Monday, August 14, 2017

ከለንደኑ ውድድር ያተረፍናቸው ሽሙጥ እና ግጥሞች


የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና አዝናንቶን አለቀ ። ኢትዮጽያን የወከለው ቡድን ሁለት ወርቅና ሶስት ብር አጥልቆ በሰባተኛ ደረጃ ውድድሩን ጨርሷል ። ከለንደን ያገኘነው ግን ሜዳሊያ ብቻ አይደለም - ሽሙጥና ቅኔዎችም ጭምር እንጂ ። በመንፈስ አብሮ ሲሮጥ የነበረው ኢትዮጽያዊም ሲበሳጭ በሃይለቃል ፣ ሲደሰት በግጥም ግራ ሲጋባም በጥያቄ ሀሳቡን በማካፈል የማይናቅ ሚና ተጫውቷል ።

ሀገራዊ ሽሙጥ

ንዴቱ የጀመረው ገንዘቤ ዲባባ ያልተጠበቀ ውጤት ባስመዘገበችበት ወቅት ነበር ። ይቺ ብርቅ አትሌት የባለብዙ ሪክርድ ባለቤት መሆኗ ይታወቃል ። በየግዜው ሪከርድን እንደ ፋሽን ከመቀያየሯ አንጻር በለንደን ያጋጠማትን ሽንፈት ለመቀበል አስቸጋሪ ነበር -ለብዙዎች ። ከገንዘብና ከሀገር ፍቅር ስሜት ጋር በማያያዝ ሽሙጡ ፣ ስላቁ እና ዝርጠጣው ተወረወረ ። ቀስቱን ሊመክቱላት የተጉ ሰዋች ቢኖሩም ስሜቷን ከመሰበር አላዳነውም ።

ስምን መልአክ ያወጣዋል የሚል ስነቃል ወርውሮ ገንዘቤን ከገንዘብ ... አልማዝን  ከእንቁነት ጋር ብቻ ማዛመድ ኢትዮጽያዊ ፍርድ ቤትን መምሰል ነው የሚሆነው ። ፍርደ ገምድልነት ግዜያዊ ቁጣና እብሪትን ያበርድ ከሆነ እንጂ ከኋላ የተቆለለውን እውነት አይሸፍነውም ። ወርቅ የመራብ ጉጉት ታላቁን በረከት መሸፈን አልነበረበትም ። ዓለምን በተደጋጋሚ ድል ጉድ ያሰኘው እግሯ ቢሆንም እጆቿም ባንዲራን በማውለብለብ የገጽታ ግንባታን ያለ ገደብ ገንብተዋል ። አለም በብቃቷ ተማርኮ ንግስትና ጀግና ያደረጋትን አትሌት በምንም ሃይል ከከፍታዋ ላይ ማውረድ አይቻልም ። አጉል ግራ መጋባት እንጂ ።

ይልቅ በአደጋገፋችን ላይ የሚሰነዘረውን ሽሙጥ መመርመር ብንችል ማለፊያ ነበር ። አንድ አትሌት ኢትዮጽያን ወክሎ ከሀገር ይወጣል ፣ መንገድ ላይ ግን በብዙ ባንዲራዎች ይደገፋል ። የውጭ ሀገር ሰዎች የተለያየውን ባንዲራ እያዩ አንተ ከየት ነህ ? ለማነው የምትደግፈው እያሉ ይጠይቃሉ ። ባንዲራ ለባሹ በኩራት ይመልሳል ። ታዛቢው ኢትዮጽያ ስንት ባንዲራ ነው ያላት ? ስንት ስያሜ ነው ያላት ? መጀመሪያ እየተደናበረ ቆይቶ ደግሞ እያሽሟጠጠ ይጠይቃል ። መላሹ እየተቆጣ ይመልሳል ። ይኅው አዙሪት እንደቀጠለ ነው ።
ግራ የገባው ሰው ምንኛ ታደለ
ቀኝም ሆነ ግራ ያልገባው ስንት አለ - ይልሃል አሽሟጣጩ ስንኝ ...

ግጥም
‹ የማይሸነፈው › ሞ ፋራ በዮሚፍ ቀጀልቻ በር አስከፋችነት ለሙክታር እድሪስ እጅ የሰጠ ግዜ ደግሞ አሽሙረኛው ሁላ ገጣሚ ሆኖ ቁጭ አለ ። ግጥም እንደ ጉድ ዘነበ ። ስድ ንባብ በደስታ ወቅት ዋጋ ቢስ ነው ለካ ? የህዝቡ እምቅ ችሎታ አፍጥጦ ወጣ ። ማን ያልገጠመ ማን ጥቅስ ያላመነጨ አለ ? የፌስ ቡክ ግድግዳዋች ከአጫጭር ግጥሞች ጎን ለጎን በፉከራዎችና ሽለላዎች ደመቁ ። እናት ሀገርም በግልባጭ ሞገስና ውዳሴ አገኘች ። ነባር የፌስ ቡክ ገጣሚዋችም ቅኔ ዘረፉ

ጥረትና ድካም
ካልታየ በስራ
ለአራዳም አልሆነ
እንኳንስ ለፋራ አሉት ።

በርግጥ በሌላኛው ጠርዝ የሚገኘው ህዝብም ለሞ ፋራ ብልጥ የሆኑ ስንኞችን ከመጠር ቦዝኖ አያውቅም ።

Born in Somalia
Trains in California
Arsenal fan, a Gooner
Running in Londinium
A superstar, a Muslim
Cheered by the Whole stadium

አለማቀፋዊ  ሽሙጥ
አልማዝ አያና አንድ ወርቅና አንድ ብር በማሸነፍ በሰሌዳ ደረጃችን ላይ ትልቅ ሚና ተጫውታለች ። አልማዝ ፣ ወርቅ ፣ ብር ደስታዊ ትስስሮሽ በመፍጠሯ ህዝቡ ወስጥ እንቁነት ፈጥራለች ። በበጎ ያዩዋት ሁሉ የአስር ኪሎ ሜትሩን ሩጫ ተአምር ነው ብለዋል ። ለ 11 ወራት ከሩጫ ርቃ ከሶስት አትሌቶች በስተቀር ሁሉንም ደርባ ማሸነፍዋ አጀብ የሚያሰኝ ነው ። የብዙዎቹን አትሌቶች የግል ሰአት እንዲሻሻል ምክንያት መፍጠሯ እና በ 46 ሰከንድ ርቃ ማሸነፏ የውድድሩ ክስተት ነበር ።

የአልማዝ ውጤት ያልተዋጠላቸው ግን ጥቂቶች አልነበሩም ። ለምሳሌ የአውስትራሊያ የሶስት ግዜ ሻምፒዮናና አሰልጣኝ ሊ ትሩፕ አለማቀፉን ፌዴሬሽን በመውቀስ ውድድሩ ቀልድ እንደሆነ ጽፏል ። የስኮትላንድ ረጅም ርቀትና የጎዳና ተወዳዳሪ የነበረችው ኤልሳቤጥ ማኮልገን ውጤቱን እንደማትቀበለው ገልጻለች ። ሌሎችም በድረ ገጻቸው የአልማዝን ተአምረኛ እግሮች እንደሚጠራጠሩት ጽፈዋል ። በሪዮ አኦሎምፒክ ለቀረበላት ተመሳሳይ ጥያቄ የኔ ዶፒንግ ስልጠና እና ፈጣሪ ነው ብትልም ዘንድሮም ሆያሆዬው አልቀረላትም ።








LIZ mccolgan @Lizmccolgan

So from 3k to 8 k Ayana 5 k split 14:30. Until Ethiopia follow proper doping procedures i for one do not accept these athletes performances


Well they might. But I would suggest the issue is broader than simply a country. It's who trains there & how often they're tested OOC? 

Won't she be tested tonight? Why pin the blame on a country then international testing is in place? Does the UK test Mo?
 But you cheer on Farah, who has hidden with Jama Aden several years?

የዚህ ሽሙጥ ፍላጻም ወገንተኛውን ሚዲያ ያጥበረበረው ይመሰለኛል ። በሚዲያ ሽፋን ቦልት እንጂ ጀስቲን ጋትሊን አዲስ ጀግና አልሆነም ። ጀግናውን ሞ ፋራ ላቆመው መሃመድ በቂ ነገር አልተሰራም ።

ሌንሱን ሞ ፋራህና ቦልት ላይ ብቻ አነጣጥሮ ብዙ ሊመረመርና ሊባልበት የሚገባውን የአልማዝ ልዩ ስትራተጂ በዝርዝር መቃኘት አልፈለገም ። ለአዲስና ልዩ ለሆነ ዘዴ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ የሚያከራክረውና የሚያመራምረው አለማቀፍ ሚዲያ እሱም አሽሟጣጭ ካልሆነ በስተቀር ጉዳዩን ችላ የሚልበት መንገድ ግልጽ አይደለም ።

የአልማዝ የ 10ሺህ ሜትር ስልት የእሷ ብቻ ምልክት ነው ወይም ስልታዊ ሪከርድ ነው ። ይህን ልዩ ስልት ሌሎች አትሌቶች እንዴት እውን ማድረግ ይችላሉ ? ነው ይህን ስልት መከተል አዋጭ አይደለም ? በተወዳዳሪነትና ልብ አንጠልጣይንት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽእኖ እንዴት ይታያል ? ምክንያቱም አንድ ሰው ገና ከጠዋቱ ቀድሞ ወጥቶ ማሸነፍ ከቻለ ተመጣጣኝ ውድድር እና አጓጊንት ይኖራል ለማለት ያስቸግራል ። ብዙ ሊጠናበት ግድ ቢልም ሚዲያው ሸውራራነትን መርጧል ። አሰልጣኞች የጉዳዩ ባለቤት ከመሆን ይልቅ ቅንድባቸውን መስቀል ፈልገዋል ።


ድንቄም ... ?! አለ አሽሟጣጭ

No comments:

Post a Comment