Sunday, August 25, 2013

የእምብርት ዘመን ሲሄድ የቂጥ ዘመን መጣ








‹‹ ምን ዓይነት ዘመን ነው  ዘመነ ዲሪቶ
አባቱን ያዘዋል  ልጁ ተጎልቶ ››

እያለ አቀንቅኗል ድምጻዊ ተሾመ ደምሴ ፡፡ ተሾመ ልማዳዊው ህግ ወይም ስርዓት ተጣርሷል የሚል ጭብጥ ለማስተላለፍ የሞከረ ይመስላል ፡፡ ዜማውን በምሳሌያዊ አነጋገር ለውጡ ብንባል

‹‹ዘመነ ግልንቢጥ
ውሻ ወደ ሰርዶ
አህያ ወደ ሊጥ ›› የሚባለውን ብሂል መጥቀሳችን አይቀሬ ነው ፡፡

በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ምን ዓይነት ዘመን መጣ ያሰኘው የሴቶቻችን አፈንጋጭ አለባበስ ነበር ፡፡ ዘንድሮ ዘመነ ግልንቢጥ የተባለው ደግሞ በወንዶች ጉዳይ ሆኗል ፡፡ ለመሆኑ እንዴት ነው አህያ ወደ ሊጥ የሄደው ? የሚለውን ጥያቄ ከመፈተሻችን በፊት ትንሽ ስለቀደመው እናውራ ፡፡

ስለሴቶቹ ...
መቼም ዘመኑን ሆን ብሎ የሚያጠና ሰው ቢኖር ስለ እያንዳንዱ ግዜና መጠሪያ ስለሚሆነው ጉዳይ ስያሜ አያጣለትም ፡፡ ለአብነት ያህል በ1997 አካባቢ ሴቶቻችን በታይት ተወረው ነበር ፡፡ ይህን ግዜ ‹‹ የታይት ዘመን ›› ብሎ መጥራት ይቻላል ፡፡ የዛኔ የዘፈን ውድድር አለመፈጠሩ እንጂ ለታይት ለባሾቻችን ‹‹ ቀይ ›› ፣ ‹‹ ቢጫ በቀይ ›› ‹‹ ሙሉ አረንጓዴ ›› እያልን ጥሩ ማነጻጸሪያ መስጠት በተቻለ ነበር ፡፡ ታይት የሰውነት ቅርጽንና ውበትን አጋልጦ የማሳየት ኃይሉ ከፍተኛ ስለነበር ራሳቸውን ‹‹ ለቁምነገር የሸጡ ›› ወጣቶችም ጥቂቶች አልነበሩም ፡፡

አንዳንድ ሴቶች ደግሞ ታይትን ያለ ግልገል ሱሪ በማጥለቅ በየጎዳናው የሚያለከልኩ ወንዶች እንዲበዙ አድርገዋል ፡፡ የነዚህኞቹ ግብ በወንዶች ላይ ‹ ሙድ › ይዞ መዝናናት ይሁን ወይም የግብዣ ማስታወቂያ መስራት በውል የሚታወቅ አልነበረም ፡፡ ለሚነሳባቸው የተጃመለ ትችትም ‹‹ መብታችን ነው ! ›› በማለት የተንዥረገገ ነገር ግን የማይበላ የወይን ፍሬ ነው የሚባልለትን ህገመንግስት ተደግፈው የሚያወሩ ሴቶች ጥቂቶች እንዳልነበሩ እናስታውሳለን ፡፡ ህገመንግስቱ እንኳን የማስልበስን ራሱ የመገንጠልን ካባ በመከናነቡ አያስገርመንም የሚሉ አሽሟጣጮች በበኩላቸው የትራክተር ጎማ የሚያህል መቀመጫ ያላት ሴት በታይት ተወጣጥራ ስትንከባለል እያየን ላለማሳፈር መጣር ከጨዋነት አያስቆጥርም ይሉ ነበር ፡፡ ድርጊቱ የሳቅ ቧንቧን ቷ ! አድርጎ በመክፈቱ በየቦታው አይንና አፍን በመሸፈን የሚንፈቀፈቁ ሰዎች እንዲበራከቱ መንገድ ከፍቷልና ፡፡

ከዚህ ዘመን በኃላ ደግሞ አጭር ቀሚስ የፋሽን መገለጫ ሆኖ መጣ ፡፡ በርግጥ አጭር ቀሚስ ከማለት ይልቅ መሃሉ የተከፈተ ቁምጣ ማለት እውነቱን ቀረብ ያደርገዋል ፡፡ ሴቶቹ ቁጭ ሲሉ ገላቸውን ላለማሳየት ያቺን ምላስ የምታህል ጨርቅ በግድ ሊያረዝሟት ሲታገሉ ማየት ያስቃል ፡፡ ‹ ለምን ለበሱት - ለምን ይጨነቃሉ ? › የሚል ገረሜታ አእምሮን ይወራል ፡፡ የሴቶችን ፍላጎት ጠንቅቀን እናውቃለን የሚሉ ሴት አውሎች ግን በለበሱት ለመጨናነቅ ፣ ለማፈር ፣ የይቅርታ ፊት ለማሳየት መሞከር ሁሉ ድምር ውጤቱ ‹ ሆን ተብሎ የሚተወን የትኩረት መሳቢያ ድራማ  › ነው ባይ ናቸው ፡፡ በርግጥ አጭር ቀሚስ ወዲህ ወዲያ ሲሄዱበት የሚያምር ከሆነ በመቀመጥ ግዜ ገላን ላለማጋለጥ ነጠላ ወይም ሻርብ ነገር እግር ላይ ጣል ማድረግ በተቻለ ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ግን ከስንት አንድ ናቸው ፡፡ ስለዚህ የአጭር ቀሚስ አላማ ከፋሽንነትም በላይ የሚሻገር ነው የሚሉ አስተያየት ሰጪዎችን ሀሳብ መናቅ የትም አያደርስም ፡፡  ዘንድሮ ይህ ድርጊት ተገልብጦ በመምጣቱ የጭን መጋለጥ ሴቶችን ‹ አያሰጋም › ፡፡ ሱሪያቸው ግን ከኃላ ሆን ተብሎ ያጠረ በመሆኑ ለምሳሌ ያህል ከታክሲ የሚወርዱ ሴቶች መቀመጫቸውን ላለማሳየት ከላይ የለበሱትን ልብስ እስኪቀደድ ድረስ ወደታች ይጎትቱታል ፡፡ እኛም ልብስ መቀየሪያ ክፍል የገባን ያህል ላለማሳፈር ይሁን ላለመሳቀቅ ፊታችንን እናዞራለን - በጨዋ ደንብ ፡፡ ከወረዱ በኃላ ደግሞ  ‹ ምን ያለበሰቸውን ሱሪ ለመልበስ ትታገላለች ! ›  በማለት እናብጠለጥላታለን - በሀሜት ደንብ ፡፡

ታይትንና አጭር ቀሚስን ተሻግሮ በአደባባይ ብቅ ያለው ሱሪም ቀሚስም አይደለም - እምብርት እንጂ ፡፡ እንኳን ከዘመነ ጭን ወደ ዘመነ እምብርት አሸጋገራችሁ - አልናቸው እህቶቻችንን ፡፡  እምብርትን አጋልጦ ለማሳየት መደበኛ ሱሪም ሆነ ታይት መጠቀም ይቻላል ፤ ከላይ ደግሞ አጭር አላባሽ ፡፡ እድሜያቸው 14 እና 15 ያልሞላቸው ህጻናት ፣ የደረሱ ወጣቶች ፣ ብዙ ልጆች ያፈሩ እናቶች ሳይቀሩ እምብርታቸውን በየአደባባዩ አሰጡት ፡፡ ለብዙ ወንዶች ትርጉሙ ግልጽ አልነበረም ፡፡

ሴቶቹ በደፈናው ‹‹ ፋራ አትሁኑ ! ፋሽን ነው ›› አሉ ፡፡ መነሻው ህንድ ይሁን ሱርማ ፤ ጥቅሙ ሀሴት ያምጣ ግርማ ልብ ያለ ግን አልነበረም ፡፡ ወንዶቹ ‹‹ ከፋሽኑ ጀርባ ምን አለ ? ›› በማለት ጠየቁ ፡፡ ይህ ጥያቄያቸው በተለይ ከውበት ጋ የተያያዘ ነበር ፡፡ ምክንያቱም ወንዶች ጸጉር ፣ አይን ፣ አንገት ፣ ጡት ፣ ዳሌ ፣ ሽንጥና ባት እያሉ ሊያዜሙ ፣ ሃሳባቸውን ሊገልጹ ወይም ሊጽፉ ይችላሉ ፡፡ እስካሁን ግን ‹‹ እምብርትሽ ›› ብሎ ያቀነቀነ ዘፋኝ ወይም የጻፈ ደራሲ ወይም ያደነቀ አፍቃሪ አልተሰማም ፡፡ ታዲያ የእምብርት ፋይዳ ምን ይሆን ? መባሉ ግድ ነው ፡፡ አንዳንድ ሴቶች እምብርታቸው ላይ ጉትቻ እስከማንጠልጠል በመድረሳቸው ወንዶቹ እንደሚከተለው አሾፉ ‹‹ እምብርት ምድር ቤት የሚገኝ ጆሮ ነው  እንዴ ? ›› ወይም ‹‹ ከላይኛው የጆሮ ገጽ የዞረ መሆኑ ነው ? ››
ስለ ወንዶቹ …

እነሆ ዘመኑ ተገልብጦ ሴቶች በወንዶች ድርጊት እያዘኑ አልፎ አልፎም እያስካኩም ይመስላል ፡፡ የሴቶቹ እምብርት ተረት ሆኖ የወንዶቹ ቂጥ ወቅታዊ ማፍጠጫ ጉዳይ ስለሆነ ፡፡ ምናለፋችሁ በከተማችን ‹‹ የሚዝረከረኩ ወንዶች ›› ተበትነዋል ፡፡  ‹ እረ ወንድ ልጅ ሴታ ሴት ሲሆን ያስጠላል ! › የሚሉ ቆነጃጅትና እማወራዎች በዝተዋል ፡፡ ‹ ልጆቻችን ምን እስኪሆኑ ነው የምንጠብቀው ? › በማለት በሴት እድሮችና ማህበሮች ላይ ጉዳዩ የመወያያ አጀንዳ እንዲሆን የጣሩ ሴቶች ሞልተዋል ፡፡ ‹ ግብረ ሶዶማዊያን በዛ እያሉ እግዚኦ የሚሉ የሃይማኖት ተቋማትና ጋዜጠኞች የወንዶችን ልብስ መጣል እንዴት ዝም ብለው ያያሉ ? › የሚሉ ተቆርቋሪ እህቶች ሰሚ ያጡ ይመስላሉ ፡፡

የሀገራችን ሴቶች ወንዶች ቀበቷቸውን እንዲያላሉ በህጋዊ መንገድ የሚጠይቁት በአንድ መንገድ ብቻ ነው  ፤ በምጥ ወቅት ፡፡ በርግጥ  በፍቅር ጨዋታ ወቅት የሚኖረውን ውልቂያ የትኛው ክፍል እንደምንመድብ ሳያስቸግርን አይቀርም ፡፡ ታዲያ ዛሬ በህገወጥ መንገድ ቀበቶ አላልቶ ፤ ሱሪውን ከወገቡ ቁልቁል አርቆ ፤ የውስጥ ሱሪውንና የቂጡን ቀዳዳዎች እያስጎበኘ ላይ ታች በሀገራዊ ኩራት የሚጓዘው ‹ ትንሽ - ትልቅ › አበዛዙ ቀላል አልሆነም ፡፡

ወደው አይስቁ አሁን ይመጣል ፡፡ አንዳንድ የውስጥ ሱሪዎች የተቀደዱና ውሃ ካያቸው ዘመናት ያስቆጠሩ ሊሆኑ ይችላሉ  ፡፡ አንዳንድ የውስጥ ሱሪዎች ደግሞ ገመዳቸው ላልቶ ነው መሰለኝ ወደ ውስጥ የሰመጡ ናቸው ፡፡ በተለያየ ምክንያት የሚጎነበሱ ፋሽነኞች ታዲያ የሚያስጎበኙት የተራቆተ መቀመጫ በንጽህ ወንድ / አፍቃሪ ግብረሶዶም እና እንስት ባልሆነ / ከታየ ለአይን የሚቆረቁር ፣ የመንፈስ ልዕልናና ክብርን ዝቅ የሚያደርግ ነው ፡፡ ምክንያቱም  የአንዳንድ ሰው ቂጥ በጎርፍ የተቆረሰ ደለል ይመስላል … የአንዳንድ ሰው ቂጥ በላብና እድፍ ተቦክቶ ልስን የሚጠብቅ ግድግዳ ይመስላል … የአንዳንድ ሰው ቂጥ ወፍጮ ቤት ከዋለ ፊት ጋር  አንድ ነው ፡፡

አሁን ደግሞ የማይገባዎትን ጥያቄ ይወረውራሉ ፡፡ ፋሽኑ ሱሪው ነው ? የላላው ቀበቶ ነው ? ፓንቱ ነው ? የፓንቱና ሱሪው ደረጃ ሰርቶ መታየቱ ነው ? ወይስ የሰውየው ቂጥ ? ከግርምት ፣ ትዝብትና ሳቅ በኃላ ለመሆኑ ምንድነው ዓላማው ? ወይም ፋሽን ተከታዮቹን ምን ያህል ያስደስታል ? ለማለት ይገደዳሉ ፡፡ አብዛኛው ፋሽን ተከታይ በጆሮ ፣ ጸጉር ፣ ጃኬት ፣ ቲሸርት ፣ ጫማ ወዘተ ላይ ሲታይ እንደቆየው የዘመናዊነት መገለጫ ሳያካብዱ መመልከት እንደሚገባ የሚያስገነዝቡ ናቸው ፡፡ ፋሽን ይመጣል ፋሽን ይሄዳል እንዲሉ … ለምን ይቅርብኝ  ወይም ከማን አንሳለሁ በሚል ድሃ መነሻ የማያምርባቸውን ብቻ ሳይሆን የማያውቁትን ነገር የሚከውኑ ወንዶችም ሴቶችም የሚታዘንላቸው ናቸው ፡፡ እነዚህ ምስኪኖች ከሚሆኑትና ከሚለብሱት ዉጪ ስለ ጉዳዩ  አነሳስና ከጀርባው ስለሚጠረጠረው ጉዳይ ለማሰብ ግዜ የሚወስዱ አይደሉም ፡፡ 
 አነሳሱ  ...
ሱሪን ከቂጥ በታች አውርዶ መልበስ የተጀመረው በአሜሪካ እስር ቤቶች ውስጥ ነው ፡፡ Sagging Pants ይሉታል ፡፡ እስረኞች ቀበቷቸውን ራሳቸውን ለመግደልና በሌሎች ላይ ወንጀል መስሪያ መሳሪያ ማድረጋቸው ስለተደረሰበት እንዳይጠቀሙ ታገደ ፡፡ በዚህም ምክንያት ሰፊ ቱታቸውን መቆጣጠር ባለመቻላቸው ሱሪያቸው ታች መውረዱ ግድ ሆነ ፡፡

የጀርባው ንባብ  ...

ይህ ‹‹ ፋሽን ›› በጥርጣሬ ጨጎጊቶች የተከበበ ነው ፡፡ አንዳንዶች በእስር ቤት ልብስን ዝቅ አድርጎ መልበስን የሚያገናኙት ከግብረ ሶዶማዊነት ተግባር ጋ ነው ፡፡ የወሲብ ግንኑነታቸው መጠቆሚያ ስልት ነው በማለት ፡፡ አንዳንዶች የእስር ቤት አስተሳሰብ መሆኑን በመግለጽ በተለይ ጥቁሮች ‹ አሁንም እስር ላይ ነን › የሚል መልዕክት ያስተላልፉበታል ይላሉ ፡፡ አንዳንድ ጉዳዩን ያጠኑ ምሁራን ደግሞ ‹‹ በአሜሪካ የባርነት ዘመን ነጭ አለቆች የአፍሪካን ጥቁር ወንዶች አስገድደው ይደፍሯቸዋል ፡፡ ተግባሩ ከተፈጸመ በኃላ ተጠቂው ሱሪውን ዝቅ አድርጎ እንዲለብስ ይደረጋል ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ አለቃው በቀጣይነትም ግንኙነት መፈጸም ሲፈልግ በቀላሉ እንዲለየው ነው ›› በማለት ቃላችን ርግጠኛ ነው ሲሉ ይደመጣሉ ፡፡ ግራም ነፈሰ ቀኝ በ 1990ዎቹ አካባቢ የሂፕ ሆፕ አርቲስቶች ሱሪን አውርዶ መልበስን በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ሚና መጫወታቸው ብዙዎችን ያስማማል ፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ባህልና ፋሽንን ከመግለጽ በተጨማሪ የነጻነት ማሳያም እንደሆነ ይጠቆማል ፡፡

በዚህ እሳቤ የኛዎቹ ፋሽን ተከታዮች ምን መልዕክት እያስተላለፉ መሆኑ ግራ ያጋባል ፡፡ በርግጥ በሀገራችን ግብረሰዶማዊነት እየተስፋፋ መሆኑ ይታወቃል ፡፡ የሱሪው መውረድ ሰምና ወርቅ ፋሽንና ያልተለመደ ወሲባዊ ግንኙነትን እያመላከተ ይሆን ?  ግብረ ሰዶማዊያን ለመግባቢያነት ይረዳቸው ዘንድ ጆሮአቸው ላይ ጌጥ ያደርጋሉ ፤ ሱሪ አውርደው ከሚፏልሉት ወገኖቻችን ገሚሶቹም ጆሮአቸውን ማስዋብ ይወዳሉ ፡፡ ግብረ ሰዶማዊያን  አንድ ጆሮ ላይ ጌጥ ካደረጉ ‹ አልተያዝኩም › ማለት ፈልገው ነው ፤ ሱሪ አውራጆቻችንስ ‹ አልተያዝኩም › ነው ወይስ  ‹ የማውቀው ነገር የለም ›  እያሉ  ነው የሚገኙት ፡፡ ሀገራችን እንደ ሌሎች አፍሪካዊያን ቅኝ ያልተገዛችና የባርነት ቀንበር ያልቀፈደዳት ቢሆንም ከሀገራዊ ባርነት መቼ ተላቀን እያሉበት ይሆን ? ነው አለማቀፉን ምልከታ ያልተረዳ ተራ የፋሽን ጉዳይ ?

ያን ግሩም ሙዚቀኛ ‹ ተቀበል ! › ማለት አሁን ነበር ፡፡
አቦ ተቀበል ! አፈሩ ይቅለልህና
‹ እሺ ልቀበል ! › …
‹‹ ምን ዓይነት ዘመን ነው በል ! ››
‹ ምን አይነት ዘመን ነው › …
‹‹ ምን አይነት ዘመን ነው - ዘመነ ዥንጉርጉር
 በምናገባኝ ቅኝት በኬሬዳሽ መዝሙር
 እንደሰጡት ሆኖ እንዳጣው የሚያድር
 አይገደውም ከቶ
 ‹ አይገደውም ከቶ › …
ለማያውቀው አንቀጽ ውል አጥብቆ ሲያስር
 በእውር ፈረስ ጀርባ ሽምጥ ሲኮረኩር ››
በልልኝ አቦ !!
 በእውር ፈረስ ጀርባ ሽምጥ ሲኮረኩር › …


ማስታወሻ፡- ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ቅፅ 12 ቁጥር 159 ላይ የወጣ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡



Tuesday, August 13, 2013

የአቅጣጫ ለውጥ --- በማህበራዊ ሚዲያዎች ?




ታይም መጽሄት ፡፡

የፌስ ቡክ መስራች የሆነውን ማርክ ዙከርበርግን የ2010 የአመቱ ምርጥ ሰው በማለት ሰየመ ፡፡
የመጽሄቱ ውዳሴ ፡፡

ለፌስ ቡክ  --

‹‹ በአሁኑ ወቅት ከምድራችን ሶስተኛው ትልቅ ሀገር ነው ፡፡ በርግጠኝነትም ለዜጎቹ ከሌላው መንግስት በተሻለ መረችን ይሰጣል ››

ለማርክ ዙከርበርግ  --  


‹‹ ከሃርቫርድ ትምህርቱን ያቋረጠው ይህ ወጣት ቲሸርት የሚለብስ የሀገሪቱ ርዕሰ ብሄር ነው ››

››››                               ››››                                    ›››››                                  ››››

አንጋፋውና ታዋቂው መጽሄት ታይም ብዙዎችን ያስደመመውን ፈጠራና ፈጣሪ በዚህ መልኩ ቢያደንቀውም አትዮጽያን ጨምሮ በርካታ ሀገሮች ፌስ ቡክንና ማህበራዊ ሚዲያን የሚመለከቱት በታላቅ ጥርጣሬና ስጋት ነው ፡፡

በርግጥ ስጋቱ ከዘርፈ ብዙ አስተሳሰቦች የሚመነጭ ነው ፡፡ በዋናነት ግን የፖለቲካ አለመረጋጋት እንዲፈጠር ፣ ብሄርና ጎሳ ተኮር ግጭቶች እንዲጫሩ ፣ አክራሪ ሃይማኖታዊ አጀንዳዎች ስር እንዲሰዱ መንገድ ይከፍታል የሚሉት ሊጠቀሱ ይችላሉ ፡፡ ወረድ ሲባልም የግለሰቦች መብት ሊጣስ ፣ የስራ ባህል ሊዳከም ፣ ምርታማነት ሊያሽቆለቁል ይችላል የሚሉ መከራከሪያዎች ይቀርቡበታል ፡፡

በቴክኖሎጂው ዙሪያ የወፈረ ቅሬታ ያላቸው ሀገሮች በአብዛኛው ራሳቸውን ከሂደቱ ውስጥ ለማውጣት ግን የሚደፍሩ አይደሉም ፡፡ አካሄዳቸው አገም ጠቀም አይነት ነው ፡፡ ከቴክኖሎጂው መሸሽ እንደማይቻል ሁሉ ለዓለም ስል ትችትም ራስን አጋልጦ ላለመስጠት ሂደቱን በስሱ ወይም ለራሳቸው በሚመቻቸው መልኩ ያከናውኑታል ፡፡

እገዳ
 
‹‹ Nigeria Good People Great Nation ›› በሚል ርዕስ የሚጽፈው ብሎገር አማኑኤል አጁቡሉ የማህበራዊ ሚዲያ ቀበኛ ሀገሮችን ዘርዝሮ ጽፏል ፡፡ ፌስ ቡክ ፣ ዩቲዩብ ፣ ትዊተር እና ዊኪፒዲያን በመዝጋት ቻይናን የሚያህል የለም ሲል ያደረገቸውን ሚዛናዊነትንም ለመግለጽ በመሞከር ነው ፡፡ ቻይና ሚዲያዎቹን የዘጋችው የምዕራቡን ዓለም ተጽዕኖ ለመቋቋም ሲሆን በተነጻጻሪ የራሷን ሳይበር ኢንዱስትሪ በመፍጠር ተደራሽነቷን አረጋግጣለች ፡፡ ለአብነት ያህል Ozone የተባለው ማህበራዊ ገጽ 600 ሚሊየን አባላት አሉት ፡፡ Weibo የተባለው ሌላኛው ድረ ገጽ የቻይናን መልክ መላበሱ እንጂ ልክ እንደ ትዊተር ነው የሚሰራው ፡፡

እንደ ናይጄሪያዊው አማኑኤል ሁሉ ፍሪደም ሀውስ የተባለው ድርጅት በ 2012 ያጠናው መረጃ ኢትዮጽያን የብሎገር ፎቢያ እንዳለባት ጠቋሚ ነው ፡፡ 65 የዜናና አስተያየት፣ 14 የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ 7 የድምጽና ምስል ዌብሳይቶች፣ 37 ብሎጎችና 37 የፌስ ቡክ ገጾች ተዘግተዋልና ፡፡

ኢትዮጽያና አለምን ሲያጨቃጭቅ የነበረ ሌላ ክስተትም መጨመር ይቻላል ፡፡ የተወካዮች ምክር ቤት ባጸደቀው አንድ ህግ በሀገሪቱ ውስጥ ስካይፒና ጎግል ቮይስን መጠቀም እስከ 15 ዓመታት እንደሚያሳስር ተገልጾ ነበር ፡፡ በሌላ በኩል መንግስት ስካይፒ መጠቀም ህገወጥ ድርጊት አለመሆኑን ፣ ህገወጥ የሚሆነው ህገወጥ ጥሪዎችን ማከናወን መሆኑን አስተባብሏል ፡፡ በተለይ ከዚህ አጨቃጫቂ ዜና በኃላ ሀገሪቱ ፌስ ቡክ ፣ ትዊተርና የመሳሰሉ ማህበራዊ ገጾችን ልትዘጋ እንደምትችል በስፋት ሲወራ ቆይቷል ፡፡ የኢህአዴግ አባላትም ከስብሰባ በኃላ ፌስ ቡክ ላይ የተጣዱ ሰራተኞችን በመታዘብ ‹‹ ግድየም ለጥቂት ግዜ ተመልከቱ ?! ›› በማለት ጉዳዩ እያበቃለት መሆኑን ያረዱ ነበር ፡፡

ፌስ ቡክ በተለይም ከአቶ መለስ ዜናዊ ሞት በኃላ ብዙ የድርጅቱ ደጋፊዎችን አቁስሏል ፡፡ በአቶ መለስ ሞት ህልፈት ኢትዮጽያዊ ብቻ ሳይሆን ዓለም ማዘን ይገባዋል ብለው ራሳቸውን በማሳመናቸው በሳቸው ላይ ይሰጥ የነበረውን ትችት ባለመቀበል ይህን የአሉባልታ ማናፈሻ ማሽን ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ መከርቸም እንደሚገባ በትንሹም ሆነ በትልቅ ስብሰባ ላይ አጠንክረው አስተያየት ሰጥተዋል ፡፡ በፌስቡክ ላይ የተማረሩ አንዳንድ መ/ቤቶች ሚዲያው እንዲዘጋ ያደረጉ ሲሆን በምሳ ሰዓት ብቻ መጠቀም የሚቻልበትን መንገድ ያመቻቹም ድርጅቶቸች አሉ ፡፡ የወረደ አፈጻጸም አሳይተዋል የተባሉ አንዳንድ ሰራተኞችም    ‹‹ ፌስ ቡክን በማባረር ቢሆን አንደኛ ነህ ! ›› የሚል ግምገማዊ ፌዝ ተቀብለዋል ፡፡ የኢንተርኔት መስመር ለመዘርጋት ያቀዱ አንዳንዶች ደግሞ በፌስ ቡክ ተጠቃሚዎች እንዳንወረር በሚል ስጋት እቅዳቸውን አዘግይተውታል ፡፡ በተለይም እንደ ሀገራችን በምግብ እህል ራሳቸውን ያልቻሉ ታዳጊ ሀገሮች ልማትን እንጂ ፌስ ቡክንና ግብረ አበሮቹን በፍጹም ማስቀደም እንደሌለባቸው  የሚያስረዱ ምሁራዊ ጥናቶችም እዚህና እዚያ ቀርበዋል ፡፡ በዚህና በመሳሰሉ ምክንያቶች መንግስት ፌስ ቡክን ከርችሞ ስሙን ከነፓኪስታን ፣ ኢራን ፣ ሶርያ ፣ ቱርክ ፣ ታይላንድና የመሳሰሉት ተርታ እንደሚያሰልፍ ብዙዎች እየጠበቁ ነበር ፡፡

ያልተጠበቀ ለውጥ
 
ታዲያ ምን ተፈጠረ ?
ታይም መጽሄት በ2010 ያደነቀውን ፌስ ቡክ ዛሬ የኢትዮጽያ መንግስት እንዴትና ለምን ሊቀበለው ቻለ ? ማለት እንዴት ሊሰራበት ፈለገ ?

በቅርቡ የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጸ/ቤት በፌደራል ደረጃ ለሚገኙ ኮሙኒኬተሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና ሰጥቶ ነበር ፡፡ በስልጠናው በርካታ ጥናታዊ ወረቀቶች የቀረቡ ቢሆንም በውይይት ጎልቶ የወጣው ‹‹ አዲሱና ማህበራዊ ሚዲያ እንደ ተግባቦት ዘዴ ›› የሚለው ምዕራፍ ነበር ፡፡ ይህ ወረቀት በአጭሩና በጥቅሉ ሚዲያው ችግር ቢኖርበትም ጥቅሙን አጠናክሮ ለገጽታ ግንባታ መስራት የማይሸሽና የግዜው አማራጭ መሆኑን አስረድቷል ፡፡ የኮሙኒኬተር ባለሙያዎች የመ/ቤታቸውን ተግባር ብቻ ሳይሆን አጨቃጫቂውን የአባይ ግድብ የተመለከቱ መረጃዎችን ማሰራጨት እንደሚገባቸውም ተመልክቶ ነበር ፡፡
የፌስ ቡክና ማህበራዊ ሚዲያ ጉዳይም ተወካዮች ም/ቤት ደርሶ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ግንዛቤ እንዲያገኙበት ተደርጓል ፡፡ ዲፕሎማትና የአለም አቀፍ ባለሙያ የሆኑት አምባሳደር ቶፊክ አብዱላሂም በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ‹‹ የግብጽ ወጣቶች ፌስ ቡክና ትዊተር በጣም ይጠቀማሉ ፡፡ ኢትዮጽያዊያን ከግብጻዊያን ጋር እነዚህን ሚዲያዎች በመጠቀም በአባይ ወንዝ ፍትሀዊ አጠቃቀም ላይ መወያየት አለብን ፡፡ ወጣቱና የተማረው ትውልድ የግብጽ ህዝብን ለማሳመን መነሳት አለበት ›› በማለት አቅጣጫ ጠቋሚ አስተያየት ሰጥተዋል ፡፡
ግራም ነፈሰ ቀኝ የመንግስት አቋም እየተቀየረ መጥቷል ፡፡ የአቅጣጫውን ለውጥ ያመነጨው አባይ ወይስ ነባራዊው እውነት የሚል መከራከሪያ ማንሳት ግን አሁንም ይፈቀዳል ፡፡ መንግስት ከማህበራዊ ሚዲያዎች ጋር ሙሉ ለሙሉ መጋባት ባይፈልግ እንኳ ከተጨባጩ እውነት ጋ አዛምዶ ፍላጎቱን ለማሳካት እንደ አጋር ሊጠቀምበት ግድ ይለዋል ብሎ ማስቀመጥ ይቻላል ፡፡

የማይሸሸው እውነት
 
በአሁኑ ወቅት ተለምዷዊ በሚባሉት ሚዲያዎች / ጋዜጣ ፣ ሬዲዮ፣ ቴሌቭዥን / ብቻ በመታገዝ ማንነትን ለዓለም ማስተዋወቅ አይቻልም ፡፡ ማህበራዊ ሚዲያን ለመጠቀም የሚያስገድዱ በርካታ እውነቶችን ቴክኖሎጂው እያቀበለን ይገኛል ፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት 751 ሚሊየን ህዝብ ሞባይል ይጠቀማል ፡፡ በ20 ደቂቃዎች አንድ ሚሊየን መረጃዎች ሼር ይደረጋሉ ፡፡ በ20 ደቂቃዎች ሁለት ሚሊየን 176 ሺህ መልዕክት ይላካል ፡፡ በ20 ደቂቃዎች 10 . 2 ሚሊየን እስተያየቶች ይጻፋሉ ፡፡ በ20 ደቂቃዎች አንድ ሚሊየን 484 ሺህ የሁነት ማስታወቂያዎች ይለጠፋሉ ፡፡

ይህን አሐዝ ወደ አህጉራችን ጠጋ አድርገን መመልከትም ይገባል ፡፡ እንደ ‹‹ The internet coaching library ›› መረጃ መሰረት በአፍሪካ ከኢንተርኔት አልፎ የፌስ ቡክ ተጠቃሚው ቁጥር በሚያስገርም ሁኔታ እየጨመረ መጥቷል ፡፡ በዚህ መሰረት ፣

ግብጽ - 12 ሚሊየን 173 ሺ 540
ናይጄሪያ - 6 ሚሊየን 630 ሺ 200
ደቡብ አፍሪካ - 6 ሚሊየን 269 ሺ 600 ፌስ ቡክ ተጠቃሚዋችን በማስመዝገብ ትልቁን ደረጃ ይዘዋል ፡፡ ሞሮኮ ፣ አልጄሪያና ቱኒዚያ በቀጣዩ ቅደም ተከተል ውስጥ የሚገኙ ሀገሮች ሲሆኑ ኢትዮጽያ በ 10 ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች ፡፡ 902 ሺ 440 በማስመዝገብ ፡፡

በአጠቃላይ ከሁለት መቶ በላይ ድረ ገጾችን ከምታስተናግደው ዓለም ርቆ ፖለቲካንም ሆነ መረጃን በሚፈለገው ልክ ማሰፋት አይሞከርም ፡፡ በተለይም 1 . 11 ቢሊየን ተጠቃሚ ካለው ፌስ ቡክ ፣ 500 ሚሊየን ተመልካች ካለው ትዊተር ፣ 225 ሚሊየን ከሚጎበኘው ሊንክደን ፣ 345 ሚሊየን ተመልካች ካለው ጎግል ፕላስ ቁርኝት አለመፍጠር የነገን መንገድ ካለማወቅ ጋር የሚገናኝ ነው ፡፡ እንግዲህ መንግስት እየቆየም ቢሆን በግድ መቆርጠም እንዳለበት የተረዳው እውነት ይህን ያህል ከድንጋይ የጠጠረ እንደሆነ መረዳት አይከብድም ፡፡

የመንግስት የቤት ስራ
 
‹ ወንድ ወደሽ ጺም ጠልተሸ አይሆንም › እንዲሉ ትግሬዎች ማህበራዊ ሚዲያዎችን ለገጽታ ግንባታ የመጠቀም ፍላጎት ካየለ ግራና ቀኙን ለመቀበል ዝግጁ መሆንን ይጠይቃል ፡፡ ቀኙ ከአዎንታዊ ውጤት ጋር የተያያዘ በመሆኑ የአደናቃፊነት ሚና ላይታይበት ይችላል ፡፡ ምናልባት የኮብል ስቶኑ መንገድ ካልተመቸ አስፋልት የማድረግ ስራ ይጠበቅ ይሆናል ፡፡ በርግጥ ማህበራዊ ሚዲያ ገጽታን ለመገንባት ፣ የገቢ ምንጭ ለማስፋት ፣ የሚዲያዎቻችንን ክፍተት ለመሙላት ፣ የዴሞክራሲና ስርዓቱን ለማጠናከር ፣ የገለሙ አሰራሮችን ለማጋለጥና ለመለወጥ ፣ የጦር ወንጀለኞችን ለማደን / ጆሴፍ ኮኒን ያስታውሷል / ፣ ምርጫን ፍትሃዊ ለማድረግም ሆነ ለማሸነፍ ፣ አምባገነኖችን ለመፈንገልና ለመሳሰሉ ጉዳዮች የላቀ ጥቅም ይሰጣል ፡፡

 ከላይ ለመጠቃቀስ እንደተሞከረው ጥቃቅኑ ችግር ገለል ሲደረግ ከስር አድፍጦ የሚገኘው ትልቁና ፖለቲካዊ ስጋቱ ወይም የግራ / ግራጋቢው / ክፍል ነው ፡፡ ማህበራዊ ሚዲያ በከፍተኛ ደረጃ የትግል መሳሪያ መሆን የጀመረው የ 26 ዓመቱ ቱኒዚያዊው ሞሀመድ ቦዋዚዝ መልካም አስተዳደር ማስፈን ያልቻለውን መንግስት ለመቃወም ራሱን በአደባባይ ካቃጠለ በኃላ ነበር ፡፡ እነዚህ ሚዲያዎች በአረብ አገራት ጭቆናና ኢ-ፍትሃዊ አሰራርን ለመዋጋት ትልቅ አስተዋጽኦ የፈጠሩ ናቸው ፡፡ በግብጽ፣ ቱኒዝያና የመን በመሳሰሉ ሀገሮች በርካታ የተቃውሞና የአመጽ ጥሪዎች ተቀናብረው የተሰራጩት በፌስ ቡክና ትዊተር ነው ፡፡ አንድ የግብጽ አክቲቪስት ‹‹ ፌስ ቡክን ለተቃውሞ ፣ ትዊተርን ለማስተባበር ዩትዩብን ደግሞ ለዓለም ለመንገርና ለማሳየት እንጠቀምበታለን ›› ማለቱን ማስታወስ ይጠቅማል ፡፡ 

በግብጽ የሚታየውን ተደጋጋሚ ትግል መነሻ በማድረግም ብዙ ዘጋቢዎች ‹‹ የፌስ ቡክ አብዮት ›› እስከማለት ደርሰዋል ፡፡ በማህበራዊ ድረ ገጾች ጥናት ያደረገቸው ማርቲን ማህበራዊ ሚዲያ የትግል መነሳሳቱ እንዲጠናከርና የግዜ ማዕቀፍ እንዲያበጅ እገዛ አድርጓል ባይ ናት ፡፡ ዜጎች የጭካኔ ተግባራት ፣ የፍትህ መጣስና መዛባት፣ የሰቆቃ ህይወት በስፋት መኖሩን እንዲገነዘቡ ብሎም የፍርሃት ስነ ልቦናቸው እንዲወገድ ትልቅ ሚና ተጫውቷል ፡፡ ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው በርካታ አክቲቪስቶችም ‹‹ እነዚህ መሳሪያዎች ባይኖሩ የሙባረክ መንግስትን የመገልበጡ ሂደት በርካታ አመታቶችን ይፈልግ ነበር ›› ብለዋል ፡፡

ስለሆነም መንግስት በሁለቱ ጥቅሞቹና ጉዳቶቹ መካከል መንገዱን አስተካክሎ መጓዝ ይኖርበታል ፡፡ ችግሩን ተቀብሎ ሊያስተካክል ፣ ብርታቱን ሊመረኮዝበት እንደሆነ ሊያጤን ግድ ይለዋል ፡፡ ‹ ወንድ ወደሽ ጺም ጠልተሸ አይሆንም › የሚባለው ተረትም ቅርጹና መልዕክቱ ይኀው ነው ፡፡

››››                               ››››                                    ›››››                                  ››››

አዲስ ራዕይ መጽሄት ፡፡

የፌስ ቡክ ተጠቃሚ የሆነውን ከተማ ቀመስ ህዝብ የ 2006 ምርጤና  ነውጤ በማለት ስያሜ ይሰጣል ፡፡ ምርጦቹ  ‹ ልማታዊ ተጠቃሚዎች › የሚል የክብር ማዕረግ የሚያገኙ ሲሆን ነውጤዎቹ  ‹ ጥገኛ ተጠቃሚዎች › የሚል  ባርኖስ ይከናነባሉ ፡፡

የመጽሄቱ ውዳሴ ፡፡

ልማታዊ ተጠቃሚዎች በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ የሚወጡ ጸረ ልማት ዜናዎችን ፣  ዘገባዎችን ፣ ፎቶዎችንና ፊልሞችን ከፍተኛ ትዕግስት በመጠቀም አይቶ እንዳላየ በመዝጋት … እነዚህን ተውሳክና ተዛማች ሀሳቦች ባሉበት ቀጭጨው እንዲቀሩ LIKE እና  SHARE ባለማድረግ እንዲሁም COMMENT ባለመስጠት ሀገራዊ ግዴታቸውን ተወጥተዋል ፡፡

ዘላለማዊ ክብር ለመስመርተኞች !!




Monday, August 12, 2013

ጠይሟ ልዕልት !!




ጠይሟ ልዕልት
የሩጫው ድማሚት
ሰዓት ጠብቃ ስትፈነዳ
አንድም ታምራለች እንደ ጽጌሬዳ
አንድም ታርዳለች እንደ ካባው ናዳ ፡፡
ጠይሟ ቀስተ ዳመና
ባለብዙ ልዕልና
የስንቱን አይን በረገደች ?
በወቸው ጉድ በለጠጠች ::
የስንቱን ልብ አሞቀች ?
በፍቅር መዳፍ ጣለች ::
እናትስ ትውለድ ያንቺን አይነቱን አቦሸማኔ
ህዝብ የሚወድ አስተኔ  ፡፡
ለሀገር የሚሞት ወያኔ ፡፡