Wednesday, April 3, 2013

ፓራdox







ኮሌጅ ገብተው ስነ ጽሁፍ የሚማሩ ተማሪዎች ለ ‹‹ PARADOX ›› ‹‹ አያዎ ›› የሚል ትርጉም ይሰጡታል ፡፡ ‹ አይ › እና ‹ አዎ › እንደማለት ፡፡ መዝገበ ቃላታችን ደግሞ እንደወረደ ‹‹ ርስ በርሱ የሚጋጭ ›› በማለት ይበይነዋል ፡፡

የስነ ጽሁፍ ጉዳይ በእግረ መንገዱ ከተነሳ የሶስት ምርጥ ደራሲያንን ‹‹ አያዎ ›› ሀረጎች ማስታወስ ለርዕሰ ጉዳያችን ቅመምነት ሳይጠቅም አይቀርም ፡፡ አየርላንዳዊ ጸሀፊና ገጣሚ ኦስካር ዋይልድ ‹‹ I can resist anything but temptation ›› የሚላት ነገር አለችው  ፡፡ ዊሊያም ሼክስፒር በሃምሌት ላይ ‹‹ Be cruel to be kind ›› ሲል እናገኘዋለን ፡፡ ጆርጅ ኦርዌል በአኒማል ፋርም ላይ ‹‹ All animals are equal, but some are more equal than others ›› ሲል ይቀኛል ፡፡

የሶስቱንም ታዋቂ ብዕረኞች አባባል ስንመረምር ጥልቅ ትርጉም የያዙ መሆናቸውን እንረዳለን ፡፡ ሶስቱም ብዕረኞች በአሽሟጣጭና ግራ ገብ በሆነ ስራዎቻቸው የተጠቃና የቆሰለ አንጀትን በቅቤ ለማራስ የገዘፈ አቅም አላቸው ፡፡

ጥናት ቢያስፈልገውም ‹ paradox › በድሃና የሶሻሊዝምን ስርዓት በሚከተሉ ሀገሮች / ምስኪን ህዝቦች / ይበልጥ የሚበዛ ይመስለኛል ፡፡ በኛ ሀገር ተጨባጭ ሁኔታ ደግሞ ፓራዶክስ ‹‹ በየዓይነቱ ›› እንደማለት ነው ፡፡ በውዴታ ግዴታችን የምንመርጠው ፡፡

ወጋችንን  በአንድ ሁለት ቆጠራ ለማሳመር  ወደ ጉሮሮ የሚወረወር ነገር እንያዝ ፡፡ ብሂሉም ነገር በምሳሌ ጠጅ በብርሌ አይደል የሚለው ፡፡

አንድ  .

በቅርቡ በሚከናወነው የወረዳና የክልል ምክር ቤቶች ምርጫ በርካታ ተቃዋሚ ድርጅቶች ‹‹ የምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አሰራር አልተመቸንም ›› በሚል ምክንያት ለራሳቸው ቀይ ካርድ አሳይተዋል ፡፡ ምርጫ ቦርድ በየሰፈሩ ግድግዳ ላይ የለጠፈው የተወዳዳሪዎች ስምም የሚጠቁመው  ከ90 እስከ 95 ፐርሰንት የሚሸፍኑት ዕጩዎች የተገኙት በኢህአዴግ አቅራቢነት ነው ፡፡ 

በኢህአዴግ በኩል የሚታየው የምረጡኝ ቅስቀሳ መጠን ሰማይ ጥግ መድረሱ ግን ሳያስገርም አይቀርም ፡፡
መቼም እንደ ዘንድሮ  በተወዳዳሪዎች ማነስ በእጅጉ ኮስምኖና ገርጥቶ የታየ ምርጫ መኖሩ ያጠራጥራል ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ መልካም ፍቃድ እንደ ዘንድሮ ምርጫ ለተቃዋሚ ድርጅቶች መቀስቀሻ የሚውል ሰፊ የአየርና የህትመት ግዜ ተሰጥቶ አያውቅም ፡፡ 50 ከመቶ ፡፡ ይህን ቁጥር የሰሙ የተወሰኑ ተቃዋሚዎችም ቋንቋ እየቀያየሩ ‹ አስገራሚ ነው › ‹ fair ነው › ሁሉ ብለውታል ፡፡

ሁለት .

ህንጻና መንገድ እያበዛች የምትገኘው አዲስ አበባ አስጸያፊ ቆሻሻዋንም እንደ ኩይሳ ከመቆለል ወደ ኃላ አላለችም ፡፡ በአዲስ አበባ መንደሮች ውስጥ ስታልፉ ለቆሻሻ ማስወገጃ የተሰሩት ፍሳሾች የሚሰቀጥጥ ክርፋት ይመግቧችኃል ፡፡ በየሰፈሩና አስፋልት ዳር የተሰየሙት ገንዳዎች እንደ ከተማው ታክሲዎች ከጭነት በላይ የሚሸከሙ በመሆናቸው የቅርናታቸው ከበሮ ከሩቅ ለአፍንጫ ይሰማል ፡፡ 

አይነምድሩ ፣ አተላውና የፋብሪካው ተረፈ ምርት ምንም ሳይሳቀቅ ወደ ተገኘው ወንዝ በዝግታ እየገማ ሲቀላቀል ይመለከታሉ ፡፡ ህግ የለም እንጂ ህግ አስከባሪ ‹‹ እጅ ወደላይ ! ›› ብሎ ቢጠይቃቸው ከጤና ቢሮና ከአካባቢ ጥበቃ የተሰጣቸውን ፍቃዶች በኩራት የሚያሳዩ ነው የሚመስሉት ፡፡

የከተማችን ቆሻሻ ፣ ግማትና ክርፋት የጥጋቡ ጥጋብ ጨረቃ ቤት ሰርቶ ያለምንም ፍርሃት እየኖረ የሚገኘው በማዘጋጃ አጥር ዙሪያ በሙሉ መሆኑ ነው ፡፡ ግቢያቸውን እንኳ ማጽዳት ያልቻሉት የከተማው አስተዳደሮች በየዕለቱ ስለ ሩቁ ይሰብካሉ ፡፡ ጽዳትና ውበት ፣ ደረቅና ፍሳሽ ፣ ጸረ ቆሻሻ ማህበራት ወዘተ በማለት ሪፖርት ላይ ይደንሳሉ ፡፡

እንግዲህ እያኖረችን የምትገኘውና ከ ሀ እስከ ፐ የምናውቃት አዲስ አበባ ይቺ ናት ፡፡ አንድ  ቡድን ግን በ 2013 ሊጎበኙ ከሚገባቸው አስር ምርጥ ከተሞች አንዷ አዲስ አበባ ናት በማለት ገራሚ ወሬ አሰማን ፡፡ ለ ‹ ቀባሪው አረዱት › ን ከጠቀሱ ላይቀር በዚህ መልኩ ነው ፡፡


ሶስት  .

የሳኡዲ አረቢያ ምክትል መከላከያ ሚ/ር የሆኑት ካሊድ ቢን ሱልጣን በሶስተኛው የአረብ ውሃ ካውንስል ስብሰባ ላይ ‹‹ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ውሃ የመያዝ አቅሙ 70 ቢሊየን ኪዩቢክ ሜትር ይደርሳል ፤ ይህን ውሃ ለመያዝ ደግሞ የግድቡ ከፍታ ወደ ላይ እስከ 700 ሜትር ሊረዝም ይችላል ፡፡ ይህ ግድብ የሚደረመስ ከሆነ ካርቱም በሙሉ በውሃ ትጥለቀለቃለች ፡፡ ጦሱም ለአስዋን ግድብ ይተርፋል ›› በማለት አስተያየት ሰጡ ፡፡

የኢትዮጽያ መንግስት ብዙ ግዜ የሚናገራት ‹‹ ትዕግስት ›› አሁን በፍጹም አልሰራችም ፡፡ በአምባሰደሩ ፣ በውጭ ጉዳይ ሚ/ርና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሳይቀር አስተያየቱ ጸብ አጫሪና ያልተገባ በመሆኑ ማብራሪያ እንዲሰጥ የሳዑዲ አረቢያ መንግስትን ማጨናነቅ ያዘ ፡፡ ቢፒአርና ቢኤስሲ ላይ የሚታወቀው ‹‹ ፈጣን ምላሽ ›› እንደዚህ ተግባራዊ ሆኖ ማወቁ ያጠራጥራል ፡፡

በሌላ በኩል የ30 ሺህ ኢትዮጽያዊያንን ደም ያፈሰሰውና አያሌ ቤቶችን ያቃጠለው የሮዶልፎ ግራዚያኒ ወንጀለኝነቱ ተፍቆ የጀግና አክሊል ሊደፋ አይገባም በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ በኛም ሆነ በምድረ ጣሊያን ተነስቶ ነበር ፡፡ ጉዳዩ ያሳሰባቸው ሸገሬዎችም  የተቃውሞ ሰልፍ በ የካቲት 12 መታሰቢያ ሃውልት አደባባይ ለማድረግ ሞክረዋል ፡፡

የግራዚያኒን አረመኔነትና ጭካኔ በሰብዓዊነት ሚዛን መለካት ያልፈለጉ የአፊሌ መንደር ነዋሪዎች ናቸው 127 ሺ ዩሮ በማውጣት ሃውልት ያሰሩለት ፡፡ ሃውልቱ ላይም ‹‹ Father land ›› እና ‹‹ Honour ›› የሚሉ ቃላቶችን  አጽፈዋል ፡፡ ይህ መቼም ለኢትጽያ መንግስትም ሆነ ህዝብ ከፍተኛ ንቀትና ውርደት ነው ፡፡ ለነጻነት የታገሉ ሰማዕታትን ክብር  የተለየ ግምት ያለመስጠትም ያስመስላል ፡፡ መንግስት የወንጀለኛና ጨፍጫፊ ኃውልት በምድረ ጣሊያን ሲቆም የዝምታ ዲፕሎማሲ ተጠቀመ  ፡፡ 

እንዳቅማቸው በጉዳዩ ላይ ያገባናል ያሉትን ደግሞ ያልተፈቀደ ሰልፍ አድርገዋል በማለት በተነ ወይም አሰረ አሉ ፡፡ የአራዳ ልጆች ‹‹ ፈጣን ምላሽ ›› አሁን የት ገባች እያሉ ነው  ፡፡

አራት  .

የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን በኢህአዴግ ስብሰባ ላይ አቶ መለስ 4 ሺህ እና 6 ሺህ ብር በፔሮል የሚከፈላቸው ብቸኛ ድሃ መሪ መሆናቸውን ይፋ አድርገዋል ፡፡ የእሳቸውን ዜና ስሰማ በቅርቡ ቢቢሲ ይፋ ያደረገው ፣ እረ እኔም አርቲክል ከጻፍኩባቸው የዓለማችን ድሃ ፕሬዝዳንት ወሬ ጋር ተጋጨብኝ ፡፡ ቢቢሲ የዓለማችን ድሃ ፕሬዝዳንት ብሎ ይፋ ያደረጋቸው የ 77 ዓመቱን የኡራጋይ ፕሬዝዳንት ጆሴ ሙጂካን / José Mujica / ነው ፡፡ በወር የሚያገኙት እውነተኛ ደመወዝ 7 ሺ 500 ፓውንድ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 7 ሺህ 15 ፓውንዱን ማለትም 90 ከመቶውን ለድሃዎች መቋቋሚያ ነው የሚሰጡት ፡፡ ይበቃኛል ብለው ወደ ቤታቸው ይዘውት የሚገቡት ገንዘብ 485 ፓውንድ ወይም 10 ከመቶውን ብቻ ነው ፡፡

ወ/ሮ አዜብ የነገሩን እውነት ከሆነ የቢቢሲውን ዜና አስተባብለው ስለ አቶ መለስ ድሃነት እንዲዘገብ ማድረግ ነበረባቸው ፡፡ ይህን የመሰለ ወርቅ መረጃ ይዞ ፍጆታውን ለሀገር ውስጥ ብቻ ማድረግ ተገቢ አይመስልም ፡፡ የአራዳ ልጆች የጊነስ ወርልድ ሪከርድንም ጉሮሮ ማሰብ ያስፈልጋል ባይ ናቸው ፡፡ ‹‹ እሱስ እኛ ካልደረስንለት ምን ይሆናል ? ››


No comments:

Post a Comment