Sunday, October 29, 2017

« አውሮራ » - የጦርነት አረር ፣ የፍቅር ቀለሃ


ሪኩ የተገነባው ዙዎቻችን በምናውቀው እውነት ላይ ነው ። ጠላትህ ጠላቴ ነው ተባብለው የተማማሉ ሁለት ብሄርተኛ ቡድኖች ለረጅም አመታት ታግለው እንደ ሀገር የሚያስበውን ቡድን አሸንፈው ስልጣን ያዙ ።

በስልጣን ማግስት ሀገር የፈለገውን ይበል ብለው መስመር ባለፈ ፍቅር ከነፉ ። እንደ ደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ‹ ሁለት አፍ ያለው ወፍ › ሆኑ ። በፍቅር ተጎራረሱ ። ተቃቅፈው በረሩ ፣ አለም ጠበባቸው ... ተጣብቀው ዘመሩ ‹ አይበላንዶ  ...  › እያሉ ።ተያይዘው ፈከሩ ! ‹ ነፍጠኛ ሰመጠ ፣ ተራራ ተንቀጠቀጠ › በማለት ... አብረው ተዛበቱ ‹ ትግል ያጣመረውን ህዝብ አይለየውም › በሚል ስልቂያ ... ኪስህ ኪሴ ነው ፤ ሚስትህ ሚስቴ ናት ፤ ግዛትህ ግዛቴ ... ምን ያልተባባሉት አለ ?

 ከአይን ያውጣችሁ ያላቸው ግን አልነበረም ።

እየቆየ አይንና ናጫ ሆኑ ... በአጎራረስህ እየተጎዳው ነው በሚል አንደኛው አፍ የጫካ ውንድሙን ካደ ። የእህል ምርቱንም ሆነ የሚያጌጥበትን ማእድን ደበቀ ። የብር ኖቶችን ቀየረ ፣ የድንበር ንግድ ግብይት በዶላር እንዲሆን ድንገተኛ ህግ አረቀቀ ። ይህ ተግባር ለሁለተኛው አፍ የማይታመን ክህደት ነበር ። ባጎረስኩ እጄን ተነከስኩ አለ ። ጠፍጥፎ በሰራው ልጅ ተናቀ ... ሹካ አያያዝ አስተምሬው ? በኔ ደም ለወንበር በቅቶ እንዴት ክብሬን ያራክሳል በማለት ለጦርነት ተዘጋጀ ።

‹ አውሮራ › ይህን የምናውቀውን ታሪክ ይዞ ነው መዋቅሩን የገነባው ። የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት እንዴት ተጀምሮ እንደምን እንዳለቀ እናውቃለን ፣ ምን እንዳስከተለም የብዙ ወገኖች መረጃ አለን ። የመንግስት ሚዲያዎችን ጨምሮ የድርጅቶቹ ልሳኖች የአውደ ውጊያውን ታሪክና የታሪክ ሰሪ ሰዎችን ህይወት በመዳሰስ አታካች በሆነ መልኩ በተከታታይ አቅርበውልናል ። ታዲያ አውሮራ ምን የተለየ ነገር ሊነግረን ታሪክ ቀመስ ልቦለድ ሆነ ? ቢባል ትክክል ነው ።

ደራሲው ሀብታሙ አለባቸው ግን ብልህ ነው ፣ ገና በጠዋቱ ፣ ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ያስተዋወቀንን የታሪክ በከራ እንዴት ሳይሰለች እያጠነጠነ እስከ ምዕራፍ 43 መዝለቅ እንዳለበት በሚገባ ተረድቷል ። ስለተረዳም ሳቢና ተነባቢ አደረገው ።

ይህን ለማከናወን ከረዳው ስልት አንደኛው የትረካውን ኳስ ለመለጋት በመረጠው የመቼት አንግል የተወሰነ ይመስለኛል ። ደራሲው 80 ከመቶ የሚሆነውን ታሪክ የሚያቀብለን ከኤርትራ አንጻር ሆኖ ነው ። በትረካው የአስመራን ውበት ፣ የወታደራዊ ካምፖችን ሚስጢር ፣ የደህንነት ተቋማት ፕሮፓጋንዳ ፣ ሳዋ ስለተባለው የሰው ቄራ ፣ የፕሬዝዳንቱን ጽ/ቤት ከነተግባርና ግዴታቸው እንመለከታለን ። የህዝቡን አበሻዊ ጥላቻ ፣ ፖለቲካዊ ሹክሹክታ እና ስነልቦና እንመረምራለን ። የባለስልጣናቱን በተለይም የፕሬዝዳንቱን እምነት ፣ አስተሳሰብ እና ፍላጎት እንታዘባለን ። በአጠቃላይ ከአስመራ የምናገኘው አዲስ መረጃ ታሪኩ ሰቃይና አጓጊ እንዲሆን ትልቅ ሚና ተጫውቷል ። የታሪኩ ልጊያ ከአስመራ እየተነሳ ወደ ኢትዮጽያ ፣ ጅቡቲና ሌሎች አካባቢዎች ሲያመራ ደግሞ ተዝናኖት ብቻ ሳይሆን አማራጭ እሳቤ ይፈጥርልናል ። በመሆኑም የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት አዲስ ሆኖ እንዲሰማን አድርጓል ።
ሌላም አለ ። ታሪኩን የሚደግፉት የሴራ ቅንብሮች ባለሁለት አፍ ወፎቹ ይፋ በሆነ መልኩ በመድፍ እንዲቆራቆሱ ብቻ አይደለም የሚያደርገው - ወፎቹ በየሰፈራቸው በተዳፈነው ረመጥ እንዲለበለቡም ጭምር እንጂ ።

የአስመራው ወፍ / ኢሳያስ / ክብሩንና ጥቅሙን ለማስጠበቅ መጠነ ሰፊ ፣ የተደራጀና ህቡዕ ተኮር እንቅስቃሴ ያደርጋል ። ኢትዮጽያዊው ወፍ / መለስ / አንድም አናት አናቱን ከሚጠቀጥቁት ወንድም ግንደ ቆርቁሮች በሌላ በኩል ከሩቅ አጎቱ የሚወረወርበትን ሞርታር ለመከላከል መከራውን ሲበላ እንመለከታለን ።

በነገራችን ላይ ከአስመራ ወደ ኢትዮጽያ የሚጋልበው የታሪክ ጅረት ሁለት መቆጣጠሪያ ቤተመንግስቶች አሉት ። የአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ እና የአቶ ሃይላይ ሃለፎም ። በፍትህ ሚ/ሩ አቶ ሃይላይ ቤት አራት የታሪኩ ቁልፍ ሰዎች ይገኛሉ ። ቤተሰቦች ናቸው ። ሳህል በረሃ የተወለደችው ፍልይቲ ፣ ወንድሟ ሰለሞን እና ባለስልጣን እናታቸው አኅበረት ። ሃይላይ በርግጥም ለሰላምና ፍትህ የቆመ ብቸኛ ሚኒስትር ነው ። ከኢትዮጽያ ጋር የሚደረገው ጦርነት መሰረት የሌለው የዜሮ ድምር ፖለቲካ በመሆኑ መቆም አለበት በሚለው አቋሙ ከዋናው ቤተመንግስት ሰውዪ ጋር ይጋጫል ።

በሌላ በኩል ኢሳያስ የሃይላን ልጅ ፍልይቲን እንደ ጆከር ሲጠቀምባት እናያለን ። ኢ/ያ ውስጥ የሚከናወነውን የዶላር ዘረፋ ፣ የስለላ ስራና ህቡዕ ግድያ ትመራለች ። በጅቡቲ ወደብ ወደ ኢ/ያ የሚገባውን ስትራቴጂካዊ ንብረት ለማውደም ተመራጭዋ ሰው እሷ ናት ። ባድመ በመዝመት ለሌሎች ያስቸገሩ የመረጃና የተመሰጠሩ መልእክቶችን የመፍታት ስራ ትሰራለች ። ፍልይቲ የፕሬዝዳንቱ ቀኝ እጅ ፣ ብሩህ አእምሮ ያላት ፣ ደፋር ፣ አፍቃሪ እና ጨካኝ ገጸባህሪ ናት ።

ከኤርትራ ህዝብ አንጻር / አማራ ጠላት ነው የሚል ቆሻሻ ሀሳብ / ግን አንድ ይቅር የማይባል ክህደት ትፈጽማለች ። ክህደቱ ለኤርትራ የቴሌ እና ኤሌክትሮኒክስ ግንባታ ትልቅ ድርሻ ያከናወነውን ኢትዮጽያዊ ሰው በማፍቀሯ ነው ። አስራደ ሙሉጌታ ይባላል ። ሻእቢያ ጉልበቱንና እውቀቱን እንደ ሽንኮራ ከመጠጠው በኋላ ሊያስወግደው ቀነ ቀጠሮ ይዞለታል ። ለአስመራ ፖለቲካ ትልቅ አይን የሆነችው ፍልይቲ ከመንግስታዊው ተልዕኮ ጎን ለጎን ፍቅረኛዋን ለማዳን ህቡዕ ትግል ስታከናውን እንመለከታለን ። የሃይላይ ወንድ ልጅ ሰለሞን ‹ ናጽነት › በሚለው ነጠላ ዜማው በከተማው የታወቀ ዘፋኝ ሆኗል ። ሙዚቃው ማዝናኛ ብቻ ሳይሆን የዘመቻ መቀስቀሻም ነው ። ናጽነት ብሎ የዘፈነው ግን በኢሳያስና በአባቱ ለተመራው ትግል ማስታወሻ ለመስራት ብቻ አይደለም ። እንደውም በዋናነት የዘፈነው ነጻነት የተባለች ቆንጆ ወጣት በማፍቀሩ ነው ። ነጻነት ለኤርትራ ወጣት የእግር እሳት ወደሆነበት ሳዋ ስትገባ እሱም እንዳላጣት ብሎ ፈለግዋን ይከተላል ። እሷን ፍለጋ ላይ ታች ሲል ነጻነት በሁለት የባደመ ጦር ጄነራሎች አይን ውስጥ ትወድቃለች ። ልክ እንደ ባድመ መሬት ሊቆጣጠሯት ሌት ተቀን ስትራቴጂክ ይነድፋሉ ።

እናም የአንደኛው ቤተመንግስት ሰውዪ ከኢ/ያ ድል ለማግኘት ሲራራጥ ፣ የሁለተኛው ቤተመንግስት አባላት ደግሞ ከራሱ ከኢሳያስ ጭቆና ለመላቀቅ እንዲሁም ፍቅረኛዎቻቸውን ለመታደግ ላይ ታች ሲሉ በታሪኩ ተወጥረን እንያዛለን ።

መጽሐፉ ጥቃቅን ቴክኒካል ችግሮች የሉበትም ማለት አይቻልም ፣ ለአቅመ ግነት የሚበቁ ስላልመሰለኝ ዘልያቸዋለሁ ። ይልቁንስ ደራሲው የራሱ እምነት የሚመስል ጉዳይ መጀመሪያ ምዕራፍ ላይ ቆስቁሶ እንዲረሳ ወይም እንዲጨነግፍ ማድረጉ የሚቆጭ ይመስለኛል ። ያነሳቸው ጥያቄዎች የአንባቢም መሰረታዊ ጥያቄዎች ሊሆኑ የሚችሉ ናቸው ። የባርካ ማተሚያ ቤት ባለቤት የሆኑ ግለሰብ አቶ ሃይላይ ሊጽፉ ባሰቡት መጽሐፍ ውስጥ አራት መሰረታዊ ጥያቄዎችን አዳብረው አንዲሰሩ ሀሳብ ያቀርባሉ ። ከቀረቡት ሃሳብ ውስጥ ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው ፣

1 . የኤርትራ ነጻነት ትግል ለምን በ 1885 ምጽዋ በኢጣሊያ መያዝን በመቃወም አልተጀመረም ?
2 . ከኤርትራ ልዩ ማንነት የተፀነሰ ትግል ከሆነ ለምን 30 አመታት ፈጀ ?

ደራሲው ስራውን ከሰሩት 285 ሺህ ናቅፋ እንደሚያገኙም ውል ታስሮ ነበር ። ሆኖም የማተሚያ ቤቱ ባለቤት ሲያዙ ፣ አቶ ሃይላይም ሲገደሉ ሃሳቡ ይመክናል ። እንደ ስነጽሁፍ ሃያሲ የሁለቱ ሰዋች መጥፋትን በአስመራ ወስጥ የመጻፍ ፣ የመናገር ፣ የማሰብ እና የዴሞክራሲ መሞትን ለመተርጎም ያስረዳን ይሆናል ። ከዚህ በላይ ግን ታሪኩ ባይጨነግፍ የበለጠ ጠቃሚ ያደርገን ነበር ብሎ መከራከር ያስኬዳል ። አቶ ሃይላይ ለእውነት የቆሙ ገጸባህሪ በመሆናቸው እየመረራቸውም ቢሆን ከኤርትራ ጀርባ የተደበቁ ጉዳዮችን ያነሱ ነበር ። ይሄን አንስተው ቢሞቱ ደግሞ ሞታቸውንም ይመጥን ነበር ። የበለጠ ጀግና መስዎዕት እናደርጋቸው ነበር ።

‹ አውሮራ › ጦርነት ላይ መሰረት አድርገው እንደተሰሩት ልቦለዶቻችን ማለትም ኦሮማይ እና ጣምራጦር የተሳካ ስራ ነው ። ድንበር ያቆራርጣል ፤ እዚህና አዚያ እንደ ቴኒስ ኳስ ሲያንቀረቅበን ጨዋታው ሰለቸኝ ብለን ከሜዳው ዞር ማለት አንችልም ። ፈጣን ነው ፤ በድርጊት የተሞላና በመረጃ የደነደነ ። መንቶ ነው ፤ ፍቅርና ጦርነትን በእኩል ጥፍጥና ከሽኖ ማቅረብ የቻለ ። ሰባኪ ነው - ፍቅር ያሸንፋል የሚል አይነት ፤ ተዛምዶ ተጋብቶ ተዋልዶ የተካደ ትውልደን የሚያባብል ። የሆነውን ብቻ ሳይሆን  የሚሆነውን ቁልጭ አድርጎ የሚናገር ። በተለይም የአንድነት አሳቢዎችን ገድለን ቀብረናል ብለው ለሚመጻደቁ ጠባቦች « ውሸት ነው ! » ብሎ ጥበባዊ ምስክርነት የሚሰጥ ።

በታሪኩ ውስጥ ማንነቱን ደብቆ ስሙን አቦይ ግርማ አስብሎ ቀን ከለሊት በባድመ የልመና ተግባር የሚያከናውነው እንኮዶ /የደርግ ኮማንዶ የነበረ / አንድ እጁ ስለተቆረጠና አይኑ ስለተጎዳ ማንም ግምት ውስጥ ያሰገባው አልነበረም ። ሆኖም መጀመሪያ የባድመን መሬት ፈልፍለው የገቡ የሻእቢያ ወታደሮችን ፣ በመጨረሻም እጁን በመጋዝ ቆርጦ የጣለውን ጄኔራል ግዜ እየጠበቀ መበቀል ችሏል « ለገንጣይና ጡት ነካሽ ዋጋው ይሄ ነው » እያለ ። ይህ ትርክት በስነጽሁፍ ቋንቋ ፎርሻዶው ወይም ንግር የሚባለው ቴክኒክ ነው - ነገ እንዲህ መሆኑ አይቀርም ለማለት ።



Sunday, October 22, 2017

በአፍሪካ ጭንቅላት ዓለምን መምራት ?


« የማይቻለውን እንደሚቻል እናረጋግጥ » በሚል መሪ መፈክር ስር ተወዳድረው የአለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጄነራልነትን ያሸነፉት አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ፣ ሮበርቱ ሙጋቤን የበጎ ፍቃድ አምባሳደር አድርገው መሾማቸው አለማቀፍ ተቃውሞ አስከትሎባቸዋል ። እኔም ሰውየው የሚመለከቱበት መነጽር እንዴት ሸውራራ ሆነ ብዪ ጥያቄ አንስቼያለሁ ።

አንዳንዶች ነጮች ሙጋቤን ስለማይወዱት በተራ ጥላቻ የተደረገ ተቃውሞ እንደሆነ ያስባሉ ። እውነቱ ግን ይሄ አይደለም ። ሙጋቤ የፈለገ ያህል ለነጭ ተንበርካኪ አይሁኑ እንጂ በሀገራቸውም የሚመሰገን የፖለቲካ ስብእና የላቸውም ። ሀገሪቱን ላለፉት ሰላሳ አመታት የገዙት የተቃዋሚዎቻቸውን ድምጽ ብቻ ሳይሆን የህዝባቸውን የዴሞክራሲ ጥማት ጨፈላልቀው ነው ። ለስሙ ያህል ምርጫ ያካሄዳሉ እንጂ ‹ በህይወት እስካለሁ ድረስ ፕሬዝዳንት ነኝ › የሚሉትን መርህ አጥብቀው እየተገበሩ የሚገኙ ሰው ናቸው ። ምን ይሄ ብቻ በቅርቡም ባለቤታቸው ግሬስ ፣ ሙጋቤ ቢሞት እንኳ ሬሳው ይወዳደራል ማለታቸው የሚዘነጋ አይደለም ። የሰው ልጆች በተፈጥሮ ያገኙትን የዴሞክራሲ መብቶች የግል በማድረግ ነጻነት እንዲጠፋ ፣ ጭቆና እንዲስፋፋ የሚተጉ ባለስልጣናትን እውቅና ከሚሰጠው ጎዳና ገለል አለማለታችን ያሳዝናል ።

  ከአፍሪካ የተገኙት ቴዎድሮስ የሙጋቤ አምባገነን መሆን ጉዳያቸው ላይሆን ይችላል - ስልጣንን አለመልቀቅ የአፍሪካ ያልተጻፈ ህግ ስለሆነ ። አንድ የአፍሪካ ባለስልጣን ወደ አለማቀፉ ደረጃ ከፍ ሲል ግን በዚያው የአሰራር ስርዓት ውስጥ ሊጓዝ ግድ ይለዋል - ምክንያቱም ከአፍሪካ መጣ እንጂ አፍሪካን ብቻ ሊመራ አይደለም እዛ የተወከለውና ። እና አንድ መሪ አዎንታዊ  ቅቡልና የሚያገኘው ለሰው ልጆች ካለው ክብርም አኳያ ነው ። ሙጋቤ በሰብዓዊ መብት አያያዝ ረገድ የረባ ሰእል የላቸውም ። ተመድ በግልጽ ከሚመራባቸው መርሆዎች አንዱ ደግሞ ሰብዓዊ መብትን ማክበር ነው ። ታዲያ ሙጋቤ በምን አንጀታቸው ነው ርህራሄ የሚፈልገውን የጤና ተቋማት መደገፍ የሚችሉት ?

ሙጋቤ 93ተኛ አመታቸው ላይ ይገኛሉ ። አለመታደል ሆኖ እንጂ ይህ የማረፊያና የጥሞና ግዜ ነበር ። በየግዜው እንደምናያቸውም በአካልም ሆነ በአእምሮ ደክመዋል ። መራመድ ተስኗቸዋል ፣ ስብሰባ መቀመጥ ባለመቻላቸው በየሄዱበት ያንቀላፋሉ ። አንድ ሰው ንቁ ካልሆነ እንዴት ለሌላ ስራ ይታጫል ? አቶ ቴዎድሮስ ለዚህ ጥያቄ አሳማኝ ምላሽ የሚኖራቸው አይመስለኝም - በሙጋቤ ቃል አቀባይ ፎጋሪ አስተያየት ካልተስማሙ በስተቀር ። ፎጋሪው ሰውየ ምን አለ መሰላችሁ « ሮበርቱ ሙጋቤ በየስብሰባው የምታዩዋቸው እየተኙ አይደለም - አይናቸውን ስለሚያማቸው እያረፉ እንጂ »

አቶ ቴዎድሮስ ለዙምባቤ ጤና አገልግሎት አሰጣጥ አዎንታዊ ድጋፍ እንዳላቸውም ተናገረዋል ። ይህ አስተያየታቸው ግን ከነባራዊው እውነታ ጋር የሚጣረስ ነው ። በርካታ መረጃዎች የሚያመለክቱት የዙምባቤ የጤና ስርአት እጅግ አሳዛኝና አሳሳቢ ደረጃ ላይ የሚገኝ መሆኑ ነው ። ሰራተኞች ያለ ደመወዝ የሚሰሩበት ግዜ ጥቂት አይደለም ፣ በመንግስት ሆስፒታሎች መድሃኒት ባለመኖሩ ሰራተኞች በቂ ህክምና ለመስጠት ተቸግረዋል ።

አቶ ቴዎድሮስ ሙጋቤ በዓለማቀፉ ጤና ድርጅት ተመርጠው መስራታቸው የሀገራቸውንም ሆነ የአፍሪካን የጤና አያያዝ ሊያሻሽሉ ይችላሉ ባይ ናቸው ። እውነቱ ግን ሙጋቤ በሀገራቸው ጤና ስርአት ላይ እምነት የሌላቸው መሆኑ ነው ። እምነት በማጣታቸውም ሲታመሙ እንኳ በሆስፒታላቸው ሊታከሙባቸው አይፈልጉም ።  አቶ ቴዎድሮስ ‹ የህክምና ቱሪስት ፕሬዝዳንቶች ›  / Medical Tourist Presidents / ስለተባሉት የአፍሪካ መሪዎች አንበው ቢሆን ኖሮ ይህን ከመሰለ ስህተት ውስጥ ባልገቡ ነበር ።

ዓለም የሚሳለቅባቸው እነዚህ የህክምና ቱሪስቶች የናይጄሪያው ሙሃመድ ቡሃሬ ፣ የአንጎላው ጆሴ ኤድዋርዶ ፣ የቤኒኑ ፓትሪስ ታሎን ፣ የአልጄሪያው አብዱላዚዝ ቡተፍሊካ እና የዙምባቤው ሮበርቱ ሙጋቤ ናቸው ። እነዚህ መሪዎች በአመት ውስጥ ደጋግመው ውጭ ሀገር ለህክምና ስለሚመላለሱ በርካታ የሀገር ሃብት ያጠፋሉ ። ሙጋቤ ባለፈው አመት ብቻ ሶስት ግዜ ወደ ሲንጋፖር ለህክምና አቅንተዋል ፣ ለዚህም 50 ሚሊየን ዶላር ወጪ ያደረጉ ሲሆን ይህ ገንዘብ የሀገሪቱን ጤና ጣቢያዎች ለማስፋፋት ከተመደበው አመታዊ በጀት በሁለት እጥፍ ይበልጣል ። ሙጋቤ ሲንጋፖር ሄደው የሚታከሙትም በጥቁር ሀኪም ነው ። ነጭ ሁሉ ጠላት ነው የሚሉት ሙጋቤ በአለም አቀፍ የህክምና መድረክ ብቅ ቢሉ እንዴት ነው በፍቅር መስራት የሚችሉት የሚለውን ጥያቄ አቶ ቴዎድሮስ መመለስ ይኖርባቸው ነበር ።

ዞሮ ዞሮ የሙጋቤ አምባሳደርነት ተፍቋል ። አቶ ቴዎድሮስ ይህን በፍጥነት ማድረጋቸው መልካም ነው ፣ ነገር ግን በብዙ መልኩ ጥያቄና ጥርጣሬ ውስጥ ወድቀዋል ። ነገሮችን የሚያዩብት መነጽር ሸውራራ እንዳይሆን ተፈርቷል ። ስለ ተመድ ያላቸው እውቀትና አረዳድ አስጊ መስሏል ። በስሜት ሳይሆን በተጨባጭ መረጃ ውሳኔ ሰጪ አይሆኑ እንዴ አሰኝቷል ። የዴሞክራሲ ማእከል ውስጥ ገብተው ዴሞክራት ላልሆኑ ሰዎች መወገናቸው አስደንግጧል ። አቶ ቴዎድሮስ ከለመዱት ‹ አብዮታዊዊ › አሰራር በፍጥነት መላቀቅ ካልቻሉ ገና ከብዙ ጉዳዮች ጋር መላተማቸው አይቀርም ። በርግጥም በኢትዮጽያና አፍሪካ ባርኔጣ ዓለምን መምራት አይቻልም - ባርኔጣው ካልተስተካከለ ::


Saturday, October 14, 2017

የ « ማዕቀብ » መሳጭ ሀሳቦች


« ማዕቀብ » ከእንዳለጌታ ከበደ ግሩም ስራዎች አንደኛው ነው ። መጽሐፉ በዋናነት ‹ ዴሞክራት ገዢዎቻችን › በድርሰት ፣ ደራሲያንና ተደራሲያን ላይ ስላስከተሉት አሉታዊ ተጽዕኖ ይተርካል ። ከዚያ በመለስ የተመረጡ ደራሲያንና መጻህፍት ሻጮችን የህይወት ውጣ ውረድ ያመላክታል ።

በመጽሐፉ ከአዳዲስ መረጃዎችና ሀሳቦች ጋር እንተዋወቃለን ፤ ከመሳጭና ሞጋች ሀሳቦች ጋር እንፋጠጣለን ። በመሳጭ ሀሳቦች እየተብሰከሰክን ከሞጋቾቹ ጋር የከረረ ምናባዊ ምልልስ እናደርጋለን ።

ከተነሱት ሞጋች ሀሳቦች አንዱ የአቶ መለስ ዜናዊ ልቦለድ ደራሲነት ጉዳይ ነው ። አቶ መለስ በብዕር ስም ‹ መንኳኳት ያልተለየው በር › እና ‹ ገነቲና › የተሰኙ ሁለት መጻህፍትን ለንባብ አብቅተዋል ። እንዳለጌታ ተማሪ በነበረበት ወቅት አንድ ተጋባዥ መምህር ስለ ትግርኛው ስነጽሁፍ የማብራራት እድል ያገኛሉ ። እኚህ ምሁር « በአማርኛው ስነጽሁፍ በቋንቋ ፣ በጭብጥ ፣ በአጻጻፍ ቴክኒክ ታዋቂ የሆነው ዳኛቸው ወርቁ እንደሆነ ሁሉ የትግርኛው ዳኛቸው ደግሞ መለስ ዜናዊ ነው » በማለት ሃሳባቸውን ያጠቃልላሉ ።

ሲጀመር በዳኛቸው ላይ የተሰጠው ዳኝነት ትክክል አይመስለኝም ። እንዳለጌታ እንደሚለው ደግሞ መለስን እንደልቦለድ ደራሲነት ማወቅ እና ማሰብ ይከብዳል ። ደራሲ የደራሲን ህይወት ያውቃል ... ይረዳል ... ባይረዳ እንኳ ያበረታታል ... ጥበብ እንዲያድግ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል ። የነበሩ ቤተመጻህፍትን እንዲጨምሩ እንጂ እንዲጠፉ አያደርግም ። ሰውየው በስልጣን ዘመናቸው ለደራሲያን ሲቆረቆሩ አልታየም ። በአንድ ወቅት አስታዋሽ ስላጡ አንጋፋ ደራሲያን ሲጠየቁ ከአንድ አርሶአደር ለይተን አናያቸውም ነበር ያሉት - በርግጥ ከአድካሚ ስራ ጋር የሚተዋወቅ ደራሲ ደራሲነትን በዚህ መልኩ ብቻ ነው የሚረዳው ? እናም ሰውየው ስለጭብጥ እና ገጸባህሪያት ቀረጻ ይበሰለሰላሉ ብሎ ማሰብ ቁንጫ ቆሞ ሲቀድስ ፣ አህያ ሞቶ ጅብ ሲያለቅስ የመስማት ያህል ነው ይላል - እንዳለጌታ ።

በርግጥ ደራሲያን እሳቸው ‹ መንኳኳት ያልተለየው በር › እንዳሉት የድርሰት ስያሜ ሁሌም ሃሳብ እንዳንኳኳ የሚኖር ነው ። እሳቸው የቤተመንግስት በር ወለል ብሎ ከተከፈተላቸው በኋላ ሰለተዘጉ በሮች አለማሰብ ፍትሃዊ አይሆንም - በር የሚያንኳኳውን እንዳልሰማ መዘንጋት ፣ ባስ ካለም በውሻና በጥበቃ ማባርረ ከባለ ብዕረኛ አይጠበቅም ።

ሌላኛው ሞጋች ሀሳብ ሳንሱር ዛሬም ቢሆን የለም ማለት ይቻላል ወይ የሚለው ጉዳይ ነው ። ሳንሱር በአዋጅ በግልጽ ይደንገግ እንጂ በውስጥ ከሳንሱር የሚተካከሉ አሰራሮች አሉ ።

ሜጋ የመጻህፍት ማከፋፈያ ስራው መጽሐፍ በአደራ ተቀብሎ ማሰራጨት ቢሆንም ይዘታቸውን እየገመገመ የሚመልሳቸው ስራዎች አሉ ። ይህ ቁልጭ ያለ እውነት ነው ። ማተሚያ ቤቶች ህትመት ከጀመሩ በኋላ የሚቋረጡ ስራዎች አሉ ። ይህም እንዳይታተሙ የሚል ቀጭን የቃል መመሪያ ከነጌቶች ስለሚደርሳቸው ነው ። አንዳንድ ማተሚያ ቤቶች የመንግስትን ቅጣት በመፍራት ያተሙት መጽሐፍት ጀርባ ላይ ድርጅታቸውን ከመጻፍ ይቆጠባሉ ። 

ፓለቲካ ነክ ፊልሞች ከተሰሩ በኋላ እንዳይተላለፉ ታግደዋል ። የቴዲ አፍሮና የአንዳንድ ሙዚቀኞች ስራ በመገኛኛብዙሃን እንዳይተላለፉ ተደርጓል ። ዝግጅት አጠናቀው መድረክ የጀመሩ ቲአትሮች መጋረጃ ተዘግቶባቸዋል ። ጋዜጦች በጻፉት ጉዳይ መጠየቅ ሲገባቸው ገና ማተሚያ ቤት እንደደረሱ ቀኝ ኋላ ዙር ተብለዋል ።
ታዲያ ይህ ሁሉ ጉዳይ ክፍል ሁለት ሳንሱር ነው የሚባለው ወይስ የዚያኛው ሳንሱር ሁለተኛው ገጽታ ? ሀገሬው አጠናክሮ ሊወያይበት የሚገባ የቤት ስራ ይመስለኛል ።

አንዳንድ መሳጭ ሃሳቦችን ደግሞ እንመልከት ።

በርግጥ የዳኛቸው ወርቁ ‹ አደፍርስ › አከራካሪ ስራ ነው ። ለዚያም ነው አንባቢያን በብዙሃን ድምጽ ጥሩነቱን መመስከር የተሳናቸው ። ደራሲው ግን ጠመንጃ ባነገበው አንባቢ አንጻር ጦርና ጋሻ ይዞ ቆመ ። እጅና እግር ለሌለው መጽሐፍህ አምስት ብር አይገባውም እያለ በሚዘምተው ተደራሲ ፊት « ዋጋውን አስር ብር አድርጌብሃለሁ ! » ሲል የተሳለ ውሳኔውን እንደ ጦር እየነቀነቀ አሰማ ። ታዳሚውና ነጋዴው የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል አሉ ።

ቆይቶ ብቅ አለና ደግሞ አንባቢው ምን እንደሚል ጠየቀ ። ማንበብ ስላልቻለ ምን ሊል ይችላል ሲሉ ነጋዴዎች መለሱ ፤ ቅናሽ እንዲያደርግም ሃሳብ አቀረቡ ። ዳኛቸው ጦሩን ነቅንቆ እረ ጎራው አለ ፤ እረ ወንዱ አለ ። የጀግንነቱን ልክ ለማሳየትም ዋጋው ወደ 15 ብር ከፍ ማለቱን አበሰረ ። በአንባቢውና በደራሲው መሃል እንደ አሸማጋይ የቆሙት ነጋዴዎች ማሰራጨት አንደማይፈልጉ ነገሩት ። ዳኛቸው ከፉከራ በላይ ተቆጣ ። ጦሩን መሬት ላይ ቸንክሮ « ንሳ ! » ሲል ትዕዛዙን አሰማ « ከእንግዲህ መጽሃፍቶቼን ለማንም እንዳትሽጥ ! ያሰራጨሃቸውን በሙሉ ሰብስበህ አስረክበኝ ! »

ማንም ያልጠበቀው ሃሳብ ነበር ። የኢትዮጽያ ደራሲ ነጋዴ ዋጋ ቀንስ ሲለው የሚቀንስ ፣ ኮንሳይመንት ጨምሯል ሲሉት እሺ የሚል ፣ የወረቀት ክምርህ ስላልተሸጠ ይዘህ ጥፋ ሲባል ተሽክሞ የሚሮጥ ነው ። ይሄኛው ደራሲ ግን ነጋዴውን የሚያሽቆጠቁጥ ሆነ ፣ ይሄኛው ደራሲ አንባቢ ካልገባው መንገዱን ጨርቅ ያድርግለት የሚል ሆነ ። ይሄኛው ደራሲ ፍጹም አፈንጋጭ ነው ። ይሄኛው ደራሲ በክብሩም ሆነ በመንፈስ ልጁ ላይ የመጣን ጥቃት ለመመከት ቆርጦ የተነሳ ነው ። ይሄኛው ደራሲ የኢትዮጽያዊያንን ለንቋሳ አንባቢነት እና እውቀት የሚራገም ሆነ ። ምንም ሳይፈራና ሳይጠራጠር ቀጥታ ወደ ህዝቡ የሚተኩስ ሆነ « እኔን ለመረዳት 20 አመት ይቀርሃል ! » እያለ ። አደፍርስ የፈለገ ባይመች የዳኛቸው ልበ ሙሉነት ግን ይደላል ባይ ነኝ ።

በኢትዮጽያ ስነጽሑፍ ታሪክ ትልቅ  ቦታ ከሚሰጣቸው ደራሲያን መካከል አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ነው ። ይህ ደራሲ በርካታ ስራዎችን ቢያቀርብልንም  በርካታ ስራዎች መስራት በሚችልበት እድሜው ላይ ነበር /54 / ያለፈው ።

አሁን እኔ ማውራት የፈለኩት ሰለ ብርሃኑ ሳይሆን ብርሃን ስለፈጠረችለት ሚስቱ ነው ። ስለ ብርሃኑ ምርጥ ባለቤት ስለ ወ/ሮ የሺ ። ዘወትር የብርሃኑ አምሽቶ መምጣት ያሰጋት ሚስት አንድ ነገር እንዳይሆን በመፍራት መጠጡን እንዲተው ትጨቃጨቅ ነበር ። እሱ ግን በደሙ ስለተዋሃደ ያለጂን ብእር ማንሳት አልቻለም ። አልኮል እያጣጣሙ  ከ 10 በላይ ግሩም መጻሕፍትን መድረስ በራሱ ገራሚ ነው ። ምክንያቱም ለብዙዎች አልኮል እንቅልፍ መጥሪያ እንጂ ለስነጽሑፍ ከራማ መዘየጃ ሲሆን አልታየምና ።

ግራ ቢገባት ጂን እየገዛች ቤት ውስጥ ትቀዳለት ጀመር ፤ አላስደሰተውም ። ምነው ? ብትለው ብቻዪን እንዴት እጠጣለሁ ? የመጠጥ ቤት ድባብ ያስፈልገኛል አላት ። ፈተና ሆነባት ። ጎረቤት እየጠራች ቤቷን እንደ ቡናቤት አታሟሙቀው ነገር ሃብት ይፈልጋል ። ቡቡዋ ሚስት መንገድ ወድቆ ከሚቀር በሚል ‹ እኔ አጣጣሃለሁ › አለችው ። ለእሱ ብላ የጠላችውን ወደደች ። ቀስ በቀስ ጨዋታውን ለመደች :: ምን ያደርጋል ታዲያ ታላቁ ደራሲ በዚሁ ጦስ ከሞተ ጥቂት ቆይቶ የእሷም ጉበት መበላሸቱ ተነገራት ። በአንድ በኩል የባለቤቷ ሀዘን በሌላ በኩል የራሷ ህመም ተባብረው ገደሏት ።

ለባሏ ብላ መስዋዕት ሆነች ። በኢፍትሃዊ መንገድ ተቀጣች ። የደራሲ ሚስቶች ታይፕ በመምታትና በመናበብ ፣ ቡና በማፍላትና ጋቢ በመደራረብ ሲተጉ ነው የምናውቀው ። የሺ ግን ለእነዚያ ለሚያምሩ ድርሰቶች ሻማ ሆና ቀለጠች ። የዓለም አስደናቂ ስራዎች መመዝገቢያ መጽሐፍ ያላየው ታሪክ ።

ማዕቀብ ብዙ አዲስ መሳጭ ታሪኮችን ይዛለች ። ስብሃትና ባለቤቱ ዋሴ በተባለው ህመምተኛ ልጃቸው እንዴት እንደተሸነፉ ... አዲሱን መጽሐፌን አይቼውና ዳብሼው ልሙት እያሉ በጉጉት ስላለፉት ማሞ ውድነህ እና ስለሌሎችም ተረክ አላት ። ማዕቀብ የአዝናኝ መልኮችም ባለቤት ናት ። አድሃሪያን በህይወት ብቻ ሳይሆን በልቦለዱ አለምም መኖር አይፈቀድላቸውም ተብሎ በግድ ስለተገደሉት ገጸባህሪም ትሰማላችሁ ። ሰው ሲሞት ይናዘዛል ፤ ስብሃት ከመሞቱ በፊት እንደምንም ተነስቶ የተናገረው ምን ይመስላችኋል ?

« እኔ የምለው መለስ ዜናዊና ሰይፉ ፋንታሁን አሁንም በኢትዮጽያ ህዝብ ላይ እየቀለዱበት ነው ወይስ አዲስ ነገር አለ ? »
ሃሃሃሃሃሃሃሃ .... ‹ ማዕቀብ › የሌለው ንግግር ይልሃል ይሄ ነው !



Monday, September 25, 2017

ደራሲው ጋዳፊ ለምን ሀሳቡን አልሆነም ?




የሊቢያው መሪ ሙአመር ጋዳፊ ፖለቲከኛ ፣ ሃሳብ አመንጪ እና ደራሲ ነው ። በረጅም የስልጣን ዘመን ቆይታው Escape to hell and others , My vision እና The Green Book የተሰኙ ሶስት ተጠቃሽ መጻህፍትን ለዓለም አበርክቷል ።

አዲስ የፖለቲካ ፍልስፍናውን በመጽሐፍ መልክ ማሳተም የጀመረው በ1975 ነበር ። የዴሞክራሲ ችግር መፍትሄ ፣ የኢኮኖሚ ችግር መፍትሄ እና የሶስተኛው ዓለማቀፍ ቲዎሪ ማህበራዊ መሰረቶች የሚሉ ሶስት ጥራዞችን በተለያዩ ግዜ ጽፏል ። ኋላ ላይ እነዚህን ጥራዞች አንድ ላይ በመሰብሰብ አረንጓዴው መጽሐፍ በሚል ለንባብ አብቅቷቸዋል ።

አረንጓዴው መጽሐፍ ዓለምን ብዙ ያነጋገረና ያከራከረ ስራ ነው ። ይህን መጽሐፍ የተማሩበት የሊቢያ ወጣቶች ብቻ አልነበሩም ። በፈረንሳይ ፣ ምስራቅ አውሮፓ፣ ኮሎምቢያ እና ቬንዚውላ ኮሌጆችና ዩኒቨርስቲዎች ተወያይተውበታል ፤ አውደጥናት ተካፍለውበታል ።

ጋዳፊ የፍልስፍና ውሃ ልኩን በአረንጓዴው መጽሐፍ ለማሳየት ሞክሯል ። በተለይ የምእራቡ ዓለም የዴሞክራሲ፣ ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ አስተምህሮ ጠማማ መሆኑን መነሻ በማድረግ የችግሮቹን መፍትሄ በአማራጭ አተያይ / ሶስተኛው አለማቀፍ ቲዎሪ / ለመተንተን ሞክሯል ።

ጋዳፊ በዚህ ጥራዝ ብዙ ርእሰ ጉዳዮችን ነው የመዘዘው ። በመጀመሪያ ክፍል ምርጫን ፣ የተወካዮች ም/ቤትንና ህዝበ ውሳኔን በእጅጉ ይኮንናል ። እንደርሱ እምነት ዴሞክራሲ የህዝቦች ስልጣን እንጂ የጥቂት እንደራሴዎች ሃብት አይደለም ። ህዝብን እንወክላለን ብለው በፓርላማ በሚሰበሰቡ አባላት ዴሞክራሲ እውን ሊሆን አይችልም ምክንያቱም እነሱ ከተመረጡ በኋላ ለራሳቸው ጥቅም ነው የሚንቀሳቀሱት ። በተለይ ፓርላማው በአንድ ፓርቲ የተዋቀረ ከሆነ የአሸናፊ ፓርቲ ፓርላማ እንጂ የህዝብ ፓርላማ መባሉ አግባብ አይደለም ። ጋዳፊ የወቅቱን የእኛ ሀገርን ፓርላማ ቀድሞ ነው የተቸው ማለት ነው ። እውነተኛው ዴሞክራሲ የሚገኘው በቀጥተኛው የህብረተሰብ ተሳትፎ ነው ። እውነተኛ ዴሞክራሲ ተግባራዊ የሚሆነው ብዙሃኑ በህብረት ወጥቶ ህዝባዊ ኮሚቴ እና ታላቅ የመማክርት ጉባኤ ሲዋቀሩ ነው ። ህዝበ ውሳኔም ቢሆን / Referendum / ዴሞክራሲን የማጭበርበሪያ ዘዴ እንደሆነ ጽፎታል ። ‹ አዎ › ወይም ‹ አይ › ብለው እንዲመርጡ የሚገደዱ ዜጎች ነጻ ሃሳባቸውን እንዲገልጹ አይደረግም ። በመሆኑም ይህ አይነቱ አሰራር ጨቋኝና አምባገነናዊ ነው ሊባል የሚገባው ።

ፕሬስንና ሃሳብን በነጻነት መግለጽን አስመልክቶም የግለሰቦችና የቡድኖች ያልተገደበ መብት እንደሆነ ይዘረዝራል « ፕሬስ ማለት ማንኛውም ሰው ራሱንና አስተሳሰቡን የሚገልጽበት ነው ፣ ሌላው ቀርቶ እብደቱን ጭምር ። የዚህ ሰውየ እብደት የሌላ ሰው ወይም ሰዎች እብደት ነው ተብሎ መቆጠር የለበትም ። በመሆኑም በጋዜጦች የሚወጡ አስተያየቶችን የህዝብን ሃሳብ አደርጎ ጥያቄ ማንሳት መሰረተ ቢስ ነው ፣ ምክንያቱም ጋዜጦች ያተሙት የዚያን ሰውየ አስተያየት ነውና »

በሁለተኛው ክፍል ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ተዳሰዋል ። እንደ ጋዳፊ ሃሳብ ደመወዝተኞች ለቀጠራቸው ግለሰብ ግዜያዊ ባሪያዎች ናቸው ። መሰረታዊ ፍላጎቶች/ ቤት ፣ ትራንስፖርት ወዘተ / በግለሰቦች ቁጥጥር ስር መዋል የለባቸውም ምክንያቱም ብዝበዛንና ባርነትን ያመጣሉና ። በሶሻሊስት ማህበረሰብ ውስጥ ሰዎች የሚሰሩት በሽርካነት እንጂ ለደመወዝ ብለው አይደለም ። በሌላ ሠው ቤት የሚኖሩ ሰዎች ማለትም ኪራይ የሚከፍሉም ሆነ የማይከፍሉት ነጻነት አላቸው ማለት አይቻልም ። መሬት የማንም ሃብት አይደለም ነገር ግን ማንኛውም ሰው በመሬት ላይ ማንንም ሳይቀጥር የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን ይችላል ። የቤት ሰራተኝነት የዘመናዊው ዓለም ባርነት ነው ። እናም የቤት ስራ መከናወን ያለበት በነዋሪዎቹ ነው ።

ሶስተኛው ክፍል ማለትም የሶስተኛው ዓለማቀፍ ቲዎሪ ቤተሰብን ፣ ጎሳን ፣ ብሄርን ፣ ሃገርን ፣ አናሳ ብሄርን ፣ ሙዚቃን ፣ ስፖርትና ሴቶችን ይዳስሣል ። ሌላው ቀርቶ ጥቁር ህዝቦች ወደፊት አለምን / ቀደም ብሎ ቢጫዎች ፣ አሁን ደግሞ ነጮቹ እየገዙ ነው / ይመራሉ ይላል ። ስፖርት ልክ እንደ ጸሎት ግላዊ ጉዳይ መሆኑን ይገነዘባል ። ቦክስ እና ነጻ ትግል ግን የሰው ልጅ ገና ከአረመኔነቱ አለመላቀቁን የሚያሳዩ ድርጊቶች ናቸው ።

ጋዳፊ ቤተሰብ ከመንግስት የበለጠ አስፈላጊ ተቋም እንደሆነ በሚከተለው መልኩ ያምናል  « ቤተሰብ እንደ እጽዋት ነው ። ቅርንጫፍ ፣ ግንድ ፣ ፍሬና ቅጠል ያለው ። እጽዋት የመነቀል ፣ የመድረቅ እና የእሳት አደጋ እንደሚያጋጥማቸው ሁሉ ቤተሰብም ህልውናው በብዙ ነገሮች ይፈተናል ። ያበበ ማህበረሰብ ማለት ግለሰቦች በቤተሰብ ውስጥ ቤተሰቦች ደግሞ በማህበረሰብ ውስጥ ማደግ ሲችሉ ነው ። ቅጠል ለቅርንጫፍ ፣ ቅርንጫፍ ለዛፍ እንዲሉ ግለሰብም በቤተሰብ ውስጥ የጠነከረ ትስሥር አለው ። ግለሰብ ያለ ቤተሰብ ትርጉም የለውም ። የሰው ልጅ እንደዚህ አይነቱን ትስስር ከጣለ ስር የሌለው ሰው ሰራሽ አበባ ነው የሚሆነው »

ጋዳፊ ለጎሳ መራሹ የአፍሪካ ህዝብም ጠቃሚ ስንቅ ያቀበለ ይመስላል ። ማህበራዊ ትስስር ፣ አንድነት ፣ ቅርበትና ፍቅር ከጎሳ ይልቅ በቤተሰብ ይጠነክራል ፤ ከሀገር ይልቅ በጎሳ ይጠነክራል ። ከዓለማቀፍነት ይልቅ በሀገር ይጠነክራል ። ጎሳ ትልቅ ቤተሰብ ነው ... ለጎሳ ትልቁ መሰረት ደም ነው ... ጎሳ አባላቱን የሚከላከለው በመበቀል ነው ። ጎሰኝነት ናሽናሊዝምን ያጠፋል ፤ ምክንያቱም የጎሳ ታማኝነት ከሀገር ታማኝነት የላቀ ነው ። በሀገር ውሰጥ የሚገኙ ጎሳዎች የሚጋጩ ከሆነ ሀገር ችግር ውሰጥ ይወድቃል ። ብሄርተኞች ፍላጎታቸውን በሃይል የሚገልጹ ከሆነና የራሳቸውን ፍላጎት የሚያሰቀድሙ ከሆነ ሰብዓዊነት ላይ አደጋ ይፈጠራል በማለት ስጋቱን ክፍላጎቱ ጋር አዛምዶ መርሁ ላይ አስፍሮታል ።

የአንድ ሀገር ህዝቦች የሚበየኑት በቦታው ላይ በመፈጠራቸው ብቻ አይደለም ። ይህ መሰረታዊ ነገር ሊሆን ይችላል ። ከዚህ በተጨማሪ ግን ለረጅም ግዜ በአንድ ላይ በመኖር የጋራ ታሪክ ፣ ቅርስ እና ተመሳሳይ እጣ ፈንታ ሲኖራቸው ነው ። ህዝቦች ከደም ትስስር ይልቅ ሀገራዊ አንድነትና የኔነትን በጋራ ይዛመዳሉ ።

ሴቶች ከወንዶች እኩል አይደሉም በሚባለው ብሂል ጋዳፊ አይስማማም ። ሴቶች እኩል መስለው የማይታዩበትንም ሳይንሳዊ ምክንያት በዝርዝር አስቀምጧል ። ሴቶች አንስታይ ወንዶች ተባእታይ ናቸው ። ባለሙያዎች እንዳረጋገጡት ሴቶች በየወሩ ደም ሲያዩ ወንዶች አይኖራቸውም ። ሴት ደም ካላየች ነፍሰጡር ናት ። ነፍሰ ጡር ስትሆን ለአመት ያህል ንቁ ተሳታፊ አትሆንም ። ልጅ ስትወልድ ወይም ሲያስወርዳት ደግሞ በ ፒዩፐሪየም / Puerperium / ትሰቃያለች ። ወንድ ይህ ሁሉ ስቃይ አይደርስበትም ። ከወለደችም በኋላ ለሁለት አመታት ታጠባለች ። ጡት ማጥባት ማለት ሴት ከልጅዋ የማትለያይበት በመሆኑ አሁንም ሌሎች እንቅስቃሴዎቿ ይቀንሳል ። በመሆኑም ሌላን ሰው ለመርዳት ቀጥተኛ ሃላፊነት መውሰድ በእሷ ላይ ይወድቃል። ያለ እርሷ ብርቱ ድጋፍ ያ ፍጡር ይሞታል ። ወንድ በሌላ በኩል አያረግዝም ፣ አያጠባም ::

ጋዳፊ በአረንጓዴው መጽሐፍ ታላላቅ ሀሳቦችን አንስቷል ። በክፍል አንድ ስልጣን የህዝብ መሆኑን እንመለከታለን ። ግለሰቦች ሊያብዱ ይችላሉ ይህ ማለት ግን ማህበረሰቡ አብዷል ማለት አይደለም በሚለው ነጥብ ዙሪያ ፕሬስ ሃሳብን መግለጫ ነጻ መሳሪያ መሆኑ ተሰምሮበታል ። በሁለተኛው ክፍል ለኢኮኖሚው ችግር መፍትሄው ሶሻሊዝም መሆኑ ተቀምጧል - በእያንዳንዱ ቤት ወስጥ የሚኖር ዜጋ የቤቱ ባለቤት እንጂ ጭሰኛ መሆን የለበትም የሚል የሚደላ አቋም ይታያል ። የአስቂኝም አስደናቂም ስብስብ በሆነው ሶስተኛ ክፍልም ሴት ከወንድ ታንሳለች ማለት የተፈጥሮ ህግን መካድ ነው የሚል ጠንካራ አቋም ይገኛል ።

ደራሲው ጋዳፊ ከፖለቲከኛው ጋዳፊ ጋር ተጣጥሞ ቢዘልቅ መልካም ነበር ። በተለይ በዙሪያህ የተኮለኮሉ ሰዎች / የተለያዩ ፍላጎት ያላቸው / የስብእና አምልኮ እየገነቡልህ ሲሄዱ ዝም ካልክ መቀበሪያህ እየተማሰ መሆኑ ማወቅ ይገባል ። ። ጋዳፊ መርሁ እንዲዘመር እንጂ እንዲሰራበት ለማድረግ ያልቻለበት አንደኛው ምክንያትም ይሄው ነው ። ጹሑፍህን ደጋግመህ በፍቅር ታነበዋለህ እንጂ ደፍረህ አርትኦት አታደርገውም ። በዚያ ላይ ፍልስፍናን ለማሰብና ለመራቀቅ እንጂ ሆኖ ለመኖር ይከብዳል ።




Wednesday, September 13, 2017

« በፍቅር ሥም » ከጥቅል አደረጃጀት አንጻር



የአለማየሁ ገላጋይን « በፍቅር ስም » ለመተቸት የሚነሳ ሀያሲ በምን ርዕሰ ጉዳይ ስር ልጻፍ ብሎ የሚጨነቅ አይመስለኝም ። መጽሐፉ በዘርፈ ብዙ የሃሳብና የትርክት ሃዲዶች ላይ ስለሚጋልብ አንዱን የታሪክ ሰበዝ መዞ ምልከታንና ሙያዊ ትንተናን ማዋሃድ ይቻላል ።

እኔ እንግዳ በመሰለኝ የመዋቅር አደረጃጀት እና ፍሰት ላይ አተኩራለሁ ። ደራሲው እኔ በተሰኘው የአተራረክ ስልቱ ጽሁፉን የሚጀምረው « በሴት የመከበብን ጥቅም የምናውቀው እኔና ጠቢቡ ሰለሞን ብቻ ነን » በማለት ነው ። የታሪኩ አባት ትንሹ ‹ ታለ  › ነው ። ታለ ይህን የሚነግረን በጥቅሙ በረከት ፈግጎ ነው ። ወጣቱ ታለ በመጽሐፉ መዝጊያ ላይ በተመሳሳይ ዜማ የሚከተለውን ይናገራል « የኛ አስር ደቂቃ በእርሱ / ቹቹ / ስንት እንደሆነ የማውቀው እኔ ነኝ » ታለ ይህን የሚነግረን በህመምና ፀፀት ውስጥ ሰምጦ ነው ።

ታለ የፍቅርና ፀፀት ጥለትን እየለበሰና እያወለቀ የሚዘልቅ ገጸባህሪ ነው ። ደራሲው ይህን የታሪክ ጉዞ የሚያሳየንና የሚነግረን በተለመደው የገጸባህሪ የበቀል/አሸናፊነት ፍትጊያ አይደለም ። የታሪኩ መረማመጃዎች ጥቅል ሰብዕናዋች/ ማንነቶች ናቸው ። አንዱ ጥቅል ቢዘንና አንጓቼ / ባልና ሚስት / ናቸው ። ይህ ጥቅል አውቶብስ በመሰለው ቤተሰባዊ ጎጆ / በነገራችን ላይ የቤተሰቡ መኖሪያ በገጽ 22-23 በአስቂኝ መልኩ ተገልዿል / ውስጥ እንደ ሹፌርና አውታንቲ ሊቆጠር የሚችል ነው ። ሹፌርና ረዳት በሳንቲም መጋጨታቸው አይደንቅም ። አንድ ቤት የሚኖሩ ባልና ሚስት ግን ወንድን ልጅ / ታለን / የግላቸው ለማድረግ የማያባራ ጦርነት መከፈታቸው ያልተለመደ / bizarre / ነው ።

« እግዚአብሄር የሰጠኝን ወንድ ልጅ የገዛ ሚስቴና ልጆቼ ነጠቁኝ » ይላል አባወራው
« ከመላእክት እስከ አጋንንት ደጅ የረገጥኩበትን ልጄንማ አልተውም » ትላለች እማወራ

በዚህ መነሻነት ጥቅሉ እየተፈታ ሌላ ግዜ እየተተረተረ ታሪኩንና የታሪኩን ማህበረሰብ ያናጋዋል ። በስድብና ሽሙጥ አረር ይጠዛጠዛሉ ። የቅናትና ጥርጣሬ ዳመራ በየግዜው ይለኮሳል ። ሰባት ሴት ልጅ መውለዳቸው ያልተዋጠላቸው አባወራ ሰባት ስድቦችን ነው የወለድኩት እስከማለት ይደርሳሉ ። በመልክ ለየት ያሉ ልጆችን ሳይቀር በተጠየቅ ይሞግቷቸዋል ። ጥቁሯን አበባ « ለመሆኑ የአፍሪካ ህብረት ሲቋቋም ተረግዛለች ? » ቀይዋ ስምረትን « መልኳ ሁሉ የእንግሊዝ ነው ፣ እኔ የምለው እንግሊዝ ሲመጣ ነው የተወለደችው ? » ረቂቅን ደግሞ « ይሄ ባኒያንኮ ያልደረሰበት ቦታ የለም » በማለት የነገር ጅራፋቸውን ይተኩሳሉ ። ባልና ሚስቱ በሚታክት መልኩ ይናቆሩ እንጂ ችግር በመጣ ግዜ እንደ ማግኔት ይፈላለጋሉ ፣ ጥቅሉ ማንነት ውስጥ ለአደባባይ አይናፋር የሆነ መተሳሰብ አለ ።

ሁለተኛው ጥቅል ሰባቱ ሴቶች ልጆች ናቸው ። አውቶቡስ በመሰለው ቤት ውስጥ ተሳፋሪ ይምሰሉ እንጂ መኪናው እንዳይገለበጥ ወይም ተበላሽቶ እንዳይቆም ምሶሶ ሆነው የቆሙ ናቸው ። ለምሳሌ የአቶ ቢዘን ጡረታ ስለማያወላዳ እናታቸውን በጉሊት ስራ ይረዳሉ ። በተቃራኒው አባታቸው ጠጅ ቤት ከሰው ጋ ሲጣላ ተሰብስበው ሄደው ወግረው በድል ይመለሳሉ ። ይህም የቢዘን ፍርጎ የሚል ስያሜ ቢያሰጣቸውም አባታቸው በሰፈሩና በየካቲካላው ቤት እንዲፈራ አድርጓል - ከሴት ልጅ ባህሪ አኳያ ግን ያልተለመደ ነው ።

ይህ ጥቅል ገጸባህሪ ለየት የሚልበት ሌላም ጉዳይ አለው ። ቤተሰባቸውን ያፍቅሩ እንጂ ለሌላው እምብዛም ፍቅር የላቸውም ። በተለይ ወንድን በማባረር ተመሳሳይ አቋም ነው ያላቸው ። የርስ በርሳቸው ምክር « እንግባ ቢልሽ አትግቢ ! እንውጣ ቢልሽ አትውጪ ! » ብቻ ነው ። ፍቅር ተፈጥሯዊ ጸጋ ስለመሆኑ ፊት አይሰጡም ። ድንገት ከመካከላቸው አንዷ ፍቅር ሽው ያለባት ግዜ እንኳ መቀመጫ ሲያሳጧት ይታያል ። ወንዳወንዴዋ ቹቹ እንኳ ሰለወደዳት ልጅ እንዲወራ አትፈቅድም ። ይህ ከሴት ልጅ ስስ ልቦናና ተቃርኗዊ ትስስር አንጻር ያልተለመደ ይመስላል ።

ሶስተኛው ጥቅል አራቱ ስፖርተኞች ናቸው ። ደራሲው በዚህ ሃዲድ እንድንጓዝ የፈለገው የልጅነትን ሌላኛው ገጽታ እንድንመለከት ብቻ አይደለም ። እንደ ሽክና አይነት ቀልደኞች ቆምጫጫውን የታሪክ ጉዞ እንዲያለሳልሱት ብቻ አይደለም ። እግርህን ከፍተህ የምትሄደው ጭገርህን ስላላበጠርክ ነው እያለ በግድ መጣላት የሚፈልገውን የ ‹ ቲኔጀር › ሞት አይፈሬነት ለመጠቆም ብቻ አይደለም ። የወንድነት ክትባት የሚፈልገውን ታለን ለማከምም ጭምር ነው ። ስፖርተኞቹ ሰፈር የምታደርሰው ወንዳወንዴዋ ቹቹ መሆኗን ስናስብ ግን በቤተሰቡ ውስጥ ያለውን ሁለተኛ ‹ ቢዛሪ ›ጉዳይ እናጤናለን ።

በሌላኛው ጥቅል አደረጃጀት ውስጥ የተቀረጹት ሶስቱ ወታደሮች ናቸው ። ወታደሮቹ በአፋዊ ገጽታቸው ይለያዩ እንጂ በሀገር ፍቅር ጽናታቸው አንድ ናቸው ። ብዙ ግዜ ለመዝመትና ለመሞት የቆረጡ ናቸው ። ተሸንፈው እንኳን አንዲት ህገር በሚለው መንግስቱ ስም ለመለመን አይሳቀቁም ። መንግስቱን ሳይሆን ታሪካዊ መርሁን አሻግረው ያያሉ ።

የወታደሮቹ ሌላኛው ውክልና ሀገር የገባችበትን ውጥንቅጥ ፈተና ማሳየት ነው ። በማህበረሰቡ ውስጥ አፈሳ ያስከተለውን የፍርሃት ቆፈንና የአስተዳደር መናጋት እንመለከታለን ። ፍርሃት ምንያህል ሀገራዊ ኩይሳ እንደሰራ ለማውቅ የአእምሮ ዝግምተኛው ቹቹ እንኳ መደበቂያ ሲፈልግ መታየቱ ነው ። ሻምበል ጠናጋሻውን ስናስብ ደግሞ ደራሲው ጦር ሰራዊቱ ውስጥ ያነበቡ ፣ የተማሩና ህዝባዊ ፍቅር የተላበሱ ግለሰቦች መኖራቸውን ለመጠቆም ብቻ እንዳልቀረጸው እንረዳለን ። ሻምበሉ ለታሪኩ እንድርድሮሽ መረማመጃነት አገልጋይ ነው ። ሻምበሉ ለታለ ያበረከተው የማይታመን ነገር ግን ጠቃሚ ስጦታ ቀጣዩ ጥቅል ስብእና የደረጀ እንዲሆን አግዟል ።

በዚህ መሰረት ለጥቆ የምናገኛቸው ታለን እና ሲፈንን ነው ። ርግጥ ነው በታለ ውስጥ ቹቹ ፣ በሲፈን ውስጥም ቹቹ አለ ። ቹቹ ‹ ኮመን ዶሚነተር › ነው ። የታለና ሲፈን ፍቅር አይኑን ገልጾ ከፍተኛ ደረጃ / Climax / የደረሰው ሻምበሉ ከከፈለው ጥሎሽ በኋላ ነው ። ጥሎሹ ሲፈን እንድትዝናና ታለ በአዲሱ አለም ላይ አይኑን እንዲከፍት አስችሎታል ።

ሲፈን በርግጥም የአውሊያ ፈረስ ትመስላለች ። ጋልባ ጋልባ ስድስተኛው ጥቅል ገጸባህሪያት ሰፈር የምታደርሰው እሷ ናት ። ደራሲው ይህን በ ‹ ጃክሰኖች › መስሎታል ። አምስቱ ጃክሰኖች የተለያዩ የሙያ ባለቤት ሲሆኑ በሚገናኙበት ጫት ቤት ውስጥ የማያነሱትና የማይጥሉት ርዕሰ ጉዳይ የለም ። እውቀት ጠገብ / ለምሳሌ ከታሪኩ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስላለው የአውሊያ ጉዳይ ተነስቶ አጥጋቢ ምላሽ ሲሰጡ ይታያል / ሆነው በሚፈልጉበት የስራ መስክ መሰማራት ያልቻሉትን የሀገራችንን ምሁራን ይወክላሉ ። ተጠየቃዊ ሙግቶች የክብርና የአደባባይ አጅንዳ ከመሆን ይልቅ በየስርቻው የሚጣሉ የጋን ውስጥ መብራት መሆናቸውንም ያሳያል ።

« በፍቅር ስም » በጥቅል ገጸባህሪያት አደረጃጀት ውስጥ ነው የሚያልፈው ። ጥቅሉ እየተፈታ የሚሰበሰብ ፣ እየተሰብሰብ የሚፈታ ነው ። ጥቅሉ ለታሪኩ መጓጓዣ ምንጣፍ ነው ። የጎሉ ተናጥላዊ ባህሪያት ቢኖሩ እንኳ በአንድም ሆነ በሌላ ምክንያት ጥቅል ውስጥ እንደቀንዳውጣ ወጣ ገባ ማለታቸው አይቀሬ ነው ። ደራሲው ተናጥላዊ ባህሪያትን አጉልቶ ለመለየት የማይረሳ ምልክት ለጥፎባቸዋል ። ለምሳሌ አቶ ቢዘን ባወሩ ቁጥር ‹ ጣ › ይላሉ ። ቹቹ ‹ ቲሽ ! › ማለት ይቀናታል ። የታለ እናት ‹ ኦሆሆይ › በማለት ግርምታቸውን ይተነፍሳሉ ። ሻምበል ሲጠይቅም ሲመልስም ‹ ጥሩ › ን ያስቀድማል ።

እንደ ጥቅልም እንደተናጠልም የሚታየው ታለ ማነው ? ምን ይፈልጋል ? ስንል ወደ ጭብጡ መንደር እንደርሳለን ። በዚህም ረገድ ጥቅል ጉዳዮች ይገኛሉ ። ወንዳወንድነትን ማግኘት በዋናነት ደግሞ አውሊያና ጥንቆላን መዋጋት ። ታለ ህብረተሰቡ « ሴታሴት » ነህ ብሎ ስለፈረደበት ከዚህ የጅምላ ንቀትና ተጽእኖ ለመላቀቅ ያላሰለሰ ትግል ያከናውናል ። ህበረተሰቡ ተፈጥሮውን ተቀብሎ እንኳ እንዲኖር አልፈቀደለትም ። ወንዳወንድ እንዲሆን የተመረጡ ወንዶች ጋር ይውላል ። ወታደር በመሆንና በመሞት ወንድነት የሚገኝ ከሆነ እዘምታለሁ እስከማለት የደረሰ ነው ። የህብረተሰቡን ጥያቄ የተቀበለው ግን ራሱ ህብረተሰቡን በመንቀፍ ነው ። ነቀፌታው ገደብ የለውም እናቱን ፣ አባቱን ፣ ጃክሰኖችን ፣ ሲፈንን ፣ እህቶቹን ፣ ቹቹን ሳይቀር ይተቻል - ያሽሟጥጣል ። ድንኳን መትከልና መንቀል የወንድ ንፍሮ መቀቅልን የሴት ስራ ያደረገው ማነው ? ይላል ። የእንስሣት ሴታ ሴት ይኖር ይሆን እያለ ደግሞ ፈጣሪውን ይሞግታል ።

በሌላ ፊቱ በጥንቆላና ድግምት የእኔን በሽታ ወደ ቹቹ አዙራ ለጥፋተኝነትና ለጸጸት የዳረገችኝ እናቴ ናት በማለት ከእናቱ ጋር የስነልቦና ጦርነት ያካሄዳል ። ሲፈንም ፍቅረኛዬ ሳትሆን በእናቴ እኔን ታገልግል ዘንድ የተመረጠች አውሊያ ናት ብሎ ያምናል ። ሻምበል ይህን ቤተሰባዊ እምነት በማስቀየር የቹቹ በሽታ የአእምሮ ዝግመት ችግር መሆኑን ቢነግረውም አይቀበልም ። ስንት የታገለችለትን እናቱን ፊት ይነሳል ። በርግጥ አውሊያ ልክ እንደ አፈሳው ምን ያህል በሰፈርተኛው እንደሚፈራ እንገነዘባለን ።

ደራሲው በፍቅር ስም ፍቅር አልባ መሆን አለ የሚል ይመስላል ።

Wednesday, August 16, 2017

የኛ ሰፈር ቡሄ ባለ ማርሽ ነበር

ፎቶ ሸገር ብሎግ
ገና ሀምሌ ሲገባደድ ነው የቡሄ መነቃቃቶች የሚፈጠሩት ፡፡ ሂሳብ ላይ ከፍ ያለ ክፍያ እንዲደርሰን በማሰብ ቡድኑን በስድስት ቢበዛ በስምንት አባላት እናዋቅረዋለን ፡፡ ከስብስብ ምስረታ ቀጥሎ የሚመጣው የዱላ ዝግጅት ነው ፡፡ ዱላ ለመቁረጥ የምናመራው ‹‹ ዝንጀሮ ገደል ›› ወደተባለው አካባቢ ነው ፡፡ ዛሬ አካባቢውን  መኖሪያ ቤቶችና የድንጋይ ካባ ተቋማት ከበውት አንድም ዛፍ አይገኝም ፡፡  ዱላው ተቆርጦ ከደረቀ በኃላ ቆርኪ እየጠፈጠፍን ‹‹ ክሽክሽ ›› እንሰራለን - ማድመቂያ ፡፡

የማታ ማደሪያ መምረጥም  ዝግጅት ምዕራፍ ውስጥ የሚካተት ነው ፡፡ ቤቱን ስንመርጥ የቤቱን  ስፋትና የወላጆችን  ባህሪ ግምት ውስጥ በማስገባት ነው ፡፡ ምክንያቱም ማታ ከመተኛት ይልቅ መተራረብና መሳሳቅ ስለሚበዛ ‹‹ ቁጫጭ ሁላ ! ዝም ብለህ አተኛም ! ›› ብሎ የሚያስፈራራንን አባወራ እንዲኖር አንፈልግምና ፡፡ ዳቦና ገንዘብ ያዥም ከወዲሁ ይመረጣል ፡፡ ዶቦ ያዥነትን እንደ ሸክም ፣ ገንዘብ ሰብሳቢነትን  እንደ ስልጣን ስለሚመነዘር ምርጫው ተቃራኒ ገጽታዋችን ማስተናገዱ ግድ ነው  ፡፡

ዛሬ ላይ ሆኜ  ጭፈራችንን ስፈትሸው የድራማ ስልት እንደነበረው ይሰማኛል ፡፡ ያልደከመ ጉልበታችንን  አስቀድመን የምንጠቀመው በሀብታሞች ቤቶች ላይ ነበር ፡፡

‹‹ መጣንኖሎት በዓመቱ  እንዴት ሰነበቱ / 2 ግዜ /
ክፈት በለው በሩን - የጌታዬን / 2 ግዜ /

በሩ የብረትም ሆነ የቆርቆሮ እየጨፈርን በዱላችን እንደበድበዋለን - ስሙን ማለታችን ነው ፡፡ አንዳንድ ተንኮለኛ ደግሞ መጥሪያውን ሊያስጮኀው ይችላል ፡፡ አሁን ውሾች ካሉ እንደ ጉድ ይጮሃሉ ፡፡ ክፉ ጥበቃ ካለም እንደ ውሾቹ እየጮኀ መጥቶ ከአቅማችን በላይ የሆነ ስድብ ያሸክመናል ፡፡ ‹‹ መናጢ የድሃ ልጅ ! በር ስበር ተብለህ ነው የተላከው ?  መጥሪያው ቢበላሽ አባትህ መክፈል እንደማይችል አጥተኀው ነው ፡፡ ሂድ ጥፋ ከዚህ ! ሰበበኛ ሁላ ! ››  ቆሌያችን እንደ ውሻ ጭራ በፍርሃት ይጣበቃል። ደግነቱ የዚህ ተቃራኒ አለመጥፋቱ  ፡፡ አዝማሚያው ደህና መሆኑን ካረጋገጥን  አሁን አንደኛ ማርሽ እናስገባለን ፡፡
 « … የኔማ ጋሼ
  ሆ.. !
  የተኮሱበት
  ስፍራው ጎድጉዶ
  ሆ.. !
  ውሃ ሞላበት
  እንኳን ሰውና
  ሆ.. !
  ወፍ አይዞርበት !
 እያልን እስከታች እንቀጥላለን ፡፡ ብዙ ካስለፈለፉንና ‹ ተወው ጮሆ ጮሆ ይሄዳል › እያሉ የሚያስቡ መስሎ ከተሰማን የጭፈራችን መልዕክት ይቀየራል ፡፡ ሁለተኛ ማርሽ እናስገባለን ማለት ነው ፡፡

‹‹ ላስቲክ ተቀብሮ አይበሰብስም
 አንዴ መጥተናል አንመለስም ::
 አባባ ተነሱ ኪስዋትን ዳብሱ !! ›› በማለት  በአንድ በኩል ጠንካራ መሆናችንን እያሳየን በሌላ በኩል ትዕዛዝ ብጤ እናስተላልፋለን ፡፡ መቼም አንዳንድ ሰው ግድ ስለሌለው ወይም ማስለፍለፍ ስለሚወድ ድምጹን ያጠፋል ፡፡ አሁን ገሚሱ እንሂድ ሲል ሌላው በቀላሉ አንለቅም በማለት ይከራከራል ። ብዙ ግዜ እነዚህን አስተያየቶች የሚያስታርቁ ሀሳቦች ያሉት ይመስለኛል  - ቡሄ ፡፡ አስታራቂው ሀሳብ የጨፋሪውን መዳከም የሚጠቁም ይምሰል እንጂ በንዴትና በምሬት ነው የሚገለጸው ፡፡ እናም  ንዴታችንን ለማፍጠን ሶስተኛ ማርሽ  እንጠቀማለን ::

‹‹ እረ በቃ በቃ
  ጉሮሯችን ነቃ
 በዚህ ማርሽ ተፈላጊው ውጤት ካልተገኘ የኃላ ማርሽ በመነጫነጭ ይገባል ፡፡

 ንጭንጭ አንድ !
 ‹ ይራራ ሆድዋ - እግዜር ይይልዎ ! › ሊል ይችላል አንዱ ቅኝቱን እንደጠበቀ

 ንጭንጭ ሁለት !
 ‹ አለም አንድ ነው የለም አንድ ነው  እኛን ማስለፋት የሚያሳፍር ነው › ማለትም የተለመደ ነው ፡፡ ከብዙ ልፋት በኃላ ስጦታው ከተፍ ካለ ደስታችን ወደር ያጣል ፡፡ ሳናውቀውም ማርሹ አራተኛ ገብቷል ፡፡

‹‹ አመት አውዳመት
  ድገምና
  አመት
  ድገምና
  የጋሽዬን ቤት
  ድገምና
  አመት
  ወርቅ ያፍስስበት
  እንዲህ እንዳለን
  ሆ …!
  አይለየን !!
  ክበር በስንዴ
  ክበር በጤፍ
  ምቀኛ ይርገፍ !! ›› በማለት እየተሳሳቅን ውልቅ ነው ፡፡ ወደሌላኛው ቤት ስንጓዝ በመሃሉ የምንጠቀመው የጭፈራ ስልትም አለ ፡፡ ‹‹ አሲዮ ቤሌማ ›› የሚባል ፡፡ የሬዲዮ ጋዜጠኞች ይህን ዓይነቱን መሸጋገሪያ ‹‹ ብሪጅ ›› ይሉታል ፡፡ እኛ ደግሞ እንደ ሞራል ማነቃቂያ መሰለኝ የምንጠቀምበት ፡፡ የምንጨፍረው እየሮጥን ነው ፤ በል ሲለን ዱላችንን ርስ በርስ እናጋጫለን ፡፡ ምናልባት ሳናውቀው ከመስቀል ጨፋሪዋች ያጋባነው ሊሆንም ይችላል ፡፡ ብቻ ዛሬ ድረስ የማይገቡኝ ቃላቶች አሉበት ፡፡

‹‹ አሲዮ ቤሌማ
  ኦ … ኦ
  አህ እንበል
  አሲዮ ቤሌማ
  ቤሌማ ደራጎማ … ›› ለአብነት ያህል ‹ ደራጎማ › ግጥሙ እንዲመታልን የተጠቀምነው ቃል ነው ወይስ ትርጉም አለው ? 

የቡሄ ዕለት ሲርበን ለምሳ ወደ ቤት መሄድ የማይታሰብ ነው ፡፡ ዳቦ ክፍሉ በጎተራው ያለውን ንብረት ያሳውቅና እንከፋፈላለን ፡፡ ዳቦ እንኳን ባናገኝ ካላቸው ላይ ገዝተን ነው የምንበላው ፡፡ አንድ ክረምት ላይ ዝናቡ ዳቧችንን አሹቆት ነበር ፡፡ በጣም የራባቸው ዳቦውን እንደ ጨርቅ ጨምቀው የቀማመሱበት ሁኔታ ነበር ፡፡ ወደ ኃላ እየቀረ ዳቦውን በጥርሱ እየከረከመ የሚያስቸግረን ባልደረባም ነበረን ፡፡ በንዴት ስንጮህበት ‹ እንዲሁ ነው የተረከብኩት ! › ብሎ ይሸመጥጣል ፡፡

 ገና ‹‹ የወንዜው ነበረ ›› ስንል ‹‹ ነብር ይብላህ ! ›› በማለት የሚያባርሩን ሰዋች እንደው ራሳቸው ከነብር ካልተሰሩ በስተቀር በአውዳመት ይህን እኩይ  ቃል መጠቀማቸው ይገርመኛል ፡፡ ለረጅም ሰዓት ከኛ ጋር ግቢው ውስጥ ጨፍሮና አስጨፍሮን  ‹‹ በሉ የዓመት ሰው ይበለን ፤ ያኔ ደግሞ ከዚህ በላይ እንጨፍራለን ›› ብሎ በነጻ የሚሸኘንም ሰው ነበር ፡፡ ያኔ በሳቅ ከመፍረስ ጎን ለጎን ዞር ብለን በተረብ ቀዳደን እንጠለው ነበር

 ‹‹ ምናባቱ ድሮ ሳይጨፍር ያለፈበትን ግዜ በኛ ያስታውሳል እንዴ ?! ብሽቅ ! .. ገገማ ! … ጥፍራም ! … ሽውደህ ሞተሃል ?! … ›› በዛሬ ዓይን ሳስበው ግን ‹ ምን ዓይነት ፍቅር ያለው ሰው ነው ?  › እላለሁ ፡፡ አደገኛ ውሻ ለቀውብን  ስንፈረጥጥ በሳቅ ብዛት የሚሰክሩትም ጥቂት አይደሉም ፡፡ በጣም የሚገርመው ከመታ የሚገላግለውን ወጠምሻ ዱላ አዝለን ከሩጫና ፍርሃት መገላገል አለመፈለጋችን ነው ፡፡ ማታ ላይ ጉዳዩ ተነስቶ ስንተራረብ ‹ እኔ የሮጥኩት ወሻውን ሳይሆን ባለቤቱን ፈርቼ ነው › በማለት እናስተባብላለን - እንዲም አድርጎ ሽውዳ የለም ፡፡ ዞሮ ዞሮ የተፈጸመብንን ግፍ ወደሌላው በማጋባትም እንታወቃለን ፡፡ ሌላ የጨፋሪ ቡድን መንገድ ላይ ስናገኝ ‹ እዛ ቤት 10 ብር አግኝተናል › በማለት ወደ ውሻው ቤት እንዲሄዱ እንጠቁማቸዋለን ፡፡ ከዛ በተራችን ራቅ ብለን የአዳኝና ታዳኝ ትርዒቱን በሳቅ እያጣቀስን መኮምኮም ነው ፡፡

 ማታ ስንተኛ የቀኑን ውሎ እያስታወስን የምንስቅበት፣ የምንተራረብበትና የምንገማገምበት መድረክ ነው ማለት ይቻላል ፡፡ የሁላችንም ዱላ ስሩ ይታያል ፤ መሬት ሲደበድብ ስለሚውል ተቸርችፎ የተጠቀለለ ሉጫ ጸጉር ይመስላል ፡፡ ይህ የጸጉር መጠን አነስተኛ የሆነበት መሬቱን በደንብ ስለማይመታ ለጋሚ ነው ተብሎ ይተቻል ፡፡ ድምጽም ሌላው መመዘኛ ነው ፡፡ በደንብ ሲጮህ የዋለ ድምጹ እንደ አለቀ ባትሪ መነፋነፉ ይጠበቃል ፡፡ ብዙም ያልተለወጠ ከተገኘ ‹ በእኛ ላይ ሲያሾፍ ስለነበር ክፍፍሉ ላይ ዋጋውን ያገኛል ! › ይባላል ፡፡ 

ታዲያ በማግስቱ ያ - ሰው እኔ ካላወጣሁ እያለ ሲያሸብር ይውላል ፡፡ በደንብ ማውጣት የማይችሉ አባላትም ሌላው የመዝናኛ ገጸ በረከቶች ናቸው ፡፡ ለምሳሌ ያህል ‹‹ መጣንሎት በዓመቱ እንዴት ሰነበቱ ›› የምትለውን የመግቢያ ስንኝ ከጨረሰ በኃላ በምን ዓይነት ዝላይ እንደሆነ ሳይታወቅ የመጨረሻውን ‹‹ እረ በቃ በቃ ጉሮሯችን ነቃ ! ›› ላይ ፊጢጥ የሚል ያጋጥማል ፡፡ በስንት ህክምናና ስለት ልጅ እምቢ እንዳላቸው እያወቀ ‹‹ ይራራ ሆድዋ እረ በልጅዋ ! ›› የሚል ልመና በማቅረብ እኛን ለመጥፎ ሳቅ ሰዋቹን ለማሳቀቅ የሚዳርግም  አይጠፋም ፡፡ አንዳንዴ ወደማናውቀው ሰፈር ጥሩ ብር ለመስራት ሄደን በሰፈሩ ጉልቤዋች የ ‹ ኮቴ › ተብሎ የምንቀማበት ሁኔታ ያጋጥማል ፡፡ ይህ ጉዳይ ከተፈጸመ  ማታ ብዙውን የክርክር ጊዜ ሊወስድብን ይችላል ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የሚወቀሰው ግን ራሱ ገንዘብ ያዡ ነው ፡፡

 ‹ ከርፋፋ ! ገንዘቡን ዝም ብለህ  ሜዳ ላይ ታስቀምጠዋለህ ?! › ሊባል ይችላል ፡፡ አንድ ሰው ገንዘብ ያዥ ሆኖ ሲመረጥ የራሱን ጥበብ መዘየድ ይኖርበታል ፡፡ ገንዘቡ በጉልቤዋች ሊበረበር ይቻላል በሚል ስጋት የሱሪው እግር አካባቢ፣ ኮሌታ ስር፣ በቀበቶው ማድረጊያ የውስጥ ክፍል ወይም በሌላ አሳቻ ቦታ ሰፍቶ በመደበቅ የማምለጫ ፋይዳዋችን ማስፋት አለበት እንጂ በድንጋጤ ንብረቱን ማስረከብ የለበትም ፡፡ ሌላው ቢቀር የተወሰኑ ወፍራም ቡጢዋችን ቢቀምስ እንኳን ‹ እረ ገና አልሰራንም ! › ብሎ መሸምጠጥ ይጠበቅበታል ፡፡

 በማታው ክፍለ ግዜ አባላቱ እየተንጫጩ ራሱን ዜሮ ማርሽ ላይ አቁሞ በጸጥታ የሚሰምጥም አይጠፋም ፡፡ ለመሆኑ የዝምታው ምንጭ ምን ሊሆን ይችላል ?  በአብዛኛው ሶስቱ ናቸው ። እዳ ፣ ነጠቃ እና ግርፊያ ::

እዳ … የሚፈጠረው በብይ ወይም በጠጠር ጨዋታ ነው ፡፡ በክረምት ገንዘብ ከሌለን ጨዋታው ሞቅ እንዲል በሚል በዱቤ እንጫወታለን - ለቡሄ ለመክፈል በመስማማት ፡፡ ብዙ የማይችሉት ታዲያ ከአሁን አሁን እናስመልሳለን እያሉ እዳው ጣራ ይነካባቸዋል  ፡፡ እናም ያስባል ፤  ብሩን አስረክቤ ቤት ምን ይሉኛል ? ድጋሚ አቤቱታ ልጠይቅ ? ልካድ ? ብክድ ምን ይመጣብኛል ? ….

 ነጠቃ … የምንለው ደግሞ በጉልቤ ቤተሰቦች የሚከናወን ነው ፡፡ ለስለስ ባለ አነጋገርና የጭንቅላት ዳበሳ ሁለት ቀን ጨፍሮ ያገኘውን ብር ይቀመጥልህ አይደል ? ይባላል … ኮስተር ባለ ግንባር ልጅ ገንዘብ ከለመደ ዱሩዬ ይሆናል ! ይባላል …  ዲፕሎማት በሆነ መንገድ አበድረኝ ሊባል ይችላል … ብቻ በብሩ እንደሌሎች የፈለገውን ማድረግ ስለማይችል የማምለጫ መንገድ ፍለጋ በሃሳብ ይኳትናል ፡፡

 ግርፊያ … የሚመነጨው ከሃርደኛ አባቶች ነው ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ‹ መጨፈር አንሶህ በዓመት በዓል ሰው ቤት ምናባህ ያሳድረሃል ?! › የሚል ነው ፡፡ በጨፈረበት ዱላ የሚወቀጥ … ባገኘው ገንዘብ በርበሬ ገዝቶ የሚታጠን … ያጋጥማል ብሎ መውሰድ ይቻላል ፡፡

 ብቻ ምንም ሆነ ምን  ባለ ማርሹ ቡሄ ደስታው የላቀ ነው ፡፡ በቡሄ  ገንዘብ ከማግስቱ  ጀምሮ እንቁጣጣሽን አንቨስት ማድረግ እንጀምራለን  ፡፡ ወረቀት ፣ ንድፍ ፣ ቀለም  ይገዛል ፡፡ የወቅቱ የእግር ኳስ ኮኮቦችና ሁሌም ቋሚ ተሰላፊ የሆኑትን መላዕክቶች በመኳል እንደሰታለን ፡፡ እናም ቡሄ ባይኖር ኖሮ እንቁጣጣሽ ይከብደን ነበር ፡፡ ኢንቨስት የምናደርግበትን ገንዘብ ማን ይሰጠናል ?


Monday, August 14, 2017

ከለንደኑ ውድድር ያተረፍናቸው ሽሙጥ እና ግጥሞች


የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና አዝናንቶን አለቀ ። ኢትዮጽያን የወከለው ቡድን ሁለት ወርቅና ሶስት ብር አጥልቆ በሰባተኛ ደረጃ ውድድሩን ጨርሷል ። ከለንደን ያገኘነው ግን ሜዳሊያ ብቻ አይደለም - ሽሙጥና ቅኔዎችም ጭምር እንጂ ። በመንፈስ አብሮ ሲሮጥ የነበረው ኢትዮጽያዊም ሲበሳጭ በሃይለቃል ፣ ሲደሰት በግጥም ግራ ሲጋባም በጥያቄ ሀሳቡን በማካፈል የማይናቅ ሚና ተጫውቷል ።

ሀገራዊ ሽሙጥ

ንዴቱ የጀመረው ገንዘቤ ዲባባ ያልተጠበቀ ውጤት ባስመዘገበችበት ወቅት ነበር ። ይቺ ብርቅ አትሌት የባለብዙ ሪክርድ ባለቤት መሆኗ ይታወቃል ። በየግዜው ሪከርድን እንደ ፋሽን ከመቀያየሯ አንጻር በለንደን ያጋጠማትን ሽንፈት ለመቀበል አስቸጋሪ ነበር -ለብዙዎች ። ከገንዘብና ከሀገር ፍቅር ስሜት ጋር በማያያዝ ሽሙጡ ፣ ስላቁ እና ዝርጠጣው ተወረወረ ። ቀስቱን ሊመክቱላት የተጉ ሰዋች ቢኖሩም ስሜቷን ከመሰበር አላዳነውም ።

ስምን መልአክ ያወጣዋል የሚል ስነቃል ወርውሮ ገንዘቤን ከገንዘብ ... አልማዝን  ከእንቁነት ጋር ብቻ ማዛመድ ኢትዮጽያዊ ፍርድ ቤትን መምሰል ነው የሚሆነው ። ፍርደ ገምድልነት ግዜያዊ ቁጣና እብሪትን ያበርድ ከሆነ እንጂ ከኋላ የተቆለለውን እውነት አይሸፍነውም ። ወርቅ የመራብ ጉጉት ታላቁን በረከት መሸፈን አልነበረበትም ። ዓለምን በተደጋጋሚ ድል ጉድ ያሰኘው እግሯ ቢሆንም እጆቿም ባንዲራን በማውለብለብ የገጽታ ግንባታን ያለ ገደብ ገንብተዋል ። አለም በብቃቷ ተማርኮ ንግስትና ጀግና ያደረጋትን አትሌት በምንም ሃይል ከከፍታዋ ላይ ማውረድ አይቻልም ። አጉል ግራ መጋባት እንጂ ።

ይልቅ በአደጋገፋችን ላይ የሚሰነዘረውን ሽሙጥ መመርመር ብንችል ማለፊያ ነበር ። አንድ አትሌት ኢትዮጽያን ወክሎ ከሀገር ይወጣል ፣ መንገድ ላይ ግን በብዙ ባንዲራዎች ይደገፋል ። የውጭ ሀገር ሰዎች የተለያየውን ባንዲራ እያዩ አንተ ከየት ነህ ? ለማነው የምትደግፈው እያሉ ይጠይቃሉ ። ባንዲራ ለባሹ በኩራት ይመልሳል ። ታዛቢው ኢትዮጽያ ስንት ባንዲራ ነው ያላት ? ስንት ስያሜ ነው ያላት ? መጀመሪያ እየተደናበረ ቆይቶ ደግሞ እያሽሟጠጠ ይጠይቃል ። መላሹ እየተቆጣ ይመልሳል ። ይኅው አዙሪት እንደቀጠለ ነው ።
ግራ የገባው ሰው ምንኛ ታደለ
ቀኝም ሆነ ግራ ያልገባው ስንት አለ - ይልሃል አሽሟጣጩ ስንኝ ...

ግጥም
‹ የማይሸነፈው › ሞ ፋራ በዮሚፍ ቀጀልቻ በር አስከፋችነት ለሙክታር እድሪስ እጅ የሰጠ ግዜ ደግሞ አሽሙረኛው ሁላ ገጣሚ ሆኖ ቁጭ አለ ። ግጥም እንደ ጉድ ዘነበ ። ስድ ንባብ በደስታ ወቅት ዋጋ ቢስ ነው ለካ ? የህዝቡ እምቅ ችሎታ አፍጥጦ ወጣ ። ማን ያልገጠመ ማን ጥቅስ ያላመነጨ አለ ? የፌስ ቡክ ግድግዳዋች ከአጫጭር ግጥሞች ጎን ለጎን በፉከራዎችና ሽለላዎች ደመቁ ። እናት ሀገርም በግልባጭ ሞገስና ውዳሴ አገኘች ። ነባር የፌስ ቡክ ገጣሚዋችም ቅኔ ዘረፉ

ጥረትና ድካም
ካልታየ በስራ
ለአራዳም አልሆነ
እንኳንስ ለፋራ አሉት ።

በርግጥ በሌላኛው ጠርዝ የሚገኘው ህዝብም ለሞ ፋራ ብልጥ የሆኑ ስንኞችን ከመጠር ቦዝኖ አያውቅም ።

Born in Somalia
Trains in California
Arsenal fan, a Gooner
Running in Londinium
A superstar, a Muslim
Cheered by the Whole stadium

አለማቀፋዊ  ሽሙጥ
አልማዝ አያና አንድ ወርቅና አንድ ብር በማሸነፍ በሰሌዳ ደረጃችን ላይ ትልቅ ሚና ተጫውታለች ። አልማዝ ፣ ወርቅ ፣ ብር ደስታዊ ትስስሮሽ በመፍጠሯ ህዝቡ ወስጥ እንቁነት ፈጥራለች ። በበጎ ያዩዋት ሁሉ የአስር ኪሎ ሜትሩን ሩጫ ተአምር ነው ብለዋል ። ለ 11 ወራት ከሩጫ ርቃ ከሶስት አትሌቶች በስተቀር ሁሉንም ደርባ ማሸነፍዋ አጀብ የሚያሰኝ ነው ። የብዙዎቹን አትሌቶች የግል ሰአት እንዲሻሻል ምክንያት መፍጠሯ እና በ 46 ሰከንድ ርቃ ማሸነፏ የውድድሩ ክስተት ነበር ።

የአልማዝ ውጤት ያልተዋጠላቸው ግን ጥቂቶች አልነበሩም ። ለምሳሌ የአውስትራሊያ የሶስት ግዜ ሻምፒዮናና አሰልጣኝ ሊ ትሩፕ አለማቀፉን ፌዴሬሽን በመውቀስ ውድድሩ ቀልድ እንደሆነ ጽፏል ። የስኮትላንድ ረጅም ርቀትና የጎዳና ተወዳዳሪ የነበረችው ኤልሳቤጥ ማኮልገን ውጤቱን እንደማትቀበለው ገልጻለች ። ሌሎችም በድረ ገጻቸው የአልማዝን ተአምረኛ እግሮች እንደሚጠራጠሩት ጽፈዋል ። በሪዮ አኦሎምፒክ ለቀረበላት ተመሳሳይ ጥያቄ የኔ ዶፒንግ ስልጠና እና ፈጣሪ ነው ብትልም ዘንድሮም ሆያሆዬው አልቀረላትም ።








LIZ mccolgan @Lizmccolgan

So from 3k to 8 k Ayana 5 k split 14:30. Until Ethiopia follow proper doping procedures i for one do not accept these athletes performances


Well they might. But I would suggest the issue is broader than simply a country. It's who trains there & how often they're tested OOC? 

Won't she be tested tonight? Why pin the blame on a country then international testing is in place? Does the UK test Mo?
 But you cheer on Farah, who has hidden with Jama Aden several years?

የዚህ ሽሙጥ ፍላጻም ወገንተኛውን ሚዲያ ያጥበረበረው ይመሰለኛል ። በሚዲያ ሽፋን ቦልት እንጂ ጀስቲን ጋትሊን አዲስ ጀግና አልሆነም ። ጀግናውን ሞ ፋራ ላቆመው መሃመድ በቂ ነገር አልተሰራም ።

ሌንሱን ሞ ፋራህና ቦልት ላይ ብቻ አነጣጥሮ ብዙ ሊመረመርና ሊባልበት የሚገባውን የአልማዝ ልዩ ስትራተጂ በዝርዝር መቃኘት አልፈለገም ። ለአዲስና ልዩ ለሆነ ዘዴ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ የሚያከራክረውና የሚያመራምረው አለማቀፍ ሚዲያ እሱም አሽሟጣጭ ካልሆነ በስተቀር ጉዳዩን ችላ የሚልበት መንገድ ግልጽ አይደለም ።

የአልማዝ የ 10ሺህ ሜትር ስልት የእሷ ብቻ ምልክት ነው ወይም ስልታዊ ሪከርድ ነው ። ይህን ልዩ ስልት ሌሎች አትሌቶች እንዴት እውን ማድረግ ይችላሉ ? ነው ይህን ስልት መከተል አዋጭ አይደለም ? በተወዳዳሪነትና ልብ አንጠልጣይንት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽእኖ እንዴት ይታያል ? ምክንያቱም አንድ ሰው ገና ከጠዋቱ ቀድሞ ወጥቶ ማሸነፍ ከቻለ ተመጣጣኝ ውድድር እና አጓጊንት ይኖራል ለማለት ያስቸግራል ። ብዙ ሊጠናበት ግድ ቢልም ሚዲያው ሸውራራነትን መርጧል ። አሰልጣኞች የጉዳዩ ባለቤት ከመሆን ይልቅ ቅንድባቸውን መስቀል ፈልገዋል ።


ድንቄም ... ?! አለ አሽሟጣጭ

Thursday, August 3, 2017

የድርሰት ሰማይን ያደመቁ ብዕረኛ

ደራሲ አማረ ማሞ ብዙ አልተባለላቸውም ። ግን ለስነጽሁፍ ብዙ ሰርተዋል ፤ በእጅጉ ደክመዋል ። እጣ ፈንታ ሊሆን ይችላል ። አንዳንድ ያደለው በአንድ ጥሩ ስራ ስማይ ላይ ሊወጣ ይችላል ። የዚህ አይነቱ እድለኛ ባለቲፎዞም ስለሚሆን ክበባቱ ፣ ሚዲያውና ማስታወቂያው እንኮኮ ያደርገዋል ።

በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ደራሲ፣ አርታኢና ተርጓሚ አማረ ማሞ ማናቸው ተብሎ አልተመረመሩም ። እኚህ ሰው ስነጸሁፍ ፍቅራቸው ብቻ ሳይሆን ህይወታቸው በመሆኑ ኖረውብታል ማለት ይቻላል ። የኢትዮጽያ መጻህፍት ድርጅት ስነጽሁፍንና ደራሲዎችን ለማሳደግ አይነተኛ ሚና ተጫውቷል ። እሳቸው ደግሞ በድርጅቱ ውስጥ ም/ስራ አስኪያጅ ነበሩ ።

በድርጅቱ አሳታሚነት ለንባብ ይበቁ የነበሩ መጻህፍትን የሚያስታውስ አንባቢ የአቶ አማረን ድርሻ በአግባቡ ለመረዳት አያዳግተውም ። የነባርና እጩ ደራሲዋችን የአሳትሙልኝ ረቂቅ ጽሁፎችን በመለየት ፣ የተለየውን ደግሞ የአርትኦት ስራ በማከናወን በድርሰት ላይ የማዋለድና ጥሩ ቁመና የመፍጠር ህክምና አበርክተዋል ።

እንዴት ላሳትም ወይም በምን መልኩ ልጻፍ ወይም የመሳሰሉ ጥያቄዋችን አንግቦ ቢሯቸው ጎራ የሚሉትን ጥበብ አፍቃሪዋች ውሃ የሚያነሳ ምላሽ ለመስጠት አያነቅፋቸውም ። የኢትዮጽያ መጻህፍት ድርጅት ከስራ ውጪ ከሆነ በኋላ እንኳ አቶ አማረን ኪነጥበባዊ እድሞሽ ላይ ማግኘት ቀላል ነበር ። በስነጽሁፋዊ ውይይቶችም ሆነ ህትመት ምርቃቶች ላይ ከፊት በመገኘት ልምዳቸውንና ሃሳባቸውን ሳይሰላቹ አጋርተዋል ።

አቶ አማረ የበርካታ መጻህፍት ደራሲና ተርጓሚ ናቸው ። ዶን ኪሆቴ ፣ አሳረኛው ፣ እሪ በይ ሃገሬ ፣ የእውነት ብልጭታ ፣ የቀለም ጠብታ እና የልብ ወለድ ድርሰት አጻጻፍ የተስኙ ስራዋችን በጥቂቱ መጠቃቀስ ይቻላል ።

እውነቱን ለመናገር የልብ ወለድ ድርሰት አጻጻፍ የተሰኘው ስራቸው ብቻ ሽልማት የሚገባው ነው ። በ1960ዎቹ የታተመው ይህ ስራ የብዙ ድርሰት አፍቃሪያንን አይኖች የገለጠ ነው ። እንደሚታወቀው ኮሌጅ/ዩኒቨስቲ የመግባት እድል ያላጋጠማቸው የሀገራችን ደራሲዎች ጥቂቶች አይደሉም ። ብዙዎቹ ታዲያ መጽሀፉን እንደ አንድ ተቋም ክብር በመስጠት የልቦለድ ባህሪና ምንነትን እንዲሁም እንዴት መቀሸር እንደሚገባው የተረዱት ይህን መጽሀፍ በማንበብ ነው ። ለመጽሀፉ ምስጋና ይግባውና ጠንካራ ምናብና ብእር ያላቸው ደራሲዎች መፈጠር ችለዋል ።

ይህ መጽሀፍ ድንበር ያጠረው አልነበረም ። ሌላው ቀርቶ በኮሌጆችና/ዩኒቨስቲዎች ለስነጽሁፍ ትምህርት አጋዥ በመሆን ለመምህራኑም ሆነ ለተማሪዎች ትልቅ ግብዓት ፈጥሯል ። በነገራችን ላይ የራሳቸውን ማንዋል አዘጋጅተው ወይም አጋዥ ስራ አሳትመው የሚያስተምሩ ውለተኛ መምህራን ቁጥር እጅግ አነስተኛ ነው ። የቲያትር ኮርስ ሲሰጥ የፋንታሁን እንግዳ የተውኔት መጽሀፍ ነው ትልቅ ድርሻ የሚወስደው ። ተማሪ እየተናጠቀ ኮፒ ለማድረግ ይራወጣል ። በዚህ ረገድ ደበበ ሰይፉና ዘሪሁን አስፋው የሚታሙ አይመስለኝም ። ርግጥ ነው ብርሃኑ ገበየሁም ኋላ ላይ ተቀላቅሏል ። መሰረታዊ ስነጽሁፍ ለኮሌጅ ተማሪዋች በተለይ የአፍሪካ ስነጽሁፍን አስመልክቶ ግን ብዙ ያልተዘመረለት መምህር አለ ። መክነህ መንግስቱ የሚባል ። ርግጠኛ ባልሆንም ከኮተቤ ወደ ዩኒቨርስቲ የተዘዋወረ ይመስለኛል ። በርካታ ድርስት ነክ ስራዎችን በእንግሊዘኛ ቋንቋ አሳትሟል ። ተማሪዎችም የእሱን ስራዎች መነሻ በማድረግ የአፍሪካን ስነጽሁፍን ለማወቅና ለመመርመር አግዟቸዋል ።

የአቶ አማረ ስራ ግን ኮሌጅ ለረገጠውም ላልገባውም ፣ ለጀማሪውም ለመምህራንም ፣ ለስነጽሁፍ አድናቂም ለተመራማሪውም ዛሬም ድረስ የውለታ ሃውልት ሆኖ ቆሟል ። እንግዲህ እዚህ ሃውልት ላይ ነው ሰሞኑን የክብር ካባ እና የወርቅ ብእር የተሰቀለው ። በሸላሚው ድርጅት ማለትም በንባብ ለህይወት የፌስ ቡክ ገፅ ላይ « አይናቸውን ያልጨፈኑ የድርሰት ሰማያችንን ያደመቁ ኮኮብ ሆነው ሆነው በመገኘታቸው የዓመቱ የወርቅ ብዕር ተበርክቶላቸዋል » የሚል ጽሁፍ ይነበባል ።

ግሩም ምስክርነት ሆኖ ስላገኘሁት ደስ ብሎኛል ። በርግጥም የድርሰት ሰማያችንን ለማድነቅ የተጉ በርካታ ጸሐፊያን አሉን ። አቶ አማረ ግን ኮኮቦቹ ከመታየታቸውም በፊት ጧፍ ሆነው ተገኝተዋል ። ብዙዎችን አርመዋል ... ኮትኩተዋል ... በርካቶችም የጧፉን ብርሃን ተከትለው  መንገድ አግኝተዋል ።


ንባብ ለህይወት በአጭር እድሜው አምባሳደር ዘውዴ ረታ ፣ አዳም ረታንና አማረ ማሞን የወርቅ ብዕር ተሸላሚ አድርጓል ። መልካም ጅምር ስለሆነ ለረጅምና ላልተቆራረጠ ጉዞ ብርታቱን እንዲሰጣችሁ እመኛለሁ ። ብርታቱ ግን እንደ አማረ ማሞ ብዙ ሰርተው ያልተነገረላቸውን ብዕረኞችን  ለማፈላለግ ጭምር እንዲሆን ማድረግ ይገባል ።