Monday, September 24, 2012

የጉራጌ ቁጥሮች



እየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል በተአምራዊነቱና በክርስቲያኖች ዘንድ ከፍተኛ ክብር የተሰጠው በመሆኑ፣ አይሁድ በቅናት ተነሣሥተው ለ300 ዓመታት ያህል በቆሻሻ መጣያ ጥለውት ነበር። ይሁንና በ326ዓ/ የቄሳር ቆስጠንጢኖስ እናት ንግስት እሌኒ ኪራቆስ በተባለ አንድ የታሪክ አዋቂና ሽማግሌ ጠቋሚነት፣ መስቀሉ የተጣለበትን አካባቢ ወቀች ። ከዚያም በኋላ ደመራ ደምራ በእሳት አቀጣጥላ ዕጣን ባጨሰች ጊዜ ፣ የዕጣኑ ጢስ ወደ ላይ ከወጣ በኋላ ተመልሶ ያረፈበትን ሥፍራ አስቆፍራ መስቀሉን አወጣች።
ንግሥተ እሌኒ በጭሱ ምልክትነት፣ መስቀሉን ለማውጣት ለሰባት ወራት ያህል ማስቆፈሯን ማለትም መስከረም 17 ቀን አስጀምራ መጋቢት 10 ቀን እንዳስወጣቸው ይነገራል። ዛሬ በኦርቶዶክስ ምዕመናን ዘንድ ደመራ የሚደመረውም ይህንን ታሪክ ተከትሎ እንደሆነ ሊቃውንቶች ይናገራሉ ፡፡
መስቀል ብዙ ነገር ነው ፡፡ ክርስትያኖች በግጥም ሲገልጹት እንደሚከተሉት ይደረደራል ፡፡

ዕፀ መስቀሉን ያዙ ጋሻ
ሰይጣን እንዲጠፋ እንዲያጣ መድረሻ ፡፡
ዕፀ መስቀለን ተሳለሙ
የአምላክ ቃል አለበት ደመ ማህተሙ ፡፡
መስቀል ኃይል ነው ለክርስቲያን
እሱን የያዘ ሰው አይደፍረውም ሰይጣን ፡፡
መመኪያችን ነው መስቀል
ተቀድሷልና በመለኮት ኃይል ፡፡

መሰቀል በዓል ብዙ ገራሚ ትውፊቶችን በየክልሉ አቅፎ የያዘ ነው ፡፡ የአዲስ አበባው በከተሜው፣ በመዘምራን፣ በሃይማኖት አባቶችና በቱሪስቶች ድብልቅ መንፈስ ተዋህዶ ልዩ ለዛና መስህብ ይፈጥራል ፡፡ በተለይም በደቡብ ክልሎች ያለው የመስቀል ስርዓት ባህላዊ ትውፊቱ እንደ ተራራ የገዘፈ ሀሴትን የሚያጭር ነው ፡፡ ይህ ባህላዊ እሴት በዓመት አንዴ የሚነገርለት እንጂ ሰፊ ምርምር ተካሂዶበት እንደሚታይ ድንቅ ቅርስ በውስጣችን የምንተክለው አልሆነም ፡፡ ዞሮ ዞሮ የጉራጌ ብሄረሰብ የበዓል አከባበርም ዩኔስኮ  እንዲመረምረውና ዕውቅና እንዲሰጠው ከወዲሁ መጠየቅ አስፈላጊ ሳይሆን አይቀርም ፡፡
አነዚህ በመስቀል ሰሞን የሚደምቁት የጉራጌ 13 ቁጥሮች ማለትም 12፣ 13 ፣ 14.፣ ……. 23፣ 24 …. የማይዳሰሱ ሃብቶች እየመሰሉኝ ነው ፡፡  በበዓል አይን ስናያቸው እያንዳንዳቸው የሚያምር የተግባር ዝናር  ታጥቀዋል ፤ ይህን ወረድ ብለን እናየዋለን ፡፡ በሌላ በኩል ግን በዓላዊ  ምሳሌያቸውን በማስፋት ለሌላ የትግል ግዳጅ ማዝመት ይቻላል ፡፡ ለምሳሌ ነው - የብሄራዊ ቡድናችን ተጫዋቾች አነዚህን ቁጥሮች ለምን ለጀርባቸው መጠሪያ አያደርጓቸውም ? ቀንደኛ ግብ አዳኝ ካለን የማሊያ ቁጥሩ ዳመራው በሚቀጣጠልበት ቀን ይሆናል ፡፡ የራቀንን ውጤት በዚህ መልክ ማምጣት ይቻላል ወይስ ለምን ጥቅም አትበሉኝ ፡፡ ለምሳሌ ነው - መስከረምን 12ኛ ወር ብለነው ጻጉሜን 24ኛ ማድረግ ይቻላል ፡፡ እንደ ጻጉሜ ሁሉንም ልዩ ለማድረግ ወይስ ለምን ጥቅም አትበሉኝ ፡፡ ለምሳሌ ነው - ....
መስቀል ለጉራጌ ብሄረሰብም ብዙ ነገር ነው ፡፡
መስቀል ደስታ ነው
መስቀል ትዳር ነው
መስቀል ምርቃት ነው
መስቀል መዝናኛ ነው
መስቀል የቁጥሮች ውበት ነው ፡፡
መስቀል በጉራጌ ሲታሰብ ከ12 እስከ 24 ያሉ ቁጥሮች ምን ያህል የተለቀ ሚና እንደሚጫወቱ ማሰብ ይቻላል ፡፡  ለመሆኑ በነዚህ ሁሉ እንደ ባቡር ፉርጎ የተቀጣጠሉ ቀናት ምን ይደረጋል መባሉ አይቀርም፡፡ እያንዳንዱ ቀን በራሱ በዓል ወይም የበዓል ድጋፍ ሰጪ ነው ፡፡ እስኪ ቀናቱን እየተረጎምን እንውረድ፡፡
መስከረም 12 ፤  የጃፎር መስቀል ይባላል ፡፡
ይህ በዓል በቡድን በመሆን በዛፍ ስር ይከበራል ፡፡ የቡድኑ አባላት መስዋዕት የሚያደርጉትን ከብት ይዘው ዛፉ ስር  የሚገናኙት ከቀኑ አስር ሰአት ላይ ነው ፡፡ የተዘጋጀው በሬ ታርዶ ደሙ ዛፍ ላይ ሲረጭ ሞራውም በእሳት ይቃጠላል ፡፡ የዚህም ምክንያት የሞራው ሽታ አካባቢውን ከበሽታ ነጻ ያደርገዋል የሚል ነው ፡፡ አባላቱ የቻሉትን ያህል ጥሬ ስጋ በልተው ቀሪውን ተከፋፍለው ወደ ቤት ሲያመሩ ዞረው እንዲያዩ አይፈቀድም፡፡ ቦታውን ከለቀቁ በኃላ ይተካል ተብሎ በሚገመተው ኃይል ችግር እንዳይደርስባቸው በመስጋት ፡፡

መስከረም 13 ፤  ወሬት ያህና ወይም እንቅልፍ ነሺ ቀን ይሉታል ፡፡
 በዚህ ቀን እንቅልፍ የሚታጣው ሁሉም ቤተሰብ መስቀልን ‹‹ እንዴት አሳልፈው ይሆን ; ›› ብሎ ስለሚያስብ ነው ፡፡ አንዳንድ     ሰዋች ቀኑን የበዓሉ መክፈቻ ይሉታል ፡፡
መስከረም 14 ፤ ይፍት ወይም የዕርድ ዋዜማ የሚል መጠሪያ አለው ፡፡
ቀን ሴቶቹ የቤቱን ጣራና ግድግዳ ካጸዱ በኃላ መሸት ሲል ለቤቱ ወለል የተሰሩት ምንጣፎች ይነጠፋሉ ፡፡ የቤት ዕቃዋችና        ጌጣጌጦች ግድግዳ ላይ ይሰቀላሉ ፡፡ ቆጮው በተለየ መልኩ በእንፋሎት ብቻ እንዲበስል ይደረጋል ፡፡ ይህም ‹‹ ዳቡዬ ›› በሚል ይታወቃል ፡፡ ይህ አይነት የቆጮ ጋገራ የተመረጠው አማልክት በምግብ ስነ ስርዓት ላይ የሚሳተፉ ባለመሆናቸው ቢያንስ ሽታው እንዲደርሳቸው በማሰብ ነው ፡፡

መስከረም 15 ፤  ወኀምያ ወይም የእርድ በዓል ተብሎ ይጠራል ፡፡
ወኀምያ ደስታና ሰላም ማለት ነው ፡፡ እለቱ በአንዳንድ አካባቢዋች ‹‹ የጨርቆስ ማይ ›› በመባል ይታወቃል ፡፡ ይህ እለት ጨርቆስን ያመለክታል ፡፡ በዚህ ቀን ለእርድ የተዘጋጁ ከብቶች በየቤቱ በራፍ ይታረዳሉ ፡፡ ከበሬው የሚፈሰው ደም በቃጫ ተነክሮ የቤቱ ደጃፍ መቃንና ምሶሶ ይቀባል ፡፡ ከበሬው የተገፈፈው ሞራም እስከ መጪው ዓመት ድረስ የቤት ምሶሶ ላይ ይሰቀላል ፡፡ የማረድ ግዴታ ያለባቸውና የሌለባቸው ሰዋች እንዳሉም መታወቅ አለበት ፡፡  የማረድ ልምድ ያለባቸው ሰዋች የወሸምያ ዕለት ካላረዱ ወሸምያ ይገድላቸዋል ተብሎ ይታመናል ፡፡ በየዓመቱ ከሚያርዱበት የተወሰነ ቦታ ፈቀቅ ለማለት እንኳን አይሞክሩም ፡፡ ልማድ የሌላቸው ሰዋች ግን ስጋም ገዝተው በዓሉን ማክበር ይችላሉ ፡፡

የማረድ ልማድ ያለባቸው ልምዱን ለመሰረዝ ከፈለጉ የሚከተለውን ህግጋት ተግባራዊ ማድረግ አለባቸው ፡፡ በየአመቱ በሬ የሚያርድ ሰው በቀጣዩ ዓመት ጥጃ ያርዳል፡፡ በሁለተኛው ዓመት ፍየል ያርዳል ፡፡ በሶስተኛው ዓመትም ፍየል ያርዳል ፡፡ በአራተኛው ዓመት ዶሮ አርዶ በአምስተኛው ዓመት ምንም ባያርድ ወሽምያ ስለሚረሳ ችግር አይመጣበትም ፡፡ አሪፍ የማካካሻ ስልት ናት ፡፡

መስከረም 16፤   ምግይር ወይም ደመራ ነው ፡፡
ደመራው በየቤቱ ደጃፍ የሚተከለው የልጆች ደመራና የአባቶች ደመራ ተብሎ ይታወቃል ፡፡ በየበራፉ የሚተከለውን ደመራ ጠዋት ወይም ማታ ማቀጣጠል ይቻላል ፡፡ የአባቶች ደመራ የሚለኮሰው ግን ከምሽቱ አንድ ሰዓት ጀምሮ ነው ፡፡ በዚሁ ግዜ አባ ተዘር / ክረምትና በጋ / የተባለውን ጨዋታ ልጆች ይጫወታሉ ፡፡ በደመራ እለትም ሆነ በሌሎች የመስቀል ቀናት ከብቶች ውጪ አይወጡም ፡፡ የተዘጋጀላቸውን ምግብ ከቤት ይበላሉ ፤ አይታለቡም ፡፡

መስከረም 17፤    ንቅባር ወይም ትልቁ በዓል ይባላል ፡፡
በዚህ ቀን ቤተዘመዶች ፣ በቡና የሚገናኙ ጎረቤቶች ተሰብስበው ደስታቸውን ይገልጻሉ ፡፡ አዛውንቶች አናታቸው ላይ ቅቤ ይደረግላቸዋል ፡፡  የከብቱ ሻኛም የሚበላው በዚህ ቀን ነው ፡፡ አንድ ሰው እናት ፣ አባት፣ ታላቅ ወንድም ወይም አያቱ እያለ የመስቀል ሻኛን ለብቻ አይበላም ፡፡ ዘመድ ከሌለው እንኳን በእድሜ የገፉ አዛውንቶች ጋ ይዞ በመሄድ ማስመረቅ ይኖርበታል ፡፡ ይሄ ሁሉ ለሻኛ  ; ካላችሁ ሻኛ በሰባት ቤት ጉራጌ የበስር ንጉስ ወይም የስጋ ንጉስ መባሉን ማወቅ ያስፈልጋል ፡፡

መስከረም 19- 23 ፤   የጀወጀ ወይም የመተያያ ቀን ይባላል ፡፡ ከመስከረም 18 በኃላ ያሉትን ቀናት የሚያመለክት ሲሆን ለአንድ
ሳምንት ያህል ባሉት ቀናት ባልና ሚስት ወገኖቻቸውን በተለይም እናት አባቶቻቸውን ስጦታ በመያዝ የሚጠይቁበት ነው ፡፡    የሙየቶቸም ጭፈራ ይከናወናል ፡፡ ሙየት ማለት በእናቶችና ሴቶች የሚዘፈን ባህላዊ ጨዋታ ነው ፡፡
ዘመዳሞች ይጠያየቃሉ፣ ይመራረቃሉ ፡፡

መስከረም 24 ፤   አዳብና ወይም መሰነባበቻ በሚል መጠሪያ ይታወቃል ፡፡ በአንዳንድ በተ ጉራጌዋች ዘንድ ከጀወጀ በተለየ መልኩ አሁንም
                   ድረስ በድምቀቱ  የሚታወቅ ሲሆን ለወጣቶችና ልጃገረዶች የተለየ የጭፈራ አጋጣሚ ነው ፡፡ ጭፈራው ከመስከረም
                    አጋማሽ ጀምሮ  ጥቅምት ድረስ ይዘልቃል ፡፡ የአዳብና ጭፈራ በገበያዋች ላይ የሚከወን ሲሆን ድንቅ ባህላዊ አልባሳትና
                   የውዝዋዜ  ትዕይንቶች ይታዩበታል ፡፡ በነገራችን ላይ ‹ መንጠየ › የቋንጣ ክትፎ የሚበላበት የመጨረሻ ስነ ስርዓት ማሳረጊያ
                    ነው ፡፡ ይህ በዓል በአንዳንድ አካባቢዋች እስከ ጥቅምት 5 ሊቆይ ይችላል ፡፡




No comments:

Post a Comment