Tuesday, July 4, 2017

እየመጣ ያለው አስቀያሚ ስያሜ



ፊንፊኔ ስላሽ አዲስ አበባ
አዲስ አበባ ወይም ፊንፊኔ
ፊንፊኔ እና አዲስ አበባ 
አዲ ሃይፈን ፊን
ፊን ነጥብ አዲ
አ ወይም ፊ

የቱ ነው እየመጣ ያለው የከተማችን መጠሪያ ? የቱ ነው እውነቱ ? የሚያስከትለው ውጤትስ ? ታዋቂው አሜሪካዊ ጋዜጠኛ ራልፍ ኤድዋርድ Truth and Consequences እንዲል ። ይህን Truth and Consequences የተባለውን የNBC ቴሌቪዥን ፕሮግራም የመመልከት እድል ያጋጠመው ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮችን ይገነዘባል ። እውነትን ማወቅ ስጋት ማራገፊያ መሆኑንና እውነታን መሳት ካልታሰበ ችግር ጋ የሚያላትም መሆኑን ።

የፕሮግራሙ ፈጣሪ ራልፍ ኤድዋርድ ከተመልካች ውስጥ የተወሰኑትን መድረክ ላይ በማቅረብ ነው ጥያቄውን የሚያቀርበው ። የጥያቄውን ምላሽ ያገኘ ነጻ ይወጣል ። እውነታውን የሳተ ግን በቀጣይ የሚቀርብለትን አስደናቂ ወይም አስቸጋሪ ወይም አሳፋሪ ትርዒት የማቅረብ ግዴታ አለበት ። ትርዒቱ ከአቅሙ በላይ ሊሆንይችላል ፣ ቢሆንም ከድርጊቱ ጋር መጋፈጥ አለበት ። ለምሳሌ ያህል አንድ ወቅት ያየሁት ተጠያቂው ባለ አንድ ጎማ ብስክሊት እንዲያሽከረክር ታዞ ነበር ። ሰውየውን እንደምንም ብለው የሳይክሉ ረጅም ወንበር ላይ ሰቀሉት ። ታዲያ ምን ያደርጋል ላይ ተንጠልጥሎ ራሱን ባላንስ ማድረግ አልቻለም ። እናም ፔዳሉን ወደፊትና ወደኋላ ከማባበል ይልቅ በሃይልና በድንጋጤ ሲንጠው ቀጥታ ወደ ተመልካቹ ተፈተለከ - ህዝቡ መሃል እንደ ቲማቲም ፈርጦ ክፉ የሽብር ተግባር ይፈጽማል ብዬ ስጠብቅ አምላክ ረድቶት አንድ ጥግ ምናምን ይዞ ዳነ ።  በሰውየው ድንጋጤና ያልተገራ ጥበብ ብዙ ሰአት እንደሳቅኩ አስታውሳለሁ ።

የዚህ ፕሮግራም አዘጋጅ ከመድረክ ኩምኩና በተጨማሪም ለአለማችን አስቂኝ የከተማ ስም በመፍጠርም ይታወቃል ። ነገሩ እንዲህ ነው ። በ1940 የተጀመረውን Truth and Consequences አስረኛ አመት ለማክበር በአዘጋጁ በኩል አንድ ጥሪ ይተላለፋል ። የከተማውን ስያሜ በፕሮግራሙ መጠሪያ ለሚቀይር ዝግጅቱ በቀጥታ ከከተማው እንዲተላለፍ ይደረጋል የሚል ። ይሄኔ የ < Hot Spring > ነዋሪዎች ፍቃደኝነታቸውን ይገልጻሉ ። ከተማዋ የበርካታ የተፈጥሮ ሙቅ ውሃ ባለቤት ናት ። እናም በመጋቢት 1 ቀን 1950 ዓም ህዝበ ውሳኔ ያከናውናሉ ።  295 ሰዎች ይህን እብደት አንደማይቀበሉ ሲገልጹ  1294 ያህሉ ግን ስማችን እንዲቀየር እንፈልጋለን አሉ ። በቀጣዩ ቀን ማለትም ሚያዚያ 1 1950 ፕሮግራሙ ከከተማዋ ተላለፈ - የከተማዋ አዲሱ መጠሪያም Truth or Consequences ሆነ ።

ይህ ስም በአለማችን ካሉት ረጅም እና ቀፋፊ ስሞች መካከል እንደ አንደኛው ሊቆጠር  የሚችል ነው ። የTruth or Consequences ከተማ ነዋሪዎች ይህ ቀፋፊ ስም እንዴት ከእናንተ ተግባር ጋር ይገናኛል ሲባሉ የሚከተለውን ሽፍንፍን ያለ ምላሽ ይሰጣሉ  « እውነታው / Truth /  በከተማችን ጤና ሰጪ ፍልውሃዎች ያለን መሆኑ ነው ፣ ይህ ያስከተለው ውጤት/ Consequences /  ከተባለ ደግሞ ሰዎች ተጠቃሚ መሆናቸው ነው » የሚል ነዋሪዎቹ ዛሬ ዛሬ በረጅሙ ስያሜ በመዳከማቸው  ቲ ኦር ሲ ወደሚል ምህፃረ ቃል ወርደዋል ።

ምናልባትም ሁለተኛው ረጅም እና ቀፋፊ ስም የአዲስ አበባው ፊንፊኔ ጥምረት ሊሆን ይችላል ። በህግ ፊት እኩል የመቆም መብት የተሰጣቸው አዲስ አበባና ፊንፊኔ በሚያስከትለው ውጤት / Consequences / ብዙ ሊፋተጉ ይችላሉ ተብሎ የተሰላ ይመስላል ። አዲስ አበባ ይቅደም ፊንፊኔ ? አቀማመጡ እና ጥምረቱስ ? በወይም ይቆለፍ ወይስ በ እና ሰረገላ ? በስላሽ ድንበር ያብጁ ወይስ  የዶት ታኮ ይሰራላቸው ?

ምፀታዊ ዋጋው የአዲስ አበባ ህዝብ መሰረታዊ ለውጥ በሚያመጣው በዚሁ ጉዳይ ሀሳብህ ምንድነው ተብሎ አለመጠየቁ ነው ። ስሙን በማስረዘሙ ልዩ ጥቅም ያገኛል ? የውሃ ፣ መብራት ፣ ስልክ ፣ ስራ እና የዋጋ ንረት ሰቆቃው በፊንፊኔ ስላሽ አዲስ አበባ ገመድ ይጠፈነጋል ? ከአንድ ወደ ሁለት ቃላት ያደረገውን ድንገተኛ ሽግግር ተመችቶት ይቀበለዋል ፣ ህጋዊና ስነልቦናዊ ግዴታስ አለበት ? ነው መንግስት ካለ አለ ነው- ተከተል አለቃህን አክብር አርማህን እንዲሉ ። ከቅርብ ግዜያት የፖለቲካ ተሞክሯችን ስንነሳ ግን በንግግርና መግባባት ላይ ያልተመሰረተ ውሳኔ ያልታሰበ ውጤት ለማስከተል ምንም የሚያግደው ነገር የለም ። በመሆኑም  የኦሮሞ ተወላጆች ፊንፊኔ ሲሉ የተቀሩት ደግሞ በአዲስ አበባ እንዲፀኑ መንገድ ይከፍታል  ። በአንድ ከተማ ሶስት ስያሜ መሆኑ ነው ።

ይህም ወደ ሌላ አላስፈላጊ ውጤት ይመራል ። ወደ ይዞታ ጉዳይ ። ከተማዋ ለእኛ ነው የምትገባው ወደሚለው  የኦሮሞ - አማራ ጭቅጭቅ ። በርግጥ ማነው ቀደምቱ ? ከአዲስ አበባ በፊት ፊንፊኔ ነበር ... ስለዚህ ከተማዋ የኛ ናት ፣ እናንተ እንግዶቹ በኛ ስር ልታድሩ ግድ ነው ይልሃል አንደኛው ጠርዝ ... ከፊንፊኔ በፊትስ እነማን በምን ስም ነበሩ ?... ኦሮሞዎቹስ ከየትና እንዴት መጥተው በሀገሪቱ ተስፋፉ ይልሃል ሌላኛው ጠርዝ   ። ጭቅጭቁና እንካሰላንቲያው በተዋረድ በሰፈርና አደባባይ ስሞች ግዘፍ ነስቶ ይመጣል ። ለመንገድ ስያሜ ከተሜው ግድ ላይኖረው ይችላል ። ግድ የሚሰጠው ግን እንደ ማተቡ ውስጡ የቆየውን የሰፈር ስያሜ ቀይር አትቀይር የሚል ሙግት ከተከተለ ነው ። መንግስት በቀጭን ትዕዛዝ አስራለሁ ቢል እንኳን ጥቁር ገበያው አይሎ ኢ- መደበኛው ኮሙኑኬሽን እንደሚልቅ አያጠራጠም ።

የአዲስ አበባን ደም መርምሮ ሁነኛ ብይን ማግኘት አይቻልም ። የደም ምርመራው ኦ ኔጌቲቭ ፣ ኦ ፖዘቲቭ ፣ ኤ ኔጌቲቭ ፣ ኤ ፖዘቲቭ ፣ ቢ ኔጌቲቭ ፣ ቢ ፖዘቲቭ ፣ ኤቢ ኔጌቲቭ እና ኤቢ ፖዘቲቭ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም ። ይህ የሚያሳየው ደግሞ አዲስ አበባ ከኦሮሞም ከአማራም በላይ መሆኗ ነው ። ከተማዋ የሁሉም ብሄር ብሄረሰቦች ሃብት ናት ። የኢትዮጽያዊነት አሻራ ወይም ቅጂ ናት ። የአፍሪካዊነት መሰረት የዝማሬያቸውም  ሰንደቅ ናት ።

ከመቶ አመታት በላይ የዘመናዊ  አስተዳደር ጽንሰ ሃሳብን ስትገነባ የመጣችን ከተማ በምን ተአምር የብሄር ካፖርት ማልበስ ይቻላል ? የዘመናዊነት ትርፉ እኮ ትላልቅ ፎቆችንና ዘመናዊ ባቡሮችን ማስገኘት ብቻ አይደለም ። ዘመናዊነት ከሁሉም በላይ አስተሳሰባዊ ዝመናን ይመለከታል ። የከተማው ህዝብ ኑሮ አጉብጦት ይሆናል እንጂ በአስተሳሰቡ ሸንቃጣ ነው ። ብዙ ትርፍና ተቀማጭም ሀብት አለው - የገንዝብ ሳይሆን  የማመዛዘን ፣ የመቻቻልና የፈሪሃ እግዚአብሄርነት ። በዚህ መሰል ችግር ወቅት እየመነዘረ የሚያካፍለው ። የማይናድ ልዩ ጥቅም አለው ከተባለ ይኸው  ነው ።

 ግራም ነፈስ ቀኝ የአዲስ አበባን እውነታ አብጠርጥሮ ማወቅ ካልተቻለ የሚያስከትለው ውጤት ከባድ ሊሆን ይችላል ።


No comments:

Post a Comment