Friday, April 19, 2013

‎በመተካካት የተጎዳው ጢስ አባይ ! ‎




የአማራ ባህል፣ ቱሪዝምና ፓርክ ልማት ቢሮ ለቱሪስቶች በሚያሰራጨው ብሮሸር ላይ ስለ ጢስ አባይ ፏፏቴ ግሩም ጽሁፍ አስፍሯል ፡፡ በየቀኑ ጢስ አባይን ለመመልከት የሚሄደው ደቀመዛምርም መምህሩ የጻፈውን ቅኔ በልቡ እያጠና ወደ ቦታው ይጓዛል ፡፡ በነገራችን ላይ ወደ ፏፏቴው ለመሄድ ሁለት አማራጮች አሉ ፡፡ አንደኛው የአባይን ወንዝ በጀልባ ተሻግሮ 15 ደቂቃ የእግር መንገድ መጓዝ ነው ፡፡ በጎዞዬ ላይ ምን አያለሁ ካሉ በመስኖ የሚበቅሉ አትክልትና ፍራፍሬዎችን ፣ ጋሽዬ ልከተሎት ላስጎበኝዎትም ካሜራ ካልያዙ እንኳ በፌስ ቡክ ላይ የሚለቁትን ምርጥ ፎቶ በሞባይልዎ ላነሳዎት እችላለሁ የሚሉ በርካታ ማቲዎችን ፣ ሻርፕና ጌጣጌጦችን ካልገዙኝ በማለት እስከመዳረሻዎ ሳይታክቱ የሚሸኝዎትን ሰዎች እንዲሁም ‹  የሰው ነገር › የሚል ስም የተሰጠውን ቅጠል ይመለከታሉ ፡፡ ይህ ቅጠል በእጅ ሲነካ ሽምቅቅ ብሎ መጠኑን ይቀንሳል ፡፡ በሌላ አነጋገር የቅጠል ኤሊ መሆኑ ነው ፡፡ ድንጋይ ውስጥ ባይሆንም ሁለመናውን ግንዱ ላይ ይለጥፋል - ከሶስት ደቂቃ ቆይታ በኃላ ደግሞ ወደቀድሞው ይዞታው ይለጠጣል ፡፡

 ሁለተኛው መንገድ መኪናዋን እስከተወሰነ ርቀት ከነዱ በኃላ ከ 30 እስከ 40 ደቂቃ በእግር ሊጓዙ ግድ የሚልዋት ነው ፡፡ ይህኛውን በዳገት የታጀበ አድካሚ መንገድ ቱሪስቶች ይመርጡታል ፡፡ ምክንያቱም አካባቢውን በአግባቡ ለመቃኘት ፣ በ 17ኛው ክፍለ ዘመን የተሰራውን ጥንታዊ የአላታ ድልድይና ሸለቆ ለመመልከት ስለሚረዳ ነው ፡፡ እኔ ሁለተኛውን አማራጭ ስለማውቀው አንደኛውን ምርጫ በመጠቀም ቦታው ተገኝቻለሁ ፡፡ እናም የብሮሸሩ ምንባብ ከጉብኝት በኃላ የሆነ አጭር መልመጃ ቢኖር እንኳ በአግባቡ አስታውሶ ለመመለስ ስለሚረዳ ጎብኚው ደጋግሞ ከኪሱ እያወጣ ያያታል ፡፡ እንዲህ ትላላች ፡፡

The Falls are found at 30 km to south of Bahir Dar near Tis Abay town. Here there is a spectacular basalt cliff Where the Nile form an incredible falls of 45 meters high, known as the Blue Nile Falls. The noise, the force and the smoke created by this fall is really worth discovering. The Blue Nile Falls is locally called the Tis Isat , meant water that smokes .

ቱሪስቱ ከጉብኝት በኃላ ወደ መረጃ ክፍል ተመልሶ ቢገባ ግን መምህሩ ሊፈትነው አይሞክርም ፤ ምናልባትም ትምህርትም ሆነ መረጃ ሰጪዎችን ላያገኝ ይችላል ፡፡ ግን በትምህርቱና በብሮሸሩ ንባብ መሰረት ራሱን መፈተኑ ይጠበቃል - እንዲህ እያለ ፡፡ ‹ በንባቡ መሰረት ትክክለኛ የሆነውንና ያልሆነውን ለይተህ አውጣ ! ትክክለኛ ባልሆኑ ጉዳዮች ዙሪያ አብሮህ ከጎበኘው ሰው ጋር በድፍረት ተወያይበት ፡፡ የመፍትሄ ሀሳቦችህንም ሀሳብ መስጫ ሳጥን ውስጥ ጨምር ! ›

ሀ . ትክክለኛ የሆነው ፤

1 . ጢስ አባይ ከባህር ዳር 30 ኪሜ ርቀት ላይ ይገኛል
2 . 45 ሜትር ቁልቁል ይወረወራል

ለ . ትክክለኛ ያልሆነው ፤

1 . የሚገርም ፏፏቴ ሊባል አይችልም
2 . ድምጹና ሁካታው እንደተባለው የተጋነነ አይደለም
3 . ታች ሲወርድ የሚፈጠር ልዩ ጢስ የለም
4 . የሚፈጠር ቀስተ ዳመና የለም
5 . ግርማ ሞገሳም ሳይሆን ቆሌ የራቀው መሆኑ ይታያል ፡፡

የመፍትሄ ሀሳብ ፤

. የሰው ነገር የተባለው ቅጠል አባባል አሁን ገና በአግባቡ ገብቶናል

በርግጥም ቱሪስቶች ብዙ ተወርቶላቸው ግዜ ፣ ገንዘብ እና ጉልበታቸውን መስዋዕት አድርገው ጢስ አባይ ዳገት ላይ ሲደርሱ ‹‹ እንግዲህ ጢስ አባይ ፏፏቴ ማለት ይህ ነው ! ›› ይላቸዋል ወጣት አስጎብኚው

‹‹ የቱ ? ››
‹‹ ይኀው ፊት ለፊት የምታዩት ! ››
‹‹ መቼም እየቀለድክ አይደለም ! ››
‹‹ እረ በስራ አንቀልድም ››
‹‹ ካልቀለድክ ታዲያ የታለ  የፏፏቴው ግዝፍና ? የቱ ነው ግርማ ሞገሱ ? የታለ ዳገት ላይ የሚደርሰው የውሃ ፍንጥቅጣቂ ? ቀስተ ዳመና የተባለውስ ? የታለ አስደማሚው ጢሱ ? ››

አስጎብኚው ያለው ብቸኛ እድል የሰው ነገር እንደተባለቸው ቅጠል ቀስ እያለ መሸማቀቅ ብቻ ነው ፡፡ ሳር እንዳጣ ከብት እንዲህ የገረጣውን ጢስ አባይ ለሃይል ማመንጫ ስለተገደበ ወዘተ … እያለ ማሳበቡ ለቱሪስቱ በቂ ምላሽ እንደማይፈጥርለት እሙን ነው ፡፡ ምክንያቱም የኃይል ጥያቄ ለሀገሬው እንጂ ለቱሪስቱ ጉዳዩ አይደለምና ፡፡ የእሱ መሰረታዊ ጉዳይ ብዙ ያወጣበትና የለፋበትን መስህብ አይቶ መርካት ነው ፤ እርካታው ከሞላ ደግሞ ወደ ሀገሩ ሲሄድ ያየውን በማውራት እግረ መንገዱን ማስታወቂያ መስራት ነው ፡፡ ዛሬ ግን አያሌ አስጎብኚዎች እንግዳቸውን ለማሳመን ሳይችሉ በርካታ ጎብኚዎች በሚሰጣቸው ምክንያት ሳይረኩ እየተበሳጩ መመለስ ግዴታቸው ሆኗል ፡፡

የፏፏቴው ጉዳይ አሳሳቢ ነው ፡፡ 75 ከመቶ ያህሉ ለሃይል ጥቅም ስለተገደበ ወደ ፏፏቴው የሚወርደው የውሃ መጠን የወፍራም ሰው ሽንት አክሏል ፡፡ ይህን ኢምንት ውሃ ደግሞ በሌላ ቦታ ማየት ይቻላል ፡፡ ወይ ያለቅጥ የሚሰማውን የተንዠረገገ ማስታወቂያ እንደ ጎጃም ልጅ ቁንጮ አስቀርቶ መከርከም አሊያም በድንጋይ ፋንታ ሙሉ ዉሃ የሚታይበትን ፕሮግራም ነድፎ መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ፡፡ ለምሳሌ ያህል ቅዳሜና እሁድ በርከት ያለ የውሃ መጠን ከግድቡ ቢለቀቅ ጎብኚው ሳምንቱን እየጠበቀ እየረካ ሊመለስ ይችላል ፡፡ የማይቻል ከሆነ ግን በቴሌቪዥን የሚታየውና በቃል የሚነገርለትን ጢስ አባይ ለሁለት ከፍሎ ማየት ሊገባ ነው ፡፡ የሚያስጎመጀውን ‹ የቀድሞው ጢስ አባይ › በማለት የአሁኗን ‹ በመተካካት የተገኘች › ማለት ይሻላል ፡፡ 
ምክንያቱም ዉሸት ስለሚያሳፍር ፡፡ ባይሆን እቺ የተተካቸው ‹ አቅም እየፈጠረች ስትሄድ መፈርጠሟና ማስደመሟ አይቀርም › እያሉ መስበክ ይሻላል ፡፡ የቱሪዝሙም ገቢ አይቅርብኝ ፣ የሃይል ጉዳይም የግድ ነው ብሎ ውሃ ውሃ የሚል ወጥ መስራት ግን መጨረሻው የበሰለውን ማበላሸት ይሆናል ፡፡ 

No comments:

Post a Comment