Monday, July 15, 2013

‎መቼ ነው የሀገራችን መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ የማይሆነው ?‎



ሞጆ ---- ሰኔ 2005 . ፡፡

የምሽት ጉዞ ክልከላን የናቀ ወይም ያልተቀበለ ሾፌር እንደሚግ እየተወረወረ መንገድ ላይ ከቆመ ትልቅ መኪና ጋር ተላተመ ፡፡ በተአምርና በተለየ ብልጠት ካልሆነ በስተቀር አንድ ሚዳቆ ዝሆንን ገፍታ ከቦታው ታርቃለች ማለት ይከብዳል ፡፡

የሆነው ግን ይኀው ነው ፡፡

ከዝዋይ ወደ አዲስ አበባ የሚፈተለከው ዶልፊን ሚኒባስ ተበላሽቶ የቆመውን ትልቁን ማርቼድስ ከነበረበት 50 ሜትር ርቀት አፈናጠረው ፡፡ ወደ ገደላማ ቦታም ሰደደው ፡፡ ሀገር ሰላም ብለው መኪና ውስጥ የተኙ ሰዎች ከለሊቱ አስር ሰዓት መኪናው ሲንቀሳቀስ በእንቅልፍ ልባቸው ወደ አንድ ጋራዥ እየተጓዙ ቢመስላቸው አያስገርምም ፡፡ ነቅተው ያሉበትን ሲረዱ ግን በታላቅ ድንጋጤና ሽብር ተርበተበቱ ፡፡ ከአደጋው መትረፋቸውን ሲያረጋግጡም ስሜታቸው ተዘበራረቀ - ደስታና ፍርሃት ፡፡

ወዲህ  22 ሰዎችን የጫነው ሚኒባስ አንድ ከዝሆን የተሰራ ሰው እንደ 4 ጨምድዶ ወደ ቅርጫት የወረወረው ወረቀት መስሏል ፡፡ ጭምድዱ በቁርጥራጭ የሰው ልጆች ስጋና አጥንት የተሞላ ቢሆንም መጠኑን አላሳደገውም ፡፡ ያለቅጥ ተደራርበው ከተጫኑት 22 ተሳፋሪዎች መካከል ሹፌሩን ጨምሮ 16 ንጹሃን ነፍስ በምሽቱ ተቀጠፈ ፡፡ የሀገራችን መኪና አደጋ ከዚህም በላይ ቁጥር በማስመዝገብ የሚታወቅ ቢሆንም የአሟሟቱ ሰቅጣጭነት ግን ከእስከዛሬው ሁሉ ይጎፈንናል ፡፡ የሰው ልጅ አንገት እዚህና እዚያ እንደ ጎልፍ ኳስ በሯል ፡፡ አካል ከዶሮ በቀጠነ መልኩ በግድ ተበልቷል ብቻ ሳይሆን ለመልቀም በሚያስቸግር መልኩ ተጨፈላልቋል ፡፡ ‹‹ የዉሃ ያለህ ! ›› በሚባልበት ሀገር ደም ያለ ቆጣሪ ፈሷል ፡፡

አለልቱ --- 1999 ፡፡

ከወደ ላይ የጣለው ዝናብ ጎርፍ ወልዶ የመኪና መንገድ ላይ ይደነፋል ፡፡ አንድ የቀይ መስቀል አምቡላንስ ለስራ ተጣድፎ ሳይሆን አይቀርም ጎርፉን ገፍቶ ለማለፍ ሲሞክር ወደ ወንዙ ይወድቃል ፡፡ ይህ ሲሆን በርካታ ሰዎችን የጫነ የህዝብ ማመላለሻ አውቶብስ ከኃላ ይመለከታል ፡፡ ሞተሩን በደንብ ኮርኩሮ ወደፊት ተንቀሳቀሰ ፡፡ ‹‹ እባክህ አትዳፈር ! ጥቂት ትዕግስት ይኑርህ ! ›› የሚሉ ድምጾችን ለማስተናገድ ፈቃደኛ አልሆነም ፡፡ ጎርፉን በጭንቅላቱ ሳይሆን በመኪናው ትልቅነት የመዘነው ሾፌር በማታውቁት ጥልቅ አትበሉ / በሆዱ ነው / በሚል እሳቤ ከባላጋራው ጋር ግብግብ ገጠመ ፡፡ ጥሶት ሊወጣ ተንፈራገጠበንዴት ጓጎረጎርፉ ግን እያስጮኀውም እያሳሳቀውም ገለበጠው ፡፡ የበርካታ ንጽሀን ነፍስም ለሰሚ በሚከብድ መልኩ በጎርፉ ተቀረጠፈ ፡፡

በጣም ትዝ ይለኛል ትራፊክ ፖሊስ ‹‹ ቸልተኛና ሃላፊነት የማይሰማው ! ›› በማለት ነበር ሾፌሩን ያወገዘው ፡፡ ይህ አይነቱ ወቀሳና ስያሜ በሀገራችን ዕድሜ ጠገብ ቢሆንም ዛሬም ሰንሰለቱ መጠናከሩን እንጂ ያለመበጠሱን የሞጆና አለልቱ ታሪኮች ያመላክታሉ ፡፡ የሞጆው አደጋ በተከሰተ በሶስተኛው ቀን በሱሉልታ ሚኒባስ 13 ሰዎችን ጨርሷል ፡፡ ጊዮርጊስ ከሀዋሳ ከነማ ለነበረበት ጨዋታ ወደ ሀዋሳ ሲጓዙ መቂ ከተማ ላይ መኪናው በመገልበጡ ሁለት ደጋፊዎች ሲሞቱ ሁለቱ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል ፡፡ በአዲስ አበባ በየቀኑ የትራፊክ አደጋ ከነሞቱ ፣ጉዳቱ እና የንብረት ውድመቱ ተመዝግቦ ለጆሮአችን እንደ ቁርስ ይቀርባል ፡፡ በቅርቡ ወደ ጎንደር ሁመራ ቋራና ጅጅጋ ለስራ አቅንቼ ነበር ፡፡ በሁሉም መስመሮች በጣም በተቀራረበ ርቀት በሚያሳዝንና በሚሰቀጥጥ መልኩ ከቤት መኪና እስከ ተሳቢዎች በየመንገዱ ተጨማደውና እግራቸውን ሽቅብ ሰቅለው በየገደሉ ‹ ዳይቭ › ጠልቀው ተመልክቼያለሁ ፡፡ ብዙዎቹ ሞተዋል፣ ለአካል ጉዳት ተዳርገዋል ሀብት ወድሟል ፡፡

ያስደነግጣል ፡፡

ወዴት እየሄድን እንደሆነ በቅጡ አልተፈተሸም ፡፡ ከጠጡ አይንዱ ፣ ከነዱ አይጠጡ የሚለው የዘወትር ምክር ከመልዕክቱ ይልቅ ጥቅስነቱ ያሸበረቀ መስሏል ፡፡ አደጋውን የሚያስገነዝቡ የነሞገስ ተካና መሰል ድምጻዊያን ዘፈን ከእንጉርጉሮነት ለምን አላለፉም ? ከፕሮግራም ማዳመቂያነት ወይም የአየር ሰዓት መሙያነት ለምን አልተሻገረም ? … በጫት ምርቃና ፣ እጅን ከመሪና ማርሽ ይልቅ ለሞባይል በማዋል ፣ በአጉል ጀብደኝነት ፣ ያለ በቂ ችሎታ በማሽከርከር ፣ አይን የመንገድ እንቅስቃሴን ከመቆጣጠር ይልቅ የሴት ዳሌ ላይ እንዲያሸልብ በመፍቀድ ፣ ከፍጥነት በላይ በመሮጥ ፣ ተሸከርካሪን መንጃ ፍቃድ ለሌለው ሰው አሳልፎ በመስጠት ወዘተ … የሚሉ ምክንያቶች የሞታችን መንስኤ ከመሆን መቼ ያቆማሉ ?

እኛና ወዘተ የተባለው ነገር የተጋመድንበት ሰንሰለት ያስገርማል ፡፡

ማለት ፈረንጅ ሲባል ሁልግዜ መኪና ይፈበርካል ፤ አበሻ ሲሆን ሁልግዜ በመኪና ሰውና እንስሳትን ይገድላል ሊሆን ነው ፡፡ ለነገሩ ወደ ሀገራችን  ብቅ የሚለው የውጭ ዜጋ ልክ እንደ ቪዛው ‹‹ ኢትዮጽያ  ውስጥ አትንዳ ! የግድ ሲሆን እንጂ ከመሳፈር ይልቅ እግርህን እመን ! መስቀለኛ መንገድ ላይ ስትሻገር እንኳ የቆሙ መኪናዎችን ተገላመጥ ! ›› የሚል የቃል ይለፍ መቀበሉም ይረጋገጣል ይባላል ፡፡ ይህን ምጸት ተራ የሀገሬ ሰውም ገና ድሮ ‹‹ መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ ! ›› በማለት አጠናክሮት እንደነበር አይዘነጋም ፡፡ የተማረውና ምርምር አድርጌበታለሁ የሚለው ከረቫት ለባሽ ደግሞ ‹‹ በተሸከርካሪ አደጋ ሶስተኛ ደረጃ ላይ እንገኛለን ›› በማለት በየስብሰባው ከጣፋጭ ኩኪስ ጋር እንድናወራርደው ያደርጋል ፡፡

እነዚህ ሁሉ ምጸቶች ምን ያሳዩናል ? የሚከተሉትን ምርጫዎች በጥሞና በማንበብ ትክክለኛውን ምላሽ ለአፍታ ያንሰላስሉ ?

ሀ . ትላልቅ መኪናዎች ትላልቅ እቃዎች ለማጓጓዝ በእጅጉ ጠቃሚ የመሆናቸውን ያህል ትላልቅ በሬዎችንና ግመሎችን መጨፍለቃቸው የሚጠበቅ ነው ፡፡
ለ . ትንሽ በማይባሉ ትራፊክ ፖሊሶች ባሉበት ሀገር በጠራራ ጸሃይ ህጻናትን እንደ ሰርዲን አጭቀው የሚሮጡ ታክሲዎች ሲፈልጉ እንዲሞቱ ይፈርዱባቸዋል ፡፡
ሐ . ሾፌሮች ፍሬን አልታዘዝ ሲላቸው  ከስልክ እንጨት ፣ ከድንጋይ አጥር ወዘተ ጋር ከማጋጨት ይልቅ ቤት ደርምሰው የሚገቡት ‹‹ ዞሮ ዞሮ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት ›› ለሚለው ጥቅስ ከፍተኛ አክብሮት ስላላቸው ነው ፡፡
መ . ቶራ ቦራ ተራራን የሚወደው አልቃይዳ እና አይሱዙዎች የሚያመሳስላቸው ራሳቸውንም ሌሎችንም ለማጥፋት ወደ ኃላ የማይሉ በመሆናቸው ነው ፡፡

ምርጫዎቹ በመኪናዎቹ አይነቶች ላይ ያነጣጠሩ ይምሰል እንጂ በውስጡ ተአምረኛው ወይም ምንተስኖት ሊባል የሚችለው ‹‹ አበሻ ›› መኖሩ ይታወቃል ፡፡ ‹‹ ምንተስኖት ›› በሞት ፍቃዱ አሰጣጥ ላይ ሳይታወቀው ድጋፍ የሚሰጥበት ሁኔታም ይታያል ፡፡

አይሱዙን እናንሳ ፡፡

የእነዚህን መኪናዎች ስያሜ ‹‹ አልቃይዳ ›› በማለት ዳቦ ቆርሷል ፡፡ መኪናዎቹ ለመገልበጥ ሾፌሮቹ ደግሞ ለመጋጨት ቅርብና ዝግጁ በመሆናቸው ነው ስያሜውን ያወጣው ፡፡ ህብረተሰቡ ሌላው ቢቀር መንጃ ፍቃድና የእቁብ ገንዘብ ለመጠየቅ ወደ ኃላ የማይለው ትራፊክ ፖሊስ እውቅና የሰጠውን ይህን ስያሜ እነሱም በደስታ መቀበላቸው ማስገረሙ አይቀርም ፡፡ የማይቃወመው ፣ የሚያጨበጭበውና አንዳንዴም የሚያሸልበው  የሀገራችን ፓርላማ  ‹‹ አሸባሪ ›› ብሎ ስማቸውን በአዋጅ ካሰፈረው ድርጅቶች መካከል ‹‹ አልቃይዳ ›› አንዱ መሆኑን ቢሰሙ እንኳ ደንታ የላቸውም ፡፡

 
ዛሬም በከተማም ሆነ በገጠር  እንደ ጄት ሲሮጡ ፖሊሱ ፣ መንገደኛውም ሆነ መኪናው ዳር ይዞ ያሳልፋቸዋል ፡፡ እኛ ለእኩይ ተግባራቸው የእውቅና ዲፕሎማ መስጠታችን እነሱ ደግሞ ይሄንኑ ሆይ ሆይታና ሳያገናዝቡ በአስፈሪ ተግባራቸው መቀጠላቸውን ቆም ብሎ ለመረመረ ገረሜታን ሳይጭር አይቀርም ፡፡ ለመሆኑ በሀገራችን መኪና የሚነዳው ለምን ዓላማ ነው ? አሽከርካሪና ተሸከርካሪ ማለትስ ? … ልብ ብላችሁ ካሰባችሁ መኪናው ያለተግባሩ የ ‹‹ ጥይት ›› ን ቦታ ተክቶ እየሰራ ነው ፡፡ አሽከርካሪው ደግሞ ቃታ ሳቢ ወታደር … እና ነገሩ እንደዚህ የሚታሰብ ከሆነ ሰላማዊ ሰዎች ከተባራሪ ወይም ደግሞ ከአባራሪ ጥይት ራሳቸውን ለማዳን በየትኛው መንገድ ይሂዱ ? ..

ለነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ትልቁን ድርሻ የሚወስደው መንግስት መሆኑ አያጠያይቅም ፡፡ መንግስት አደጋውን ለመቀነስ ለሾፌሮች ሰፊ የቀለምና የተግባር ትምህርት እሰጣለሁ በማለት አሰራሩን ከዘረጋ ቆየ ፡፡ አሰራሩ ስልጡን መሆኑን ለመግለጽ ‹‹ ሁለተኛ መንጃ ፍቃድ ያለው ስልጠናውን እስከወሰደ ድረስ በአንድ ዝላይ ባለአምስተኛ ከመሆን የሚያግደው የለም ! ›› በማለት በመግለጫ ተቀናጣ ፡፡ ይህ አሰራር ግን በየቦታው በስፋት እየታጨደ ያለውን ሞት ለማስቆምና ለህይወት ሁነኛ ዋስትና ለመስጠት ቃል አልገባም ፡፡ ይህ አሰራር እንደምንጠብቀው ምጡቅ ሾፌሮችን ለማምረቱ ልበ ሙሉ መስካሪዎች አላደረገንም ፡፡ ይህ አሰራር ዛሬም መንጃ ፍቃድ ቤት ድረስ በአፋጣኝ መልዕክት ከመድረሱ እንዲቆጠብ ዘብ አልቆመም ፡፡ በዚህ ሳይንሳዊ አሰራር መሰረት የኢትዮጽያ በመኪና የመሞት ሰቆቃ ቢያንስ እንደ እግር ኳሱ ጥቂት ደረጃዎችን ማሻሻል አልቻለም ፡፡ 
ምናልባትም ብሶበታል ፡፡

ታዲያ ምንድነው ዲስኩሩ ?
 ምንድነው ጥሩንባው ?
በየመንገዱ የሚወድቀውን ንጽሃን ቅበሩ ነው ?
መቼስ ነው የሀገራችን መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ ላለመሆኑ የተኛው ፓርላማ በነጋሪት ላይ የሚነግረን ?
‹‹ የአመለካከት ችግር ሲቀየር ነው  ›› --- እኮ የማ ?



No comments:

Post a Comment