Wednesday, June 24, 2020

ተሰርቆ የታሰረው ልጅ ታሪክ



ጥቅል ታሪክ

 « My name is Why » የተሰኘው የለምን ሲሳይ መጽሀፍ በራሱ የልጅነት ህይወት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ስራ ነው ። መንግስት ልጅ ሰርቆ እስር ቤት ከቷል ፣ የህይወት ታሪኩም እንዳይታወቅ ድብቋል ይላል ደራሲው ገና ከመነሻው ። የለምን  እናት እንግሊዝ ሀገር ለትምህርት የደረሰችው በ1966 ዓም  ነበር ። በወቅቱ ነፍሰ ጡር ነበረች ፣ መውለጃዋ ሲደርስ ዊጋን አካባቢ በሚገኝ አንድ ሆስፒታል ደራሲውን ተገላገለች ። ብዙም ሳይቆይ አባቷ ስለታመሙ  ወደ ኢትዮጽያ  መመለስ ነበረባት ፤ ያኔ ነው እንግዲህ ህጻኑ ለአሳዳጊ ተላልፎ የተሰጠው ። ኖርማን ግሪንውድ የተባለ ስምም  አገኘ  

ለለምን ሲሳይ ህይወት ፈተና ነበረች ። ገና በ12 አመቱ ነበር አሳዳጊዎቹ ከቤት ያባረሩት ።  ከ 12 እስከ 17 አመቱ ደግሞ በአራት የተለያዩ ማሳደጊያ ቦታዎች በተለያዩ ምክንያቶች ተወርውሯል ። በግራ እጁ ላይ NG / Norman Green wood / የሚል ንቅሳት ቢያጽፍም እውነተኛ ስሙ ይህ ንቅሳት አለመሆኑን የተገነዘበው በ 17 አመቱ ነበር ።

ደራሲው ለ30 አመታት ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ትግል ገጥሟል ። ትግል የገጠመው ከልጅነት እስከ እውቀት ሲመዘገብ የቆየው የህይወቱ ታሪክ / ማንነት / ተላልፎ እንዲሰጠው ነበር ። በ2015 የዊጋን ካውንስል ሃላፊ አራት ትላልቅ ዶሴዎችን አስረከቡት ። ከዚህ በኋላ ነበር ይህ መጽሀፍ የተወለደው ። ማንነቱን ለአለም ለማብሰር ስሙ ኖርማን ሳይሆን ለምን መሆኑን ለማስረዳት  ይደክማል ... MY Name is Why…

ስለ ልጅነቱ ፣ ስለትምህርቱ ፣ ስለ አሳዳጊዎቹ ስብእና ፣ ስለ ባህሪው ፣ እናቱ ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ስለተፃፃፈቻቸው ደብዳቤዎች  ምን አለፋችሁ እያንዳንዱ ትንፋሹ ዶሴው ውስጥ እየተመዘገበ ነው የቆየው ። ደራሲው ደብዳቤዎቹን አባሪ በማድረግ ነው እንግዲህ ታሪኩን በቅደም ተከተል የሚተርክልን ።

ለአሳዳጊዎቹ ስለመተላለፍ

ህፃኑ ለምን ሲሳይ ሆስፒታሉ ውስጥ ለ 228 ቀናት ብቻውን ተኝቶ ነበር ። የዚህ መሰረታዊ ምክንያት ደግሞ ዘረኝነት ነው ። ህፃኑን የጎበኘ ሁሉ ጥቁር መሆኑን በማየት ብቻ ቀኝ ኋላ ዙር ይላል ። መጨረሻ ላይ የግሪንውድ ቤተሰቦች እያመንቱ ‹ እስኪ ለማንኛውም በጥልቀት እንፀልይበት ›  ሲሉ መከሩ ፣ ከቆይታ በኋላም ፍቃደኝነታቸውን  ገልፀው ህፃኑን ተረከቡ ።

ይህ ሁሉ ፍጥጥም ጥር 3 ቀን 1968 የተደረገው  ያለእናቱ  ስምምነት ነው ። እናቱ ለአጭር ግዜ ትምህርት ስትመጣ ችግር ላይ ነበረች ። በመሆኑም የምትማርበት ኮሌጅ ርግዝናዋን አስመልክቶ ወደ ቅዱስ ማርጋሬት ነበር የላካት ። ለምንን በሰላም ከተገላገለች በኋላ የማደጎ ስምምነቱን ትፈርማለች ተብሎ ይጠበቅ ነበር ። ነገር ግን ማደጎ ምን እንደሆነ በሚገባ ታውቅ ስለነበር ስምምነቱን አልፈረመችም ። ይህ በእንዲህ እንዳለ ደግሞ አባቷ  በፀና በመታመማቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለስ ነበረባት ። ቆይቶም ለምንን ጥላ በመሄዷ ልጁ በመንግስት ሃላፊነት ስር መውደቁን የሚገልፅ  ደብዳቤ በምትከታተልበት ቤተክርስትያን በኩል ተላከላት ። ተቃውሞ ካላትም በ30 ቀናት ውስጥ ብቻ እንድታቀርብ ያስጠነቀቀ ነበር መልእክቱ ።

ደራሲው ይህ ደብዳቤ ተፈፃሚ ሊሆን እንደማይችል በማስላት የተላከ ነው ባይ ነው ። ምክንያቱም ፍርድ ቤት ጉዳዩን ለማስረዳት ብቻ  14 ቀናት ያስፈልጋል ፣ የተላከው መልእክት ኢትዮጵያ ለመድረስ አንድ ወር ወስዶበታል ይህ ማለት የእሷም ምላሽ ወይም አቋም እንግሊዝ ለመድረስ አንድ ወር ይፈጅበታል ። በሌላ በኩል በግዜው ከአዲስ አበባ ለንደን ቀጥታ በረራ አልነበረም ። ቦታው ለመድረስ ከአዲስ አበባ አቴንስ ፣ ከአቴንስ ደግሞ ለንደን መብረር ያስፈልጋል ፣ ይህ ማለት በተሰጠው የግዜ ገደብ መድረስ የማይቻል ነው በማለት ። ለምን ቅዱስ ማርጋሬት ሃውስን ከሚሰጠው ተግባር አንጻር በሚከተለው መንገድ ያጣጥለዋል

 « በመሰረቱ ይህ ቦታ የልጆች እርሻ ነው ። እናቶች መሬት ሲሆኑ ልጆች ደግሞ ሰብል ናቸው ። ቤተክርስቲያንና መንግስት ገበሬዋች ሲሆኑየማደጎ አሳዳጊዎች ደግሞ ተጠቃሚዋች ናቸው »

 ሰቆቃና መከራ

መምህርና ነርስ የሆኑት አሳዳጊዎቹ ሁለት ልጆች አላቸው ። ክርስቶፈርና ሄለን የተባሉ ። ለምን ክርስቶፈርን በአንድ አመት ይበልጠዋል -  ሄለን  በጣም ትንሽ ናት ። ክወንድሙ ጋር ጠረጴዛ ቴንስ ሲጫወቱ አውቆ ይሸነፍለት ነበር - እንዳይናደድ ።

ለምን በሰባት አመቱ ጠያቂ መሆን ጀምሯል ። ቤተክርስቲያን ሲሄድ ያልገቡትንና ቅር የሚሉትን  ነገሮች ሁሉ እንዴት  እያለ ይጠይቃል ። ጥያቄዋቹ  ምላሾች ነበራቸው « ሁላችንም ሃጢያቶች ስለሆንን » የሚል ። ትምህርት ቤት አካባቢ ለሚፈጠሩበት የዘርና የቀለም ጥያቄ ግን ምላሸ አላገኘም ። « እናትህ ጥላህ ሄደች … አትፈልግህም … እኔ ባገኘት አይኗን እቦጫጭረው ነበር … እንዴት አይነት ክፉ እናት ናት … » በትንሸ ጭንቅላቱ ይህን ጥያቄ ቤት ይዞ ይሄዳል - ምላሸ ለማግኘት ። የአሳዳጊው እናት መልስ ግን ወላጅ እናቱን አበክራ እንደምትጠላት የሚያስረዳ  ነበር ።

የህይወት ፋይሉ ላይ እንደተመዘገበው በስምንት አመቱ ብስኩት ሰርቆ በልቷል ፣ ቁራጭ ኬክ ሲወስድም ‹ እባክህ › እና ‹ አመሰግናለሁ › ሳይል ነው ። ሰርቆ መብላቱ ወላጆቹን ያበሳጫቸው ሲሆን ሰይጣን ውስጡ እንደገባ ያምኑ ነበር ። ደራሲው ኋላ ላይ High Profiles ለተባለ መጽሄት በስጠው ቃለመጠይቅ  « እጃቸውን ጭንቅላቴ ላይ ጭነው ሰይጣን ከዚህ ልጅ ላይ ውጣ ! » ይሉ ነበር ብሏል ።

አይወደንም ፣ ሰይጣናም ሆኗል ከሚሉ ምክንያቶች በተጨማሪ በ 12 አመቱ ለመባረሩ ምክንያት የሆነው የትንሿን ሄለንን ወሬ በመስማታቸው ነው ። ሄለን ለወላጆችዋ  ‹ ኖርማን ከእኔ በስተቀር ሁላችሁንም እገላለሁ ሲል ሰምቼያለሁ › ብላ ታወራለች ። ይህ ወቅት ገና ወደ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የተሸጋገረበት ነበር ። የስምንት አመት ልጅ ቤተሰቡን ሊጨርስ እየዛተ ነው ብሎ ማመን ብሎም የከፋ ርምጃ ይወስዳል ብሎ መደምደም ተቀባይነት እንደሌለው ደራሲው ይናገራል ።

አሳዳጊዎቹ ይህ ሰይጣንም ልጅ እንደማያስፈልጋቸው ውሳኔ ላይ ደረሱ ። እናም አንጠልጥለው  ለአንድ አሳዳጊ ድርጅት አስረከቡት ፣ ዝም ብለው ቢሄዱም ጥሩ ነበር ። ከዚህ ይልቅ የማይታይ አርጩሜ ህሊናው ውስጥ አስቀመጡ « እየመጣን አንጠይቅህም ፤ ድብዳቤም አንጽፍልህም » በማለት ። በደህናው ዘመን ወንድም ፣ እህት ፣ አክስት ፣ አጎት እና  አያት እንዳለው እንዳልሰበኩት « አውጥተው ሲጥሉኝ ማንም ሰው እንዳይገናኘኝ አድርገው ነበር » ብሏል በቁጭት ። ጥር 3 ቀን 1968 ዓም ተግባራዊ የሆነው የማደጎ ወላጆች ስምምነት ሰባት አንቀፆችን ይዟል ። አንደኛው ኖርማንን ልክ እንደራሳቸው ልጆች ማሳደግ እንደሚኖርባቸው ይደነግጋል  ። ሁለተኛው ደግሞ ልጁ የራሱን ሃይማኖት እንዲከተል ማድረግን ይመለከታል ። ክነዚህ ድንጋጌዋች አንፃር በለምን ላይ የደረሰው ቅጣት ከሚታሰበው በላይ ነው ። ለመሆኑ ለምን ስለአሳዳጊዎቹ ምን አስተያየት አለው የሚል ጥይቄ ቢነሳ የሚከተለውን የሚገርም ምላሸ ሲሰጥ እናገኘዋለን « በጣም ጥሩ ሰዎች ነበሩ ፣ መጥፎ ነገርን የሚያደርጉ »

የቦብ ማርሌይ ሞራላዊ ድጋፍ

በ 12 አመቱ ውድፊልድ ወደተባለ ማሳደጊያ ተቋም ሲገባ የእድሜ አቻዎቹ ቾኪኋይት የሚል ቅጽል ስም ሰጥተውት ነበር ። በዚህ ስፍራ ሰራተኞቹ ልጆች ሲጋራ ማጨስ እንደሌለባቸው አይመክሩም ይልቁንም የማጨሻ ልዩ ስፍራ አዘጋጀተዋል - እናም ማጨስ ለመደ ። በዚህ ስፍራ መፅሀፍ የለም ፣ አንብብ የሚል አበረታችም አይገኝም - በተቃራኒው ግን ለመጀመሪያ ግዜ ግጥም መፃፍ ጀመረ ። ግጥሙም ስለ ዛፍ የምታወሳ እንደነበረች ያስታውሳል ። ባልተጠበቀ መልኩ ግን ገጣሚ መሆኑን የተረዳችው የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር « The Mersey sound » የተባለ የግጥም መፅሀፍ እንዲያነብ ሰጥተዋለች ። አሁንም በተቃራኒ እይታ ደራሲው ስለግጥሙ ይዘት አይደለም የሚነግረን - ገጣሚው በመጀመሪያ ገጹ ላይ ስለ ሙት ልጆች መፃፉን እንጂ ።

በአንድ ወቅት በጓደኛው ምክንያት ከቦብ ማርሌይ ስራዋች ጋር ተዋወቀ ። ቦብ ማርሌይ የመጀመሪያው ጥቁር ጓደኛ ፣ የመጀመሪያው ጥቁር መምህር ሆነለት ። በርግጥ ከ ቦብ የወሰደው ዘፈኑን ብቻ ሳይሆን አደገኛ እፅንም ጭምር ነበር ። ቦብ ለሰው ልጆች እኩልነትና ነፃነት ይጮሃል ፣ ስለ ጭቆና ስለ ታሪክ ስለ አለም እውነት ይናገራል ። ደራሲው ቦብን የወደደበት ሌላኛው ምክንያት በዘይቤያዊ አነጋገር የሚያስተላልፋቸው ውብ መልእክቶች ናቸው ። በዚህ ረገድ Ride Natty Ride በሚለው ዘፈን ውስጥ ግንበኞች የናቁት ድንጋይ እርሱ የማእዘን ራስ ሆነ የሚለውን መጽሀፍ ቅዱሳዊ አባባል ለጉድ ይወደዋል ።

But the stone that the builder refuse
Shall be the head cornerstone
And no matter what game they play
We’ve got something they could never take away .

እናም ለመጀመሪያ ግዜ ከነጮች ባህር ውስጥ የተገኘ ጥቁር ሰው መሆኑን አመነ « በኔ ዙሪያ የተሰበሰቡ ሰዎች ሁሉ የኔን ዘርና ቀለም የካዱት የቀለም አይነስውርነት ስላለባቸው መሆኑን  አመንኩ » ብሏል

ጥቅል መደምደሚያ

በጽንሰ ሀሳብ ደረጃ አውቶባዮግራፊና ሚሞይር ስለ አንድ ሰው ህይወት ስለሚያትቱና በአንደኛ ደረጃ የአጻጻፍ ይትበሃል ስለሚዋቀሩ የመመሳሰል ጸባይ ያላቸው ይመስላል ። ፈታ አድርገን ስንመለከታቸው ግን መሰረታዊ ልዩነት አላቸው ። አውቶባዮግራፊ የደራሲውን መላ ህይወት በቅደም ተከተል የሚዳሥስ ሲሆን ሚሞይር የደራሲው የተወሰነ የህይወት ክፍል ላይ አጠንጥኖ ይሰራል ። አውቶባዮግራፊ ታዋቂ ሰዎች ላይ ሲያተኩር ሚሞይር ሰው አይመርጥም ። ሰዎች ለማንበብ የሚፈልጉት አጠቃላይ ህይወቱን ቢሆን ከርእሰ ጉዳዩ ወይም ከጭብጡ አንፃር በመነሳት ነው ። አውቶባዮግራፊ ለእውነትና ታሪክ ልዩ ትኩረት ሲሰጥ ሚሞይር ስሜት ነክ ልምዶችን ይቃኛል ።

በዚህ ረገድ የለምን ሲሳይ ሚሞይር የማንነት ፍለጋ ላይ ላይ ያነጣጠረ ነው ማለት ይቻላል ። እናት ብትርቀው ፣ አሳዳጊ ቢገፋው ፣ ማህበረሰቡ ቢያገለው እንኳ ያላሰለሰ የራስ ጥረት ካለ ውጤት እንደሚገኝ ያስተምራል ። ለምን ሲሳይ እስከ 17 አመቱ አንድ አይነት ፣ ከ 17 አመቱ በኋላ ደግሞ ሌላ አይነት ሰው ነበር ። በ 14 አመቱ እጁ ላይ የነቀሰው Norman Greenwood አንደኛው ሲሆን ከ 17 አመት ጀምሮ ያወቀው ‹ ለምን ሲሳይ › ደግሞ ሁለተኛው ማንነት ነው ። ሁለተኛውን ማንነቱን ሲያገኝ የተረዳው ስሙን ብቻ ሳይሆን እውነተኛ እናቱን ፣ እውነተኛ ሀገሩን ፣ የጥቁርነቱን ምክንያትና የግጭቱን መሰረት ነው ። ለዚያም ነው ገጽ 137 እና 138 ላይ « የልደት ማስረጃዬ ላይ ያለው ስም ለምን ሲሳይ መሆኑን ለሚጠቁኝ ሁሉ እነግራቸዋለሁ » በማለት 90 ያህል ግዜ My name is Lemn Sisay ተደጋግሞ ተጽፎ የምናየው ። የድግግሞሹ ወይም / Alliteration / ሚና ትኩረት መጠቆሚያ ነው ።

ለምን ሲሳይ እውነተኛ ስሙንና ማንነቱን ካወቀ በኋላ ሙሉ ለሙሉ ያልመለሰልን አንድ ጥያቄ አለ ። ርግጥ ነው በቅጣይ / Epilogue / ምእራፍ ላይ እናቱ የማርሸት ከአማራ ህዝቦች እንደተገኘች በዚሁ ክልል ባህል ደግሞ በመጀመሪያ ልጅ መልእክት ማስተላለፍ የተለመደ መሆኑን በመጠቆም ለምን ‹ Why › የሚል ፍቺ እንዳለው ያሰረዳናል ። ጥያቄው ግን ይህ አይደለም ። ጥያቄው እናቱ እንዴት ‹ ለምን › አሉት የሚለው ነው ። ከስሙ ፍካሬያዊ ፍቺ ከተነሳን ለምን ትምህርቴን ሳልጨርስ … ለምን በውጭ ሀገር …. ለምን ከጋብቻ በፊት … ወዘተ የተሰኙ ህሊናዊ ሙግቶች እንዳሉበት እንገነዘባለን ።

ስለምንነት ካወራን ደግሞ እናቱን አስታውሶ አባቱን መግደፉ መሉ አያደርገውም ። ለምን ሲሳይ ከመጽሀፉ ህትመት በኋላ በሰጣቸው ቃለመጠይቆች አበቱ የኢትዮጽያ አየር መንገድ አብራሪ እንደነበር ፣ በ1973 ከኢትዮጽያ ወደ ኤርትራ እየበረረ መብረቅ ክንፉን መቶት በሰሜን ተራሮች ላይ መሰዋቱን ተናግሯል ። ሰሜን ተራራሮችን ከጎበኘ በኋላም ለአባቱ ግጥም መጻፉን አስረድቷል ። እነዚህ ቀጥተኛ ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች በድሉ የመጨረሻ ምእራፍ ላይ ቢዳሰሱ የበለጠ ጠንካራ ያደርገው ነበር ።

ደራሲው በዚህ ስራው የተበላሸ የማደጎ ስርአት አሰራርን አጋልጦበታል ። የቸልተኛ ባልስልጣናትን የተረገመ ተግባር እንዲሁም የቢሮክራሲን ጭካኔ አሳይቶበታል ።  በዘር ፣ በቀለምና በሞራል ላይ የሚደረገውን ልዩነት ኮንኖበታል ። በ 30 ምእራፎች የተከፋፈለው ስራ ሁለት ልዩ ባህሪያት አሉት ። የመጀመሪያው አብዛኛው ምእራፍ ከመረጃ ጋር ተሰናስሎ የመቅረቡ ጉዳይ ነው ። ሁለተኛውና ዋነኛው ሀሳብ ሁሉም ምእራፎች የሚጀምሩት በ ኳትሬይን / Quatrain / አይነት ግጥሞች መሆኑ ነው ። ለአብነት ያህል በምእራፍ  14 ላይ የሚከተለውን  ግጥም እናገኛለን
 
Night can’t drive out night
Only the light above
Fear can’t drive out fear
Only love

ጨለማን ጨለማ አያባርረውም
ብርሃን እንጂ
ፍርሃትን ፍርሃት አያባርረውም
ፍቅር እንጂ

ግጥሞቹ በቀጣይ ከምናነበው ታሪክ / ሃሳብ / መረጃ ጋር እናገናኘው ካልን ሊገኛኝ ይችላል ። እነዚህ  ባለ አራት መስመር የግጥም ስንኞች በተለይ በእንግሊዝ ስነ ጽሁፍ ታሪክ ውስጥ ላቅ ያለ ሚና አላቸው ። ርግጥ ነው ይህ ስነጽሁፋዊ ዘውግ በጥንታዊ ቻይና ፣ ሮም ፣ ግሪክ እና ህንድ ቀደምት ልእልና ነበረው ። ቀጥሎም በአውሮፓ የጨለማው ዘመን በስፋት ተሰርቶበታል ። በተለይም በመካከለኛው ምስራቅ ኦማር ካያም ሩባያ በሚል ስያሜ ገኖበታል ። በተመሳሳይ መልኩም ኖስትራዳመስ ለዝነኛ ትንቢቶቹ መጠቀሚያ አድርጓቸዋል ።

ታዲያ ለምን ሲሳይ እነዚህን የግጥም አይነቶች በምን አላማ ተጠቀመባቸው ብሎ መጠየቅ ግድ ይላል ። ግጥም ያለውን ትልቅ ጉልበት ለማሳየት … ግጥም መጻፍ የጀመረው እስር ቤትን በሚስተካከሉ/ እንደርሱ አመለካከት /  የህጻናት ማቆያ ቦታዎች መሆኑን ለመዘከር … በስቃይና ችግር ያሳለፈውን የልጅነት ህይወት ያቃለለት ኪነጥበብ / ግጥምና ሙዚቃ / መሆኑን አስረግጦ ለማስረዳት … ጽሁፉን ተነባቢ ለማድረግ … ወዘተ ማለት ይቻላል ። እንደ እኔ እምነት ግን ባለአራቱ ስንኞች ገዝፈው የተቀረጹት በአራት አስቸጋሪ ማሳደጊያ ቦታዎች ህይወቱን መምራቱን ተምሳሌታዊ ለማድረግ በመፈለጉ ነው ።

Friday, June 19, 2020

የፍትህ መዶሻ ይዛ ፍትህ የምትጠይቅ ሀገር



ኢትዮጽያ አይኗን በጨው ካጠበችው  ግብፅና አይኗን በአግባቡ መታጠብ ካቃታት ሱዳን ጋር እሰጥ አገባ ከገባች አመታትን አስቆጠረች ። ድርድሩ የፓለቲካውና ዲፕሎማሲውን መንገድ ይከተል በሚል እንጂ በጉንጭ አልፋው ንግግር  ውጤት ይገኛል ተብሎ አይጠበቅም ።

ፈጣጣዋ ግብፅ የቅኝ ግዛቶችን ውል ከትከሻዋ ላይ ማውረድ አትፈልግም ። ከግፈኛዋ እንግሊዝ የተቀበለችውን የውሃ ድርሻ እንደ ጄነራል ክፍ አድርጎታል ። ይህን ማእረግ ወደ ሻምበልነት የሚያወርድ ተጋፊ ሃይልን አትቀበልም ። እናም በእሷ ቀመር የውሃው ባለቤትነት የሚመዘነው ከሚመነጭበት ቦታ ሳይሆን በተፈጥሮ ቀድሞ በያዘ ነው - ላለው ይጨመርለታል የሚባለውን የወንጌል ጥቅስ እንድናስታውስ በማድረግ ።

ሱዳን ከቅኝ ገዢዋ መሃንዲስ የሚበቃትን ያህል ድርሻ ተቀብላለች ። የአባይ ወንዝና የግድቡ ወሬ ሲነሳ የምታዳምጠው አይናር የማይጠፋውን አይኗን እየሞዥቀች ነው ። አይናሩ ሲለቃት ግድቡ ይጠቅመኛል ከኢትዮጽያ ጎን ነኝ ትላለች ። አይናሩ አንቆ ሲይዛት የግብጽ ማስፈራሪያ ነው ቀድሞ የሚሰማት ። ያኔ ግብፅን በአረብኛ ማናገር ትጀምራለች - አቋም እንዲኖራት አትፈልግም ።
እነዚህ ሀገሮች ከያዙት ሀገወጥ ጥቅምም ሆነ ከሚያስተሳስረቸው ፖለቲካዊ ውግንና አንጻር ወደ መሃል ተስበው የሚመጡ አይደሉም ። ወደታች ወርደው የእውነት ባልጩት ላይ ከቆሙ ድንጋዩ ያበቀለው አልጌ አዳልጦ እንደሚጥላቸው ይረዳሉ ። የሚደራደሩት አዲሱን እውነት ለመቀበልና የቆየውን ክብር ለማጣት አይደለም ።

ለዚያም ነው በተለይ ግብፅ ከድርድር ይልቅ አደራዳሪን ምርኩዝ ማድረግ የምትመርጠው ። ለቡራኬ ሰጪዎች ትልቅ ቦታ አላት ። ድሮ ለዚህ ያበቃቻት እንግሊዝ ዛሬ ባትጠቅማትም አሜሪካንን መተካት አላቃታትም ። ትላልቆቹ በስሟ እንዲያስፈራሩላትና የረባሽ ሀገራትን ጆሮ እንዲቆነጥጡላት ትፈልጋለች ። የያዘችው እውነት ለዛሬው አለም ባይሰራም አይኗን አፍጣ አለም መንግስታት ፊት ስሞታ ታቀርባለች ። ጩኸቷን እንዲጮሁላት አጥብቃ ነው የምትሰራው ። አልፋም ትሄዳለች - ሁሉንም አማራጮች እጠቀማለሁ የሚል ማስፈራሪያ በመልቀቅ ።

እንደሚታወቀው የውሃው መነሻም ሆነ የግድቡ መድረሻ ከኢትዮጽያ ነው ወይም ኢትዪጽያ ናት ። በውሃ የመጠቀም አለማቀፋዊ መብቷ ጥያቄ ውስጥ ባይገባም የምትደራደረው ግን በድርድር ተጎጂልን ከሚሏት ፈጣጣ ሀገራት ጋ ነው ። ድርድሩን አለም ይውቅልኝ ፣ ፍትሃዊነቱንም ይገንዘብልኝ የምትለው የሌሎችም አጋር መሆናን ለማሳየት ነው ። ሀገሬ ግን ነገ ጠባ እየከሰሷት ፣ አለፍ ሲልም እያስፈራሯት ፍትሃዊ አካሄዴ ይታወቅልኝ በሚል ባዘነች ።

እንደ እውነቱ ከሆነ ግድቡን ለመስራትም ሆነ ውሃውን ለመሙላት የማንንም ፍቃድ መጠየቅ አያስፈልግም ። መጠንቀቅ ያለብን ሌሎችን በጭፍን ጥላቻ ላለመጉዳታችን ብቻ  ነው ። ከዚያ ውጪ ወንዙም ግድቡም የኛ ነው ። በያዝነው ነገር ላይ መያዛችንን ከማይቀበል ቡድን ጋር ለምን ሃይላችንን እናጠፋለን ? ብለህ ብለህ አልቀበል ካለህ የያዝከውን አስተማማኝ የፍትህ መዶሻ በራስህ ጠረጼዛ ላይ መምታት ተገቢ ነው ። ከዚያ ለፍርድ አፈጻጸም ወደሚመለከተው አካል በየአድራሻው መላክ - ይኅው ነው ። ውሃውን መሙላት ስትጀምር ትላንት አልቀበል ያለህ ሁሉ ሰልፉን ካንተ ጋ ያሳምራል ፤ ቋንቋውንም ይለውጣል ። ዋ ! የሚልህን ረስቶ ‹ እባክህ › ማለት ይጀምራል ። አለም የምታሳየን እውነት ይሄንን ነው ። ከወሬው ቀንሰን ይህን ለማድረግ እንፍጠን ። ያኔ የመታኸው መዶሻ ጠብቆ መግባቱን ቢያንስ ቢያንስ ደግሞ ትክክል መሆኑን ትገነዘባለህ ።

በርግጥ ሌሎችን ተደግፎም ሆነ በራሱ የሚያስፈራራው ቡድን ምንም አያመጣም ብሎ መዘናጋት ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል ። ግልጽ ጦርነት ባይከፍትብህ እንኳ ሌሎችን በገንዝብ በመግዛት ጥቅምህን ለመናድ ሌት ተቀን ይሰራል ። ሱዳን እና የኛ ሀገር ባንዳዋችን በዋናነት እንደሚጠቀም መጠራጠር አይኖርብንም ። ግድቡ ድንበር ላይ እንዲሰራ መደረጉ ምናልባት የሚጎዳንም በዚህ መሰሉ አጣብቂኝ ግዜ ነው ። እናም በአንድ በኩል ግድቡን ለመጨረስ እየተጉ በሌላ በኩል ግድቡንና አካባቢውን በአስተማማኝ መከላከያ ማጠር ያስፈልጋል ። የሀገር ቤቶችን ባንዳዎች እግር በእግር ተከታትሎ ግባቸውን ለማጨናገፍ ፣ የጆሮ ጠቢውን መስሪያ ቤት ሚና ከመቼውም ግዜ በላቀ መልኩ ማሳደግ ተመራጭ ይሆናል ።

Sunday, June 7, 2020

የእንግሊዝ ሃውልቶች አዲስ ፈተና …




ኤድዋርድ ኮልስቶን የብሪስቶል ነዋሪዋች ኩራት ነበር ። ሲበዛ ቅን ነው ይሉታል - ተወላጆቹ ። ኋላ ላይ ከተማዋን እየተቀላቀሉ የመጡ ጥቁሮችና ሌሎች ግን የክፋት መጨረሻ እንደሆነ ነው የሚሰማቸው ። ከነጋዴ ቤተሰቦቹ በ 1636 ተወልዶ በ 1721 ዓም አረፈ ። እዚህ ከተማ ላይ ሃውልት የቆመለት በ 1895 ሲሆን መሰረታዊው ምክንያት በጎ አድራጊነቱ ነው ። በኖረበት ዘመን ለበጎ አድራጊ ድርጅቶች ከ 71 ሺህ ፓውንድ በላይ ለግሷል ። ለትምህርት ቤቶች ፣ ለእምነት ተቋማትና ለሆስፒታሎችም በመርዳት ስሙ ይጠቀሳል ። አንዳንዶች የገንዘብ ምንጩ ቱባ ነጋዴ በመሆኑ ነው ይበሉ እንጂ ብዙዋችን የሚያስማማው ጥቁሮችን በመሸጥ ያካበተው ነው ።

የዚህ ሃውልት ህጋዊነት ለበርካታ ግዜ የብርስቶል ከተማን ህዝብ አወያይቷል ፣ አጨቃጭቋል ። የሰውየው ሌጋሲ ለምሳሌነት አይበቃም በሚል የሃውልቱን መቆም የሚቃወሙት ሰሚ ሳያገኙ ቆይተዋል ። ዛሬ ከ 125 አመታት በኋላ ‹ ታላቁ › ኤድዋርድ ኮልስቶን አደባባይ ላይ በትዝብት እንደቆመ አልቀጠለም ። ዘረኝነትን በሚቃወሙ / Black Lives Matter / ሰልፈኞች እንደ በሬ በገመድ ተጠልፎ እንዲወድቅ ተደርጓል ። ከወደቀ በኋላ እንደ ሳዳም ሁሴን ሃውልት ተረግጧል ፣ ተተፍቶበታል ፣ ተረግሟል ። እንደ ጆርጅ ፍሎይድ ገዳይ አንገቱ ተረግጦ ‹ መተንፈስ አልቻልኩም › እንዲል ተጠብቋል ። በመጨረሻም ድሮ ባህር አቋርጠው አውሮፓና አሜሪካ የመጡ ጥቁሮችን ያስታውስ ዘንድ ይመስል ወደ ባህር ተጥሏል ።

ኤድዋርድ ኮልስቶን በ1689 ጥቁሮችን እያስመጣ በመሸጥ በሚታወቀው / Royal African Company / ድርጅት ውስጥ ምክትል ሃላፊ ነበር ። በዚህ ካምፓኒ ውስጥ እየሰራ 84 ሺህ 500 የሚደርሱ ጥቁሮችን በመርከብ አጓጉዟል ። ከዚህ ውስጥ 23 ከመቶ ወይም 19 ሺህ 300 ያህሉ ወደብ ሳይደርሱ መንገድ ላይ በውሃ እጥረት ፣ በተቅማጥና በንጽህና ጉደለት ሞተዋል ። ይህ ሰው ሌላም የሚታወቅበት ጉዳይ አለ ። በ 70ቹ እድሜው የፓርላማ አባልነቱን ተጠቅሞ የባሪያ ንግድ እንዲስፋፋ ፔቲሽን እስከ ማሰባሰብ ደርሷል ።

እንግሊዝ ለህብረተሰቡም ሆነ ለሀገር ጥሩ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ተብለው የሚታሰቡ / በክፉም ሆነ በደግ /  ስመጥር ዜጎችን ሃውልት በማቆም በቀጣዩ ትውልድ እንዲታወሱና እንዲዘከሩ የማድረግ የረጅም ግዜ ባህል አላት ። አንዳንድ መረጃዋች እንደሚጠቁሙት በመላው ሀገሪቱ ከ828 የሚበልጡ ሃውልቶች በተለያዩ ከተሞች ቆመዋል ። እስካሁንም አንዳቸውም ላይ በተቃውሞ መልኩ የመፍረስ አደጋ አላጋጠማቸውም ። ነገር ግን ከቅርብ ግዜ ወዲህ ያልተለመዱ ትችቶችን ያስተናገዱ ሃውልቶች ታይተዋል ። ሁለተኛ አለም ጦርነትን ለማስታወስ በተደረግ ዝግጅት ላይ አንዳንድ ሃውልቶች ላይ ACAB የሚል ጽሁፎች ተነበዋል - All Cops are Bastars የሚል ትርጉሙ እንደያዙ ተገምቷል ።በቅርቡ ለንደን ውስጥ በተደረገው ሰላማዊ ሰልፍም የቀድሞው የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትር ዊንስተን ቸርችል ሃውልት ላይ ዘረኛ ነበር የሚል ጽሁፍ ተለጥፎበት ነበር ።

በአንድ በኩል « የባሪያ ንግድ ውርስ ነው » በሌላ በኩል « አይደለም የበጎ አድራጎነት ምልክት ነው » እየተባለ ሲያጨቃጭቅ የኖረው ሃውልት መፍረሱ የእንግሊዝን መንግስት አስቆጥቷል ። የሆም ሴክሬቴሪ ሃላፊ ፕሪቲ ፓታል ድርጊቱን አሳፋሪ በማለት ተጠርጣሪዋቹን እንፋረዳለን ብለዋል ። በነገራችን ላይ ኤድዋርድ ኮልስቶን በብርስቶል ከተማ በስሙ የኮንሰርት አዳራሽ ፣ ጎዳና እና ትምህርት ቤት ተሰይመውለታል ። ትግሉ እነዚህም እንዲፈርሱ ይዋጋል ወይስ ባፈረሰው ሃውልት ተጠያቂ እስከመሆን ይደርሳል ? እየከረረ ከመጣው የእንግሊዝ ተቃውሞ አንጻር ይህን ጥያቄ በቀላሉ መመልስም ሆነ እንደዋዛ መተውም የሚቻል አይሆንም ።

Saturday, April 11, 2020

ከአዳም ረታ ‹ አፍ › እስከ መንጌ ‹ እንባ ›…



የኮሮና ቫይረስን ወረርሽኝ የመከላከያው አንደኛው መንገድ በራስ ላይ ማእቀብ መጣል ነው ፤ ቤት ውስጥ መከተት ። ቀኑን ለመግፋት ታዲያ በሆነ ስራ መጠመድ ግድ ይላል ። የቤት ስራ ባይሆንልኝም የማንበብ ልምዴ ድብርትን ታድጎታል ። ምክንያቱም ሁለት ተጋምሰው የነበሩ እና ሁለት ያልታዩ መጽሃፍትን እንዳጣጥም ስለረዳኝ ። ስራዎቹ የዶ/ር አለማየሁ ዋሴ « እመጓ » ፣ የአዳም ረታ « አፍ » ፣ የለምን ሲሳይ « My name is Why » እና የሀብታሙ አለባቸው « የቄሳር እንባ » ናቸው ። በአንዳንዶቹ ላይ ሰፊ ትንታኔ ከመስራቴ በፊት አጭር ምልከታዬን እንካችሁ ፤ ታነቧቸው ዘንድም ስሜቴን ለመጋባት ።

 በቀላል አቀራረብና ቋንቋ የተጻፈው « እመጓ » ምርጥ ሃሳብ የያዘ ስራ ሆኖ አግኝቸዋለሁ ። ይህ መጽሐፍ ያስታወሰኝ የግራም ሃንኩክን The Sign and The Seal  / ታቦተ ጽዮንን ፍለጋ / የተባለ ስራ ነው ። ሃንኩክ ቅዱስ ጽዋ ሊገኝባቸው ይችላል ብሎ ከሚጠረጥራቸው ሃገሮች አንደኛዋ ኢትዮጽያ ናት ። የአለማየሁ ዋሴ « እመጓ »ግን ቅዱስ ጽዋ መንዝ ውስጥ ይገኛል የሚለው በርግጠኝነት ነው ። ይህን የሚያዳብሩት ታሪካዊ ፣ ሃይማኖታዊና መላምታዊ መረጃዋች በሚያስደምም ቅንብር ይተረካሉ  ። ቅዱስ ጽዋ የሚገኘው ቫቲካን ፣ ለንደን ፣ ማርሴይ ፣ ቆጽሮስ ፣ ደማስቆ ወይም ኬብሮን ሳይሆን ኢትዮጽያ ነው ይላል ተራኪው ሲሳይ ። እመጓ በእንግሊዘኛ ተተርጉሞ ሃንኩክም ሆነ ያገባናል የሚሉ ሀገሮች ቢያነቡት እንዴት መልካም ነበር ብያለሁ ።

የአዳም ረታን « አፍ » የጨረስኩት እንቅፋት እየቦዳደሰኝ ነው ። ዋናውን ታሪክ ይዤ ስጓዝ ድንገት ብቅ ከሚለው « የግርጌ ማስታወሻ » ጋር እጋጫለሁ ። ማስታወሻው በጣም ረዝሞ ዋናውን ታሪክ ይገዳደራል ፣ አንዳንዴ ደግሞ ማስታወሻ አይደለም ራሱን የቻለ ተዛማጅ ታሪክ እንጂ የሚያሰኝ ቅርጽ ይታይበታል ። ለምሳሌ ያህል ዋናው ታሪክ ላይ የገለታ ጉንጭ ስንቡክ ነው ይላል ። ስንቡክ የሚለው ቃል አናት ላይ አንድ ቁጥር ተጽፏል ። እንግዲህ ይህን ስንቡክ ይረዱ ዘንድ ነው ሶስት ገጽ የሚያነቡት ። አዳም ሰላሳ ያህል የማስታወሻ / የታሪክ / ቁጥሮችን ተጠቅሟል ። አንዳንዴ ለብቻው ተሰምሮ የተቀመጠውን « የግርጌ ማስታወሻ » ጨርሼ ወደ ኋለ ስመለስ ዋናው ታሪክ ይጠፋብኛል ። ። የልቦለዱን ቅርጽ ለየት የማድረግ መንገድ የመሻት ሃሳብ ይመስላል ። እንደሚታወቀው አዳም ብዙ ቅርጾችን አሳይቶናል - ጥሩዎችም ነበሩ ። ይህኛው ግን በጣም ያደክማል ። እንደኔ እንደኔ አዳም ረታ ታላላቅ ሃሳቦች /ይዘት / ላይ ቢያተኩር እመርጣለሁ ።

የለምን ሲሳይ « My name is Why » በራሱ የልጅነት ህይወት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ስራ ነው ። መንግስት ልጅ ሰርቆ እስር ቤት ከቷል ፣ የህይወት ታሪኩም እንዳይታወቅ ድብቋል ይላል ደራሲው ገና ከመነሻው ። የሲሳይ እናት እንግሊዝ ለትምህርት የደረሰችው በ1966 ነበር ። በወቅቱ ነፍሰ ጡር ነበረች ። መውለጃዋ ሲደርስ ዊጋን አካባቢ በሚገኝ አንድ ሆስፒታል በ1967 ደራሲውን ተገላገለች ። በወቅቱ አባቷ ስለሞቱ ወደ ሀገሯ መመለስ ነበረባት ፤ ያኔ ነው እንግዲህ ኖርማን ግሪንውድ ተበሎ ለአሳዳጊ የተሰጠው ። እናቱ ወደ ሀገሯ ስትመለስ ልጅዋ ለአሳዳጊ ተላልፎ እንዲሰጥ ፍቃድዋን አልሰጠችም ።

ለለምን ሲሳይ ህይወት ፈተና ነበረች ። ገና በ12 አመቱ ነበር አሳዳጊዎቹ ያባረሩት ። አሳዳጊዎቹ ለሁለቱ ልጆቻቸው የሚያሳዩት ፍቅር፣ ክብርና እንክብካቤ ለእሱ የራቀ በመሆኑ ነው ግጭቱ እንዲያድግ ምክንያት የሆነው ። ከ12 እስከ 17 አመቱ ደግሞ በአራት የተለያዩ ማሳደጊያ ቦታዎች ተወርውሯል ። በግራ እጁ ላይ NG የሚል ንቅሳት ቢያጽፍም እውነተኛ ስሙ ይህ ንቅሳት አለመሆኑን የተገነዘበው በ17 አመቱ ነበር ። ደራሲው ለ30 አመታት ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ትግል ገጥሟል ። ትግል የገጠመው ከልጅነት እስከ እውቀት ሲመዘገብ የቆየው የህይወቱ ታሪክ ተላልፎ እንዲሰጠው ነበር ። በ2015 የዊጋን ካውንስል ሃላፊ አራት ትላልቅ ዶሴዎችን አስረከቡት ። ከዚህ በኋላ ነበር ይህ መጽሀፍ የተወለደው ። ማንነቱን ለአለም ለማብሰር ስሜ ኖርማን ሳይሆን ለምን ነው በማለት የሚደክመው MY Name is Why…

ስለ ልጅነቱ ፣ ስለትምህርቱ ፣ ስለ አሳዳጊዎቹ ስብእና ፣ ስለ ባህሪው ፣ እናቱ ከእንግሊዝ መንግስት ጋር ስለተፃፃፈቻቸው ደብዳቤዎች  ምን አለፋችሁ እያንዳንዱ ትንፋሹ ዶሴው ውስጥ እየተመዘገበ ነው የቆየው ። ደራሲው ድብዳቤዎቹን አባሪ በማድረግ ነው እንግዲህ ታሪኩን በቅደም ተከተል የሚተርክልን ። በአሳዳጊዎቹ ብቻ ሳይሆን በቆዳ ቀለሙ ይደርስበት ስለነበረው ዘረኛ ጥላቻ ይነግረናል ። አካላዊና ሞራላዊ ጥቃቱን ሳያማርር ተርኳል ። እዚህና እዚያ የምትላጋው ህይወቱ ከክፋት አንፃር ከአንደንዥ እፅ ጋር ያስተዋወቀችውን ያህል ፤ በጥሩ ጎን ሲታይ ደግሞ ገና በ12 አመቱ ብእርና ወረቀት አዋዶ መግጠም እንዲችል ጥሪውን አሳይታዋለች ። ዛሬ ይህ ሰው በምድረ እንግሊዝ አንቱ የተባለ ገጣሚ ነው ። በ2015 ታላቅ ተግባር ለፈፀሙ ሰዎች የሚሰጠውን Order of the British Empire ተሽልሟል ።

የሀብታሙ አለባቸውን « የቄሳር እንባ »ን እንደተለመደው በተመስጦ ነው ያነበብኩት ። የቄሳር እንባ የውድቀትና የስንብት እንባ ነው ። የመጽሀፉ ዛቢያ ኮሎኔል መንግስቱ ሃይለማርያም ሲሆኑ በእሳቸው ዙሪያ ቤተሰባቸውና ዘመዶቻቸው ፣ ደርግና ጦር ሰራዊቱ ሲሽከረከሩ እንመለከታለን ። ጦርነት ፣ ንቅዘት፣ በስልጣን መባለግና ፖለቲካዊ ድንቁርና ለአብዮታዊ ስህተት መነሻ ሆነው ብዙ ዋጋ ሲያስከፍሉ እንታዘባለን ። ደራሲው በሱፍ አበባ ላይ « ገበርዲን » እንዳለው የፍልስፍና ሃሳብ እዚህ ስራ ላይም « ልግመት ሶሻሊዝም»ን አስተዋውቆን የፓለቲካውን ግለትና ቆፈን እንዲሁም መነሻና መድረሻውን ያብጠረጥረዋል ። የቄሳር እንባ የሴራ አወቃቀርና የገፀባህሪ አሳሳል ድንቅ ነው ። ፓለቲካዊ ትንታኔውና የፍቅር በከራው አንባቢን ላይና ታች ይንጣል ።

በነገራችን ላይ ሀብታሙ አለባቸውን ለመጀመሪያ ግዜ በስራው ያወኩት በ « አውሮራ » ነው ። የኢትዮ ኤርትራን ጦርነት መሰረት ባደረገው በዚህ ስራ ተደንቄ ነበር ። በድርጊትና በመረጃ የደነደነ ፈጣን ታሪክ አለው ። ፍቅርና ጦርነትን በእኩል ጥፍጥና ከሽኖ የቀረበ የምናብ ውጤት ነበር ማለት ይቻላል ። ቀጥሎ ደግሞ « የሱፍ አበባ» ን አነበብኩ ። የኢህአፓ ዘመንን ድብብቆሽና ፍልሚያ ። ይህም መጽሀፍ ፍልሚያና ፍቅርን ተራ በተራ እንኮኮ ሲያደርግ አይደነቃቀፍም ። በዚህ መጽሀፍ የፖለቲካ ቅኔ ብቻ ሳይሆን የፍልስፍና ጥብብም ሲደንስ ታይቷል -  የሚያምር ብእር ። ለሶስተኛ ግዜ ደግሞ የቄሳር እንባን ።

ደራሲዋች አንዳንዴ ጥሩ ስራ ሲያቀርቡ ሌላ ግዜ ደግሞ ከደረጃ ይወርዳሉ ። በሀብታሙ ስራዋች ላይ የወጥነት ችግር አላየሁም ። በተከታታይ ምርጥ መሆን መታደል ብቻ ሳይሆን ልዩ ችሎታን ይጠቁማል ። የሚያነሳቸው ርእሰ ጉዳዮች ወይም ጭብጦች ትላልቅ ናቸው ። በኢትዮጽያ ስነፅሁፍ ደረጃ ያጣናቸውን ወይም ያልታዩ ክፍተቶችን ነው እየሞላልን የሚገኘው ። ይህ ደራሲ ከምንም በላይ እውቀትን መሰረት አድርጎ ነው የሚጽፈው ። ብዙ ያነበበ ወይም ብዙ ለፍቶ የሚጽፍ መሆኑን ስራዎቹ አፍ አውጥተው ይናገራሉ ። ምናለፋችሁ የደራሲውን ቀሪ ስራዋች ማለትም ‹ ታላቁ ተቃርኖ › እና ‹ አንፋሮ ›ን ለማንበብ ቸኩያለሁ ።



Thursday, February 13, 2020

ተስፋዬ ገብሬ ያስፈልገናል



እናት ኢትዮጽያ ውዲቷ ሀገሬ
በጣም ይወድሻል ተስፋዬ ገብሬ

በዚህና በመሳሰሉት ጥቂት ዘፈኖቹ እኛም እንወደው እናከብረው ነበር ፡፡ ዛሬ ደግሞ ማርቆስ ተግይበሉ በተባለ አጥኚ አማካኝነት / የበጎ ሰው ሽልማት የሚገባው / በስፋት አወቅነው ፡፡ ያልተሰሙ ሙዚቃዎቹን አዳመጥን .... ያልተሰሙ የህይወት ታሪኮቹን ሰማን ... ያልተነገሩ ህመሙን ፣ ህልሙንና ስሜቱን ተጋራን ፡፡

ተስፋዬ ገብሬ በብዙ ቋንቋዋች ዘፍኗል ፡፡ ጥበቡን ለጥበብነት ማቀንቀኑ ብቻ ሳይሆን ብዙ ርምጃ ተጉዞ ስለ ሀገሩ ኢትዮጽያ ለውጩ አለም ሰብኳል ፡፡ የቀለምና ቋንቋ ልዩነት ሰብዓዊነትን በደፈጠጠበት በዛን ወቅት ሙያውን ለማንገስ ፣ ስውነቱን ለማስከበር  ብሎም ሀገራዊ ክብሩን እንደ ሰንደቅ ከፍ አድርጎ ለማውለብለብ የላቀ ሚና ተጫውቷል _ እሱ እንደሚለው በነጮች ሰፈር ብቸኛው ጥቁር አቀንቃኝ በመሆን ፡፡

በአርትስ ወግ ላይ የቀረበው የተስፋዬ ገብሬ ተከታታይ ፕሮግራም አስደሳች፣ አሳዛኝና ልብ የሚነካ ነበር ፡፡ ለሀገሩ፣ ለቤተስቡና ለህዝቡ  የነበረውን ጥልቅ ፍቅር በመለኪያ ቀምሮ ይሄን ያህል ነበር ለማለት ይከብዳል ፡፡ ሀገሩን ውዲቷ እንዳላት ሁሉ አባቱ አቶ ገብሬንም በስም እየጠቀሰ አወድሷል ፡፡ ሌላው ቢቀር የሀገሩ ተራራና ዛፎቹ ምን ያህል እንደናፈቁት እንዲያውቁለት ይመኝ ነበር ፡፡ እስትንፋሱ እስከተቋረጠበት እለት ድረስ ታላቅ ክብር ስለሚገባት ኢትዮጽያ ልብ በሚያርደው ድምፁ አቀንቅኗል ፡፡

ወደድንም ጠላንም የተስፋዬ ገብሬ ዜማና ሀሳብ ዛሬም ያስፈልገናል ፡፡ ለታመመችው ፣ ለቆሰለችው ከዚያም አልፎ ስጋት ተራራ ላይ አቁመው ክኋላ በርግጫ ቁልቁል ለመጣል ላሰፈሰፉት < እንክርዳድ > ልጆቿ የተስፋዬ ዜማና ሀሳብ መታደጊያ መንገድ አለው ፡፡ ተስፋዬ እናት ነው ነው የሚላት ፟ ኢትዮጽያን ፡፡ የላቀች መሆኗን ለማሳየት ውዲቷን ይጠቀማል ፡፡ ይሄ ሁሉ አልበቃ ብሎት በጣም እወድሻለሁ እያለ ነው ፡፡ በጣሊያንኛና በእንግሊዘኛ የሚወዳት ሀገሩን ሌሎች እንዲያውቁለትና እንዲወዷት መፅሀፍ አዘጋጅቷል / ወደፊት ያገባናል ባዮች ካሉ ሊታተም የሚችል / ካሴቱና መፅሃፉ ተሸጦ እንዲሰጥለት የተናዘዘው ደግሞ ውሃና መብራት ለሌላቸው ህዝቦች ነበር ፡፡

በተቃራኒው ዛሬስ ?...  < እቺ ሀገር ...  > እያለ የሚያንጠለጥላት ህዝብ ቁጥሩ ቀላል አይደለም ፡፡ ሀገሩን በእናቱ ለመመሰልም ሆነ ውዴ ብሎ ለመጥራት በራስ የመተማመን ትከሻ አጥቷል ፡፡ ወሽመጡ በራሱ አይናፋርነት ወይም በፖለቲካ ያገባናል ባዮች ሴራና ማስፈራሪያ ተበጥሷል ፡፡ ስለወለደችው ኢትዮጽያ ሳይሆን በማደጎነት ሰለተሾሙለት ክልሎች አብዝቶ ተጨናቂ ሆኗል ፡፡ እውነቱ ግን የሺህ እንጀራ እናቶች ልጥ የአንዷን ወላጅ እናት ፍልጥ ለማሰር አለመቻሉ ነው ፡፡

ዜማችንም ሆን ተግባራችን ከትልቁ ግንድ ወደ ቅርንጫፍች እንዲፈስ መትጋት ግድ ይላል ፡፡ የጋራ እናታችንን አንድም በሞራል  ሲቀጥልም በህግ የምናከብርበት አሰራር በሁሉም አካላት ተግባራዊ መሆን ይኖርበታል ፡፡ ስለጋራ እናታችን ሳናዜም ሰላም እና ብልፅግን መመኝት ከንቱነት ነው ፡፡ እናም በልበ ሙሉነትና ሳንሸማቀቅ የተስፋ
ዬን ዜማ ተውሰን የሚከተለውን ማዜምም መሆንም ይጠበቅብናል ፡፡

እናት ኢትዮጽያ ውዲቷ ሀገራችን
እናስበልጥሻለን ከየክልሎቻችን

Sunday, March 24, 2019

ሚዛናዊነት ከራስ ቢጀምር ...



ፍ/ቤት የቆመችው የፍትህ ምስል / Lady Justice / ተጠሪነቷና ምሳሌነቷ ለፍ/ቤት ስራ ብቻ አይመስለኝም ፡፡ አይኗን ሸፍና ያላጋደለ ሚዛን የያዘችው አስተዳዳሪዎች በሞራል ህግ ተመርተው ለዜጎች ሁሉ ሚዛናዊ አገልግሎትና ውሳኔ እንዲያስተላልፉ ነው ፡፡
ዶ/ር አብይ አህመድ ደጋግመው ስለሚዛናዊነት ይሰብካሉ ፡፡ ጋዜጠኞች የተመጣጠነ ዜና እንዲያቀርቡ ፣ አክቲቪስቶች ከዋልታ ረገጥ ሀሳብ ወደ መሃል እንዲመጡ ፣ ፖለቲከኞች እኔ ብቻ ነኝ አዳኝህ ወይም የማውቅልህ ከሚለው አባዜ ተላቀው ለሌላውም ስራ እውቅና እንዲሰጡ ወዘተ ወዘተ...

የሚዛን መንሻፈፍ ግለሰብን ፣ ማህበረሰብንና ሀገርን እየቆየ እንደሚጎዳና ለማይጠገን ቀውስ እንደሚዳርግ የሚገነዘብ ሁሉ በዚህ ሀሳብ ይስማማል ፡፡ ችግሩ ዶ/ር አብይ እንዳሉት ሁሉም ቀድሞ ጣቱን የሚቀስረው ሌሎች ላይ የመሆኑ አባዜ ነው ፡፡ ይህ የጣት ቅሰራ ራሳቸው ዶ/ር አብይንም ይመለከታል ፡፡ አንዱን ትልቅ ጥፋት ሸፋፍነህ ሌላው ላይ ጣትህን ስትቀስር ሚዛናዊነት ይንጋደዳል ፡፡ አንዱን ትልቅ ጥፋት አላየሁም ብለህ አይንህን ከሸፈንክ ሌላኛው ጥፋት ላይ የአይንህን መጋረጃ ቀደህ ለመጣል ሞራል ታጣለህ ፡፡

           ከብዙ ምሳሌዎች የተወሰኑትን ብቻ እናንሳ ፡፡ ገና በጠዋቱ ሀገሪቱ መሪ እያላት ስርዓት አልበኝነት ነገሰ ፣ ህግ ረከሰ ፣ የንፁሃን ደም በከንቱ ፈሰሰ የሚል ጩኸት ብዙዋች ቢያሰሙም የሽግግር ባህሪው ነው በሚል ሚዛናዊ ምላሽ መስጠት አልተቻለም ፡፡ ከዚህ ይልቅ በቅድሚያ ለውጡ ያመጣቸውን ትሩፋቶች ሳትደባብቁ አሞግሱ ማለት መጣ ፡፡ ትክክል ነው ሚዛናዊ ለመሆን የበርካታ ባህሪያት/ ጥሩ ተናጋሪ ፣ ትዕግስተኛ ፣ ይቅር ባይ ፣ ትሁትና የሰላም አጋር / መሆናቸውን መመስከር ይቻላል ፡፡ በዚህ ጥሩ ባህሪ  በመታገዝም መንግስታቸው አስደሳች ፖለቲካዊ ድሎች አስመዝግቧል ፡፡ ይህ ማለት ግን ለውጡ መሳ ለመሳ እየተጓዘ ያለው ከነውጥ ጋር ነው ነው ማለት ስህተት አይደለም ። ህገወጥነት ሀገሪቷን የወረረው ይቅርባይነት ስለበዛ ነው የሚል የቄለ ግምገማ የለኝም - በዚህ ረገድ መንግስታቸው ስትራተጂካዊ ብቃት የለውም የሚለው ሀሳብ የበለጠ ቅርብ ነው ። አሁን በቅርቡ እንኳን የሀገራችን ስርዓት አልበኝነት ተግባር ከ 8 እስከ 10 ወራት ይቀጥላል በማለት እንደ አመታዊ እቅድ ነግረውናል ፡፡ ህገወጥነትን አምርሮ ከመታገል ይልቅ ከህገወጥነት ጋር ተቻቻሎ ለመኖር ማሰብ ገራሚ አቋም ነው ፡፡ በተሸፋፈነች ፍትሃዊ አይን ሚዛናዊነትን እንይ ከተባለ ከዚህም በላይ ነው ፡፡

መንግስት ባለበት ሀገር አስራ ምናምን ባንኮች በጠራራ ፀሃይ ሲዘረፉ የሽግግር ሂደት ባህሪው ነው የምትል ከሆነ ሌላውን ሌባ ወይም ሙሰኛ ለመገሰጥም ሆነ ፍርድቤት ለማቆም ይከብዳል ፡፡ ምክንያቱም ፍ/ቤት የቆመችው የፍትህ ምስል ስለምትታዘብ ፡፡ ለተቃውሞ ዱላና ገጀራ አደባባይ ይዞ የወጣ ማህበረሰብ በቸልታ አልፈህ ያለዱላ ስብሰባ የከተመውን ወጣት በማያሳምን ምክንያት አስረህ የምታሸማቅቅ ከሆነ የሚዛናዊነት መሰረትህ ተናደ ማለት ነው ፡፡ ይከበር እየተባለ የሚለፈፈው ህግ ባለመከበሩ ዱላና ገጀራው አድጎ እነሆ ዛሬ የጦር መሳሪያ ይዞ አደባባይ መውጣት ተጀምሯል ፡፡ በገዛ ፍቃድህ ሚዛናዊ ካልሆንክ ብሎም ቸልተኝነት እንደ ኩይሳ ካሳደግክ ሌሎች አደባባይ የተገተረውን የፍትህ ሚዛን በሌላ ጡንቻ ይሰብሩብሃል ፡፡ ትርፉና ውጤቱም ይሄው ነው ፡፡

የቸገረው የከተማ ህዝብ ከሰውነት ተራ ወጥቶ በሰራው ኮንዶሚኒየም አትገባም ተብሎ ገጀራ ሲወደርበት<< የባለገጀራዋች ሀሳብ ይለምልም >> ብሎ መግለጫ ማውጣት እንዴት ሚዛናዊ ሊሆን ይችላል ? በቡራዩና ለገጣፎ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የደረሰው መፈናቀል ፣ እንግልትና አግላይ ርምጃዋች ከልብ ሳታወግዝ ሌላ ታፔላ ለጥፎ አደባብሶ ማለፍ የሚዛናዊነትን ጥያቄ ያስነሳል ፡፡ ጠ/ሚ/ሩ ሀገር የሚበትኑ ሀሳቦች ይወገዙ ይላሉ ፡፡ በሀገሪቱ ያለው ሁለት መንግስት የአብይና የቄሮ ይባላል የሚል ትንታኔ የሚሰጠው ጃዋር የበርካታ በታኝ ሀሳቦች ባለቤት ቢሆንም ውግዘት አይመለከተውም ፡፡ ኦሮሞ ከቋንቋው ውጭ ሌሎችን ማነጋገር የለበትም ፣ ከሌሎች ጋር መጋባትም ማቆም አለበት የሚለው የ < ምሁሩ > በቀለ ገርባ አፖርታዳዊ አስተያየት ለመመርመርም ሆነ ለመተቸት አልተፈለገም ፡፡ በተቃራኒው የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን ጥቅም ለማስጠበቅ በሚንቀሳቀሰው እስክንድር ነጋ ላይ ግልጽ ጦርነት እናውጃለን ተብሏል ፡፡ ሲጠቃለል ዶ/ር አብይ በበቀለ ፣ በኦነግ ፣ በጃዋር ፣ በህገወጥ ፖለቲከኞችም ሆነ በእስክንድር ሀሳብ ላይ ሚዛናዊ መሆን አልቻሉም ፡፡

ለዚህም ነው ማንኛውም ሚዛናዊ ለመሆን የሚጥር ስው ለምን የሚል ቀጥተኛ ጥያቄና እንዴት የሚል የጀርባ ምፀት ለማንሳት የሚገደደው ፡፡ ግዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ እንዲሰብር ብሂሉ ስለሚያስገድድ ? ምንም ቢሆን ዘር ክልጓም ስለሚስብ ? ... ኢትዮጵያዊነትን መርህ አድርጌያለሁ የሚል መሪ ለጃዋርም ሆነ ለእስክንድር ሀሳቦች እኩል የድጋፍም ሆነ የተግሳጽ መስፈርት ማበጀት ካልቻለ መርሁ ሁሉ Backfire ያደርግበታል ፡፡ ዶ/ር አብይ ከግዜ ወደግዜ እየገረጣ የመጣባቸውን ህዝባዊ እምነት ስር ሳይሰድ ለማከም ከፈለጉ ሚዛናዊነት ከራሳቸው መጀመር ያለባቸው ይመስለኛል ፡፡ ጥሩ መሪ ደግሞ እንደዛ ነው ፡፡ መንገዱን የሚያውቅ ፣ በመንገዱ የሚሄድ እና መንገዱን የሚያሳይ ስለሚሆን ፡፡ ባለግዜ ነን በሚሉ ቡድኖች የሚሰሩ አስከፊና አቀያያሚ ጉዳዮችን አደብ ማስገዛት ፣ አቅም ቢያጥር እንኳን በግልጽ አካፋን አካፋ በማለት ማውገዝ መጀመር አለባቸው ፡፡ ከዚህ ከጀመሩ ሌላኛውን ብልሹ ሀሳብና ተግባር ለማረቅ ምቹ መደላድል ይፈጥራል ፡፡ ይህ አካሄድ ልበ ሙሉነትን በቀላሉ ማትረፍ የሚያስችል ሲሆን ከሁሉም አቅጣጫ በቂ ድጋፍ ያስገኛል ፡፡ አክባቢዋን በሚያውቋቸው ሰዋች መሙላት ብቻ ሳይሆን ገለልተኛና ሚዛናዊ ሀሳብ የሚሰጡትንም አማካሪዋች ቢያበዙ ጭልጥ ብሎ ከመሳሳትም ያድናል ፡፡

Saturday, September 8, 2018

አርበኞች ግንቦት 7 እንኳን ደህና መጣህ




ወያኔ በግዳጅ በጫነው ፖለቲካዊ አደረጃጀት ሳቢያ ህዝባቸውን ለመታደግ ሲሉ ብሄር ተኮር አደረጃጀት ፈጥረው የተንቀሳቀሱ ድርጅቶችን ማክበር ተገቢ ነው ፣ በተለይም የእውነት ለታደጉትና እየታደጉ ለሚገኙት ፡፡ ሁሉን በአንዲት ታላቅ ሀገር ስም ፣ ሁሉን በኢትዮጵያዊነት ጥላ ደምረን እንሰራለን የሚሉ ድርጅቶች ሲገኙ ደግሞ ክብራችን ሌላ ጋት ይጨምራል ፡፡

አስጊ ጫፍ ላይ የተንጠለጠለችውን ኢትዮጵያ ወደ መሃል ስቦ ሚዛኗንና ሚዛናዊነትን ለማስጠበቅ እሰራለሁ የሚለውን አርበኞች ግንቦት 7ን ማበረታታትና መደገፍ የውዴታ ግዴታ ሆኗል ፡፡ ለምን ? ነባራዊው የፖለቲካ ሁኔታ የሚነግረን ጥቂት የአንድነት ወይም ኢትዮጵያዊያን ሃይሎች በየትየለሌ ብሄር ዘመም ድርጅቶች ተውጠው መገኘታቸውን ነው ፡፡ ብሄር ተኮር ድርጅቶች እድል አግኝተው ምርጫ ቢያሸንፉ እንኳ በኢትዮጵያ ላይ የሚኖራቸው የመጨረሻ ግብ ግልፅ አይደለም ፡፡ ኢትዮጵያ እንዳትፈራርስ ዋስትና የሚሰጥ ጠንካራ የፖለቲካ ፕሮግራምም የላቸውም ፡፡

ሌላው ቀርቶ ኢትዮጵያዊነትን እያዜመ የሚገኘው < አዲሱ ኢህአዴግ > እንኳ የአቅጣጫና የርዕዮት መስመሩን አላሻሻለም ፡፡ አራቱ እህት ድርጅቶች ሜጀር ተግባራቸውም ሆነ ቀጣይ ግባቸው ብሄር ተኮር ድልድይ መገንባት ይሆናል ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን የሚጠቃቅሱት በማይነር አስተምህሮት ነው ፡፡ በዚህ ስሌት ኢትዮጵያነት እንደምን ገዝፎና አሸንፎ ሊወጣ እንደሚችል ግልፅ አይደለም ፡፡ ከአቅጣጭ አንፃርም ኢህአዴግ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መንገዱን እንደማይለቅ ዶ/ር አብይ በቅርቡ መናገራቸው ይታወሳል ፡፡ በልምድ እንዳየነው ደግሞ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ዘብነት ወይም ጥብቅና ለብሄሮች እንጂ ለኢትዮጵያዊ ዜግነት አይደለም ፡፡

በብሄር ብቻ ሳይሆን በሃሳብ እና በአመክንዮ የሚወዳደሩ ጠንካራና ብስል ድርጅቶች ያስፈልጉናል ፡፡ በብሄርም ሆነ በዜግነት ማሰብ የወገንተኝነት መዳረሻ አለው ይባላል ፤ ትክክል ነው ፡፡ ፍትሃዊ ትክክለኝነት የሚመነጨው ግን የአግላይነት ድንበር ሲነሳ ነው ፡፡ የብሄር እሳቤ ትልቁ በሽታ ቀስ በቀስ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል ወደፈጠረው የአሳማዋች ፍልስፍና የማዳረሱ ክፋት ነው ፡፡ እንደሚታወቀው በአኒማል ፋርም አብዮት ያነሱት አሳማዋች የመጀመሪያ መፈክራቸው ውብ ነበር ፡፡ < ሁሉም እንስሣት እኩል ናቸው > እያሉ ነበር የሚዘምሩት ፣ ለውጡን በሙሉ ልብ ለመደገፍ የቆሙት ፡፡ እየዋለ እያደር ግን ብሄራዊ መፈክራቸው ወይም ህገ መንግስታቸው  < እኛ የተሻልን ነን > በሚሉ አሳማዋች ተቀይሮ ALL ANIMALS ARE EQUAL BUT SOME ANIMALS ARE MORE EQUAL THAN OTHERS የሚለውን ዘረኛ አንቀፅ ተሸካሚ ሆነዋል ፡፡ ሃሳቡን የማይደግፉ ሁሉ ትምክህተኛ እየተባሉ ተዘልፈዋል ፣ እንዲሸማቀቁ ተደርጓል ፣ ከመኖሪያ ቀያቸውም ተፈናቅለዋል ፡፡ የብሄር እሳቤ ትልቁ በሽታ < እኔ ከሌሎች የተሻልኩ ነኝ > የሚል ስስታም ተቀጥላ ስለሚያመነጭ ለዘወትር ብጥብጥና ግጭት መንሳኤ መሆኑ ነው ፡፡

ይህን በመሰሉ 40 እና 50 ድርጅቶች ተውጦ ፖለቲካን መስራት ደግሞ ያሰጋል ፡፡ መቼም ቢሆን ስነልቦናዊ መረጋጋትን ፈጥሮ በኢኮኖሚውም ሆነ ማህበራዊ ሰልፍ ወስጥ ራስን ለማስገባት ያስቸግራል ፡፡ የዳር ተመልካቹን ፣ የምናገባኝ አቀንቃኙን ፣ ባለግዜዎቹ  ይዘውሩት ባዩን ያበራክታል ፡፡ ሀገር ሰልላ እንድትሞትም አሉታዊ ሚና ይጫወታል ፡፡ ለዚህም ነው ፖለቲካው በቋንቋና ብሄር ብቻ ሳይሆን በሃሳብ ይሞገት የሚባለው ፡፡ ሃገር የሚያሳድገውና የሚያስከብረው ለሁሉም የሚጠቅም የዳበረ ሃገራዊ ሃሳብ ሲመነጭ ነው ፡፡ ሃሳብ ሳይገደብ ሊፈስና ሊመነጭ የሚችለው ደግሞ አጥር ሲፈራርስ ነው ፡፡ ከጠባብና የሚያፍን ክፍል ወጥቶ ማለቂያ በሌለው መስክ ላይ እንደልብ መሯሯጥ ሲቻል ፡፡

ህዝቡ በቅርቡ የተገኘውን ለውጥ የደገፈው ኢትዮጵያዊነት ከፍ ብሎ ስለተዘመረለት ነው ፡፡ በኢትዮጵያዊነት ውስጥ አንድነት ፣ ሰላምና ፍቅርን አበለፅጋለሁ ብሎ ስላሰበ ነው ፡፡ ይህ ከፍታ ደረጃውን ጠብቆ ይጓዝ ዘንድ እንደምሶሶ ጠልቀው የተቸነከሩ ድርጅቶች እዚህና እዚያ መታየት ይኖርባቸዋል ፡፡

ተወደደም ተጠላ ኢትዮጵያ ታላቅ ሀገር ናት ፡፡ የሚመጥናት ትልቅነቷን ጠብቆ ከተቻለም አልቆ የሚጓዝ ድርጅት ነው ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን ዳግም ለማንገስ ተስፋ ከተጣለባቸው ድርጅቶች አንዱ አርበኞች ግንቦት 7 ነው ፡፡ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ ኢትዮጵያዊያን ስለ ኢትዮጵያዊነት ሆ ! ብለው ቢዘምሩ ሳያፍርና ሳይሸማቀቅ የግጥምና ዜማ ድርሰት ለማበርከት መዘጋጀት ስለሚችል ነው ፡፡ ሌላ ጠንካራ ህብረ ብሄራዊ ድርጅት እንደ አማራጭ እስኪወጣ ድረስም ግንቦት 7 እንዳይደናቀፍ አጥርና ጋሻ ሆኖ መመከት ያስፈልጋል ፡፡ ይህ ድርጅት በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ወስኖ ወደ ኢትዮጵያ መግባቱ ትልቅ ትርጉም አለው ፡፡ ከመሰል ድርጅቶች ጋር ህብረት ፈጥሮ ስለሚንቀሳቀስም የተፈጠረው ኢትዮጵያዊነት እሳቤ እንዲቀጣጠልም ይረዳል ፡፡ ቢያንስ በዘውገኞች የተከበቡ ዜጎች ተስፋ እንዳይቆርጡ ተስፋ እና ዋስትና ይፈጥራል ፡፡ አርበኞች ግንቦት 7 በትክክለኛው ግዜና ቦታ የተገኘ ድርጅት ስለሆነ እንኳን ደህና መጣህ ሊባል ይገባል ፡፡

Saturday, August 18, 2018

በግማሽ ሜዳ መጫወት ...



ሶሎ ጎል ይሉታል ፈረንጆቹ ፡፡ አንድ ተጫዋች በርካታ ባላጋራዎቹን አልፎ ጎል ሲያስቆጥር ፡፡ በጥበብ ፣ አካላዊ ብቃት ፣ ብልጠትና ድፍረት መሞላትን ስለሚጠይቅ ሁሉም ተጫዎቾች ሊያከናውኑት አይችሉም ፡፡ እናም ለግብ አግቢው ከወንበር ተነስቶ የረዘመ ጭብጨባና ክብር መስጠት ግድ ይላል ፡፡

ልክ እንደ ሶሎ < ዋው > የሚያስብል ሌላ ጥበብም እለ በእግር ኳሱ ዘንድ ፡፡ ከግማሽ ሜዳ ኳስን በትክክል መትሮ ጎል ማስቆጠር ፡፡ ይህንም ሲያደርጉ ያየናቸው ጥቂት የዓለማችን ተጫዋቾች ናቸው ፡፡ ጁዋን ካርሎስ ፣ ናቢ ፍቅርና ዋይኒ ሩኒን እንደ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል ፡፡ ኤቨርተንና ዌስትሃም ሲጫወቱ ዋይኒ ሩኒ ያደረገው ምንድነው ? ከክልሉ ወጥቶ ኳሷን ወደ መሃል ያወጣትን በረኛ ሁኔታ በመገንዘቡ ኳሷ ስትደርሰው ቀጥታ ወደፊት አጎናት ፡፡ ዳኛው የተለጋውን ኳስ እንዳይነካ አፈገፈገ ... ሁለት ተጫዋቾች ባለ በሌለ ሃይላቸው ወደላይ ለቴስታ ዘለሉ ... የመጨረሻው ተከላካይ ከሩቅ የተለጋ ኳስ ከሚቆጠርብን በእጄ ለኤሪጎሬ ባስቀራት ይሻላል ብሎ ወደ ላይ ዘለለ – አላገኛትም ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግብ ጠባቂው ወደጎል ሮጦ በማያውቀው ፍጥነት እየተፈተለከ ነበር ፡፡ ልብ አንጠልጣይ ድራማ ካየን በኋላ ኳሷ ከመረቡ ጋ ተሳሳመች ፡፡

ዶ/ር አብይ በእነዚህ አብዶኛ ተጫዎቾች ይመሰላሉ ፡፡ ከግማሽ ሜዳ የጠለዟቸው የፖለቲካ ኳሶች ጅቡቲ ፣ ሱዳን ፣ ግብፅ ፣ ሳዑዲ ፣ ኡጋንዳና ኤርትራ አርፈው ድል አስቆጥረዋል ፡፡ በአንድ በኩል የዲፕሎማሲውን ግንኙነት ሲያጠናክሩ በሌላ በኩል ማንም ሀሳብ ውስጥ ያልነበሩ ዜጎችን ከእስር አስፈትተዋል ፡፡ ወደክልሎች በመጓዝ ጥበብ ፣ ብልጠትና ድፍረት የተሞላበት ሃገራዊ ምክክር አድርገዋል ፡፡ በጎሳና ዘረኝነት ክፋት ተሰነጣጥቆ ሊበተን የነበረውን ኢትዮጵያዊ ትሪ ጠግነዋል ፡፡ የተራራቁ ሰዋች በአንድነት ተሰባስበው ባዛው ትሪ ላይ ማዕድ እንዲቀርቡ ፣ የጋራ ፀሎታቸውም ፍቅር ፣ ሰላምና ኢትዮጵያዊ ድማሬ እንዲሆን መንገድ አሳይተዋል ፡፡ ርቆ የተቀበረው ኢትዮጵያዊነት ክብሩ ተመልሶ ከባንዲራ በላይ እንዲውለበለብ አድርገዋል ፡፡

ዶ/ር አብይ በአጭር ግዜ ውስጥ ያስመዘገቧቸው ድሎች አመርቂና ተስፋ ሰጪ ቢሆኑም እየተጫወቱ የሚገኙት በግማሽ ሜዳ ነው ፡፡ ከትልቁ ጥያቄ አንደኛው ስንቱን ህዝባዊ ጥያቄ ከግማሽ ሜዳ እየመተሩ ማስገባት ይችላሉ ? የሚለው ነው ፡፡ ከትልቁ ጥያቄ ሁለተኛው ስንቱን እግር ሰባሪ ተከላካይ በአብዶ እየሸወዱ ውጤት ያስመዘግባሉ የሚለው ነው ፡፡

ዶ/ር አብይ ብዙ ተከላካዮችን አብዶ ሰርተው አልፈው ጎል የሚያስቆጥሩት ኢትዮጵያዊነትን ከዳር እስከ ዳር ለማሳደግ ነው ፡፡ ይሁንና ጥቂትም ሳይቆይ ሲዳማው ፣ አገው ፣ ጉራጌው በኔ ልክ የተሰፋ ክልል ይገባኛል ብሎ ጥብቆ ሲናፍቅ ታገኘዋለህ ፡፡ ዶ/ር አብይ ብዙ ተከላካዮችን አብዶ ሰርተው አልፈው ጎል የሚያስቆጥሩት  እንደ < ገነት > የምንናፍቀውን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እናይ ዘንድ ጥርጊያ መንገዱን ለመገንባት ነው ፡፡ ይሁን እንጂ ለድሃ ዳቦ እንጂ ነፃ ስርዓት አያስፈልገውም የሚሉ አምባገነኖች በተሰነጣጠቀው መንገዳችን ላይ የሚፈነዳዳ ፈንጂ ከመቅበር ሊቆጠቡ አልቻሉም ፡፡ ዶ/ር አብይ ከመሃል ሜዳ ለግተው ጎል የሚያስቆጥሩት የማሸነፍ ረሃብን ለማስታገስና ሮል ሞዴሎችን ለመቅረፅ ነው ፡፡ ይሁን እንጂ ማጥቃትንም ሆነ መከላከል እርግፍ አድርገው ትተው ጨዋታ የሚያቆሙ ብዙሃንን ታያለህ ፡፡ በሌላ አነጋገር ጨዋታውን አቋርጠው በፎርፌ ማሸነፋችን ይታወጅልን የሚሉ ፡፡ እነዚህ ወገኖች በጥቂት ወይም ሚዛን በማያነሳ ምክንያት ዱላ ፣ ገጀራና ክብሪት አንስተው ቀጣዩን ጥፋት ለማከናወን የማያመነቱ ሆነዋል ፡፡ ነገር ቆስቋሾች ፣ ገዳዳ አክቲቪስቶች ፣ በቀልተኛ ፖለቲከኞች ጃስ ባሏቸው ቁጥር ለምን ? እና እንዴትን ? ሳያነሱ ዘለው ንጹሃንን የሚናከሱ ወገኖቻችን እየበዙ መጥተዋል ፡፡ እነዚህን ሁሉ መግራት ከባድ ነው ፡፡ በአንድ ቀን ምክክርና የእርቅ ጉባኤም አጀንዳውን መዝጋት አይቻልም ፡፡

ጠ/ሚ/ሩ በየክልሉ በዘር ፣ ቋንቋና ሃይማኖት የሚለኮሱ ግጭቶችን ለማብረድና ለማስታረቅ የሚሯሯጡ ከሆነ ሌላውን አንገብጋቢ ስራ መስራት አይችሉም ፡፡ የፖለቲካ መዋቅሩም ሆነ ህዝቡ ጥሩ ጎል አግቢ ስለሆኑ እሳቸውን ብቻ የሚጠብቅ ከሆነ ሽምግልና እንጂ መንግስታዊ አሰራር ውሃ ይበላዋል ፡፡ ለዚያም ነው ጠ/ሚ/ሩ በግማሽ ሳይሆን በሙሉ ሜዳ መጫወት የሚችሉበት ቋሚ አሰራር መፈጠር አለበት የሚባለው ፡፡ ለዚያም ነው ከቅርብም ሆነ ከሩቅ ለግተው ግብ የሚያስቆጥሩ ኮኮቦችን ማፍራት ይገባቸዋል የምለው ፡፡

ርግጥ ነው በሀገራችን ያንዣበበውን ስጋት ለመቅረፍ ክፋትንና ድህነትን ተጭኖና አጥቅቶ በመጫወት ተደጋጋሚ ግቦችን ማስቆጠር ያስፈልጋል ፡፡ አለበለዚያ አቻ መውጣትና መሸነፍም ያጋጥማል ፡፡ አቻ መውጣት ክፋትንና ድህነትን አቅፎ መኖር ነው ፡፡ ወንድም ጋሼ ... ጌታ መሳይ... እያልከው ፡፡ ከተሸነፍክ ያለውድ በግድ < ጅቦች ለዘላለም ይኑሩ ! > የሚል መፈክር ተሸክመህ ትዘልቃለህ ፡፡ እነሱ የሚጥሉትን ቅንጥብጣቢ አያሳጣኝ እያልክ ፡፡ የሰላምና የፍቅርን ኳስ በማራኪ አጨዋወት እስከተቃራኒው ክልል ደርሶ ያማረ ጎል ማስገባት ያስፈልጋል ፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ለዋናው አጥቂ ኳስ አመቻችተው የሚሰጡ ደጀኖች ፣ አጥቂው ሲደክም ጎል ማስቆጠር የሚችሉ ቁርጠኛና ጥበበኛ ተጫዋቾች መሰለፋቸው መረጋገጥ ይኖርበታል ፡፡

በየክልሉ የሚለኮሱ ጎሳዊ ግጭቶችን ለመቀነስና ለመከላከል የተጠናከረ ትምህርትና ስልጠና ግድ ነው ፡፡ ለ27 ዓመታት የዘውጌ ስርዓት በማበቡና ብሄርተኝነት የተሻለ አማራጭ ተደርጎ በመሰበኩ ኢትዮጵያዊነትን በቀላሉ ማስረፅ ሳይከብድ አይቀርም ፡፡ ይህን ስራ የሚሰሩ የሲቪክ ተቋማትን ማስፋፋት ይጠይቅ ይሆናል ፡፡ ተመሳሳይ የፖለቲካ መስመር የሚከተሉ ድርጅቶችንና ቲንክታንኮችን Add እና Tag ማድረግ ግድ ይመስላል ። በውስጥ አሰራር ደግሞ ለንቋሳ አመራሮችን እየሻሩ ፣ ጠንካሮቹ ንቃተ ህሊናን ለማዳበር የሚያስችሉ የምክክር መድረኮችን ረጅም የስራ አካልና ግብ አድርገው እንዲተጉ ማሳሳብ ይጠበቃል ፡፡

ዘረኝነትና ጎሰኝነት አይደለም በአፍሪካ በአውሮፓ መሞት አልቻለም ፡፡ ጉዳት እንዳያደርስ ሸብቦ የያዘው ግን ጠንካራ ህጋቸው ነው ፡፡ ዶ/ር አብይ የፍቅርና ይቅርባይነትን ሎጎ ከፍ በማድረግ አስተዳደራቸው እንዳይንገጫገጭ ማድረግ ቢችሉ ሸጋ ነበር – ድብቁና ውስብስቡ ፖለቲካ ግን በዚህ ቀመር የሚሰራበት አግባብ በእጅጉ የሰለሰለ ነው ፡፡ አሸባሪ ፖለቲከኞችን ፣ የዘረኝነት ፈንጂ ቀማሚዋችን ፣ ብሄርን ከብሄር ለማጋጨት ሃሳብ ፣ ክብሪትና ጥይት የሚያቀብሉ የደም ነጋዴዋችን በአጠቃላይ ህገወጦችን መስመር የሚያሲዙበት ህጋዊ ማእቀፍ ያስፈልጋቸዋል ፡፡

Thursday, August 9, 2018

የኦሕዴድ የነገ ፈተና ...




ስልጣኑ ያለው ኦህዴድ ውስጥ ነው ፤ ኦሮሚያ ልብ ውስጥ ግን ኦነግ ከፍ ብሏል ፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ለዶ/ር አብይ አህመድ ፣ ለአቶ ለማ መገርሳና ለቲም ለማ ከፍተኛ ፍቅርና አክብሮት አለው ፡፡ ማሳያዎቹ ብዙ ናቸው ፡፡ ለምሳሌ በርካታ የሜኔሶታ ነዋሪ የሆኑ ኦሮሞዋች ሁለቱን መሪዎች በላቀ ደስታና የጀግንነት ስሜት ነው የተቀበሏቸው ፡፡ ነዋሪው የወደደው ግን ግለሰቦቹን ወይም የቲም ለማ ቡድንን እንጂ ባልሰልጣናቱ የቆሙበትን ድርጅት ጭምር አይደለም ፡፡ ድርጅታቸው የሰራውን ተግባር ዋጋ ለመስጠት አልፈለገም ፡፡ የዚህ አይነተኛ መገለጫ ደግሞ ከኢህዴድ ባንዲራ ይልቅ የኦነግ መለያ አዳራሹን ማጥለቅለቁ ነው ፡፡

በወቅቱ ባለስልጣናቱ ምን ያህል እንደተገረሙ ወይም ምን እያሰቡ እንደሆነ ማወቅ ቢቻል እንዴት መልካም ነበር ብዬ አስቤ ነበር ፡፡ ግን ስሜታቸውን ደብቀው ወይም ተቆጣጥረው መውጣት ችለዋል ፡፡ አንዳንዶች ይህ ጉዳይ ሜኔሶታ የተፈጸመው ኦነግ ለበርካታ አመታት የፓለቲካ ድልድዩን በእያንዳንዱ ሰው አካል ላይ መገንባት ስለቻለ ነው ይሉ ይሆናል ፡፡ አሁን በቅርቡ እንኳ ኦ ኤም ኤን አዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ ባዘጋጀው ዝግጅትም ላይም የኦነግ ባንዲራ ግዘፍ ነስቶ ታይቷል ፡፡ አዲስ አበባና አካባቢዋ ደግሞ ኦህዴድ እንጂ ኦነግ የፖለቲካ ድልድይ ለመገንባት እድል አልነበረውም ፡፡ ከለውጡ በፊትና በኋላም ቢሆን በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች በተካሄዱ ሰልፎች ላይ የኦነግ ምልክት በዋዛ የሚታይ አልነበረም ፡፡ ታሪካዊና ገራሚ አባባሎችን እንዲሁም ሳቅ ጫሪ መፈክሮችን ሲያውለበልብ ያየነው ህዝብ < ኦህዴድ ደማሪ ድርጅታችን ነው > ለማለት ባይደፍር እንኳ < እናመሰግለን > የሚል ባነር ከፍ ለማድረግ እጁን ምን እንደያዘው አጠያያቂ ነው ፡፡

ነገሩ ፓራዶክስ ይመስላል ፡፡ ቄሮና የፖለቲካ ድርጅቶች ከመላው ህዝብ ጋር በመተባበር ለውጡን አፋጥነውት ይሆናል ፡፡ የትግሉ መስመር በተለይ በኢትዮጵያዊነት ሃዲድ ላይ ዳግም እንዲጓዝ ያደረጉት ግን አብይና ለማ ናቸው ፡፡ የአነዚህን ሰዎች የላቀ ጥረት ዋጋ ሳይሰጡ መጓዝ ይከብዳል _ ኢትዮጵያዊነትን ቸለል ካላሉት በስተቀር ፡፡ የአንደበት ወዳጁ ህልቆ መሳፍርት የለውም ፣ በተግባር ልብ ውስጥ ያለው ማህተም ግን ንባቡ ሌላ እየመሰለ የሚከተሉትን ጥያቄዎች እንደዋዛ እንድንጠይቅ እያደረገ ነው ፡፡ ህዝቡ የምንወዳችሁ እኛ የያዝነውንም ስትወዱልን ነው እያለ ነው ? የድልድይ ሚናነት ስለተጫወታችሁ እናመሰግናለን እኛ ግን ከዚህኛው ወገን ነን እያለ ነው ? ወይስ የቲም ለማ ቡድን ነገ ከኦነግ ጋር እንዲቀላቀል በንግር / Foreshadowing / ቴክኒከ እያመላከተ ይሆን ?

ዶ/ር አብይ ዋና አላማዬ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ማካሄድ ነው ብለዋል ፡፡ መሬት ላይ የሚታየውን እውነት ተከትለን እንበይን ወይም እንገምት ካልን ማለትም ሁኔታዎች በዚሁ መልክ ከተጓዙ በኦሮሚያ የቀጣዩ ምርጫ አሸናፊ ኦህዴድ መሆኑ ያጠራጥራል / ምንም እንኳ የቲም ለማ ቡድን አባላት ወንበር ማግኘት ባይከብዳቸውም / ፡፡ ታዲያ የቡድኑ ልፋትና ጥረት ምንድነው ? ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ? ጥሩ ነው ፡፡ ግን ሽግግሩ ከኢትዮጵያዊነት ቆዳ የተሰራ ጠንካራ ኦህዴድን ለመገንባት የሚያስችል ነው ? ያጠራጥራል ፡፡ ነው ወይስ አንዳንዶች በግልፅ እንደሚሰጉት ኦህዴድ ቀስ በቀስ በህዝባዊ ማእበል እየተሸረሸረና እየተገፋ በኦነግ ሼል ውስጥ ይዋጣል ?

አንድን ሰው ከወደድክ ከነምናምኑ ነው ይባላል ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ መሰረት ፣ ለለውጡ ትልቅ ሚና የተጫወተው ኦህዴድ እውቅና ተነፍጎት የተወሰኑ መሪዎቹ ብቻ የሚወደሱ ከሆነ ድርጅቱ የአደጋ ቀጠና ውስጥ ይገኛል ማለት ነው ፡፡ የድርጅቱ አደጋ ውስጥ መውደቅ ደግሞ የራሱ ጉዳይ ተብሎ የሚታለፍ አይሆንም ፡፡ ምክንያቱም ይህ ድርጅት ለግዜውም ቢሆን አትዮጵያዊነትን በውክልና የተሸከመ ነውና ፡፡ በተራ የሎጂክ ትንታኔ እሳቤ ኦህዴድ < ባለ ተራው > መንግስትም ጭምር ነው ፡፡ እና እንዴትስ ቢያደርጉ ነው ግለሰባዊ ዝናን ተሻግረው ፖለቲካዊ / ድርጅታዊ አሸናፊነትን የሚቀዳጁት ? ነገሩ ቀላል ይምሰል እንጂ የመሆን _ አለመሆን ጥያቄ አለበት ፡፡ የቀድሞው መሪ እንዳሉት ኦህዴድ ሲፋቅ ኦነግ ይሆናል ወይስ ኦህዴድ ሲፋቅ ለመላው ህዝብ አንድነት ይበጃል ?

የኦህዴድ የነገ ፈተና በፍጹም ቀላል አይሆንም ፡፡ ሳይንሳዊ ድጋፍም የሚፈልግ ጭምር ፡፡


Friday, March 30, 2018

የደበበ ሰይፉ የ ‹ ብርሃን ፍቅር › ምስጢር ምንድነው ?



የታላቁ ገጣሚ ደበበ ሰይፉ የግጥም መጽሐፍ ‹ የብርሃን ፍቅር › ይሰኛል ። በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት አማካኝነት በ1980 ዓ.ም ለህትመት የበቃ ቢሆንም ዛሬም እንደ አዲስ ቢነበብ የማይጎረብጥ ይልቁንም በተክለቁመናው የሚመስጥ ስራ ነው ። ማለትም የዜማው ፣ የቃላት አጠቃቀሙ ፣ መልእክቱ ፣ የቤት አመታቱ እና የስንኝ አወራረዱ የአንባቢን ቀልብ ይስባል ።

አንባቢያንና የዘርፉ ባለሙያዎችም ተክለቁመናውን መሰረት በማድረግ ያሳደረባቸውን ስሜት በአስተያየትና በሂስ መልክ ሲጽፉ ኖረዋል ። የማያረጅ ወይም ዘመን ተሻጋሪ ስራ ነውና ነገም ብዙ እንደሚባልለት አያጠራጥርም ።

ደበበ የመጽሐፉን ስያሜ ለምን « የብርሃን ፍቅር » እንዳለው ግን ምንም የተባለ ነገር የለም ። ምንም ያልተባለው ሚዛን የሚደፋ ቁም ነገር ስለጠፋ አይደለም ። እንደሚመስለኝ ትችቶቹ ከተክለቁመናው ባሻገር ያለውን ገጽታ ማየት ባለመቻላቸው ነው ። ደበበ እንደ ብዙ ገጣሚዎች አንደኛውን ትልቅ ወይም ገዢ ሃሳብ ያለው ግጥም አንስቶ ለመጽሐፍ ርዕስነት አላደረገም ፤ በውስጡ ‹ የብርሃን ፍቅር › የሚል ግጥም የለምና ። የመጽሐፉን አጠቃላይ አንድምታ በመለካትም መዞ ያወጣው ነው ለማለት በቂ አይደለም ። ይልቁንም ብርሃናዊ ሚስጢራትን በመስቀለኛ ሃሳቦች እንድንመረምራቸው የፈለገ ነው የሚመስለው ፤ ማለትም ርዕሰ ጉዳዩን ከቀጥታ እይታ ፣ ከተምሳሌት ፣ ከአሊጎሪ አውድና ከመሳሰሉት ፈትሸን እንድናይ ከተቻለም የተገለጸውን ብርሃን እንድንሞቅ ።

ደበበ በስሜት ብቻ ሳይሆን በእውቀትም የሚጽፍ ባለቅኔ በመሆኑ ይህንን አያስብም ብሎ መከራከር አይቻልም ። ጸሐፊ ተውኔትነቱና ተመራማሪነቱም ይህን ሃሳብ ለመደገፍ እገዛ ያደርጋሉ ። ለምሳሌ ያህል ገጸባህሪ ፣ ሴራ ፣ መቼት እና ቃለ - ተውኔት የተባሉ ስነጽሑፋዊ ቃላትን በመፍጠር ሙያዊ እገዛ አድርጓል ።

አጋጣሚ ሆኖ እነዚህ የአማርኛ ፍቺ ያገኙ ሙያዊ ቃላት ይጠቀሱለታል እንጂ በግጥሞቹ ውስጥም በርካታ ያልተባለላቸው ስልቶች የሚገኙ ይመስለኛል ። አንደኛው ቃላትን በሚያዝናና መልኩ ደቅሎ መልእክትን የማስተላለፍ ጥበቡ ነው ።

ለምሳሌ ያህል ‹ ልጀቱ የዘመነችቱ › በተሰኘው ግጥሙ ውስጥ ዘማኒዋ ሱሪዋን - ሱርት ፣ ጫማዋን - ጭምት ፣ ቀበቶዋን - ቅብትት ፣ ጃኬቷን - ጅክት ነው የምታደርገው ። እነዚህ ከስም ውስጥ የተደቀሉ መገለጫዋች የገጣሚውን ምናበ ሰፊነት ያስረዳሉ - አንድም ቋንቋን ከመፍጠር አንድም ምስል አከሳሰትን ከማጉላት ።

እንደ እኔ እምነት የደበበ ሰይፉን ስራዎች በጥልቀት የመረመረ ባለሙያ አንድ ተጨማሪ የግጥም አይነት መታዘቡ አይቀርም ። ከወል ፣ ሰንጎ መገን ፣ ቡሄ በሉ ፣ ሆያሆዬ እና ከመሳሰሉት ውጪ ማለቴ ነው ። ደበበ ልክ እንደ ፀጋዬ ገ/መድህን የራሱ ቀለማት ፣ አወቃቀርና ምት የሚጠቀም ባለቅኔ ይመስለኛል ። በተለይ ከግጥም አወራረዱ አንጻር የአንድ ቃል ዜማ / ሽግግር / ወይም የአንድ ቃል መድፊያን በሚጥም መልኩ በብቸኝነት ተጠቃሚ ነው ።

ሰማይና ምድር ፣ ልጅነት ፣ በትን ያሻራህን ዘር ፣ ያቺን ሟች ቀን የተሰኙ ግጥሞች የዚህ አባባል ማሳያ ናቸው ። በ ‹ ሰማይና ምድር › ውስጥ

በጀርባዪ ተንጋልዬ
አውዬ
በቅጽበት የፈተልኩትን ለብሼ
ሞቆኝ
በእኔው አለም ነግሼ
ደልቶኝ
ከፅድቁ ገበታ ቀምሼ
ጣፍጦኝ
እያለ ይወርዳል ።
አውዬ
ሞቆኝ
ደልቶኝ
ጣፍጦኝ ... የሚሉ ነጠላ ቃላት ያነከሱ ይመስላሉ እንጂ ያለክራንች ነው የቆሙት - ለዛውም ጠብቀው ። በ ‹ ያቺን ሟች ቀን › ውስጥም እንዲሁ ብቻቸውን ቁጭ ያሉት ትብነን ! ... ትምከን ! ... የሚሉ ቃላት ርግማናዊ ግዝፈታቸው ከምላሰ ጥቁር የሰፈር ሽማግሌዎች ወይም መጋረጃ ካገዘፋቸው ታዋቂ ጠንቋዮች የላቀ ነው ።

ይህ ሃይለኛ የአወራረድ ስልት በ ‹ ደበበ ቤት › ተይዞ መጠናት ያለበት ይመስለኛል ። ደበበ እንግዲህ እንዲህ ከምናውቀው በላይ ብዙ ነው ። የብርሃን ፍቅር ሚስጢርነትም ሰፊ ፍቺ የሰነቀ ነው ። በመድብሉ ውስጥ 49 ግጥሞች ተካተዋል ። ከእነዚህ ውስጥ 24 ግጥሞች ብርሃንን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ያነሳሉ ። 15 የሚደርሱ ግጥሞቹ ብርሃንን የሚያወሱት ፀሃይንና ጨረቃን መሳሪያ በማድረግ ነው ። ማለትም ፀሃይና ጨረቃ በተፈላጊው ቦታና አውድ በግልጽ ተጠቅሰዋል ። ዳኢቴ ፣ አዴላንቃሞ ፣ እቴቴ ፣ ዛሬ እንኳን ፣ ብቻ መገኘትሽ ፣ ሀዘንሽ አመመኝ ፣ ይርጋለም እና የመሳሰሉትን ለአብነት መጠቃቀስ ይቻላል ።

ዘጠኝ በሚደርሱ ግጥሞች ደግሞ ‹ ብርሃን › የተወከለው ራሱን ችሎ ወይም ተምሳሌታዊ ሻማ በማብራት ነው ። ሰማይና ምድር ፣ ያቺ ቆንጂት ፣ ወለምታ ፣ ስንብት ፣ መንታ ነው ፍጥረትሽ እና የመሳሰሉት እዚህ ምድብ ወስጥ የሚወድቁ ናቸው ። ለአብነት ያህል ‹ ያቺ ቆንጂት › በሚለው ግጥም

ጋሼ ላጫውትህ ትለኛለች
ያይኔን ብርሃን እየሞቀች  › የሚል ተደጋጋሚ ስንኝ አለ ። እዚህ ላይ ብርሃን የተወከለው ፍቅርና መልካምነትን ለመግለጽ ነው ።
በግጥም መድብሎች ላይ በተለይም አንድን ጉዳይ በስፋትና በጥልቀት መወቀር የተለመደ አይደለም ። ምክንያቱ የተለያየ ቢሆንም በዋናነት ግን ገጣሚው ራሱ ሊያመነጫቸው በሚችለው ውስን ሀሳቦች ባለመርካቱ ሲሆን አልፎም ተርፎም አንባቢን አሰለቻለው ብሎ መፍራቱ ነው ።

የብርሃን ፍቅር ብርሃናዊ ጨረሮቹን በተለያየ መልክ ሳይሰስት ነው የሚያደርሰን ። በርግጥ ለደበበ ሰይፉ ብርሃን ምንድነው ? ብርሃንን የሚያስረዳን የጨለማ ተቃርኗዊ ውጤት መሆኑን ነው ? ወይስ ከሳይንሳዊ ፣ አፈታሪካዊ እና ሃይማኖታዊ ዳራዎች ጋር የተያያዙ ሃሳቦች አሉት ?

በ ‹ እሱ ነው - እሱ › ግጥሙ ላይ
እሱ ነው - እሱ
አይን ሳይኖረው
      ለምን ብርሃን ኖረ የሚለው
እግር ሳይኖረው
      ለምን መንገድ ኖረ የሚለው
እሱ ነው - እሱ
ከቀናቴ
      ፀሃይቱን የሰረቀ
በመንገዴ
      አሜከላ ያፀደቀ
እያለ የሚበሳጨው ለምንድነው ? ይህ ግጥም የምናወራበትን የ ‹ ብርሃን › ጉዳይ በሚገባ የሚገልጽ ነው ። ምክንያቱም የገጣሚውን ያገባኛል ባይነት ደምቆ እንመለከታለን ። በተጠየቅ የሚሞግትባቸው ቃላዊ - ሃሳቦች ብርሃን ፣ መንገድ እና ፀሃይ ናቸው ። ሃሳቦቹን በቤተዘመድ ጉባኤ አይን ካየናቸው አንድም ሶስትም ናቸው ። ገጣሚው በእውቀት ፣ እድገት እና እውነት ላይ የማይደራደር መሆኑ ይሰማናል ።

የደበበ ሰይፉ የብርሃን ትኩረት አንደኛው ምንጭነት ከህይወት ተምሳሌትነት የመቀዳቱ ጉዳይ ይመስላል ። ፈጣሪ በመጀመሪያ ሰማይና ምድርን ከፈጠረ በኋላ የምድር ጨለማ የተሸነፈው በብርሃን ውልደት አማካኝነት ነው ። ፈጣሪ ብርሃንን የፈጠረው ለድምቀት ብቻ አይደለም ። በብርሃን አማካኝነት ሃይል ተሞልቶ ለፕላኔታችን መቀጠል ትልቅ አስተዋፅኦ አድርጓል ። የመሬት ሰርዓተ ምህዳር የተመሰረተው በፀሃይ ከሚገኘው ብርሃን ነው ። ምክንያቱም አጽዋት የፀሃይ ብርሃንን ምግባቸውን ለማዘጋጀት ይጠቀሙበታል ። በሌላ በኩል ሰውና እንስሣት ምግባቸውን ከእጽዋት ስለሚያገኙ ሰንሰለቱ የጠነከረ ነው ።

ደበበ ሰይፉ የብርሃን ሰረገላ የማይታየውን ወይም የማይደፈረውን ነገር ሁሉ እውነት ለማድረግ የሚያስችል መሳሪያ መሆኑን የመረዳቱ ጉዳይም ርዕሰ ጉዳዩን አጥብቆ እንዲይዝ አግዞታል ።

ምነዋ ባየሁኝ › በሚለው ግጥም
ምነው ባየሁኝ
መሬቷን ሰቅስቄ
ዛፉን ተራራውን ቤቷን ሰዋን ሁሉ
አንድ ላይ ጠቅልዬ
በብርሃን ፍጥነት በሚምዘገዘግ ዘንግ
ወዲያ አንጠልጥዬ
እያለ ቀስተ ዳመናንና ጨረቃን ሁሉ ቀላል መጫወቻ እንዲሆኑለት ይመኛል ። ይህ ምኞት መለኮታዊ መሻትም ጭምር ነው ። ምክንያቱም መላዕክት የሚታዩት ብርሃን ባለበት ነው ። ብርሃንን ከመሬት ወደ ሰማይ ለመጓጓዝ እንደ ኤሌክትሮማግኔቲክ ሃይል ይጠቀሙበታል ። ሰዋች ጸሎትና ምሰጣ ሲያከናውኑ እንደ ሻማ አይነት ብርሃናዊ ነገሮችን የሚጠቀሙትም መለኮታዊ ግንኙነት ለመፍጠር በማሰብ ነው ።

ሌላው የደበበ ግጥሞች መሰረታዊ መለያ ፀሃይንና ጨረቃን የብርሃን ምሶሶ ወይም ኪናዊ ምርኩዝ የማድረጋቸው ጉዳይ ነው ። ከላይ እንደገለጽኩት 15 የሚደርሱ ግጥሞች ላይ ምርኩዝ ሆነው ቆመዋል ። አንባቢም በገባው መልኩ በዛቢያቸው እንዲሽከረከሩ ያደርጋቸዋል ። ገጣሚውም አልፎ አልፎ ለብቻ አንዳንዴ ደግሞ አንድ ላይ ያቀርባቸዋል ።

የጥንት ሰዋች የሁለቱን አብሮነት Duality በማለት ይገልጹታል ። ምክንያቱም እንደ ብዙ ሀገሮች አፈታሪክ ከሆነ ፀሃይና ጨረቃ ባልና ሚስት ፣ ወንድምና እህት ወይም ወንድማማቾች ሆነው ይወከላሉ ። የስው ልጅ ሲፈጠር ጀምሮ የሁለትዮሽ ውጤት ነው ። ሁለት እጅ ፣ ሁለት እግር ፣ ሁለት አይን ፣ ሁለት ጆሮ ወዘተ ያለው ። ይህ ጥምረት የፀሃይን ግማሽ እና የጨረቃ ግማሽ ውህደትንም ይወስዳል ። ፀሃይ የቀኝ ጎን ስትሆን ጨረቃ የግራ ናት ፤ የቀኝ ጎን ወንድ የግራ ደግሞ ሴትነትን ወካይ ነው ይላሉ ።

ደበበ ‹ አዴ ላንቃሞ › በተሰኘው ግጥም / አንድ የሲዳሞ ወንድ ነው / ተጠቃሹ ሰው ባሉት ሶስት ሚስቶችና ወንድ ሆኖ በመፈጠሩ ሲደሰት እናያለን ። በደማቅ የጨረቃ ብርሃን ታጅቦ ለሶስቱም ሚስቶች ለአዳር እንደሚመጣ ትእዛዝ ሰጥቶ እንዴት ሽር ጉድ እንደሚሉ በማሰብ ነው የሚስቀው ። ሊያድር የሚችለው ግን አንዷ ጋ ብቻ ነው ።

ብርማይቱ ጨረቃ
የብርሃን ጠበል አፍልቃ
ተፈጥሮን ስታጠምቃት
እንደገና ስትወልዳት
እያለ ነው ግጥሙ የሚዘልቀው ። እንደ ጨረቃዋ ልዩ ድምቀት ሶስቱ ሚስቶቹ ጋ በነበረው ሃያል ሙቀት እየረካ ነበር ። ምክንያቱም ሶስቱም ‹ እኔ ጋ ነው የሚያደረው › በሚል ያሻቀበ ጉጉት ጎጆውን በፍላጎት ፍላት እንደሚያነዱት ስለማይጠረጠር ። ጨረቃዋና ሴቶቹ በፈጠሩት ግለትም ሆነ ጾታዊ አንድነት የተመሳሰሉ ይመስላል ። በግጥሙ መሰረትም አዴ ላንቃሞ የወንድነቱን ፅድቅ አድናቂ ነውና ከጨረቃ በትይዩ የቆመ የፀሃይ ወገን ሊሆን ይችላል ።

ደበበ በተለይም ‹ ገና በልጅነት › እና ‹ ዛሬ እንኳን › በተሰኙ ግጥሞቹ ውስጥ ፀሃይና ጨረቃን በጋራ እየገለጸ ተጠቅሞባቸዋል ። ፀሃይን ሲያነሳ ሃይልን ፣ ህይወትን ፣ ጤናን ፣ ጥልቅ የፍቅር ስሜት መገለጫነትን በመወከል ሲሆን ጨረቃን ሲገልጻት ሚስጢርን ፣ ብቸኝነትን ፣ ውበትን የመሳሰሉትን እንድናስብ በማመላከት ነው ። የደበበ ሰይፉ የብርሃን ፍቅር ብርሃን አስሶ ፣ በብርሃን ተማርኮ ብርሃን የሚሰብክ ኪናዊ ዳመራ ነው ። ‹ የብርሃን ፍቅር › አንድ አይኑን ፀሃይ ሌላውን ጨረቃ አድርጎ ብርሃናማ መሃልየ የሚሰብክ ኪናዊ ካህን ነው ።

Wednesday, December 20, 2017

« አብዮት የራት ፓርቲ አይደለም ! » . ቀይዋ መጽሐፍ



በዓለማችን በብዛት እየተነበቡና እየተሸጡ ያሉ መጻህፍት ልቦለዶች አይደሉም ። መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የመጀመሪያ ደረጃን በመያዝ የወርቅ ሃብል እንዳጠለቀ የሚገኘው መጽሐፍ ቅዱስ ነው ። እንደ ጊነስ ወርልድ ሪከርድ መረጃ ከሆነ የሁልግዜ አንደኛ የሆነው መጽሐፍ ቅዱስ ህትመት ከ 5 ቢሊየን በላይ ይሆናል ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ተከታታይ ተሸላሚነት ላይገርም ይችላል ፣ ምክንያቱም ለአይሁድና ክርስትና እምነት የእምነት መሰረት የሆኑ ሃሳቦችን የያዘ ግሩም መድብል በመሆኑ ። ይልቅ የሚገርመው ስለሃይማኖት የማይሰብከው መጽሀፍ የዓለማችን ሁለተኛ መጽሐፍ ሆኖ የብር ሃብል ማጥለቁ ነው ። ርግጥ ነው የመደብ ተጻራሪ የሆኑት ምዕራባዊያን ፓለቲከኞች የ « ማኦ መጽሐፍ ቅዱስ » እያሉ ነው የሚጠሩት ። እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ ተከታይ በማፍራቱ ።

ይህ መጽሐፍ ከቢሊየን ኮፒ በላይ ታትሞ ተነቧል ። ሪከርድ ያሰጠው መጠሪያ « የሊቀ መንበር ማኦ ጥቅሶች » የሚል ቢሆንም ብዙዎቹ እያንቆለጻጸሱ የሚጠሩት « ትንሿ ቀይዋ መጽሐፍ » በማለት ነው ።

ይቺ ትንሽ መጽሐፍ በጥቅስና አባባሎች የተከበበች ትምሰል እንጂ መልዕክቷና ዓላማዋ ከቻይና አልፎ የዓለማቀፉን ማህበረሰብ ትኩረት መሳብ ችሏል ። አያሌ ምሁራን የቻይናው ህዝባዊ ሪፐፕሊክ መስራች የሆነውን ማኦ « የማይጠግብ አንባቢ » ይሉታል ። ማኦ እንደ ሆዳም አንባቢነቱ ሆዳም ፀሀፊ ነበር ። ጥሩ ፖለቲከኛ ብቻ ሳይሆን ጥሩ የፖለቲካ ጸህፊ ለመሆኑ On New Democracy እና On Coalition Government የተሰኙ ስራዎቹን መጥቀስ ይቻላል ። ጥሩ አሳቢ ብቻ ሳይሆን ጥሩ የፍልስፍና ጸሀፊ ለመሆኑ Four essays on Philosophy የተባለውን ስራ ማገላበጥ ይጠቅማል ። ጥሩ ወታደራዊ መሪ ብቻ ሳይሆን ጥሩ የወታደራዊ ሳይንስ ጥበብ ጸሀፊ መሆኑን The art of war እና On Guerrilla warfare የተሰኙ ስራዎቹን ማንበብ ይቻላል ። ማኦ ከ 30 በላይ ስራዎች ሲያበረክት አንደኛዋ ግጥም ነበረች ። ከአብዮቱ በፊት እና ከአብዮቱ በኋላ በሚል ንኡስ ርዕስ የተከፋፈሉ 36 ግጥሞችን የያዘች መድብል ።

ከሁሉም ታዲያ በአጋጣሚ ገና የወጣችው ቀይዋ መጽሐፍ ናት ። ዋነኛ ምክንያቱም ቻይና ባከናወነችው የባህል አብዮት / 1966- 1976 / ለህዝቡ በተለይም ለቀዩ ዘብ መሰረታዊ መመሪያና ምክር በመሰነቋ ነው ። በነገራችን ላይ ማኦ ያከናወናቸው ሁለት ታላላቅ ጉዳዮች Great Leap forward እና Cultural revolution ባስከተሉት የረሃብና የግጭት ቀውስ ለበርካታ ሚሊየን ዜጎች መጥፋትም ምክንያት ሆነዋል ።

በባህል አብዮት ዘመን በተለይ ከመስመር የወጡ ተማሪዎች ‹ አራቱን አሮጌዎች አስወግድ ! › በሚል መርህ አሮጌ ባህል ፣ አሮጌ ልማድ ፣ አሮጌ ወግ እና አሮጌ አስተሳሰቦችን እናስተካክላለን በማለት በከተሞች ላይ ትልቅ ጥፋት አድርሰዋል ። በሌላ በኩል የማኦ ቀይ መጽሀፍ ያፈነገጡትን በመመለስ ፣ መስመር ውስጥ ያሉትንም ስራቸውን በምን መልኩ አጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው ታድጋለች ። ምክንያቱም አብዮት ሲባል የቀድሞውን እያጠፉ ብቻ ንፋስ ወደነፈሰብት መረማመድ አይደለም ። ለዚህም ነው ቀይዋ መጽሀፍ ጠቃሚ ርዕሰ ጉዳዮችን እያነሳች መንገዱን ያሳየችው ። ኮሙኒስት ፓርቲ ፣ የመደብ ትግል ፣ ጦርነትና ሰላም ፣ ዲስፕሊን ፣ አንድነት ፣ የህዝብና የመከላከያ ሰራዊት ግንኙነት ፣ ካድሬ ፣ የመሳሰሉ ርዕሰ ጉዳዮችን በማንሳት ነገረ አንድምታቸውን ታወጋለች ።

እንዲህ በማለት ።

የመደብ ትግል በሚለው ሃሳብ ስር አብዮትን በሚከተለው ንፅፅር ፍርጥ አደርጎ ነው ያስቀመጠው « አብዮት የራት ፓርቲ አይደለም ፣ አብዮት ወግ መቸክቸክ ፣ ሰዕል መጫጫር ወይም ጥልፍ መስራት አይደለም ። አብዮት አንዱ መደብ ሌላውን ለመገልበጥ የሚያነሳው ሁከት ወይም ብጥብጥ ነው »

ማኦ አሜሪካ የምትኩራራበትን የአቶሚክ ቦንብ የወረቀት ላይ ነብር ነው በማለት ሀገሬው ስጋት ላይ እንዳይወድቅ ያበረታታል ። የጦርነት ውጤት የሚወሰነው በህዝቦች እንጂ በአንድ ወይም በሁለት አይነት መሳሪያ አለመሆኑን በማስገንዘብ ። ብዙሃንን መጨፍጨፊያ መሳሪያ ቢሆንም እንደ ቻይና የህዝብ ብዛት ያላቸውን ሀገራት ማሸነፍ እንደማይቻል ነው የሚያስገነዝበው ።

ሰላምና ጦርነት በሚለው ርዕሰ ጉዳይ ስርም ዓለም ስለሚሰጋበት የሶስተኛው ዓለም ጦርነት አንስቷል ። ሶስተኛው የዓለም ጦርነት የሚነሳ ከሆነ ለኢምፔሪያሊስቶች የሚሆን ቦታ እንደማይኖር በስሌት በማስቀመጥ ። በአንደኛው ዓለም ጦርነት 200 ሚሊየን ስዎች ሶቪየት ህብረትን ተከትለዋል ። በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወደ ሶሻሊስት ካምፕ የተቀላቀለው 900 ሚሊየን ህዝብ ነው ። ሶስተኛው ዓለም ጦርነት ከመጣ ግን አለም ለኢምፔሪያሊስቶች የሚሆን ቦታ እንደሌላት ምስክር ይሆናል ።

አለም በሁለት ርዕዮት በመከፈሏ የተፈጠረውን ብሽሽቅ የሚያጠናክሩ አባባሎችም በስፋት ይታያሉ ። በአለም ላይ ካሉ ቀላል ነገሮች አይዲያሊዝም እና ሜታፊዚክስ ይገኙበታል የሚለው ማኦ ለዚህ የሚሰጠው ምክንያት ደግሞ ያለምንም ተጨባጭ ግብ ጠቃሚ ያልሆኑ ዝባዝኬዎችን ማውራታቸው ነው ። ተጨባጩን አለም መሰረት ያደረጉ ሁለት ፍልስፍናዎች ደግሞ ማቴሪያሊዝምና ዴያሌክትስ ናቸው ። ማኦ ተራማጅና ምክንያታዊ አስተሳሰብ አላቸው የሚላቸውን ሶሻሊዝምና ኮሙኒዝም ከፍ ከፍ በማድረግ ፣ የፊውዳሊዝም እና ካፒታሊዝም ብቸኛው ቦታዎች ሙዚየሞች መሆናቸውን ይገልጻል ።

ጥሩ ፒያኖ ለመጫወት ሁሉንም ጣቶች በአንድ ግዜ ማንቀሳቀስ አይመከርም ፤ እንደዛ ከሆነ ዜማ ስለማይኖር ። አስሩም ጣቶች በየተራ በጥሩ ምት እና ቅንብር መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል ። የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትም ችግሮችን ለመፍታት የግድ ፒያኖ መማር እንዳለባቸው ዘይቤያዊ በሆነ መልኩ አሳስቧል ። ለማኦ ጥሩ መሪነት ከፒያኖ ጨዋታ ጋር ይመሳሰላል ።

ወታደሩና መኮንኑ ፣ ጦር ሰራዊቱና ሲቪሉ ማህበረሰብ ለሀገሩ በፍቅርና በአንድነት ሊቆም የሚችለው የመተሳሰቢያ ድልድዮች ሲኖሩት ነው ። እነዚህ የመተሳሰቢያ ድልድዮች ደግሞ በዋነነት መዋቀር ያለባቸው በጦር ሰራዊቱ ትከሻ ላይ ነው ። በመሆኑም ጦር ሰራዊቱ ሶስቱን ደንቦችና ስምንቱን ነጥቦች ተግባራዊ ማድረግ ይጠብቅበታል ይላል ማኦ ።

ሶስቱ ደንቦች የትኞቹ ናቸው ?
1.      ሁሉንም ትዕዛዞች በስርዓት ተቀበል
2.     ከብዙሃኑ ሰባራ መርፌ ወይም ብጣሽ ክር እንዳትወስድ
3.     የማረከውን ሁሉ አስረክብ

 ስምንቱ ትኩረት የሚሰጣቸውስ ?
      1. በትህትና ተናገር        
      2. ለምትገዛው ሁሉ አግባብ ያለው ክፍያ ክፈል
      3. የተዋስከውን ሁሉ መልስ
      4. ለምታጠፋው ሁሉ ክፈል
      5. ህዝብ ፊት አትማል
      6. ስብል አታበላሽ
      7. ከሴት ጋር አትባልግ
      8. ምርኮኛ ላይ የጭካኔ ተግባር አትፈጽም ።

ከማኦ እምነት እና ደንብ የምንማረው ጦር ሰራዊቱ የሃይል አበጋዝ ቢሆንም በጉልበቱ ተማምኖ ዋልጌነትና ሙስና መስክ ላይ እንዳይጨፍር ዛብ የሚያስፈልገው መሆኑን ነው ። የትህትና እና የፍቅር ተምሳሌት ከሆነ የእውነተኛ ህዝባዊነትን ማዕረግ ከእያንዳንዱ ቤት በሶጦታ ያገኛል ።

እንደሚታወቀው ማኦ ሀገሪቱን በእንዱስትሪ የቀደመች ለማድረግ The Great Leap Forward መርሃ ግብር ክተት ካለ በኋላ እቅዱ ሀገሪቱ ባጋጠማት አደገኛ ድርቅ ሊከሽፍ ችሏል ። ይህ ውድቀትም ማኦ ስልጣኑን እንዲያጣ አድርጎታል ። ሆኖም የሀገሪቱ ወጣቶች እሱን በመደገፋቸው እንደገና መነሳት ችሏል ። ወጣቱ የንባብ ማእከላትን አጠናክሮ በማጥናትና በመከራከር ሌላው ቀርቶ ማንበብ የማይችለው ህብረተሰብ ጋር ተደራሽ በመሆን ትልቅ ሚና ተጫውቷል ። ቀይዋ መጽሐፍ በህዝብ አውቶብስ ውስጥ ሌላው ቢቀር በሰማይ ላይ ሁሉ ይጠና ነበር -  የቻይና ሆስቴሶች የማኦን የጥበብ ቃላት ለተሳፋሪያቸው ይሰብኩ ነበር ። ማኦና ወጣቱ እንደ ጣትና ቀለበት ስምሙ መሆኑ የቻሉት ቀይዋ መጽሐፍ ወጣቱን የሚያቀልጥ ሃሳብ በመያዟ ይመስለኛል ።

እንዲህ በማለት ።

« አለም የናንተ ናት ፣ የኛም ጭምር ። እንደ መጨረሻ ትንታኔ ከሆነ ግን የናንተ ናት ። እናንተ ወጣቶች እንደምታብብ ህይወት ... ልክ ሁለት እና ሶስት ሰዓት እንደምትወጣው የጠዋት ፀሃይ ብርታትና ጥንካሬ የተሞላችሁ ናችሁ ... »

ማኦ በቀይዋ መጽሐፍ ላይ « የማርክስ ፣ ኤንግልስ ፣ ሌኒንና ስታሊን ቲዎሪ አለማቀፍ ተቀባይነት ያገኘ ነው ። እኛ የምንቀበለው እንደ ቀኖና ሳይሆን እንደ መንገድ መሪ ነው » ይላል ። በርግጥ ማኦ በመሰረተ ሃሳብ ደረጃ ማርክሲስቶችን ቢያከብርም የራሱን ቲዎሪ  የገነባ ብሎም ተጽእኖ የፈጠረ ሰው ነው

ስሙን መሰረት ያደረገው « ማኦኢዝም » የኢንዱስትሪ መስፋፋት ከበርቴው ይበልጥ ህዝቡን እንዲበዘብዝ መንገድ ይፈጥራል ባይ ነው ። በዚሁ ፍልስፍናው የፋብሪካው ሰራተኛ ሳይሆን ገበሬው የኮሙኒስት አብዮትን መምራት አለበት ብሎ ያምናል ። ከማርክሲዝም ርዕዮት ጋር ልዩ የሚያደርጋቸውም ሀሳብ ይኸው ነው ። ማርክሲስቶች የከተማው ሰራተኛ ላይ ትኩረት ሲያደርጉ ማኦ ኢዝም ለገበሬው ይወግናል ።

ምዕራባዊያን ማኦ የበርካታ አስገራሚ ጥቅሶች ፈጣሪ እንደሆነ ይቀበላሉ ። ከአስገራሚው አንዱም « ብዙ መጽሐፍ ያነበበ አደገኛ ነው » ያለው እንደሚገኝበት ጽፈዋል ። የአንባቢ ወታደሮችን መጽሐፍ ሰብስቦ ያቃጥል ነበር የሚሉትም አሉ ። ነገሩ ተረት ይመስላል ። ቀይዋ መጽሐፍ አንባቢነትን አትቃረንም - ይልቅ ስለ ትምህርትና ስልጠና አስፈላጊነት ነው የምትሰብከው ። እንግሊዞች ማኦን እንደሚተርቡት ሁሉ አድንቀው ፓርላማ ውስጥ ጥቅሱን ለንግግራቸው ማዳመቂያነት የሚያውሉም አሉ ።በቀይዋ መጽሐፍ የተሰባሰቡት ጥቅሶችና አባባሎች የማኦን ፍልስፍናና እምነት ያንጸባርቃሉ ::

እንዲህ በማለት ።

መጥረጊያህ ቆሻሻው ጋ ካልደረሰ ቆሻሻው በራሱ ግዜ አይጠፋም ።
ጦር ሰራዊታችን ለጠላት ጨካኝ ለወገን ደግሞ ደግ መሆን አለበት ።
የጓዶቻችን ጭንቅላት ምናልባት አቧራ ይሰበስብ ይሆናል ፣ በመሆኑም በግምገማና ግለ ሂስ መጠረግና መታጠብ ይፈልጋል ።
ማኦ በዛሬይቷ ቻይና ብቻ ሳይሆን በዛሬዋ አለማችን ዙሪያ አንድ መሰረታዊ ተጽዕኖ ፈጥሮ ማለፍ ችሏል

እንዲህ በማለት ።

« የፖለቲካ ስልጣን የሚመጣው ከጠመንጃ አፈሙዝ ነው ! » ለዚያም ነው በርካታ የዓለማችን መሪዎች ማቆሚያ የሌለው የጦር መሳሪያ እሽቅድድም እና ግንባታ ውስጥ የገቡት ።