Wednesday, June 24, 2020

ተሰርቆ የታሰረው ልጅ ታሪክ



ጥቅል ታሪክ

 « My name is Why » የተሰኘው የለምን ሲሳይ መጽሀፍ በራሱ የልጅነት ህይወት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ስራ ነው ። መንግስት ልጅ ሰርቆ እስር ቤት ከቷል ፣ የህይወት ታሪኩም እንዳይታወቅ ድብቋል ይላል ደራሲው ገና ከመነሻው ። የለምን  እናት እንግሊዝ ሀገር ለትምህርት የደረሰችው በ1966 ዓም  ነበር ። በወቅቱ ነፍሰ ጡር ነበረች ፣ መውለጃዋ ሲደርስ ዊጋን አካባቢ በሚገኝ አንድ ሆስፒታል ደራሲውን ተገላገለች ። ብዙም ሳይቆይ አባቷ ስለታመሙ  ወደ ኢትዮጽያ  መመለስ ነበረባት ፤ ያኔ ነው እንግዲህ ህጻኑ ለአሳዳጊ ተላልፎ የተሰጠው ። ኖርማን ግሪንውድ የተባለ ስምም  አገኘ  

ለለምን ሲሳይ ህይወት ፈተና ነበረች ። ገና በ12 አመቱ ነበር አሳዳጊዎቹ ከቤት ያባረሩት ።  ከ 12 እስከ 17 አመቱ ደግሞ በአራት የተለያዩ ማሳደጊያ ቦታዎች በተለያዩ ምክንያቶች ተወርውሯል ። በግራ እጁ ላይ NG / Norman Green wood / የሚል ንቅሳት ቢያጽፍም እውነተኛ ስሙ ይህ ንቅሳት አለመሆኑን የተገነዘበው በ 17 አመቱ ነበር ።

ደራሲው ለ30 አመታት ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ትግል ገጥሟል ። ትግል የገጠመው ከልጅነት እስከ እውቀት ሲመዘገብ የቆየው የህይወቱ ታሪክ / ማንነት / ተላልፎ እንዲሰጠው ነበር ። በ2015 የዊጋን ካውንስል ሃላፊ አራት ትላልቅ ዶሴዎችን አስረከቡት ። ከዚህ በኋላ ነበር ይህ መጽሀፍ የተወለደው ። ማንነቱን ለአለም ለማብሰር ስሙ ኖርማን ሳይሆን ለምን መሆኑን ለማስረዳት  ይደክማል ... MY Name is Why…

ስለ ልጅነቱ ፣ ስለትምህርቱ ፣ ስለ አሳዳጊዎቹ ስብእና ፣ ስለ ባህሪው ፣ እናቱ ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ስለተፃፃፈቻቸው ደብዳቤዎች  ምን አለፋችሁ እያንዳንዱ ትንፋሹ ዶሴው ውስጥ እየተመዘገበ ነው የቆየው ። ደራሲው ደብዳቤዎቹን አባሪ በማድረግ ነው እንግዲህ ታሪኩን በቅደም ተከተል የሚተርክልን ።

ለአሳዳጊዎቹ ስለመተላለፍ

ህፃኑ ለምን ሲሳይ ሆስፒታሉ ውስጥ ለ 228 ቀናት ብቻውን ተኝቶ ነበር ። የዚህ መሰረታዊ ምክንያት ደግሞ ዘረኝነት ነው ። ህፃኑን የጎበኘ ሁሉ ጥቁር መሆኑን በማየት ብቻ ቀኝ ኋላ ዙር ይላል ። መጨረሻ ላይ የግሪንውድ ቤተሰቦች እያመንቱ ‹ እስኪ ለማንኛውም በጥልቀት እንፀልይበት ›  ሲሉ መከሩ ፣ ከቆይታ በኋላም ፍቃደኝነታቸውን  ገልፀው ህፃኑን ተረከቡ ።

ይህ ሁሉ ፍጥጥም ጥር 3 ቀን 1968 የተደረገው  ያለእናቱ  ስምምነት ነው ። እናቱ ለአጭር ግዜ ትምህርት ስትመጣ ችግር ላይ ነበረች ። በመሆኑም የምትማርበት ኮሌጅ ርግዝናዋን አስመልክቶ ወደ ቅዱስ ማርጋሬት ነበር የላካት ። ለምንን በሰላም ከተገላገለች በኋላ የማደጎ ስምምነቱን ትፈርማለች ተብሎ ይጠበቅ ነበር ። ነገር ግን ማደጎ ምን እንደሆነ በሚገባ ታውቅ ስለነበር ስምምነቱን አልፈረመችም ። ይህ በእንዲህ እንዳለ ደግሞ አባቷ  በፀና በመታመማቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለስ ነበረባት ። ቆይቶም ለምንን ጥላ በመሄዷ ልጁ በመንግስት ሃላፊነት ስር መውደቁን የሚገልፅ  ደብዳቤ በምትከታተልበት ቤተክርስትያን በኩል ተላከላት ። ተቃውሞ ካላትም በ30 ቀናት ውስጥ ብቻ እንድታቀርብ ያስጠነቀቀ ነበር መልእክቱ ።

ደራሲው ይህ ደብዳቤ ተፈፃሚ ሊሆን እንደማይችል በማስላት የተላከ ነው ባይ ነው ። ምክንያቱም ፍርድ ቤት ጉዳዩን ለማስረዳት ብቻ  14 ቀናት ያስፈልጋል ፣ የተላከው መልእክት ኢትዮጵያ ለመድረስ አንድ ወር ወስዶበታል ይህ ማለት የእሷም ምላሽ ወይም አቋም እንግሊዝ ለመድረስ አንድ ወር ይፈጅበታል ። በሌላ በኩል በግዜው ከአዲስ አበባ ለንደን ቀጥታ በረራ አልነበረም ። ቦታው ለመድረስ ከአዲስ አበባ አቴንስ ፣ ከአቴንስ ደግሞ ለንደን መብረር ያስፈልጋል ፣ ይህ ማለት በተሰጠው የግዜ ገደብ መድረስ የማይቻል ነው በማለት ። ለምን ቅዱስ ማርጋሬት ሃውስን ከሚሰጠው ተግባር አንጻር በሚከተለው መንገድ ያጣጥለዋል

 « በመሰረቱ ይህ ቦታ የልጆች እርሻ ነው ። እናቶች መሬት ሲሆኑ ልጆች ደግሞ ሰብል ናቸው ። ቤተክርስቲያንና መንግስት ገበሬዋች ሲሆኑየማደጎ አሳዳጊዎች ደግሞ ተጠቃሚዋች ናቸው »

 ሰቆቃና መከራ

መምህርና ነርስ የሆኑት አሳዳጊዎቹ ሁለት ልጆች አላቸው ። ክርስቶፈርና ሄለን የተባሉ ። ለምን ክርስቶፈርን በአንድ አመት ይበልጠዋል -  ሄለን  በጣም ትንሽ ናት ። ክወንድሙ ጋር ጠረጴዛ ቴንስ ሲጫወቱ አውቆ ይሸነፍለት ነበር - እንዳይናደድ ።

ለምን በሰባት አመቱ ጠያቂ መሆን ጀምሯል ። ቤተክርስቲያን ሲሄድ ያልገቡትንና ቅር የሚሉትን  ነገሮች ሁሉ እንዴት  እያለ ይጠይቃል ። ጥያቄዋቹ  ምላሾች ነበራቸው « ሁላችንም ሃጢያቶች ስለሆንን » የሚል ። ትምህርት ቤት አካባቢ ለሚፈጠሩበት የዘርና የቀለም ጥያቄ ግን ምላሸ አላገኘም ። « እናትህ ጥላህ ሄደች … አትፈልግህም … እኔ ባገኘት አይኗን እቦጫጭረው ነበር … እንዴት አይነት ክፉ እናት ናት … » በትንሸ ጭንቅላቱ ይህን ጥያቄ ቤት ይዞ ይሄዳል - ምላሸ ለማግኘት ። የአሳዳጊው እናት መልስ ግን ወላጅ እናቱን አበክራ እንደምትጠላት የሚያስረዳ  ነበር ።

የህይወት ፋይሉ ላይ እንደተመዘገበው በስምንት አመቱ ብስኩት ሰርቆ በልቷል ፣ ቁራጭ ኬክ ሲወስድም ‹ እባክህ › እና ‹ አመሰግናለሁ › ሳይል ነው ። ሰርቆ መብላቱ ወላጆቹን ያበሳጫቸው ሲሆን ሰይጣን ውስጡ እንደገባ ያምኑ ነበር ። ደራሲው ኋላ ላይ High Profiles ለተባለ መጽሄት በስጠው ቃለመጠይቅ  « እጃቸውን ጭንቅላቴ ላይ ጭነው ሰይጣን ከዚህ ልጅ ላይ ውጣ ! » ይሉ ነበር ብሏል ።

አይወደንም ፣ ሰይጣናም ሆኗል ከሚሉ ምክንያቶች በተጨማሪ በ 12 አመቱ ለመባረሩ ምክንያት የሆነው የትንሿን ሄለንን ወሬ በመስማታቸው ነው ። ሄለን ለወላጆችዋ  ‹ ኖርማን ከእኔ በስተቀር ሁላችሁንም እገላለሁ ሲል ሰምቼያለሁ › ብላ ታወራለች ። ይህ ወቅት ገና ወደ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የተሸጋገረበት ነበር ። የስምንት አመት ልጅ ቤተሰቡን ሊጨርስ እየዛተ ነው ብሎ ማመን ብሎም የከፋ ርምጃ ይወስዳል ብሎ መደምደም ተቀባይነት እንደሌለው ደራሲው ይናገራል ።

አሳዳጊዎቹ ይህ ሰይጣንም ልጅ እንደማያስፈልጋቸው ውሳኔ ላይ ደረሱ ። እናም አንጠልጥለው  ለአንድ አሳዳጊ ድርጅት አስረከቡት ፣ ዝም ብለው ቢሄዱም ጥሩ ነበር ። ከዚህ ይልቅ የማይታይ አርጩሜ ህሊናው ውስጥ አስቀመጡ « እየመጣን አንጠይቅህም ፤ ድብዳቤም አንጽፍልህም » በማለት ። በደህናው ዘመን ወንድም ፣ እህት ፣ አክስት ፣ አጎት እና  አያት እንዳለው እንዳልሰበኩት « አውጥተው ሲጥሉኝ ማንም ሰው እንዳይገናኘኝ አድርገው ነበር » ብሏል በቁጭት ። ጥር 3 ቀን 1968 ዓም ተግባራዊ የሆነው የማደጎ ወላጆች ስምምነት ሰባት አንቀፆችን ይዟል ። አንደኛው ኖርማንን ልክ እንደራሳቸው ልጆች ማሳደግ እንደሚኖርባቸው ይደነግጋል  ። ሁለተኛው ደግሞ ልጁ የራሱን ሃይማኖት እንዲከተል ማድረግን ይመለከታል ። ክነዚህ ድንጋጌዋች አንፃር በለምን ላይ የደረሰው ቅጣት ከሚታሰበው በላይ ነው ። ለመሆኑ ለምን ስለአሳዳጊዎቹ ምን አስተያየት አለው የሚል ጥይቄ ቢነሳ የሚከተለውን የሚገርም ምላሸ ሲሰጥ እናገኘዋለን « በጣም ጥሩ ሰዎች ነበሩ ፣ መጥፎ ነገርን የሚያደርጉ »

የቦብ ማርሌይ ሞራላዊ ድጋፍ

በ 12 አመቱ ውድፊልድ ወደተባለ ማሳደጊያ ተቋም ሲገባ የእድሜ አቻዎቹ ቾኪኋይት የሚል ቅጽል ስም ሰጥተውት ነበር ። በዚህ ስፍራ ሰራተኞቹ ልጆች ሲጋራ ማጨስ እንደሌለባቸው አይመክሩም ይልቁንም የማጨሻ ልዩ ስፍራ አዘጋጀተዋል - እናም ማጨስ ለመደ ። በዚህ ስፍራ መፅሀፍ የለም ፣ አንብብ የሚል አበረታችም አይገኝም - በተቃራኒው ግን ለመጀመሪያ ግዜ ግጥም መፃፍ ጀመረ ። ግጥሙም ስለ ዛፍ የምታወሳ እንደነበረች ያስታውሳል ። ባልተጠበቀ መልኩ ግን ገጣሚ መሆኑን የተረዳችው የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር « The Mersey sound » የተባለ የግጥም መፅሀፍ እንዲያነብ ሰጥተዋለች ። አሁንም በተቃራኒ እይታ ደራሲው ስለግጥሙ ይዘት አይደለም የሚነግረን - ገጣሚው በመጀመሪያ ገጹ ላይ ስለ ሙት ልጆች መፃፉን እንጂ ።

በአንድ ወቅት በጓደኛው ምክንያት ከቦብ ማርሌይ ስራዋች ጋር ተዋወቀ ። ቦብ ማርሌይ የመጀመሪያው ጥቁር ጓደኛ ፣ የመጀመሪያው ጥቁር መምህር ሆነለት ። በርግጥ ከ ቦብ የወሰደው ዘፈኑን ብቻ ሳይሆን አደገኛ እፅንም ጭምር ነበር ። ቦብ ለሰው ልጆች እኩልነትና ነፃነት ይጮሃል ፣ ስለ ጭቆና ስለ ታሪክ ስለ አለም እውነት ይናገራል ። ደራሲው ቦብን የወደደበት ሌላኛው ምክንያት በዘይቤያዊ አነጋገር የሚያስተላልፋቸው ውብ መልእክቶች ናቸው ። በዚህ ረገድ Ride Natty Ride በሚለው ዘፈን ውስጥ ግንበኞች የናቁት ድንጋይ እርሱ የማእዘን ራስ ሆነ የሚለውን መጽሀፍ ቅዱሳዊ አባባል ለጉድ ይወደዋል ።

But the stone that the builder refuse
Shall be the head cornerstone
And no matter what game they play
We’ve got something they could never take away .

እናም ለመጀመሪያ ግዜ ከነጮች ባህር ውስጥ የተገኘ ጥቁር ሰው መሆኑን አመነ « በኔ ዙሪያ የተሰበሰቡ ሰዎች ሁሉ የኔን ዘርና ቀለም የካዱት የቀለም አይነስውርነት ስላለባቸው መሆኑን  አመንኩ » ብሏል

ጥቅል መደምደሚያ

በጽንሰ ሀሳብ ደረጃ አውቶባዮግራፊና ሚሞይር ስለ አንድ ሰው ህይወት ስለሚያትቱና በአንደኛ ደረጃ የአጻጻፍ ይትበሃል ስለሚዋቀሩ የመመሳሰል ጸባይ ያላቸው ይመስላል ። ፈታ አድርገን ስንመለከታቸው ግን መሰረታዊ ልዩነት አላቸው ። አውቶባዮግራፊ የደራሲውን መላ ህይወት በቅደም ተከተል የሚዳሥስ ሲሆን ሚሞይር የደራሲው የተወሰነ የህይወት ክፍል ላይ አጠንጥኖ ይሰራል ። አውቶባዮግራፊ ታዋቂ ሰዎች ላይ ሲያተኩር ሚሞይር ሰው አይመርጥም ። ሰዎች ለማንበብ የሚፈልጉት አጠቃላይ ህይወቱን ቢሆን ከርእሰ ጉዳዩ ወይም ከጭብጡ አንፃር በመነሳት ነው ። አውቶባዮግራፊ ለእውነትና ታሪክ ልዩ ትኩረት ሲሰጥ ሚሞይር ስሜት ነክ ልምዶችን ይቃኛል ።

በዚህ ረገድ የለምን ሲሳይ ሚሞይር የማንነት ፍለጋ ላይ ላይ ያነጣጠረ ነው ማለት ይቻላል ። እናት ብትርቀው ፣ አሳዳጊ ቢገፋው ፣ ማህበረሰቡ ቢያገለው እንኳ ያላሰለሰ የራስ ጥረት ካለ ውጤት እንደሚገኝ ያስተምራል ። ለምን ሲሳይ እስከ 17 አመቱ አንድ አይነት ፣ ከ 17 አመቱ በኋላ ደግሞ ሌላ አይነት ሰው ነበር ። በ 14 አመቱ እጁ ላይ የነቀሰው Norman Greenwood አንደኛው ሲሆን ከ 17 አመት ጀምሮ ያወቀው ‹ ለምን ሲሳይ › ደግሞ ሁለተኛው ማንነት ነው ። ሁለተኛውን ማንነቱን ሲያገኝ የተረዳው ስሙን ብቻ ሳይሆን እውነተኛ እናቱን ፣ እውነተኛ ሀገሩን ፣ የጥቁርነቱን ምክንያትና የግጭቱን መሰረት ነው ። ለዚያም ነው ገጽ 137 እና 138 ላይ « የልደት ማስረጃዬ ላይ ያለው ስም ለምን ሲሳይ መሆኑን ለሚጠቁኝ ሁሉ እነግራቸዋለሁ » በማለት 90 ያህል ግዜ My name is Lemn Sisay ተደጋግሞ ተጽፎ የምናየው ። የድግግሞሹ ወይም / Alliteration / ሚና ትኩረት መጠቆሚያ ነው ።

ለምን ሲሳይ እውነተኛ ስሙንና ማንነቱን ካወቀ በኋላ ሙሉ ለሙሉ ያልመለሰልን አንድ ጥያቄ አለ ። ርግጥ ነው በቅጣይ / Epilogue / ምእራፍ ላይ እናቱ የማርሸት ከአማራ ህዝቦች እንደተገኘች በዚሁ ክልል ባህል ደግሞ በመጀመሪያ ልጅ መልእክት ማስተላለፍ የተለመደ መሆኑን በመጠቆም ለምን ‹ Why › የሚል ፍቺ እንዳለው ያሰረዳናል ። ጥያቄው ግን ይህ አይደለም ። ጥያቄው እናቱ እንዴት ‹ ለምን › አሉት የሚለው ነው ። ከስሙ ፍካሬያዊ ፍቺ ከተነሳን ለምን ትምህርቴን ሳልጨርስ … ለምን በውጭ ሀገር …. ለምን ከጋብቻ በፊት … ወዘተ የተሰኙ ህሊናዊ ሙግቶች እንዳሉበት እንገነዘባለን ።

ስለምንነት ካወራን ደግሞ እናቱን አስታውሶ አባቱን መግደፉ መሉ አያደርገውም ። ለምን ሲሳይ ከመጽሀፉ ህትመት በኋላ በሰጣቸው ቃለመጠይቆች አበቱ የኢትዮጽያ አየር መንገድ አብራሪ እንደነበር ፣ በ1973 ከኢትዮጽያ ወደ ኤርትራ እየበረረ መብረቅ ክንፉን መቶት በሰሜን ተራሮች ላይ መሰዋቱን ተናግሯል ። ሰሜን ተራራሮችን ከጎበኘ በኋላም ለአባቱ ግጥም መጻፉን አስረድቷል ። እነዚህ ቀጥተኛ ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች በድሉ የመጨረሻ ምእራፍ ላይ ቢዳሰሱ የበለጠ ጠንካራ ያደርገው ነበር ።

ደራሲው በዚህ ስራው የተበላሸ የማደጎ ስርአት አሰራርን አጋልጦበታል ። የቸልተኛ ባልስልጣናትን የተረገመ ተግባር እንዲሁም የቢሮክራሲን ጭካኔ አሳይቶበታል ።  በዘር ፣ በቀለምና በሞራል ላይ የሚደረገውን ልዩነት ኮንኖበታል ። በ 30 ምእራፎች የተከፋፈለው ስራ ሁለት ልዩ ባህሪያት አሉት ። የመጀመሪያው አብዛኛው ምእራፍ ከመረጃ ጋር ተሰናስሎ የመቅረቡ ጉዳይ ነው ። ሁለተኛውና ዋነኛው ሀሳብ ሁሉም ምእራፎች የሚጀምሩት በ ኳትሬይን / Quatrain / አይነት ግጥሞች መሆኑ ነው ። ለአብነት ያህል በምእራፍ  14 ላይ የሚከተለውን  ግጥም እናገኛለን
 
Night can’t drive out night
Only the light above
Fear can’t drive out fear
Only love

ጨለማን ጨለማ አያባርረውም
ብርሃን እንጂ
ፍርሃትን ፍርሃት አያባርረውም
ፍቅር እንጂ

ግጥሞቹ በቀጣይ ከምናነበው ታሪክ / ሃሳብ / መረጃ ጋር እናገናኘው ካልን ሊገኛኝ ይችላል ። እነዚህ  ባለ አራት መስመር የግጥም ስንኞች በተለይ በእንግሊዝ ስነ ጽሁፍ ታሪክ ውስጥ ላቅ ያለ ሚና አላቸው ። ርግጥ ነው ይህ ስነጽሁፋዊ ዘውግ በጥንታዊ ቻይና ፣ ሮም ፣ ግሪክ እና ህንድ ቀደምት ልእልና ነበረው ። ቀጥሎም በአውሮፓ የጨለማው ዘመን በስፋት ተሰርቶበታል ። በተለይም በመካከለኛው ምስራቅ ኦማር ካያም ሩባያ በሚል ስያሜ ገኖበታል ። በተመሳሳይ መልኩም ኖስትራዳመስ ለዝነኛ ትንቢቶቹ መጠቀሚያ አድርጓቸዋል ።

ታዲያ ለምን ሲሳይ እነዚህን የግጥም አይነቶች በምን አላማ ተጠቀመባቸው ብሎ መጠየቅ ግድ ይላል ። ግጥም ያለውን ትልቅ ጉልበት ለማሳየት … ግጥም መጻፍ የጀመረው እስር ቤትን በሚስተካከሉ/ እንደርሱ አመለካከት /  የህጻናት ማቆያ ቦታዎች መሆኑን ለመዘከር … በስቃይና ችግር ያሳለፈውን የልጅነት ህይወት ያቃለለት ኪነጥበብ / ግጥምና ሙዚቃ / መሆኑን አስረግጦ ለማስረዳት … ጽሁፉን ተነባቢ ለማድረግ … ወዘተ ማለት ይቻላል ። እንደ እኔ እምነት ግን ባለአራቱ ስንኞች ገዝፈው የተቀረጹት በአራት አስቸጋሪ ማሳደጊያ ቦታዎች ህይወቱን መምራቱን ተምሳሌታዊ ለማድረግ በመፈለጉ ነው ።

Friday, June 19, 2020

የፍትህ መዶሻ ይዛ ፍትህ የምትጠይቅ ሀገር



ኢትዮጽያ አይኗን በጨው ካጠበችው  ግብፅና አይኗን በአግባቡ መታጠብ ካቃታት ሱዳን ጋር እሰጥ አገባ ከገባች አመታትን አስቆጠረች ። ድርድሩ የፓለቲካውና ዲፕሎማሲውን መንገድ ይከተል በሚል እንጂ በጉንጭ አልፋው ንግግር  ውጤት ይገኛል ተብሎ አይጠበቅም ።

ፈጣጣዋ ግብፅ የቅኝ ግዛቶችን ውል ከትከሻዋ ላይ ማውረድ አትፈልግም ። ከግፈኛዋ እንግሊዝ የተቀበለችውን የውሃ ድርሻ እንደ ጄነራል ክፍ አድርጎታል ። ይህን ማእረግ ወደ ሻምበልነት የሚያወርድ ተጋፊ ሃይልን አትቀበልም ። እናም በእሷ ቀመር የውሃው ባለቤትነት የሚመዘነው ከሚመነጭበት ቦታ ሳይሆን በተፈጥሮ ቀድሞ በያዘ ነው - ላለው ይጨመርለታል የሚባለውን የወንጌል ጥቅስ እንድናስታውስ በማድረግ ።

ሱዳን ከቅኝ ገዢዋ መሃንዲስ የሚበቃትን ያህል ድርሻ ተቀብላለች ። የአባይ ወንዝና የግድቡ ወሬ ሲነሳ የምታዳምጠው አይናር የማይጠፋውን አይኗን እየሞዥቀች ነው ። አይናሩ ሲለቃት ግድቡ ይጠቅመኛል ከኢትዮጽያ ጎን ነኝ ትላለች ። አይናሩ አንቆ ሲይዛት የግብጽ ማስፈራሪያ ነው ቀድሞ የሚሰማት ። ያኔ ግብፅን በአረብኛ ማናገር ትጀምራለች - አቋም እንዲኖራት አትፈልግም ።
እነዚህ ሀገሮች ከያዙት ሀገወጥ ጥቅምም ሆነ ከሚያስተሳስረቸው ፖለቲካዊ ውግንና አንጻር ወደ መሃል ተስበው የሚመጡ አይደሉም ። ወደታች ወርደው የእውነት ባልጩት ላይ ከቆሙ ድንጋዩ ያበቀለው አልጌ አዳልጦ እንደሚጥላቸው ይረዳሉ ። የሚደራደሩት አዲሱን እውነት ለመቀበልና የቆየውን ክብር ለማጣት አይደለም ።

ለዚያም ነው በተለይ ግብፅ ከድርድር ይልቅ አደራዳሪን ምርኩዝ ማድረግ የምትመርጠው ። ለቡራኬ ሰጪዎች ትልቅ ቦታ አላት ። ድሮ ለዚህ ያበቃቻት እንግሊዝ ዛሬ ባትጠቅማትም አሜሪካንን መተካት አላቃታትም ። ትላልቆቹ በስሟ እንዲያስፈራሩላትና የረባሽ ሀገራትን ጆሮ እንዲቆነጥጡላት ትፈልጋለች ። የያዘችው እውነት ለዛሬው አለም ባይሰራም አይኗን አፍጣ አለም መንግስታት ፊት ስሞታ ታቀርባለች ። ጩኸቷን እንዲጮሁላት አጥብቃ ነው የምትሰራው ። አልፋም ትሄዳለች - ሁሉንም አማራጮች እጠቀማለሁ የሚል ማስፈራሪያ በመልቀቅ ።

እንደሚታወቀው የውሃው መነሻም ሆነ የግድቡ መድረሻ ከኢትዮጽያ ነው ወይም ኢትዪጽያ ናት ። በውሃ የመጠቀም አለማቀፋዊ መብቷ ጥያቄ ውስጥ ባይገባም የምትደራደረው ግን በድርድር ተጎጂልን ከሚሏት ፈጣጣ ሀገራት ጋ ነው ። ድርድሩን አለም ይውቅልኝ ፣ ፍትሃዊነቱንም ይገንዘብልኝ የምትለው የሌሎችም አጋር መሆናን ለማሳየት ነው ። ሀገሬ ግን ነገ ጠባ እየከሰሷት ፣ አለፍ ሲልም እያስፈራሯት ፍትሃዊ አካሄዴ ይታወቅልኝ በሚል ባዘነች ።

እንደ እውነቱ ከሆነ ግድቡን ለመስራትም ሆነ ውሃውን ለመሙላት የማንንም ፍቃድ መጠየቅ አያስፈልግም ። መጠንቀቅ ያለብን ሌሎችን በጭፍን ጥላቻ ላለመጉዳታችን ብቻ  ነው ። ከዚያ ውጪ ወንዙም ግድቡም የኛ ነው ። በያዝነው ነገር ላይ መያዛችንን ከማይቀበል ቡድን ጋር ለምን ሃይላችንን እናጠፋለን ? ብለህ ብለህ አልቀበል ካለህ የያዝከውን አስተማማኝ የፍትህ መዶሻ በራስህ ጠረጼዛ ላይ መምታት ተገቢ ነው ። ከዚያ ለፍርድ አፈጻጸም ወደሚመለከተው አካል በየአድራሻው መላክ - ይኅው ነው ። ውሃውን መሙላት ስትጀምር ትላንት አልቀበል ያለህ ሁሉ ሰልፉን ካንተ ጋ ያሳምራል ፤ ቋንቋውንም ይለውጣል ። ዋ ! የሚልህን ረስቶ ‹ እባክህ › ማለት ይጀምራል ። አለም የምታሳየን እውነት ይሄንን ነው ። ከወሬው ቀንሰን ይህን ለማድረግ እንፍጠን ። ያኔ የመታኸው መዶሻ ጠብቆ መግባቱን ቢያንስ ቢያንስ ደግሞ ትክክል መሆኑን ትገነዘባለህ ።

በርግጥ ሌሎችን ተደግፎም ሆነ በራሱ የሚያስፈራራው ቡድን ምንም አያመጣም ብሎ መዘናጋት ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል ። ግልጽ ጦርነት ባይከፍትብህ እንኳ ሌሎችን በገንዝብ በመግዛት ጥቅምህን ለመናድ ሌት ተቀን ይሰራል ። ሱዳን እና የኛ ሀገር ባንዳዋችን በዋናነት እንደሚጠቀም መጠራጠር አይኖርብንም ። ግድቡ ድንበር ላይ እንዲሰራ መደረጉ ምናልባት የሚጎዳንም በዚህ መሰሉ አጣብቂኝ ግዜ ነው ። እናም በአንድ በኩል ግድቡን ለመጨረስ እየተጉ በሌላ በኩል ግድቡንና አካባቢውን በአስተማማኝ መከላከያ ማጠር ያስፈልጋል ። የሀገር ቤቶችን ባንዳዎች እግር በእግር ተከታትሎ ግባቸውን ለማጨናገፍ ፣ የጆሮ ጠቢውን መስሪያ ቤት ሚና ከመቼውም ግዜ በላቀ መልኩ ማሳደግ ተመራጭ ይሆናል ።

Sunday, June 7, 2020

የእንግሊዝ ሃውልቶች አዲስ ፈተና …




ኤድዋርድ ኮልስቶን የብሪስቶል ነዋሪዋች ኩራት ነበር ። ሲበዛ ቅን ነው ይሉታል - ተወላጆቹ ። ኋላ ላይ ከተማዋን እየተቀላቀሉ የመጡ ጥቁሮችና ሌሎች ግን የክፋት መጨረሻ እንደሆነ ነው የሚሰማቸው ። ከነጋዴ ቤተሰቦቹ በ 1636 ተወልዶ በ 1721 ዓም አረፈ ። እዚህ ከተማ ላይ ሃውልት የቆመለት በ 1895 ሲሆን መሰረታዊው ምክንያት በጎ አድራጊነቱ ነው ። በኖረበት ዘመን ለበጎ አድራጊ ድርጅቶች ከ 71 ሺህ ፓውንድ በላይ ለግሷል ። ለትምህርት ቤቶች ፣ ለእምነት ተቋማትና ለሆስፒታሎችም በመርዳት ስሙ ይጠቀሳል ። አንዳንዶች የገንዘብ ምንጩ ቱባ ነጋዴ በመሆኑ ነው ይበሉ እንጂ ብዙዋችን የሚያስማማው ጥቁሮችን በመሸጥ ያካበተው ነው ።

የዚህ ሃውልት ህጋዊነት ለበርካታ ግዜ የብርስቶል ከተማን ህዝብ አወያይቷል ፣ አጨቃጭቋል ። የሰውየው ሌጋሲ ለምሳሌነት አይበቃም በሚል የሃውልቱን መቆም የሚቃወሙት ሰሚ ሳያገኙ ቆይተዋል ። ዛሬ ከ 125 አመታት በኋላ ‹ ታላቁ › ኤድዋርድ ኮልስቶን አደባባይ ላይ በትዝብት እንደቆመ አልቀጠለም ። ዘረኝነትን በሚቃወሙ / Black Lives Matter / ሰልፈኞች እንደ በሬ በገመድ ተጠልፎ እንዲወድቅ ተደርጓል ። ከወደቀ በኋላ እንደ ሳዳም ሁሴን ሃውልት ተረግጧል ፣ ተተፍቶበታል ፣ ተረግሟል ። እንደ ጆርጅ ፍሎይድ ገዳይ አንገቱ ተረግጦ ‹ መተንፈስ አልቻልኩም › እንዲል ተጠብቋል ። በመጨረሻም ድሮ ባህር አቋርጠው አውሮፓና አሜሪካ የመጡ ጥቁሮችን ያስታውስ ዘንድ ይመስል ወደ ባህር ተጥሏል ።

ኤድዋርድ ኮልስቶን በ1689 ጥቁሮችን እያስመጣ በመሸጥ በሚታወቀው / Royal African Company / ድርጅት ውስጥ ምክትል ሃላፊ ነበር ። በዚህ ካምፓኒ ውስጥ እየሰራ 84 ሺህ 500 የሚደርሱ ጥቁሮችን በመርከብ አጓጉዟል ። ከዚህ ውስጥ 23 ከመቶ ወይም 19 ሺህ 300 ያህሉ ወደብ ሳይደርሱ መንገድ ላይ በውሃ እጥረት ፣ በተቅማጥና በንጽህና ጉደለት ሞተዋል ። ይህ ሰው ሌላም የሚታወቅበት ጉዳይ አለ ። በ 70ቹ እድሜው የፓርላማ አባልነቱን ተጠቅሞ የባሪያ ንግድ እንዲስፋፋ ፔቲሽን እስከ ማሰባሰብ ደርሷል ።

እንግሊዝ ለህብረተሰቡም ሆነ ለሀገር ጥሩ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ተብለው የሚታሰቡ / በክፉም ሆነ በደግ /  ስመጥር ዜጎችን ሃውልት በማቆም በቀጣዩ ትውልድ እንዲታወሱና እንዲዘከሩ የማድረግ የረጅም ግዜ ባህል አላት ። አንዳንድ መረጃዋች እንደሚጠቁሙት በመላው ሀገሪቱ ከ828 የሚበልጡ ሃውልቶች በተለያዩ ከተሞች ቆመዋል ። እስካሁንም አንዳቸውም ላይ በተቃውሞ መልኩ የመፍረስ አደጋ አላጋጠማቸውም ። ነገር ግን ከቅርብ ግዜ ወዲህ ያልተለመዱ ትችቶችን ያስተናገዱ ሃውልቶች ታይተዋል ። ሁለተኛ አለም ጦርነትን ለማስታወስ በተደረግ ዝግጅት ላይ አንዳንድ ሃውልቶች ላይ ACAB የሚል ጽሁፎች ተነበዋል - All Cops are Bastars የሚል ትርጉሙ እንደያዙ ተገምቷል ።በቅርቡ ለንደን ውስጥ በተደረገው ሰላማዊ ሰልፍም የቀድሞው የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትር ዊንስተን ቸርችል ሃውልት ላይ ዘረኛ ነበር የሚል ጽሁፍ ተለጥፎበት ነበር ።

በአንድ በኩል « የባሪያ ንግድ ውርስ ነው » በሌላ በኩል « አይደለም የበጎ አድራጎነት ምልክት ነው » እየተባለ ሲያጨቃጭቅ የኖረው ሃውልት መፍረሱ የእንግሊዝን መንግስት አስቆጥቷል ። የሆም ሴክሬቴሪ ሃላፊ ፕሪቲ ፓታል ድርጊቱን አሳፋሪ በማለት ተጠርጣሪዋቹን እንፋረዳለን ብለዋል ። በነገራችን ላይ ኤድዋርድ ኮልስቶን በብርስቶል ከተማ በስሙ የኮንሰርት አዳራሽ ፣ ጎዳና እና ትምህርት ቤት ተሰይመውለታል ። ትግሉ እነዚህም እንዲፈርሱ ይዋጋል ወይስ ባፈረሰው ሃውልት ተጠያቂ እስከመሆን ይደርሳል ? እየከረረ ከመጣው የእንግሊዝ ተቃውሞ አንጻር ይህን ጥያቄ በቀላሉ መመልስም ሆነ እንደዋዛ መተውም የሚቻል አይሆንም ።