Wednesday, June 20, 2012

‎የዶክተር ያዕቆብ ኃይለማርያም በልሃ



አሰብ የማን ናት ?

ይህ ጥያቄ የተጠየቀው ከግንቦት 1983 በፊት ቢሆን አብዛኛው ምላሽ  ‹‹ የኢትዮጽያ ! ›› የሚል ይሆን ነበር ፡፡ ሻዕቢያና ኢህአዴግ ደግሞ ከጫካቸው ሆነው የተለየና የሰለለ ድምጽ ያሰማሉ ፡፡
ጥያቄው የተጠየቀው ግን በ2003 ዓ.ም ሆነ ፡፡
ጠያቂው ዶክተር ያዕቆብ ኃ/ማርያም ናቸው ፡፡
አጠያየቁ ይፋዊ ነው ሊባል ይችላል - በመጽሀፍ መልክ ስለወጣ ፡፡

እና ምን ምላሽ አለ ?

ሻዕቢያና ኢህአዴግ ከከተማ ሆነው ደማቅና ይፋዊ ምላሽ ሰጥተዋል ፡፡ ‹‹ የኤርትራ ! ›› በማለት ፡፡ ቁጥሩን በቀላሉ ማሰላት የሚያስቸግር  ህዝብ  ልብ ውስጥ   ‹‹ የኢትዮጽያ ነበረች ?! ›› የሚል የሰለለ ድምጽ ይሰማል፡፡  ድምጸቱ  የፈሰሰ ውሃ አይታበስም የሚባለውን ብሂል የሚያቀነቅን ይመስላል ፡፡ ሀገራችን ውስጥ የነበሩ ጠንካራ ፓርቲዋች ምርጫ በመጣ ቁጥር አሰብን ወደ ኢትዮጽያ ግዛት ለመመለስ እንደሚጥሩ በክርክራቸው ወቅት ያሰሙ ነበር ፡፡ እና ቢያንስ  አሪፍ ቴርሞሜትሮች ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ የባህር በራችን … ባሉ ቁጥር የብዙዋች የሙቀት መጠን ጣራ ያልፍ ነበርና፡፡ ይህን መለኪያ አጥኚዋች እንደ አንድ ግብዓት ቢያስተውሉት ሊጠቅም ይችላል፡፡

ዶ/ር ያዕቆብ የአሰብ ጉዳይ የፈሰሰ ውሃ ውሃ ሳይሆን የተዳፈነ እሰት ነው ባይ ናቸው ፡፡ ከኤርትራ ጋር በቦሌም ሆነ በባሌ የማትገናኘው አሰብ በስጦታነት የቀረበችው  ኢ-ፍትሃዊ በሆነ አግባብ ነው ይሉናል፡፡ አሰብን ማጣትና የባህር በር ተጠቃሚ አለመሆን በኢኮኖሚ፣ በዲፕሎማሲና በጦርነት የሚያስከትለውን ተጽእኖ ይተነትናሉ፡፡ የኢትዮጽያን የባህር በር ባለቤትነት ታሪክ ሳያወላዳ የሚመሰክር ሲሆን በተለያዩ ግዜያቶች በወራሪዋች ቦታው ሲያዝ ከአጼ ቴዋድሮስ ጀምሮ እስከ መንግስቱ የተደረጉ ያላሰለሱ ጥረቶችን በምሳሌነት ያቀርባሉ፡፡ በአልጀርስ ስምምነት ወቅት ኢትዮጽያ የባህር በር የማግኘት እድሏ ሰፊ የነበረ ቢሆንም ፍላጎት ባለማሳየቷ እንዳማረን ቀርቷል ሲሉም ይቆጫሉ ፡፡

እንግዲህ የዶ/ር ያዕቆብ የ ‹‹ አሰብ የማን ናት ? ›› ጥያቄ የተወረወረው ጉዳትን፣ መብትን፣ ታሪክን  ከሁሉም በላይ የህግ ጽንሰ ሀሳብን በማዘል ነው ፡፡ በ13 ምዕራፍ የተዋቀረው ይህ መጽሀፍ ኃይለኛ አጠያያቂ ሙግቶችን ይዟል ፡፡ እንተንትነው ፤

ኢኮኖሚያዊ በልሐ ፣

በቦሃ ላይ ቆረቆር እንዲሉ እቺ ከድህነት ተርታ የተሰለፈች ሀገር ዛሬ በቀን ሶስት ሚልዮን ዶላር ለጅቡቲ ወደብ ኪራይ ትከፍላለች ፡፡ ይህ አኀዝ እውነት ከሆነ ትንፋሽን ቀጥ ሊያደርግ አሊያም አጥወልውሎ ሊደፋ ይችላል ፡፡ ይህን ቁጥር በ265 ቀናት ስናባዛው 795 ሚሊዮን ዶላር ይሰጠናል ፡፡ ይህን የሚያሰጎመጅ ዶላር በጥቂቱ በ17  ስናበዛው ቁልጭ ያለ 13 ቢሊዮን 515 ሚሊዮን የኢትዮጽያ ብር እናገኛለን፡፡

የሀገራችን የ2005 በጀት 137.8 ቢሊዮን ብር ነው ፡፡ እንግዲህ ለወደብ የሚከፈለው ገንዘብ የበጀቱን አስር ከመቶ ያህል ይቆርሳል ማለት ነው፡፡ ቋንቋችንን ወቅታዊ እናድርገው ካልን የወደቡ ክፍያ በስድስት ዓመት ውስጥ የሚሊኒየሙን ግድብ ወጪ ይሸፍናል፡፡ ዶ/ር ይዕቆብ ደግሞ ሃያና ሰላሳ ፋብሪካዋችን ሊገነባ ይችል ነበር ይሉናል፡፡ ቻውድሪ እና ኤርዳነቢልግ የተባሉ ምሁራን ባደረጉት ጥናት ወደብ አልባ አገሮች በኢኮኖሚ ዕድገት በ1 ከመቶ ወደብ ካለው አገር ወደ ኃላ ይቀራል፡፡ ይህ ማለት ወደብ ያለው አገር በ24 ዓመት ውስጥ ኢኮኖሚው በእጥፍ እንዲያድግ 36 ዓመታት ይፈጅበታል፡፡

ሌላው ነጥብ የወደብ ርቀትን ይመለከታል፡፡ በመሰረቱ ለኢትዮጽያ ከሞምባሳ፣ ፓርት ሱዳን፣ ሞቃዲሾ፣ በርበራና ከጅቡቲ ይልቅ ይቀርባት የነበረው የአሰብ ወደብ / ከአ.አ 624 ኪ.ሜ / ነው፡፡ በሌለ ነገር ላይ ማውራት አጉል ግፍ ነው ካልተባለ በስተቀር የወደብ ርቀት መፈጠር በኢንቨስትመንት ላይ  ተጽዕኖ ይፈጥራል፡፡ በሀገራችን የኢንዱስትሪም ሆነ የእርሻ ውጤቶች የሚመረቱት በመሃልና በምዕራብ የሀገሪቱ ክፍል ስለሆነ ምርቶችን ወደ ወደብ ለማዝለቅ ብዙ ወጪ ይጠይቃል፡፡ ስለሆነም ከባድ ዕቃ ለማምረት ለሚፈልግ ኢንቨስተር ወደብ አልባዋ ኢትዮጽያ የመጀመሪያ ምርጫ አትሆንም፡፡

የበልሃው ምላሽ፣

በአንድ ወቅት ጠ/ሚ መለስ ለዶ/ር ያዕቆብ ስጋት ለሆነው ሃሳብ ቀጣዩን ምላሽ ሰጥተዋል  ‹‹ ወደብ አለመኖሩ ረሃብ አያመጣም፡፡ በጎረቤት ሀገር ወደብ በመጠቀም መስራት ይቻላል፡፡ ያለ ነገር ነው፤ ስለዚህ ኢትዮጽያ ያለ ወደብ ቀረች ብለን የምንቆጭበትና የምናዝንበት ምክንያት የለም፡፡ ወደብ አለመኖሩ አይጎዳንም ፣ ሊጎዳንም አይችልም፡፡ ወደብ በነበረን ግዜ ኢትዮጽያ ድሃ ነበረች ፡፡ አሁን ወደብ የለንም፡፡ ዕድገት ግን እያስመዘገብን ነው ››

ዲፕሎማሲያዊ በልሃ፣

አረቦች ከብዙ ግዜ ጀምሮ ብቸኛ የቀይ ባህር ተቀናቃኛቸው የነበረችውን ኢትዮጽያ ከባህሩ አካባቢ አግልለው ቀይ ባህርን የአረብ ሃይቅ ለማድረግ ሲታገሉለት የነበረውን ዓላማቸውን አሳክተዋል፡፡ ዶ/ር ያዕቆብ በቀይ ባህር በተለይ በአሰብ የኑክሌር መሳሪያ ቢጠመድበትና የጠላት ጦር ቢሰፍርበት፣ ለህልውናችን ስጋት የሚፈጥር ሁኔታ ቢጠነሰስ  ልታደርገው የምትችለው ነገር አይኖርም ይላሉ፡፡

ወታደራዊ በልሃ ፣

ግራና ቀኝ በጠላት የተከበበቸው ኢትዮጽያ ራሷን ለመከላከል የሚያስችል የጦር መሳሪያ ከውጭ በባህር ማስገባት የግድ ይላታል፡፡ ይሁን እንጂ ባለ ወደብ ሃገሩ ከፈለገ ይህን ያህል ብቻ ይበቃሃል ብሎ ማስተላለፍ ላይ ገደብ ሊጥልበት ይችላል፡፡ እናም የሉዓላዊነት ገዳይ ዘወትር በቋፍ ላይ ይንጠለጠላል ማለት ነው ፡፡

ወረራም ሌላው ስጋት ነው ፡፡ ጄኔራል ናፒዮር አጼ ቴዋድሮስን ለመውጋት ወደ ሀገራችን የገባው በቀይ ባህር ወደብ ነው፡፡ ወራሪዋች ከስትራተጂክ አንጻር ከየብሱ ባህሩን ይመርጣሉ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የቀለለ ስለሆነ ነው ፡፡ ዶ/ር ያዕቆብ በስፋት ያነሱት ሌላው ነጥብ የባህር በር ባለቤትነትን ይመለከታል፡፡ ይህም አሰብ የኛ አይደለችም የሚሉ ወገኖችን ጠንከር ያለ መረጃ ለመስጠት አሊያም የተጨፈነ ልቦናን ገርበብ ለማድረግ ያለመ ይመስላል፡፡

ኢትዮጽያን የባህር በር ባለቤት ያደረጓት አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ናቸው፡፡ ግዜው ደግሞ ከ1434- 1468 መሆኑ ነው፡፡ ከዚያም በኃላ በቱርኮች፣ ግብጾችና ሌሎች መቀማማቱ ቀጥሎ ነበር፡፡ እንግሊዝ፣ ፈረንሳይና ጣሊያን አፍሪቃን ለመቀራማት ሰፊ ዘመቻ ካካሄዱ በኃላ ደግሞ ጠንከር ያሉ ችግሮች ተከስተዋል፡፡ በተለይም ጣሊያን በእንግሊዝ ሃይ ባይነት ያለምንም መከላከያ ትገኝ የነበረችውን ምጽዋ በ1885 ዓ.ም በቁጥጥር ስር አደረገች፡፡ ኮሎኔል ሳሌታ 802 ወታደሮችን ብቻ ይዞ ነው የገባው፡፡ ይህ ማለት እንግዲህ ቄስ ጁሴፔ ሳፒቶ የተባለ ጣሊያናዊ አሰብን አሁንም ያለማንም ከልካይ ከገዛ ከአስር ዓመታት በኃላ የተፈጸመ ነው፡፡ ይህ ቄስ ለሩባቲኖ ኩባንያ አሰብንና አካባቢውን በ8100 ማርያ ቴሬዛ የገዛው ከአካባቢው ሱልጣኖች ኢብራሂምና ሱልጣን ሀሰን በን መሀመድ ነበር፡፡ አሰብን ከነነፍሷ ሲሸጡ በሙቀቱ ምክንያት ብዙም ክትትል የማያደርገው የኢትዮጽያ መንግስት አያውቅም ነበር፡፡ አሰብ በወቅቱ ትስስርዋ ከወሎ እንጂ ከኤርትራ ጋር አልነበረም፡፡

እናም ጣሊያኖች ግዛታቸውን በማጠናከር  ‹‹ የአሰብ የኢጣሊያ  ቅኝ ግዛት ››  ይባል የነበረውን ስያሜ በመሻር  ‹‹ በቀይ ባህር የኢጣሊያ የቅኝ ግዛቶች ››  በሚል አሻሻሉት፡፡ የአሰብና የምጽዋ ግዛቶቻቸውን በማጠቃለልም በ1890  ‹‹ ኤርትራ ››  የሚል ስም ሰጥተው ቅኝ ግዛት መሰረቱ፡፡ ጣሊያኖች ለግዛታቸው ሲሉ ሁለት በባህል፣ ቋንቋ፣ ዘር ወዘተ የማይገናኙትን ሀገሮች በመጨፍለቃቸው እነሆ እስከዛሬም ግርታና ክርክር እንዲቀጥል አድርገዋል፡፡
በርግጥ ኢትዮጽያ የሰሜን ግዛቶችዋና ጠረፎቿ በ1895 ዓ.ም በቱርኮች፣ በግብጾች፣ በጣሊያኖችና በፈረንሳዮች ሴራ ከተያዙባት ግዜ ጀምሮ የባህር በሮችዋን ለማስመለስ ከፍተኛ ጥረት አድርጋለች፡፡

ማስረጃ - ቴዋድሮስ፣

አጼ ቴዋድሮስ እኤአ በ1855 ለንግስት ቪክቶሪያ ደብዳቤ ጽፈው ነበር፡፡ ‹‹ ቱርኮች የአባቶቼን መሬት ልቀቁ ብላቸው እምቢ ብለውኝ በእግዚአብሄር ኃይል ይኀው ልታገል ነው …. ››

ማስረጃ - ዮሐንስ ፣

አጼ ዮሀንስ አራተኛ ስልጣን ላይ ሲወጡ የባህር በሮችዋ በወራሪዋቹ ተነጥቆ ሙሉ በሙሉ ወደብ አልባ ነበረች፡፡ እሳቸው ሰኔ 10 ቀን 1872 ለእንግሊዝ ንግስት የእርዳታ ደብዳቤ ጽፈው ነበር፡፡
‹‹ …. ጥንቱንም በእግዚአብሄር ፈቃድ ለመንግስት የበቃሁት እርስዋ በሰጡኝ መድፍ፣ ነፍጥና ባሩድ ነው፡፡ ….. የምጽዋ በር የአባቶቼ የነገስታት ኢትዮጽያዊያን ነው፡፡ አሁንም በእርስዋ ወኪልነት እርዳታ የምጽዋን እንድይዝ ያድርጉልኝ ብዮ እለምናለሁ …. ››

ማስረጃ - ሚኒሊክ ፣

ሚኒሊክ የግዛታቸው መጠንና የሀገሪቱ ወሰን የት ድረስ እንደሚያካልል ለዓለም መንግስታት ለማስታወቅ ለንግስት ቪክቶሪያ  ‹‹ ከሃምቦሳ አንስቶ የአስልን ባህር ጨምሮ የጥንት ዜጋችን የሞሀመድ ሃንፍሬን / አፋርን ያስተዳድሩ የነበሩ / ግዛት ሙሉ ይዞ እየሄደ አረፋሊ ይደርሳል ››  የሚል ደብዳቤ ጽፈው ነበር ፡፡

በንግስት ዘውዲቱ፣ በአጼ ሃይለስላሴና በመንግስቱ ኃ/ማርያም ስርዓትም የባህር በርን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ስራዋች መሰራታቸውን የዶ/ር ያዕቆብ መጽሀፍ ይተርካል፡፡ ዞሮ ዞሮ ኤርትራ በ1952 ዓ.ም በኤርትራ ህዝብ ተወካዮች ፍላጎትና በተመድ ውሳኔ ከኢትዮጽያ ጋር በፌዴሬሽን ስትቀላቀል ለዘመናት ትግል ሲደረግለት የነበረው የባህር ጥያቄም ምላሽ አገኘ፡፡ ፌዴሬሽኑ ፈርሶ ውህደት ሲደረግ ሁለቱም ወደቦች የኢትዮጽያ ሉዓላዊ ግዛት ሆኑ፡፡ ይህ ድል በተገኘ በማግስቱ ግን የፌዴሬሽኑ መፍረስ የኤርትራን የመገንጠል ጥያቄ አስነስቶ ሻቢያ፣ ጀብሃ በኃላም ህወሃት ከኢትዮጽያ ነጻ ለመውጣት የትጥቅ ትግል ጀመሩ፡፡
እንግዲህ እነዚህን ጥረቶች ነው ህውሃትና ኢህአዴግ ለመሰረዝና ከናካቴው ለማጥፋት ሲታገሉ የነበሩት ይሉናል - ዶ/ር ያዕቆብ ፡፡ በተለይም አቶ መለስ በ1979 ኤርትራን አስመልክቶ በጻፉት መጽሀፍ ኤርትራ የኢትዮጽያ ቅኝ ግዛት ነች ማለት ትክክለኛና ሳይንሳዊ ነው … ኢትዮጽያ የ3 ሺህ ዓመት ታሪክ የላትም በማለት በግልጽ ጽፈዋል፡፡ በዚህ አባባል ኢትዮጽያ የአክሱም ወራሽ ልትሆን አትችልም፡፡ ጥንታዊ የባህር በርም ሊኖራት አይችልም ፡፡

በመሆኑም ህወሃት/ኢህአዴግ የኤርትራን መገንጠል የደገፈው ኤርትራ የኢትዮጽያ ቅኝ ግዛት ነች ከሚል እምነት በመነሳት ነው፡፡ የአፍሪካ መሪዋች በካይሮ ጉባኤ ያሳለፉት የድምበር ውሳኔ የአፍሪካ አገራት ነጻ ሲወጡ በቅኝ ግዛት ግዜ የነበረው ወሰን ተከብሮ ነው ይላል፡፡ ኢህአዴግ ከዚህ አባባል ጋር መመቻቸቱም ተገልጾል፡፡

በርግጥ ዶ/ር ያዕቆብ ቅኝ ግዛትን በተመለከተ ትልቅ ጥያቄ አንስተዋል፡፡ የቅኛ ገዢዋች ዓላማ በተገዢዋቹ ኪሳራ ለመበልጸግ፣ የሃይማኖትና የፓለቲካ እምነታቸውን ለማሰፋፋት፣ ባህልና ስብዕናቸውን ለማንቋሸሽ፣ የጌታና የሎሌ ግንኙነት እንዲመሰረት ማድረግ ነው፡፡

ታዲያ በሁለቱ ሀገሮች የነበረው ግንኙነት ከላይ የተገለጸውን ብይን ይመስል ነበር ? ኢትዮጽያዊያን የትኛውን የኤርትራዊያን መሬት ነው የቀሙት ?  ከዚህ  ይልቅ በፍቅር  ተዋልደው ኖረዋል፡፡ ኤርትራዊያን ባላቸው አቅም ሁሉ ከፍተኛ ስልጣን አግኝተዋል፡፡ እናም የኢትዮጽያ አካል የነበረችውን ኤርትራ ቅኝ ግዛት ነበረች ማለት ትንሽ እውቀት አደገኛ ነው ከሚባለው አባባል የመነጨ ነው ይላሉ - ዶ/ሩ፡፡

ኢትዮጽያ ከኤርትራ ጋር ጦርነት አድርጋ ካሸነፈች በኃላ ወታደራዊ ጠቀሜታ ያላቸውን ቦታዋች ይዛ ነበር ፡፡ በዓለማቀፍ ህግ ደግሞ ተወራሪ ሀገር ጠላቱን ካሸነፈ በኃላ ግዴታ ውስጥ ማስገባት የሚችልበት አጋጣሚ አለ፡፡ ከዚህ ግዴታ አንዱ የአሰብን የባህር በር ማስመለስ ሊሆን ይችል ነበር፡፡ ይህ ግን እንዳይሆን ተድርጓል፡፡ እንደውም በአልጀርስ ስምምነት አሰብና ሌሎች ቦታዋች ለእኛ እንዳይወሰኑ ብዙ ስህተቶች ሆን ተብለው እንዲፈጠሩ ተደርጓል ባይ ናቸው፡፡

-       ስምምነቱ የተፈረመው  ኢትዮጽያና ጣሊያን በ1900፣ በ1902 እና በ1908 በተፈራረሟቸው የቅኝ ግዛት ውሎች መሰረት ነው፡፡ በወቅቱ አጼ ሚኒሊክ ውሉን የፈረሙት ተገደውና ጫና ውስጥ ገብተው ነበር፡፡ እንዲህ ዓይነት ስምምነት በህግ ፊት ዋጋ እንደሌለው እየታወቀና ለማሸነፍ አማራጭ መፍትሄዋችን መጠቀም እየተቻለ በዛው ውል እንከራከራለን ተብሏል፡፡ ይህም አሰብን ለኤርትራ የሰጠ ምቹ ስምምነት አድርጎታል፡፡

-       በስምምነቱ ወቅት ኢትዮጽያን ከወከሉት ተደራዳሪዋች መካከል በህግ አማካሪነትና በጥብቅና ዘርፍ የተሰማራ ኢትዮጽያዊ ሰው አልነበረም፡፡

-       የድርድሩ  ዋና  አጋፋሪ ሚስተር አብዱል አዚዝ ቡተፍሊካ አልጄሪያ ከሻቢያና ከጀብሃ ጋር ለነበራት ግንኙነት ፓሊሲ ቀራጺና ለኤርትራ መገንጠል ሌት ተቀን የሰሩ ሰው መሆናቸው እየታወቀ በዝምታ ታልፏል፡፡

-       የድንበር ውዝግብ በሚፈጠር ግዜ ሀገሮች ጉዳያቸውን ወደ ዓለም አቀፍ ፍ/ቤት ይወስዳሉ፡፡ ይህ ፍርድ ቤት በቅኝ ግዛት ውሎችን ብቻ ሳይሆን ዓለማቀፍ ስምምነቶችን፣ የተደረጉ ውሎችን፣ የፍርድ ቤት ውሳኔዋችን ፣ የህግ ልሂቃን የጻፏቸውን ጽሁፎች በሙሉ ይመለከታል፡፡ ሂደቱ ባለቀ ግዜ ያልቃል እንጂ አያጣድፍም ፡፡ሆኖም ወደዚህ ፍ/ቤት መሄድ አልተፈለገም ፡፡

ዶ/ር ያዕቆብ እነዚህን ማስረጃዋች አንድ ሁለት እያሉ ይዘርዝሩ እንጂ በመንግስት በኩል አሰብን በተመለከቱ የተሰጡ ምላሾች የማያወላዱ ናቸው፡፡ የአሰብ ወደብ የኤርትራ ሉዓላዊ ግዛት በመሆኑ የኛ ጥያቄ ውስጥ የለም የሚል፡፡

መጽሀፉ በመጨረሻው ምዕራፎች አማራጮችን ይገልጻል፡፡ ከአማራጮቹ አንዱ አሰብን ሁለቱም ሀገሮች በጋራ ይዘውት ሁለቱም ጣምራ ሉዓላዊነት / joint sovereignty / እንዲኖራቸው ሊስማሙ ይችላሉ የሚል ነው ፡፡ ለዚህም ደግሞ ህንድና ፓኪስታን የሚፋጠጡበት የካሽሚር ግዛት፣ ፈረንሳይና ስፔን ለ700 ዓመታት የሚያስተዳድሯትን አንዶራ የተባለች ሀገር በምሳሌነት ያስረዳሉ፡፡

የዶ/ር ያዕቆብ በልሀ ልበልሃ ፣

ኢትዮጽያ የባህር በርዋ አሰብ እስካልተመለሰላት ድረስ ኢህአዴግ ከየትኛውም በጎም ይሁን መጥፎ ስራዋች የባህር በር ማዘጋቱ ከሁሉም በላይ ጎልቶ ይወጣል፡፡ አሰብ ለኢትዮጽያ እስካልተመለሰ ድረስ ዘመናት አልፈው ዘመናት ሲተኩ በግዜው ኢህአዴግ ማን ነበር ሲባል መልሱ መንገዶችን፣ ት/ቤቶችን ወይንም ሀኪም ቤቶችን ያነጸው አይሆንም ፡፡ መልሱ የኢትዮጽያን የባህር በር ያዘጋው መንግስት ነው የሚሆነው፡፡

እውነት ይህ ጥያቄ በይርጋ ይታገዳል ?
እውነት ይህ ጥያቄ ከመጠየቅ ያመልጣል ?
እውነት ይህ ጥያቄ የተለየ ምላሽ ያገኛል ?










No comments:

Post a Comment