Thursday, November 1, 2012

እውነት ሱዳን እያሴረችብን ነው ?



አባይ በካርቱም

የጉዳዩ መነሻ ፤

በአባይ ወንዝ ላይ ‹‹ ቬቶ ፓወር ›› አለኝ የምትለው ግብጽ ኢትዪጽያ የጀመረቸውን ግድብ ለመደብደብ እቅድ መንደፏን ዊክሊክስ መዘገቡ ይታወሳል ፡፡ ከዚህ ዘገባ ይፋ መሆን በኃላ በኢትዮጽያና ግብጽ መካከል ያለው ግንኙነት መወጣጠሩ እንደቀጠለ ነው ፡፡

ግብጽ ‹ ወዳጄን › ኢትዪጽያን ለመተናኮል አላሰብኩም በማለት ማስተባበያ ብትሰጥም በ1929 በጸደቀው ስምምነት መሰረት በናይል ወንዝ ላይ ችግር ሲፈጠር የምንፈታበት ስምምነት ላይ ነው ከሱዳን ጋር የመከርነው ብላለች ፡፡ ነገሩ አልሸሹም ዞር አሉ ዓይነት መሆኑ ነው ፡፡ በወራሪዋ እንግሊዝ የጸደቀው የ1929ኙ ስምምነት ለግብጽ 55፣ ለሱዳን ደግሞ 18.5 ቢሊዮን ኩዩቢክ ሜትር ውሃ በዓመት እንዲያገኙ ፈቅዶላቸዋል ፡፡ በዚሁ መሰረትም ላለፉት 84 ዓመታት ሁለቱ ሀገራት ያለማንም ተቀናቃኝ ተጠቅመውበታል ፡፡

እነሆ ቤንች ላይ ተቀምጠው የውሃ ላይ ቦሊቦል ፣ የጀልባ ውድድር፣ የጠብታ መስኖ የመሳሰሉትን ጨዋታዋችና ስራዎችን  ሲመለከቱ የነበሩ ሀገሮች አጉራ ጠናኝ በማለት የአባይ ተፋሰስ ሀገሮችን ጥምረት አቋቁመው የእኩል ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ስምምነት እስከመፈረም ደርሰዋል ፡፡ ሞኝ ካመረረ በግ ከበረረ መመለሻ የለውም እንዲሉ የስምምነቱን የመጀመሪያ ምዕራፍ የሚያበስረውን ስራ  በተግባር ለማስደገፍ ይመስላል ኢትዮጽያ 5250 ሜጋዋት የኤትሪክ ኃይል የሚያመነጭ ግድብ በመስራት ለኩሳለች ፡፡ ሌሎቹም የሌላውን ጥቅም በማይጎዳ መልኩ ቀጣይ ስራቸውን ያከናውናሉ ተብሎ ይጠበቃል ፡፡

ግብጽ እስካሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የውሃው ከፍተኛ ተጠቃሚ በመሆኔና ትልቁ ስልጣንም በእኔ እጅ ያለ በመሆኑ ኢትዪጽያ የምትሰራውን ግድብ መመርመርና መረዳት አለብኝ ብትልም ኢትዪጽያ ይህን ለማድረግ መጀመሪያ ስድስቱ ሀገራት የተስማሙበት ሰነድ ላይ ፊርማሽን  አስቀምጪ በማለት ጀርባዋን ሰጥታታለች ፡፡

የግብጽ ስጋቶች ጥቂት አይደሉም ፡፡ ግድቡ በወንዙ ፍሰት ላይ ተጽዕኖ ይፈጥራል … ወደ ግብጽ ከሚፈሰው የውሃ መጠን በ 25 ከመቶ ያህል ይቀንሳል … ኢትዪጽያ ግድቡን ለሃይል ማመንጫ አለች እንጂ ለመስኖ መጠቀሟ አይቀርም የሚሉት ዋነኛዎቹ ናቸው ፡፡ በተለይም የግድቡ ጥልቀት ከ90 ሜትር ወደ 150 እንዲያድግ መደረጉ ከኃላ የመስኖ ስራ ለማከናወን የሚደረግ መደላድል  ነው በማለት ትጨምርበታለች ፡፡ ይህ ሁሉ ነገር ተደማምሮ ነው እንግዲህ ‹ የኢትዪጽያ ግድብ የብሄራዊ ደህንነቴ ስጋት ነው › እስከማለት የደረሰቸው ፡፡

በዚህ ስዕል መሰረት የዊክሊክስ ዘገባ ሀሰት ነው ለማለት ይከብዳል ፡፡ እናም የዲፕሎማሲያዊ ጥረት የማይሳካ ከሆነ ጉልበትን ለመጠቀም አቅዳለች ፡፡ ለዚህ ደግሞ በሁለተኛ ደረጃ ‹ የቬቶ ፓወር › ያላትን ሱዳን ፈረስ ታደርጋለች ፡፡ ለጀት መንደርደሪያም በምዕራብ ሱዳን ዳርፉር የምትገኘው ‹ ኩርሲ › ናት የተመረጠችው ፡፡ አስገራሚውና አጠያያቂው ጉዳይ ሱዳን በጭብጡ ዙሪያ ትንፍሽ አለማለቷ ነው ፡፡ መቸም ግብጽ ብዙ ሴራ ብትሸርብ ከማንነቷ አንጻር አይገርምም ፡፡ በርግጥ ሱዳን ‹ ከማንም አቀርባታለሁ › የምትላትን ኢትዪጽያ ለመውጋትም ሆነ ለማስወጋት ፍላጎት አላት ? ከምን አንጻር ?  ብዙ ተጽዕኖና በደል ፈጽማብኛለች የምትላትን ግብጽ መርዳቷ ከኪሳራና ትርፍ ስሌት አኳያ እንደምን ይታያል ? ሱዳን ካላት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ አንጻር በኢትዪጽያ የምትታመን ሀገር ናት ? የሚሉትን ጉዳዮች በአግባቡ መፈተሽ ተገቢ ይሆናል ፡፡

 የህዳሴው ግድብ በሱዳን ዓይን ፤

ኢትዪጽያ ግድቡን በራሷ አቅም እንደምትሰራ ይፋ ስታደርግ በማሾፍ፣ በመገረምና በመደንገጥ ውሰጥ ከነበረው ዓለም ቀድማ አስተያየት የሰጠችው ሱዳን ነበረች ፡፡ ግድቡ ከኢትዪጽያ ይልቅ ሱዳንን ይበልጥ ተጠቃሚ ያደርጋል በማለት ፡፡ የመስኖና ውሃ ሃብት ሚንስትሩ ፕሮፌሰር ሰይፍ አዲን ሃመድ አብደላ ‹‹ የአባይ ውሃ ሲገደብ ወደ እኛ የሚመጣውን ደለል እንዲቀንስ ያደርጋል ፡፡ ደለሉን ለማስጠረግ ደግሞ በየዓመቱ ብዙ ሚሊዮን ዶላሮችን ወጪ እናደርግ ነበር ፡፡ ለመስኖ እርሻና ለኃይል አቅርቦትም ያግዘናል ፡፡ በአጠቃላይም ለሱዳንም ሆነ ለግብጽ የሚጠቅም ዕቅድ በመሆኑ ሊበረታታ ይገባል ›› ብለው ነበር ፡፡

ይህ አስተያየት የመነጨው የባለሙያዎችን ጥናት  መሰረት ከማድረግ አንጻር በመሆኑ በጤናማ አይን የታየ ነው ማለት ይቻላል ፡፡  እያደር የተንሸዋረረው መረጃው ነው ወይስ የፖለቲከኞቹ አይንና ጭንቅላት የሚለው አጠያያቂ ጉዳይ ነው ፡፡ እውነቱ በውሸት የሚታይበት ወይም የሚቀለበስበት አካሄድ ግር ሲያሰኝ ‹ የሱዳን አይን እንደ ቆዳ ስፋቷ ትልቅ ነው እንዴ ? › የሚል ጥያቄ ያጭራል ፡፡ የአህያ ትልቅ ዓይን ትልቅ የማየት ችግር አለበትና ፡፡

የመሆን አለመሆን ጉዳይ ፤

 አሸባሪዎችን በገንዘብና በቁሳቁስ በመርዳት፣ ስልጠና በመስጠት በአጠቃላይ በማስጠለል ምክንያት ‹ አሸባሪ ሀገር › በሚለው ጥቁር መዝገብ ውስጥ የሰፈሩት ኩባ፣ ኢራን፣ ሶርያና ሱዳን ናቸው ፡፡ በዚህም ፍረጃ ምክንያት ሀገሪቱ ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስተጋብሮቿ ተናግተው ቆይተዋል ፡፡ ከደረሰባት መገለልና እቀባ በተጨማሪ ምዕራባዊያን ለሀገሪቱ ጥሩ ምስል እንዳይኖራቸውና ግንኙነታቸውን እንዳያጠናክሩ ተጽዕኖ አሳድሯል ፡፡

ይህን መጥፎ ገጽታ ለማስወገድ ብዙ ሰርቼያለሁ በማለት ከተመዘገበችበት የአሸባሪነት ዝርዝር ውስጥ እንድትፋቅ ጥያቄም አቅርባ ነበር ፡፡ ይሁን እንጂ የለም የተባለው ሀማስ  በሀገሪቱ ውስጥ በግልጽ  የገንዘብ ማሰባሰቢያ መድረክ  ሲያዘጋጅ ታይቷል ፡፡ አሸባሪዎችን ከሀገሬ አስወጥቻለሁ ብትልም አልቃይዳና ሌሎች ድርጅቶች በሱዳን ስላለው እንቅስቃሴያቸው የሚያደርጉት የንግግር መረጃዎች ተይዘዋል ፡፡ ይህም ሀገሪቱ ያቀረበቸው ማመልከቻ እንዲዘገይ አድርጓል ፡፡ ከዚህ ምስል ሱዳን የምትናገረውን የማታደርግ ሀገር ናት እንዴ ? የሚል ጥያቄ ማመንጨት ከባድ አይደለም ፡፡

በአሸባሪዎች የምታደርገው ጨዋታ ፤

እንደ ሱዳን ለበርካታ አሸባሪዎች ድጋፍም ሆነ መጠለያ በመስጠት የሚታወቅ ሀገር መኖሩ ያጠራጥራል ፡፡ ለአልቃይዳ፣ ሂዝቦላ፣ የፍልስጤም እስላሚክ ጂሃድ፣ የግብጽ እስላሚክ ጂሃድ፣ የአልጄሪያ አርመዲ እስላማዊ ቡድን፣ እንዲሁም እስላማዊ ያልሆኑ የኢትዮጽያ፣ የኤርትራ፣ የኡጋንዳና ታንዛኒያ ሸማቂ ቡድኖችን ስልጠና በመስጠትና ቦታዎችን በማመቻቸት ትረዳለች ፡፡ በመላው ዓለም እንዲደረጉ በሚታቀዱ የሽብር ጥፋቶች ላይ ፍላጎቷን እግረ መንገድ ትወጣበታለች ይሏታል ፡፡ ለምሳሌ ያህል ሎርድ ረሲስታንስ አርሚ በሚባለው የኡጋንዳ አማጺ ቡድን ጥቃት 25 ሺህ የሚደርሱ የደቡብ ሱዳን ዜጎች እንዲፈናቀሉ መደረጉን የተመድ ሪፖርት ያመለክታል ፡፡ ሱዳን ባላንጣዎን ለማጥቃት ሌላ ረጅም እጅ አላት ማለት ነው ፡፡

በሌላ በኩል ዩዌሪ ሙሴቪኒ ‹ ሱዳን ፍቃድ ብትሰጠኝ ይህን አማጺ ቡድን በሰላሳ ደቂቃ ውስጥ አጠፋዋለሁ › ብለው ነበር ፡፡ አልበሽር ይህ አማጺ ቡድን ለክፉ ቀን ስለሚጠቅማቸው የረጅም ግዜ ጓደኛቸውን ጥያቄ መቀበል አልፈለጉም ፡፡ ከራስ በላይ ንፋስ በማለት ፡፡ የአፍሪካ ህብረት በአንድ ወቅት ይህን አማጺ ቡድን ለማንበርከክ ሱዳንን ጨምሮ ከአፍሪካ የተውጣጣ ብርጌድ አቋቁሞ መላክ ሲፈልግ አሪፍ ስልት ነው ተብሎ ነበር ፤ እያደር ግን አልበሽር ለሀሳቡ ከአንገት በላይ ሆኑ ፡፡ የሱዳን የዳማ ጨዋታ በነጩም በጥቁሩም ሜዳ ላይ በመሆኑ ፋውልም ሆነ ኦፕሳይት አይታወቅም ፡፡ ይህም ግድየለሽነትን ወይም አደገኛነትን ሳይጠቁም ይቀራል ?

ሚሳይልን እንደ ሚዝል የምትቅም ሀገር ፤

በቅርቡ ያርሙክ የተባለው የጦር መሳሪያ ፈብሪካዋ ከራዳር እይታ መሰወር በሚችሉ አራት የእስራኤል ጀቶች ወድሟል ፡፡ ይህ ፋብሪካ ሮኬትና ሌሎች ከባድ መሳሪያዋችን የሚያመርት ሲሆን በኢራን፣ ግብጽና ሱዳን ሽርካነት የሚንቀሳቀስ ነበር ፡፡ የፋብሪሳው ዓላማ ሀማስና ሌሎች ተዋጊ / አሸባሪ ድርጅቶችን ማጠናከር ነው ፡፡

ሱዳን ለዚህ መሰሉ ጥቃት አዲስ አይደለችም ፡፡ በሚያዚያ 2011 ፖርት ሱዳን አካባቢ መኪና ውስጥ የነበሩ ተጠርጣሪ አሸባሪዎች ተገድለዋል ፡፡ በ2009 ሰሜን ምስራቅ ሱዳን ውስጥ ወታደራዊ ኮንቮይ ተደብድቦ 119 ሰዎች አልቀዋል ፡፡ ብዙዎቹም ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ አጓጓዦች ነበሩ ፡፡ በ1998 አል ሺፋ የተባለ መድሃኒት ፋብሪካ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ያመርታል ተብሎ የአሜሪካ ሚሳይል ሰለባ ሆኗል ፡፡ እስራኤል በጥቃቱ ዙሪያ ቀጥተኛ አስተያየት ሰጥታ ባታውቅም ጮክ ብላ  ‹‹ ሱዳን አደገኛ የአሸባሪዎች ሀገር ናት ! ›› ከማለት ግን ወደ ኃላ ብላ አታውቅም ፡፡ ሱዳንም ጠብ አጫሪዋንና ህገ ወጧን እስራኤል  እከሳለሁ እያለች ከመፎከር የዘለለ የተጨበጠ እንቅስቃሴ አታደርግም ፡፡ ይህም ‹ መድሃኒቱ › የተስማማት ወይም የታዘዘላት አስመስሎባታል ፡፡ ለነገሩ በ ‹ ICC › የሚፈለጉት አልበሽር ሌላውን ለመክሰስ ምን ሞራል አላቸው ?

ዞሮ ዞሮ ሱዳን አሸባሪነትንም ሆነ የአሸባሪዎችን ዓላማ መሾፈር የምትፈልግ ሀገር ከሆነች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በኢትየጽያ ጥቅሞች ላይ እጆቿን ትዘረጋለች ለማለት የሚያስችል መነሻ አይኖርም ?

ጉርብትና ለመቼ ነው ?

ሁለቱ ሀገሮች ተራ ጎረቤታሞች አይደሉም ፡፡ ከናይል ወንዝ ተመሳሳይ ውሃ ጠጥተዋል ፡፡ በአረብ ሊግ ስብሰባ ላይ በተመሳሳይ ቋንቋ አንድ አይነት ሀሳብ ያስተጋባሉ ፡፡ ሁለቱም የሮምን ስምምነት/ ICC / አልፈረሙም ፡፡ ፕሬዝዳንት አልበሽር የሙስሊም ብራዘር ሁድ አባል ናቸው ፡፡ የሙባረክ መንግስት ከወደቀ በኃላ ግብጽን የጎበኙ የመጀመሪያው መሪ ናቸው ፡፡ ሁለቱም ሀገሮች ዕድሜ ለቅኝ ገዢዎች ውል በናይል ውሃ ላይ ‹ Veto power › አላቸው ፡፡ ስድስቱ ሀገራት የፈረሙትን የእንቴቤ ስምምነት አይመለከተንም ብለዋል ፡፡ ሱዳን ለሁለት በመከፈሏ ሁለቱም ደስተኞች አይደሉም ፡፡

ሱዳን ለሁለት መከፈሏን ደግሞ ሀገራችን ትደግፋለች ፡፡ ይህ በራሱ ለመቃቃር አይነተኛ ጥንስስ ይፈጥራል ፡፡ የሁለቱን ሀገሮች የዘመናት የ ‹ Veto power › እንዲናድ የሰራቸው ኢትዮጽያ ገና ከጠዋቱ ትልቁን የስልጣን ካፖርት እያጠለቀች በመሆኑ አይሰማትም ማለት አይቻልም ፡፡ በ 25 ከመቶው የውሃ ድርሻዋ ደስተኛ ባትሆንም ዛሬ ትክክለኛ ድርሻሽ መቶ ሲካፈል ለአስር ሀገሮች ነው እየተባለች ነው ፡፡ የምክትል ሰብሳቢ ፈላጭ ቆራጭነት ሚናም አይኖራትም ፡፡ ይህ የመውረድና የመወራረድ ፖለቲካ የሚፈጥረው ግዜያዊ ራስ ምታትም ሚዛናዊ ብይኗን አያስትም ማለት አይቻልም ፡፡ እናም በተመሳሳይ ቀለም ከግብጽ ጋር ለመብረር ‹‹ ኩርሲ ›› ላይ መንደርደሪያ ሰርታ ጀባ ለማለት አቅዳ ከሆነስ ?

ከማያውቁት መልዓክ … ፤

የሱዳንን ግብጽ ግንኙነት እድሜ ጠገብ ቢሆንም የተመሰረተው በአሸናፊና ተሸናፊ፣ በአለቃና ምንዝር ምህዳር ላይ ነው ፡፡ 790 ማይልስ ርዝመት ያለው የድንበር ወሰን አጨቃጭቋቸዋል ፡፡ ሃይላንድ ትሪያንግል የተባለው ቦታ የሱዳን ነው ቢባልም ግብጽ በጡንቻዋ የራሷ አድርገዋለች ነው የሚባለው ፡፡ በዚህ የሚበሽቁት አልበሽር -  ሙባረክ አዲስ አበባ ለስብሰባ ሲመጡ በእጃቸው መዳፍ ውስጥ ካሉት አሸባሪዎች ጋር መክረው ሊያስገድሏቸው እንደነበር ተጠርጥሯል  ፤ እረ ተዘግቧል ፡፡

 ትንሽ ቆይቶ ደግሞ አልበሽር ‹ ግብጽ መንግስቴን ልትገለብጥ እያሴረች ነው › በማለት መጮህ ጀመሩ ፡፡ ይህን የሰሙት ሙባረክ ‹ ግብጽ የአንተን መንግስት መገልበጥ ብትፈልግ አስር ቀናት ብቻ ይበቃታል ! › ሲሉ አናዳጅና የበላይነታቸውን የሚያስረግጥ ምላሽ ሰጡ ፡፡ በነገራችን ላይ ግብጾች ይህን የመሰለ ጉራ በማምረት የሚተካከላቸው የለም ፡፡ በሀገራችን ግድብ ዙሪያም ማስተባበያ ሲሰጡ   ‹‹  የዲፕሎማሲያዊው ጥረት የማይሳካ ከሆነ ጀቶቻችን ግድቡን ደብድበው በአንድ ቀን ይመለሳሉ ! ›› ብለው ነበር ፡፡ እንዴት ነው ነገሩ እንደ እስራኤልም ያደርጋቸዋል ልበል ? እኛ የምናውቀው በስድስቱ ቀን ጦርነት እነሱ ፣ ሶርያና ጆርዳን በእስራኤል ታስረው መገረፋቸውን ነው ፡፡ ታዲያ ይህን በስድስት ቀን ፣ በአስር ቀን የሚባለውን ተሞክሮ ከየት አመጡት ?  ‹ ወገኛ ! › የሚባለው ሀገር የዚህ ዓይነቱ መሆን አለበት ፡፡ ያም ሆነ ይህ ሱዳን ከነጭቆናዬ የማውቃትን ግብጽ መደገፍ ስትራቴጂያዊ ርምጃ ነው ብትል ከልካይ የላትም ፡፡ ኢትዮጽያን ደግፋ ጀግና ከምትባል ለግብጽ አድራ ተቀምቻለው የምትለው መሬት እንዲሰጣት አሳዛኝ ማመልከቻ ብታስገባ ሊጠቅማት ይችላል ፡፡

የጉዳዩ መድረሻ ፤

ሱዳንና ኢትዮጽያ ከማህበራዊና ባህላዊ ትስስር አንጻር በተለይም የህዝብ ለህዝብ ግንኙነታቸው ጠንካራ ነው ማለት ይቻላል ፡፡ ከዘላቂ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥቅም አንጻርም ሱዳን ከኢትዮጽያ የኤሌትሪክ ኃይል እና ሰላማዊ የድንበር ደህንነት ትፈልጋለች፡፡ ኢትዮጽያ የሱዳንን ነዳጅ፣ ወደብና ገበያዋ በአማራጭነት ያስፈልጋታል ፡፡

በርካታ ኢትዮጽያዊያን በፖለቲካም ሆነ በኑሮ ሲንገፈገፉ ወደዚች ሀገር ማምራታቸውም ይታወቃል ፡፡ ሁለቱ ሀገሮች በቀለም፣ በቋንቋና ስነ ጥበብ ይመሳሰላሉ ፡፡ በተለይም የስዕል፣ ዳንስ፣ ቅርጻ ቅርጽና ሙዚቃ ስራዎቻቸው  የተቀራረቡ ናቸው ፡፡ ታዋቂዎቹ ሳኢድ ከሊፋና መሃመድ ዋርዴ ሀገራችንን እንደ ቤታቸው በመቁጠር ጣፋጭ ስራቸውን አስኮሙኩመውናል ፡፡ በተለይም ሳኢድ ከሊፋ

‹‹ ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ከሱዳን መጣን ልናያችሁ … ›› በማለት ውስጣችንን ኮርኩሮታል ፤ እኛንም መስሏል፡፡ በብዙዎቻችንም ክብርና ሞገስ አግኝቷል ፡፡ ታዲያ ይቺ ቅርብ የመሰለች ሀገር እውነት ዛሬ ፊቷን እያዞረችብን ፣ በፖለቲካም ቋንቋ እያሴረችብን ነው ? ነው ወይስ የጠላት ወሬ ነው ? እውነት ከሆነማ የቀጣዩ ‹ ሲንግል › ግጥም ቁልጭ ብሎ ይታየኛል ፡፡ ….

‹‹ ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ከግብጽ ጋር አበርንባችሁ
  ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
  ‹ ኩርሲ › ላይ መሸግንባችሁ
   ጤና ይስጥልኝ እንደምናችሁ
   በናይል ጉዳይ ከዳናችሁ
   ጤና ይስጥልኝ ….

 እነሆ ሱዳን የምንሰማው ሁሉ እውነት ከሆነ ትጣሊናለሽ ፤ ማርያምን አንለቅሽም !! ከዚያ በኃላ ለቁጥር የሚታክተውን የሽለላና የቀረርቶ ዜማችንን ምንጭ እየጠቀስሽ እንደሚከተለው ታዜሚልን ይሆናል
1.
ደሞ፣ደሞ፣ደሞ ግለሌ
ገስግሶ ገዳይ በሰው ቀበሌ
ግለሌ ምሳው ግለሌ እራቱ
መለቃለቂያው ደም ራጨቱ
ገለል በሉለት አንድ ግዜ ለእሱ
ግልግል ያውቃል ከነፈረሱ
2.
የፍየል ወጠጤ ትከሻው ያበጠ ልቡ ያበጠበት
እንዋጋ ብሎ ለነብር ላከበት
የማትረባ ፍየል ዘጠኝ ትወልዳለች
ልጆቿም ያልቃሉ እሷም ትሞታለች
እረ ጎራው - ጎራው እረ ደኑ - ደኑ ...



No comments:

Post a Comment