መንገድም እንደሀገራችን ብሄር ብሄረሰቦች የሰፋና የሚያምር ነው ። የመሰላቸውን የመናገር ነጻነትም እንዳላቸው መረዳት ይቻላል ... >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ስሜታቸውን መቆጣጠር እያቃታቸው ።
ተማሪዎች እንደ ማዕበል በሚንጠው የሳቅ ጎርፍ ሳይናጡ እጃቸውን ለተሳትፎ በጉጉት ከማውጣት አልተቆጠቡም ። በምስጋናው የተነቃቃው መምህር ተሻለ ለመጀመሪያ ግዜ የሴት እጅ በማየቱ ተሳትፎውን ለማሰባጠር የመናገር እድሉን ትእግስት ለተባለች ተማሪ ሰጣት
<< አቋረጠ ማለት ንግግር አቋረጠ ማለት ነው ። ንግግር የሚያቋርጠው ደግሞ አበበ ገላው የተባለ ሰው ነው ። አበበ ገላው የጠላውንም ሆነ የወደደውን ሰው ንግግር ያቋርጣል ። አበበ ያቋረጠው ሰው የሀገር ውስጥ ስሪት ከሆነ ሰውየው ይሞታል ። ለምሳሌ ያህል ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ። አበበ ያቋረጠው ሰው የውጭ ሀገር ስሪት ከሆነ ሰውየው አይሞትም ። ለምሳሌ ያህል ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ >>
በሳቅ ሲታመስ የነበረው ክፍል በሚያስደነግጥ ጸጥታ ተወጣጠረ ። የባለስልጣናቱ ግንባር እንደ በረሃ መሬት እየተሰነጣጠቀ አስፈሪ የቦይ ምስል ሲፈጥር በግልጽ ይታያል  ። በግልባጭ በመምህር ተሻለና ዳይሬክተሩ ጆሮ ግንድ ስር መነሻውን አናት ያደረገ የላብ ጎርፍ ወደታችኛው የሰውነት ክፍሎች ደለል እየጠራረገ በፍጥነት ያሽቆለቁል ነበር ።
<< ምን እየተካሄደ ነው አቶ ዘሩ ?! ትምህርታዊ ኩዴታ እያደረጋችሁ ነው ! >> ተቀዳሚው ሚኒስትር ከወንበራቸው ተነስተው  ጸጥታውን በረጋገዱት
<< በእውነት አይን ያወጣና የተቀነባበረ የሽብር ተግባር ይመስላል ! >> ቃለ አቀባዩ እንደ ነብር ገሰሉ
<< በጣም ይቅርታ እጠይቃለሁ ። ምሳሌዎቹ በዚህ መልኩ ይቀርባሉ ብዬ አልጠበኩም ። የትምህርት ማቋረጥ ፣ የጽንስ ማቋረጥ ፣ የመንገድ መቋረጥ ፣ የወንዝ ማቋረጥ የሚኖራቸውን ተጽዕኖ አጉልቶ በማውጣት ... >>
<< ዝም በል አንተ ! ራስህ አቋርጥ ! ... ንግግርህን አቋርጥ ! ... >> የፖሊስ ኮሚሽነሩ ሌባ ጣታቸውን ቀስረው እየተንቀጠቀጡ የመምህር ተሻለን ቀልብ ገፈፉት ። ተክዘው የቆዩት አንደኛው ሚኒስትር ጣልቃ ገብተው <<  ያሳዝናል ! በተለይ ከዚህ ትምህርት ቤት ይህን የመሰለ ተራ አሉባልታ መስማት ያሳፍራል ... ትዕግስት ለመሆኑ የማን ልጅ ነሽ ? >> ሲሉ ለስለስ ባለ ድምጽ ጠየቋት
<< የአበበ >> አለች ልጅቱ ፈራ ተባ እያለች
<< የአበበ ? >> አንደኛው ሚኒስትር አንዴ ልጅቱን ሌላ ግዜ ባለስልጣናቱን እያፈራረቁ ተመለከቱ
<< የቱ አበበ ?! >> አሉ በመገረምም በመኮሳተርም
<< የአበበ ገላው እኮ አይደለም ! የጄኔራል አበበ ... >> የክፍሉ አለቃ በላይ ነበር ጣልቃ ገብቶ የመለሰላት ፤ ትዕግስት ጭንቅላቷን  አወዛወዘች
አንደኛው ሚኒስትር ተጨማሪ አስተያየት ሳይሰጡ ከክፍሉ ሲወጡ ባለስልጣናቱም እየተጣደፉ አጀቧቸው ። ፖሊስ ኮሚሽነሩና አንድ የደህንነት ባለስልጣን የአቶ ዘሩንና የመምህር ተሻለን ክንድ እንደ ምርኩዝ ተጠቅመው ተከተሉ ። የክፍሉ አለቃ በላይ እየሮጠ በሩን ከፍቶ የእንግዶቹን መራቅ ካረጋገጠ በኌላ ጥቁር ሰሌዳው ላይ << ማቋረጥ >> ሲል በትልቁ ጻፈ ። የክፍሉን ግራና ቀኝ ካሰተዋለ በኌላ
<< ቃሉ ማቋረጥ ቢሆንም እኛ እንቀጥላለን - ተጨማሪ ሃሳብ ያለው አለ  ? >> ሲል እጁን ኪሱ ከቶ ጠየቀ ። ዘላለም እጁን አወጣ
<< እሺ ዘላለም >>
<< ማቋረጥ ማለት የመምህር ተሻለን ትምህርት ማቋረጥ ነው >>
<< ትስማማላችሁ ? >>
<< በጣም ! በጣም ! ሰሌዳው ላይ ጻፈው ! ጻፈው ! >> ሲሉ ተንጫጫቡት ። በላይ የተነገረውን ጹሁፍ በትልቁ ጻፈው ። ቀጥሎ እጅ ያወጣችው ትዕግስት ነበረች
<< እሺ ትዕግስት ተጨማሪ ነው ? >>
<< ዋናው ጥያቄ የስድስተኛ ቢ የእውቀት ጉዞ ለምን በድንገት ተቋረጠ የሚለው ይመስለኛል ? >> ስትል ጥያቄ አዘል አስተያየት ወረወረች ። አለቃው የትዕግስትን ጥያቄ አሁንም ሰሌዳው ላይ አሰፈረው ።
<< እውነት የስድስተኛ ቢ የእውቀት ግጥሚያ ለምን ተቋረጠ ? >> ሲል የክፍሉ አለቃ እየንተጎራደደ ጠየቀ ። አያሌው እጅ በማውጣቱ እንዲናገር ተፈቀደለት ።
<< የእውቀቱ ጉዞ የተቋረጠው  ብዙ ቀበሮዎች ክፍላችንን ስላቋረጡት ነው ! ይህን አያቴ የነገሩኝ ሳይሆን አይኔ የተመለከተው ነው >> ሲል የክፍሉ ተማሪዎች በመልስ አሰጣጡ በሳቅ መንፈራፈር ጀመሩ ። አሳሳቃቸው የባለስልጣናቱን የሳቅ ከፍታ በልጦ መገኘትን ያለመ ይመስል ነበር ።
<< ምንድነው እንዲህ የሚያደርጋችሁ ... ?! >> የሚለው ደንገተኛ ድምጽ ከወደ በሩ ብቅ ብሎ የሳቁን ወላፈን በአንድ ግዜ ጤዛ አለበሰው ።
የነገር ሽታን የሚያነፈንፈው የደህንነቱ ሰው ኮሚሽነሩን አስከትሎ ወደ ክፍል ገባ ። ከዚያም የስድስተኛ ቢን ተማሪዎች ትምህርት ከጥቁር ሰሌዳው ላይ በቅደም ተከተል በጥንቃቄ ማንበብ ጀመረ ።
< ቀበሮዎች > የሚለው ቃል ጋ ሲደርስ ግን ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም ። የስድስተኛ ቢ ክፍል ተማሪዎች በባለስልጣኑ ድራማዊ ተግባር  ተገርመው ሳቁን ሊያጅቡት ቢገባም በፍጹም አልሳቁም ። በሚከብድ ጸጥታ የአሳሳቁን አይነት እየመረመሩና ቃሉን በነገር እያራቡ ነበር ። ከልቡ ሳቀ ... ከአንገት በላይ ሳቀ... እንደ ማሽላ ሳቀ...
ሳቀ ...
ይሳቅ ...
ስቆ...
አሳሳቆ ...

Monday, May 12, 2014

የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ?




ፖሊስ ረብሻንና ብጥብጥን ለማረጋጋት መጀመሪያ መጠቀም ያለበት ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርሱ በማይችሉ ነገሮች ነው ። ምክንያቱም ሰው የመኖር ፣ ከግርፋትና ሰብዓዊነት ከጎደለው አያያዝ የመጠበቅ መብት አለውና ። ለዚያም ነው ቆመጥ ፣ ውሃ ፣ አስለቃሽ ጋዝ ፣ የፕላስቲክ ጥይትና የመሳሰሉት በመጀመሪያ ረድፍ የግድ መታየት የሚኖርባቸው ።
በርግጥ እነዚህ ድርጊቶች በራሳቸው ጉዳት ሊያመጡ ስለሚችሉ ተግባራዊ ሲደረጉም ጥንቃቄና ሰብዓዊነት የተላበሰ መርህን ይፈልጋሉ ። ለምሳሌ ያህል ፖሊስ ዱላ ሲጠቀም በፍጹም ጭንቅላት ፣ አንገት ፣ አከርካሪ አጥንት ፣ ልብና ኩላሊት ላይ ማነጣጠር የለበትም ። የፕላስቲክ ጥይትም ቢሆን ከደረት በታች ባሉ የሰውነት ክፍሎች ላይ ነው ተግባራዊ መሆን ያለበት ። አስለቃሽ ጋዝም መጠኑና ደረጃው ከፍ እንዳይል ጥንቃቄ ይፈልጋል ።
የሀገራችን እውነታዎች ግን ለዚህ መርህ ጀርባቸውን የሰጡ መሆኑ ይታያል ። ፌዴራል ፖሊስ በአንድ ምት ጭጭ የሚያደርገውን ዱላውን በቀጥታ የሚሰነዝረው ለጭንቅላት ነው ። አጋጣሚ ሆኖ በሁለት ምክንያቶች ኢላማዎች ግባቸውን ይስታሉ ። አንዱ እንደ አይን ሁሉ የጭንቅላት አምላክ አትርፎህ ዱላው ጀርባህን እንደ ሙሴ ዘመን ባህር ይሰነጥቀዋል ። ሁለተኛው ራስህን ለመከላከል ወደላይ የሰነዘርከው እጅህ ተሰብሮም ቢሆን አንጎልህን ከመፈጥፈጥ ይታደገዋል ። በጣም የሚያሳቅቀው ግን አንዱ ፖሊስ መምታት ሲጀምር ሌላውም ሰልፍ ጠብቆ የጭካኔውን ደርሻ ማዋጣቱ ነው ። በሰብዓዊ ስሜት ተገፋፍቶ < እረ ይበቃዋል ? > ብሎ የሚከላከል አለመገኘቱ ሌላኛው አሳዛኝ ክስተት ነው ። ሰው ሬሳ እስኪሆን ድረስ እንደ እባብ መቀጥቀጥ ምን የሚባል ትምህርት እንደሆነ ግልጽ አይደለም ። ሰብዓዊው ህግ ብዙ ደም ለፈሰሰው የመጀመሪያ እርዳታ እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፈጠር እንዳለበት ሁሉ ያዛል ። በመሰረቱ እንደዚህ አይነት ክስተቶች የመሰረታዊ መብት ጥያቄዎች ግብግብ እንጂ ድንበር የመቁረስ ወይም ሀገር የማስገበር ጦርነት አይደለም ። በለየለት የሁለት ሀገር ጦርነት ላይ እንኳን የተማረከ ወታደር በቁጥጥር ስር ይውላል እንጂ ሰብዓዊና ሞራላዊ ህግን በመተላለፍ አይጨፈጨፍም ። ጀግኖች የሚቀጡህም ሆነ ጠማማ ካለብህ የሚያስተካክሉህ በማስተማር ነው ።
ለህይወት አስጊ የሆነው ተኩስ በአስገዳጅ ሁኔታ ተፈጻሚ ሊሆን የሚችለው በተለያዩ አጥጋቢ ምክንያቶች ነው ። ፖሊሱ ሁሉንም ስልቶች ውጤት አጥቶበት በተለይም ሁከቱ በህይወቱ ላይ አደጋ የሚያስከትልበት ከሆነ ራሱን ለመከላከል ፣ ሁከቱ የሌሎች ሰዎችን ህይወት ሊያጠፋ የሚችል ከሆነ ተመጣጣኝ ርምጃ ሊወስድ ይችላል ። ከረብሻና ተቃውሞ ዉጪም አንድ ወንጀለኛ ካመለጠ ሌሎችን ይጎዳል ተብሎ የሚታሰብ ከሆነ መሳሪያ ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል ።
ይህ ማለት ግን ከላይ የተቀመጡትን ምክንያቶች ሰበብ በማድረግ ፖሊስ ወይም የተደራጀው ሃይል ፍጹም ሊተካ የማይችለውን የሰው ልጅ ህይወት ይቀጥፋል ማለት አይደለም ። በተመድ ለፖሊስ የተዘጋጁ ደረጃቸውን የጠበቁ የስልጠና ማንዋሎች እንደሚያስረዱት እያንዳንዱ ፖሊስ ወደ ስራ ከመግባቱ በፊት በስልጠና ወቅት ራስን ስለመከላከል ፣ ስለ ሰብዓዊ አያያዝ ፣ ስለመጀመሪያ ርዳታ ፣ ስለተሰበሰበ ህዝብ ባህሪ ፣ ስለግጭት አፈታት ፣ ስለውጥረት አስተዳደር ወዘተ በቂ ትምህርት የሚያገኝ ቢሆን በችግር ግዜ አንድና አንድ ወደሆነው ግድያ ወይም የፈሪ ዱላ በፍጥነት አያመራም ። በስልጠና የበለጸገ እንዲሁም የሃላፊነቱ ሚና ከህዝባዊነት የመነጨ መሆኑን የሚገነዘብ ፖሊስ ቢያንስ በመጨረሻው ሰዓት ሲተኩስ እንኳ ወንጀለኛን ለመቆጣጠር እንጂ ነፍስን ለማቋረጥ አያልምም ። ጭንቅላት መምታት ነጥብ የሚያሰጠው በስልጠና ወቅት የተኩስ ሰሌዳ ላይ እንጂ የራስህ ቤተሰብና ወገንህ ተቸግሮ ተቃውሞ በሚያሰማበት ወይም ሁከት በሚፈጥርበት አንድ ቀን አይደለም ። ዞሮ ዞሮ ህዝብ ጠላት ሆኖ ስለማያውቅና ሊሆንም ስለማይችል እግሩን መምታትም ሲበዛበት ነው ።
አዲስ አበባንና በዙሪያዋ የሚገኙ የኦሮሚያ ከተሞችን በማካተት የተዘጋጀውን የጋራ ማስተር ፕላን በመቃወም በየቦታው የተቀሰቀሰው ቁጣ የብዙ ሰላማዊ ዜጎችን ህይወት በልቷል ። መንግስት የሟቾቹን ቁጥር 11 ቢልም ተቃዋሚ ድርጅቶች እስከ 45 ያደርሱታል - የውጭ መገናኛ ብዙሃን ደግሞ አስከ ሰላሳ ። የቁጥር ዝቅታና ከፍታ የሚመነጨው ኌላ የሚቀርበውን ዓለማቀፍ ስሞታና ክስ ታሳቢ ከማድረግ አንጻር ነው ። አነስተኛ ሰው ከሞተ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድኩት በማለት ቁጣን ለማርገብ ይቻላል ። የኢትዮጽያ መንግስት በዛ ያሉ መብት ጠያቂዎችን በአደባባይ የመግደል ልምድ ከግዜ ወደ ግዜ እያደበረ የመጣ ይመስላል ።
በምርጫ 97 ማግስት በተቀሰቀሰ ቀውስ የሰው ልጅ ክብር ህይወት በጥይት ሲረግፍ አቶ መለስ ዜናዊ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድነው በማለት መጠነኛ አሃዝ በመጥቀስ መግለጫ ሰጥተው ነበር ። ሆኖም ጉዳዩን እንዲያጣራ የተሰየመውና በአቶ ፍሬህይወት ሳሙኤል የሚመራው ቡድን << መንግስት ያልተመጣጠነ/ ከመጠን ያለፈ /  ርምጃ ወስዷል >> የሚል ያልተጠበቀ ሪፖርት አቀረበ ። በሪፖርቱ መሰረት 193 ሰዎች በጥይት ሲሞቱ 763 ያህል ቆስለው ነበር ። ሪፖርቱ ጓዳ የነበረን ራቁት ገላ ድንገት ለአደባባይ ያጋለጠ አውሎ ንፋስ ነበር ።
ተቃውሞ የሚበርደው ሰዎች ሲሞቱ ነው የሚለው ፍልስፍና ያልተለወጠ መሆኑም የዛሬው እውነታ እያሳበቀ ነው ።  በ1997 ግርግር አንዳንድ የአዲስ አበባና ፌዴራል ፖሊስ አባላት አጋዚ የተባለው ልዩ ጦር እንጂ እኛ ሰላማዊ ህዝብን አልገደለንም እያሉ ራሳቸውን ነጻ ሲያወጡ ነበር ። መጸጸቱ በራሱ ጥሩ ይመስለኛል - ግን ይህ አይነቱ ደመ ንጹህነት መሰዎዕትነት ለሚከፈልለው ሲቪል ማህበረሰብ ትርጉም አልባ ነው ። መደበኛው ፖሊስ የመግደል አማራጭን በመርህ ደረጀ የማይቀበል ከሆነ የገዳዩንም ጣልቃ ገብነት ማለዘብ የሚከብደው አይሆንም ። ምናልባት መቋቋም የማይችለው የአስገዳዩን ቀጭን ትዕዛዝ ከሆነ አላውቅም ። ዞሮ ዞሮ በኛ ሀገር ፖሊሲያዊም እንበለው አጋዚያዊ ቀመር የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ? ስንት ሰው ሲሞትና ስንት ሰው ሲቆስል ? ይህ ወለል ካልታወቀ እንዴት ነው < የወሰድኩት ርምጃ ተመጣጣኝ ነው > ማለት የሚደፈረው ? ግድያን ለማስቀረት መጣሩ ነው የሚሻለው ወይስ እየገደሉ በቁጥር ጅዋጅዌ መጫወት ?
የዛሬ የገደላ ዜና በሁላችንም የባንክ ደብተር ውስጥ የሚቀመጥ የቁጠባ ቦንድ ነው ። ይህን ኖት ነገ እያወጣን ስንመዝረው ውስጣችንን የሚሞላው ፍርሃት አፋችንን የሚሞላው ደም ነው ።
 እናም ነገ ያስፈራል ።
ውሃ ጠማኝ ፣ ደመወዝ አነሰኝ ፣ መሬቴን በህገወጥ መንገድ ተቀማሁ ፣ አስተዳደሩ ገለማኝ ብሎ ለተቃውሞ አደባባይ የሚወጣ ሰው ባልጠበቀው መልኩ ስሙ አሸብር ፣ ነውጤ ፣ ነፍጤ ተብሎ ቢቀየር እስር ቤት ሊያደርሰው ይችላል ።
ያስፈራል ።
የተቃውሞ ሰልፍ ድንገት ተደናቅፎ ግርግር ከፈጠረ ወይም ነፍሰጡሩ ተቃውሞ ድንገት ሜዳ ላይ ብሶታዊ ልጅ ቢገላገል ሊያስገድል ይችላል ።
በ2001 በወጣው የጸረ ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀጽ 21 << ናሙናዎችን የመስጠት ግዴታ >> ላይ ተጠርጣሪው ለምርመራ ፍቃደኛ ካልሆነ ፖሊስ አስፈላጊ የሆነ ተመጣጣኝ ሃይል ተጠቅሞ ከተጠርጣሪው ናሙና ሊወስድ ይችላል ይላል ። ተመጣጣኝ ሃይል  እዚህም ጋ አለች ።  እንግዲህ ሰውየው መረጃ አልሰጥም ብሎ ግግም ካለ ፖሊስ ገድሎትም ቢሆን ናሙና ይወስዳል ማለት ነው ? -  አያስቅም - ያስፈራል ።

           

Tuesday, May 6, 2014

እናትነት






ፍቅር - ቋንቋ - ቀንዲል ውበት

የልብ - የአንጀት - ጠሊቅ እውነት

እናትነት...                                                                                               

የደም ውህድ - ክፋይ ስጋ

የምጥ ስርፀት - የአጥንት ዋጋ ።


/ ለእናቴ የብርጓል ዘውዴ /