Sunday, October 14, 2012

‎ዋሊያዎቹ ከተራራ ወረዱ‎




‹‹ የቆየ ከሚስቱ ይወልዳል ይሉሃል ይሄ ነው ›› ብሄራዊ ቡድናችን ዋሊያዎቹ ከ 31 ዓመታት ቆይታ በኃላ ለአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ አለፉ ፡፡ ይህን አባባል በሌላ ቅርጽ መድገም ያስፈልጋል  ‹‹ ዋሊያዎቹ ከ31 ዓመታት ቆይታ በኃላ የአፍሪካን ዋንጫ አሸነፉ ሳይሆን መከራ የሆነባቸውን የማጣሪያ ግንብ ደርምሰው አለፉት !! ›› ማጣሪያን የደፈረ ቡድን ማለት እንችላለን ፡፡

ኩሩው፣ አይናፋሩና ግርማ ሞገስ የተቸረው ዋሊያ በኢትዮጽያ ለዛውም በሰሜን ተራራዋች  ብቻ የሚገኝ አጥቢ እንስሳ ነው ፡፡ ይህን ብርቅ እንሰሳ ለመጎብኘት ከመላው ዓለም ወደ ሀገራችን የሚያቀናው ቱሪስት ቁጥር ቀላል አይደለም ፡፡ ግና ቱሪስቶቹ እንደ ጅብ፣ የሜዳ አህያና ሌሎቹም እንስሳት በቀላሉ በቅርበት ስለማያገኙት ትንፋሽ የሚያሳጥረውን የሰሜን ተራራዋች መውጣት ይጠበቅባቸዋል ፡፡ ዋልያዋች በአብዛኛው የሚኖሩት ከ 2500 ሜትር በላይ፣ ከ 4000 ሜትር በታች በሆኑ አካባቢዎች መሆኑ ይታወቃል ፡፡

ዋሊያ በዚህ ባህሪው እሱ ተራ ወደሚለው ‹ ሜዳማ ስፍራ › ለመውረድ ፍቃደኛ ሳይሆን ህይወቱን ይገፋል ፡፡

የብሄራዊ ቡድናችን ‹ ዋሊያም › ለ31 ዓመታት የአፍሪካም ሆነ የዓለም ዋንጫ አይመቸኝም የሚል የመሰለ አስተሳሰብ ወዶም ይሁን ተገዶ በማዳበሩ ‹‹ ብርቅና በኢትዮጽያ ብቻ የሚገኝ ብሄራዊ ቡድን ›› የሚል ቅጽል እስከማግኘት ደርሶ ነበር ፡፡ በርግጥ እንደ ቀንዳሙ ዋሊያ የሚጎበኙት ነጫጭ ሰዎች አልነበሩም ፡፡ በዚህ የተደፋፈሩት እነ ሶማሊያና ትናንሽ ቡድኖች ሁሉ ባገኙት ቁጥር የሚያቃጥል ጥፊና የሚያሳክክ ኩርኩም ሲያቀምሱት ቆይተዋል ፡፡ ህመሙ ቢጋባብንም ላለው ይጨመራል እንዲሉ ‹‹ ይሄ ውሽልሽል ! አሰዳቢ ! ወኔ ቢስ ! ቡድን ›› እያልን በጎን አገጩን ስናጣምም ነበር ፡፡

ዛሬ ተመስገን ሆነ ፡፡

‹ ቀንዳሙ ዋሊያ ታች ወርዶ የማይታየው ከስነ ፍጥረታዊ ግዴታው አኳያ ነው ፡፡ ታዲያ የኔ ተራራ ላይ መቆለል ምን ሊረባኝ ነው ? ተራራ ላይ ከመኖር አስተሳሰብን ተራራ ማሳከል ይሻላል › የሚል ጥሞና ውስጥ ቆየ ፡፡ ይኀው ስድቡን፣ ኩርኩሙን፣ ቁጭቱን በጉያው ይዞ የምሽት ድል አበሰረ ፡፡

በዚህም ምክንያት የአበሻ ምድር ቀውጢ ሆኖ አመሸ ፡፡ ህዝቡ አበደ ፡፡ ከመናገር ይልቅ መጮህ መረጠ ፡፡ መንገድ ሞልቶ እንዳለቀሰ ሁሉ መንገድ አጣቦ ጨፈረ ፡፡ ብርጭቆ እያጋጨ ዘመረ ፡፡ ከመተቃቀፍ  ይበልጥ አስፋልት ላይ ተንከባለለ ፡፡ ቀሪው ዓለም ‹ የኢትዮጽያ ህዝብ ምን ዓይነት ወገኛ ቢሆን ነው ለማጣሪያ እንዲህ መጠን የሚያልፈው ? › ቢል ‹ በሰው ቁስል እንጨት አይሰደደም ! › ብሎ ለመመለስ ግዜ ያጣረው መስሏል ፡፡  ‹ እረ እንደ አሪፎቹ ዋንጫ ቢያነሳ ምን ሊያሳየን ነው ? › የሚል አሽሙር ንፋሱ ቢያደርሰው የፍቅሩን፣ የአንድነቱን፣ የደስታውን፣ የድል ናፍቆቱን፣ የጥቃቱን ልክ በሀገርኛው ቀመር ለማስረዳት እንደሚያስቸግረው ይገመታል ፡፡

ሀገሬው ግን እንደ ዉጩ አይደለምና ራሱን ‹ ቃሉን የደፈረ ተመልካች ! › ብሎ የሳሳ ትከሻውን በኒሻን ሊያጥለቀልቀው ይችላል ፡፡ አምስት ጎል የገባበትን ቡድን ‹ ታሸንፋለህ ! › ብሎ ያነቃውና ያበረታታው እሱ ነውና ፡፡

እነሆ ዋሊያዎቹ ከተራራ ወረዱ ፡፡

አዲስ ታሪክ ሰሩ ፡፡

ለካስ ዋሊያ ሜዳ ላይም ሮጦ ማሸነፍ ይችላል ፡፡

ነገና ከነገ ወዲያ ደግሞ በነጮች ብቻ ሳይሆን በጥቁሮችም ቱሪስቶች ይታያሉ ፡፡

No comments:

Post a Comment