Monday, September 23, 2013

በፍተሻዎቻችንን እንሳቅ ወይስ እንዘን ?!





በቅርቡ የሶማሌ ክልል ርዕሰ ከተማ ወደሆነችው ጅጅጋ ለስራ አቅንቼ ነበር ፡፡ ከሞላ ጎደል ከተማዋን ከዚህ በፊት የማውቃት በደራ የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴዋ ፣ ርዕሰ ብሄርን እንደ ሸሚዝ በመቀያየርዋ ፣ በአቧራ አፍቃሪነቷ ፣ በነዋሪዎቿ የእኩል ተናጋሪነትና የእኩል አዳማጭነት ጥበባቸው ነበር ፡፡ አሁን አንድ የጥበቃ ስርዓት ጨምራ አገኘኃት ፡፡ ከተማዋ ሰላም ብትሆንም በየቡናቤቱ ፣ ሆቴሎች ፣ የምሽት ክለቦችና ሌሎች ተቋማት በር ላይ ዩኒፎርም የለበሱ ወንድና ሴት ጥበቃዎች ተሰይመዋል ፡፡ 

በክልሉ የሚገኙ አንዳንድ ታጣቂዎች ወደ መንግስት ስርዓት መቀላቀላቸውን በመገናኛ ብዙሃን የሰማን ቢሆንም በሰላም ሀገር ጥበቃን የማብዛት ጉዳይ እንቆቅልሽ ይፈጥራል ፡፡ በርግጥም ታጣቂዎች ሳይታሰብ በሆቴሎችና በአንዳንድ ቦታዎች ቦንብን እንደቀልድ ጣል ያደርጋሉ ነው የተባለው ፡፡ የሶማሌ ባለስልጣናት ደግሞ ከቢሮ በአጃቢዎች ወጥተው ሆቴል በረንዳ ላይ መወያያት  ይወዳሉ ፡፡ የምዕራባዊያን ዘይቤ ይመስላል ፡፡ አጃቢዎቹ የሰጉ ዕለት ታዲያ በሆቴሉ ውስጥ የሚዝናናውን ሰው እየገፈተሩ በማስወጣት ፊትና ጀርባ ሆነው ኤኬያቸውን ይወድራሉ ፡፡

ይህን መሰረት አድርጎ ምድረ ቡናቤትና ሆቴሎች በር ላይ ጥበቃዎቹን ማሳየት ይኖርባቸዋል ፡፡ በጣም የሚገርመው ጥበቃዎቹ ወንበር ላይ ቁጭ አሉ እንጂ ተጠቃሚውን አይፈትሹም ፡፡ ጥቂት ወገብዋ የሚዳሰሰው ማታ ላይ አንድ ሁለት ለመቀማመስ ቡና ቤት ጎራ ሲሉ ነው ፡፡ የጥበቃዎቹን ብዛት ያየ እንኳን ጥቂት ነገር ፈላጊ ታጣቂዎች ሌላ ወራሪ ኃይል ቢመጣ ድባቅ ተመቶ የሚመለስ ነው የሚመስለው ፡፡ ይሄ ሁሉ ሰው በአግባቡ ስራውን የማይሰራ ከሆነ የክልሉ መንግስት ዋና ዓላማ ወጣቱን አደራጅቶ ስራ ማስያዝ ነው ማለት ነው ፡፡ ዘርፉን በጥቃቅንና አነስተኛ ጥላ ስር እንደ ኮብልስቶን ወይም ዶሮ እርባታ የሚዋቀር ንዑስ ዘርፍ አድርገን ልንመለከት እንችላለን ፡፡ መላምታችንን በአቋም መግለጫ ስናጠቃልለው ግን ‹‹ የሶማሌ ፍተሻ - ፈታሹ በሽበሽ ፍተሻው ትንሽ ›› ከሚል መፈክር ጋ ሊሆን ነው ፡፡

ለነገሩ በርካታ መስሪያ ቤቶች በር ላይ ‹‹ ለፍተሻ ተባበሩ ! ›› ወይም ‹‹ ለጋራ ደህንነታችን ሲባል ሁላችንም እንፈተሸ ! ›› የሚሉ መፈክሮችን ተውበው ማየት የተለመደ ነው ፡፡ በመርህ ደረጃ ትክክለኛና ብዙዎቻችንን የሚያግባቡ ናቸው ፡፡ ከተግባር አኳያ ሲፈተሹ ግን የፍተሻ እንከኖቻችን ቆጥረን ለመዝለቅ ያስቸግረናል ፡፡ አንድ ሁለት ማሳያዎችን እያነሳን እናውጋ ፡፡

የሚያስቁ ፍተሻዎች

ጠመንጃቸውን ግድግዳ እያስደገፉ እንግዶችን የሚፈትሹ ጥበቃዎች አላጋጠሟችሁም ?  እነዚህ በእነሱ ቤት መሳሪያቸውን ለግድግዳ የሚያስረክቡት ማንንም ስለማያምኑ ነው ፡፡ ‹ ጠርጥር ገንፎ ውስጥ አይጠፋም ስንጥር › በተሰኘው መርሃቸው እንግዶችን የሚፈትሹ ቢሆንም ከእንግዶቹ አንዱ ዞር ብሎ በቀላሉ መሳሪያዬን ይቀማል ብለው ግን በፍጹም አይጠራጠሩም ፡፡ በተቃራኒው መሳሪያቸውን በእንግዶች እጅ ላይ በማስደገፍ ፍተሻቸውን የሚያቀላጥፉ አይኖሩም ማለት አይቻልም ፡፡ እነዚህ ደግሞ ሰው አማኞች መሆናቸው ነው  ‹ እንግዳ እዚህ የሚመጣው ጉዳዩን ሊተኩስ እንጂ መሳሪያ ሊተኩስ አይደለም › በማለት ፡፡

በዚህም ምድብ ሊጠቃለሉ ከሚችሉ ጥበቃዎች አንዳንዶቹ ደግሞ ፍተሻውን በቃለ መጠይቅ የሚጨርሱት ናቸው ፡፡ የሚጠይቁት ከፍተኛ የሆነውን የማውራት ሱሳቸውን ለማስተንፈስ  ሊሆን ይችላል ፣ የሚጠይቁት መቆሙና ወዲህ ወዲያ ማለቱ አታክቷቸው እንደማስተንፈሻነት ለመጠቀም ሊሆን ይችላል ፡፡ የሚጠይቁት የአስጊ ሰውን አይነ ውሃ በሩቁ ማወቅ ይቻላል ከሚለው ልምዳቸው በመነሳት ሊሆን ይችላል ፤ ብቻ ይጠይቃሉ

‹‹ ሽጉጥ ይዘሃል ? ›› 
‹‹ አልያዝኩም ›› የሚል ምላሽ ካገኙ ‹‹ ይግቡ ጌታዬ ›› ን ያስከትላሉ ፡፡ እነዚህን ሰዎች አንድ የተገረመ ጋዜጠኛ ጠጋ ብሎ ‹‹ ይህን ልበሙሉነት ከየት አዳበራችሁት ? ›› ቢላቸው ‹‹ እድሜ ለቢኤስሲ ›› የሚሉ ይመስላል ‹‹ ስራን በፍጥነት፣ በብዛትና በጥራት ይላል ሳይንሱ ! ››
‹‹ በዚህ አይነት አፈታተሸ ጥራቱ ከየት ይመጣል ? ›› ከተባሉም ቢያንስ ምሳሌያዊ ምላሽ አያጡም ‹‹ መንግስታችን በአንድ ግዜ ሃያ ዩኒቨርስቲዎች የገነባው ጥራትን ማዕከል አድርጎ ነው እንዴ ? አይደለም ! ምሶሶዎቹ ብዛትና ፍጥነት ናቸው  ፤ ጥራት በሂደት ይመጣል ›› ለማለት አይቸገሩም ፡፡

የልብስና የሰውነት መጠንም በአንዳንድ ዋዘኛ ፈታሾች አይን የወጣላቸው መመዘኛዋች ናቸው ፡፡ የአምባሳደር ማስታወቂያን የመሰለ ፣ ሽክ ብሎ የሚታይና ሳምሶናይት ያንጠለጠለ  የተማረ ፣ የተከበረ ወይም ጨዋ ተደርጎ ስለሚቆጠር ከመልካም ፈገግታ ጋር ወደ ውስጥ እንዲዘልቅ ይደረጋል ፡፡ አንገቱን ፣ ሆዱን ወይም መቀመጫውን በከበሩ ጠቦቶችና ሰንጋዎች ያድበለበለም ስጋት ፈጣሪ ነው ተብሎ ስለማይገመት ለጥቂት ሰከንዶችም ቢሆን በር ላይ እንዲጉላላ አይደረግም ፡፡ ወፍራሙ ሰው ፈጣሪን ካልፈራ በስተቀር ‹‹ ና እስቲ ማነህ ! እዚህ ተገትረህ ወዴት ነህ ? ምንድነህ ? ከምትል ይህን ቦርሳ ሰባተኛ ፎቅ አድርሰህ ጠብቀኝ ! ›› ቢል ጥበቃው የሚያስጨንቀው ግዴታውን የሚወጣበትን በር ወለል አድርጎ መሄዱ አይደለም ፡፡ እራሱን የሚወቅሰው ‹ እኚህን የተከበሩ ባለስልጣን እንዴት እስካሁን ሳላውቃቸው ቀረው ? › በሚለው መልስ አልባው ጥያቄው እንጂ ፡፡  ለወፋፍራም ሰዎች መታዘዝንና አክብሮትን የሚያበዙ የዚህ ምድብ ጥበቃዎች አንዳንዴም ግራ የሆነ ተግባር ሊፈጽሙ ይችላሉ ፡፡ ለምሳሌ የሰማይ ስባሪ የሚያህለው እንግዳ ከአንድ የመነመነ ጓደኛው ጋ በሩን ሲያቋርጥ እጁን ወይም ኮሌታውን ስበው በማስቀረት አብጠርጥረው ከላይ እስከታች ሊፈትሹት ይችላሉ ፡፡ ካስፈለገም በላዩ ላይ ‹‹ ምነው እዚህ ቆመን ስታየን የፊልም ቤት ሬክላም መሰልንህ እንዴ ?! ›› የሚል የአሽሙር ፎጣ ጣል ሊያደርጉበት ይችላሉ ፡፡ ይሄ ሁሉ አጭር ድራማቸው ከሲታውንም ዶፍዳፋውንም አፍ ማስከፈቱ ይጠበቃል ፡፡

የሚያናድዱ ፍተሻዎች

አንዳንድ ጥበቃዎች ስራቸውን መስራታቸውን ብቻ እንጂ እንግዳ መከበር እንዳለበት በጥልቀት የሚረዱ አይደሉም ፡፡ የያዘውን እቃ አቧራ ላይ እንዲያስቀምጥ ሊያዙ ይችላሉ ፡፡ በአንድ ወቅት የተማሩትን ወታደራዊ ትምህርት ለማስታወስ በሚመስል መልኩ አንዴ እጅ ወደፊት ! አንዴ አሳርፍ ! አንዴ አንድ እርምጃ ወደኃላ ሂድ ! ከማለት አይቆጠቡም ፡፡ ሽንኮራ አገዳ እየገነደሹ ወይም ቡርቱካን እየመጠጡ ወይም መሳሪያቸውን በዘይት እያጸዱ እንኳ የእንግዶችን ልብስ በፍተሻ ለመዳፈር ወደ ኃላ አይሉም ፡፡

ከመታወቂያ ጋ የተያያዘ አናዳጅ ጉዳይም አለ ፡፡ የስራ መታወቂያ እረሱ እንበል - እረ ዝርክርኩ መ/ቤትዋ ነገ ዛሬ እያለ ሳያዘጋጅልዋ ቀርቶም ይሆናል ፡፡ የቀበሌ መታወቂያ አሳይተው ወደ አንድ ተቋም ሊገቡ ሲሉ ጥበቃዎች በዚህ መታወቂያ መስተናገድ እንደማይችሉ  ይነግሩዋታል ፡፡ መታወቂያ የማንነት መገለጫ መሆኑን ለማስረዳት ጥረት ሲጀምሩ ‹‹ ተማሪና ስራ አጦችን አናስገባም ! ›› የሚል መከላከያና ፍረጃ ይከተላል ፡፡

‹‹ ለምን ? ››
‹‹ በመጀመሪያ ለስራ ፈላጊዎች ማስታወቂያ ስላልወጣ ! ››
‹‹ ጓድ እኔ እኮ ስራ አጥ አይደለሁም ››
‹‹ ምንም ማረጋገጫ የለህም ጓድ ! ›› ሊባሉ ይችላሉ በመልስ ምቱ  ‹‹ ተማሪስ እዚህ ምን ያደርጋል ? ››
‹‹ ይሰሙኛል እኔ ተማሪ አይደለሁም ፡፡  የመጣሁት … ››
‹‹ አንዳንዶች እንግዳ መስለው እየገቡ በየጠረጼዛው የሚያገኙትን ንብረት ሌላው ቢቀር የሴቶችን ቦርሳ አፋፍሰው ይወጣሉ ፡፡ እህስ …  ከዛ ማነው የሚጠየቀው አልክ ?  አቶ ጥበቃ ነው ፡፡ ማነው መጠቋቆሚያ የሚሆነው አልክ ? ንጽሁ ጥበቃ ነው ፡፡ ተወኝ ብዙ አታናግረኝ ባክህ ፣ በጣም የሚገርመው ለስራ ብለው ገብተው የኤድስ የምናምን በሽተኛ ነኝ እያሉ የልመና ወረቀት ሲያዞሩ የደረስንባቸው አሉ ፡፡ ይሄ የስራ እንጂ የልመና ቦታ ይመስልሃል ?!  እንዲህ የሚያደርጉትን ደግሞ ከልምድ አውቀናቸዋል ›› ይህን የመሰለ ፈጣንና የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ የሚደርሱ ሰዎችን በቀላሉ ማሳመን ከባድ ነው ፡፡ አጓጉል ትንታኔያቸውና ፍረጃቸው አብሻቂ መሆኑ ባያጠያይቅም ትዕግስት ኖሮት ለሚሰማቸው ግን በኮሜድያነታቸው ፈታ ማለቱ አይቀርም ፡፡

አንዳንድ ፈታሾች ደግሞ ከአባታቸው ድብድብ ፤ ከእናታቸው ቁንጥጫን በላቀ ጥናት ተምረው የወጡ ይመስላሉ ፡፡ ሰውነትን የሚዳስሱት እንደ ሎሚ በማሸት ነው ፡፡ ስልቱ የተደበቀ መሳሪያ ከማግኘት ጋር የሚያያይዘው ነገር ግልጽ አይደለም ፡፡ የመሃል እግርዋን ለማስከፈት ታፋዋን ሊቆነጥጥዋት ይችላሉ ፡፡ ያለምንም መሳቀቅ የብልትዋን ፍሬ ወዲያና ወዲህ ሊንጡት ይችላሉ ፡፡ አንዳንድ ሴቶችም በሴት ፈታሾች የማህጸን ምርመራ የመሰለ ጥልቅ ፍተሻ አልፎ አልፎ እንደሚያጋጥማቸው ይናገራሉ ፡፡ ፈታሾቹ እነዚህን ስስ ብልቶች ስለምንጠራጠራቸው ማጉላላታችን አይታየንም ባይ ናቸው ፡፡

የጠመንጃቸውን አፈሙዝ ወደ እንግዶች አዙረው የሚሰሩትስ ? ‹‹ እረ እባክህ አፈሙዙን አዙረው ? ›› የሚል ቅን አስተያየት ሲያጋጥማቸው በቀላሉ የሚቀበሉ አይሆንም ፡፡ ‹‹ ጥርሴን የነቀልኩት በፍተሻ ስራ ነው ፡፡ ጠመንጃ ካልነኩት አይጮህም ፤ ለዛውም ስለያዝከው ብቻ ሳይሆን ምላሱን ካልሳብከው አይጮህም ! እና ምላሱ ጋ ምን ያደርስሃል ?! ለዛውም ምላሱን እንደ እብድ ዉሻ አፍ ከፍቶ የሚተው ጥበቃ የለም ፤ ምላሱ ይዘጋል ፡፡ አንዳንዶች በር ብቻ የሚዘጋ ይመስላቸዋል ፤ ጠመንጃም ይዘጋል ፡፡ በማናውቀው ስራ ባንገባ ጥሩ ነው ! ›› የሚል ሙያዊ ትንታኔ ከመስጠት ወደ ኃላ አይሉም ፡፡

የሚያሰጉ ፍተሻዎች

ይህኛው ምድብ አስፈሪ ነው ፡፡ መቼም እስከዛሬ በሰላም የቆየነው በጠንካራ ጥበቃዎች ዋስትና ስለተሰጠን ሳይሆን በአንድዬ ድጋፍ ነው ፡፡ ለምን ከተባለ  በአግባቡ እየተጠበቅን ባለመሆኑ ይሆናል ፡፡ ብቻ ለስሙ ያህል ብብት ስር እጃቸውን ከተው ‹ እለፍ › ማለት የሚቀናቸው ጥበቃዎች ጥቂቶች አይደሉምና ፡፡ መቼም የሽጉጥም ሆነ የቦንብ መቀመጫ ብብት እንዳልሆነ ያስማማናል ፡፡ ቦርሳ አስከፍተው በእጃቸው የሚዳስሱትን አንዳች ነገር ‹ ምሳ ነው አይደል ? መዝገበ ቃላት መሆን አለበት ! › በማለት ሌላ ምላሽ ለመስማት ግዜ ሳይፈጥሩ እንግዳውን ሲያስገቡ ምን ይባላል ፡፡ ሌላው ችግራቸው የሚግባቡትን ወይም ሰላምተኛቸውን አለመፈተሻቸው ነው ፡፡ በርግጥ ወደነዚህ ሰዎች ተንደርድረው የሚሄዱት እጃቸውን በሰላምታ ጥፊ ለማስጮህና በትከሻ ‹ ግጨው › ለመባባል ነው ፡፡ በአንዳንድ መ/ቤቶች ደግሞ ‹‹ ሴቶች ታማኞች ናቸው ›› በተሰኘው ያልተጻፈ ተግባራዊ ህግ ያለፍተሻ  ወደ ውስጥ እንዲያልፉ ይደረጋል ፡፡ በነዚህና በመሳሰለው ምክንያት አይደለም ሽጉጥ ታጣፊ ክላሽ ፤ አይደለም ተወርዋሪ ቦንብ ተለጣፊው ፈንጂ በየቢሮአችን ሊገባ እንደሚችል መገመት አይከብድም ፡፡

በበርካታ መስሪያ ቤቶች የሚገኙ ጥበቃዎች ግዴለሾች ፣ ስልችዋችና የተቃራኒ ጉዳይ ደጋፊዎች ናቸው ፡፡ ይሄ ከምን መነጨ ? የሚል ጥያቄ መወርወር ብዙ ምላሽ ያስከትላል - ለአብነት Girl ን ጀርል እያለ ሲያስተምር የተደረሰበት መምህር ‹ ምነው አንተ እንደዚህ ነው እንዴ የሚባለው ? › ሲባል  ‹ በ 230 ብር ደመወዝ ዋናው ጋ እንዴት መድረስ ይቻላል › ብሏል አሉ ፡፡ ከሚያገኙት ደመወዝ በላይ የሚዘንጡና የሚዝናኑ ጥበቃዎች ካጋጠሟችሁ ምድባቸው አስጊ ውስጥ መሆናቸውን ተጠራጠሩ ፡፡ ደንበኛ የሚበዛበት መ/ቤት ውስጥ ሰዓት አልፏል ወይም ኃላፊዎቹ የሉም በማለት በተዘዋዋሪ መደለያ ይጠይቃሉ ፡፡ ማዉጫ ያለው ዕቃ ሰበብ ፈልገው አይወጣም በማለት በግድ ኪስዋትን ያስበረብራሉ ፡፡ በተቃራኒው መዉጫ የሌለው ዕቃ ይለፍ ሰጥተው ከሽያጭ በኃላ ስላለው ክፍያ ተራጋግተው ያስባሉ ፡፡ እጅግ ውድ ዋጋ ያላቸው የሀገር ቅርሶችን ለመዝረፍ ለሚዶልቱ ኃላፊዎችና ሰራተኞች በጥቂት መደለያ ድምጽ ለመስጠት ወደ ኃላ አይሉም ፡፡ በብዙ መቶ ሺህ ብሮች የሚያወጡ የዝሆን ጥርሶችና ማሽኖችን በትርፍ ሰዓት ስራ አስመስለው በድፍረት አሰጭነው ለማውጣት አይፈሩም ፡፡ መ/ቤቱ ውስጥ ያለውን ንብረት በመጠቆም የአብሪነት ሚናም ይጫወታሉ ፡፡

የተጋነኑ ፍተሻዎች

በሚደርስብዎት መጉላላትና ውክቢያ ‹ ምነው እግሬን በሰበረው ! › እስከማለት የሚደርሱበት አጋጣሚምም አለ ፡፡ የፍተሻው የቀጠነ ህግጋትና የፈታሾቹ ከእርስዎ በላይ መደናገር ስጋትዎ እንዲንር ያደርገዋል ፡፡ የተወካዮች ምክር ቤትና የጠ/ሚ/ር ጽቤት በዚህ ምድብ ውስጥ ከሚገኙ ቋሚ ተሰላፊዎች መካከል እናገኛቸዋለን ፡፡ የተወካዮች ም/ቤት የፍተሻ ማሽን እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ የሚጠብቅዎት ጠ/ሚ/ሩ ሪፖርት በሚያቀርቡበት ግዜ ነው ፡፡ ጋዜጠኛው ፣ የም/ቤት አባላት ፣ ሚኒስትሮችና ትላልቅ እንግዶች የሚገቡበት በር ተመሳሳይ ሲሆን ያን ሁሉ ሰው የሚያስተናግዱት ሁለት ማሽኖች ናቸው ፡፡

ጫማና ቀበቶ ሲያወልቁ ወደ እስር ቤት የሚገቡ ሊመስልዎት ይችላል ፡፡ ብረት ነክ ጉዳዮችን ሁሉ ከኪስዎ አራግፈው ይጥላሉ ፡፡ ክፉ ነገር አልያዝኩም ብለው በማሸኑ በር ሰተት ሲሉ እሳት ለባሹ እሪታውን ያቀልጠዋል ፡፡ ሁልግዜም ትላልቅ ሆቴሎች ፣ አልፎ አልፎ በራሱ በፓርላማ ማሽኑ ባልተለመደ መልኩ ድምጽ ሲያሰማ ሰውየው በሩን አልፎ በትንሷ መዳበሻ በእጅ ተፈትሾ እንዲገባ ይደረጋል ፡፡ ፓርላማ በተለይም ጠ/ሚ/ሩ በሚመጡበት ዕለት ግን እንደዚህ አይነት ቀና ስራ አይሞከርም ፡፡ ማሽኑ በአንድ በኩል ፌዴራልና ደህንነቶች በሌላ በኩል የጩኀትና ግልምጫ እሳታቸውን ይተፋሉ እንጂ ፡፡

‹ የቀረህን ነገር ሁሉ አውልቅ ! › ሊባሉ ይችላሉ ፡፡ በአንድ ወቅት አንድ የተከበሩ ሚኒስትር ጫማቸውን አውልቀው በባዶ እግራቸው በሩን ለማለፍ ሞከሩ ፡፡ ማሽኑ ተቃወመ ፡፡ ‹‹ ተመለስና ራስህን ፈትሽ ›› ተባሉ እንደማንኛችንም ፡፡ እንደ ሞኝ ሁኔታውን ፈዝዤ እመለከታለሁ ፡፡ ሚኒስትሩ ፈገግ እያሉ ኪሳቸውን ዳበሱ ፤ ያገኙት ነገር አልነበረም ፡፡ ኃላ ትዝ ያላቸውን መነጽር አውልቀው በጠባብዋ በር ሰተት አሉ ፡፡ ማሽኑ እሪ አለ ፡፡ ‹‹ ሌላ ነገር ፈልግ ! ›› አለ ሲቪል ለባሹ ጆሮ ጠቢ ፡፡ በጣም ተሳቀቅኩ ‹ አያቃቸውም ማለት ነው ? › ስል ራሴን ጠየቅኩ

የቀራቸው ኮታቸውን ማውለቅ ነው ፡፡ ኮታቸው ላይ እንኳ የተለመደውን ባለብረት ባንዲራ አለጠፉም ፡፡ የኮቱ የውስጥ ኪስ ቁልፎች እንደማይክል ጃክሰን ጃኬት ዚፕ የበዛባት ይሆን ? ብሎ መገመት ያስቸግራል ፡፡ የማሽኑ ሰይጣን ከሄደለት ብለው ትንሽ ቆይተው ሲገቡ ብረቱ አለቀቃቸውም ፡፡ ኮታቸውን ገልብጠው ለፈታሾቹ አሳዩ - ምንም የለብኝም እንደማለት ፡፡ እንደነገሩ ወደተከለለች ክፍል አስገቧቸው ፡፡ ስገምት እዚህ ክፍል ሊታየው የሚችለው የውስጥ ሱሪ ብቻ ነው - ምናልባትም በብረታብረት ከተጌጠ ፡፡ ከጥቂት ቆይታ በኃላ ከክህሉ ወጥተው አንድ - ካልሲያቸውን ፤ ሁለት - ጫማቸውን ፤ ሶስት - ቀበቷቸውን ፤ አራት - ሰዓታቸውን ፤ አምስት - መነጽራቸውን ግዜ ወስደው በጸጥታ ተራ በተራ አደረጓቸው ፡፡

በዚህ ጸጥታ ውስጥ ቢሯቸውን ያስቡ ይሆን ? የሚል ሀሳብ መጣብኝ ፡፡ … ገና ወደ በሩ እንደቀረቡ ሁለት እሳት የበሉ ፖሊሶች በሩን ወዲህና ወዲያ ወርውረው መሬት የሚያርድ ሰላምታ ሲሰጧቸው… ልበ ሙሉው  ሾፌርም በመጣበት ፍጥነት ክፍተቱን ሰንጥቆ ወደ ውስጥ ሲዘልቅ… መኪናው እንደቆመ ወይ ሹፌሩ ወይ የሆነ ጋርድ በፍጥነት ጎንበስ በማለት በሩን ከፍቶ ሲያስወርዳቸው … የያዙትን ሳምሶናይት ወይም ቦርሳ ተቀብሎ መንገድ የሚጠርግላቸው የፕሮቶኮል ሰራተኛ … በየኮሪደሩ ‹‹ እንደምን አደሩ ክቡር ሚኒስትር ! ›› የሚሏቸው መምሪያ ኃላፊዎች … አበባ ብቻ ማሳቀፍ የሚቀራት ፍልቅልቅዋ ጸሀፊ …
‹ የሀገሪቱን የካቢኔ አባልን እንኳ የማያምን ፍተሻ  › ስል እሳቸውን በመንፈስ ወክዬ አጉረመረምኩ ፡፡

ተራዬ ደርሶ እኔም ብረት የሌለውን ጫማዬን አወለቅኩ ፡፡ ቀበቶ ፣ ሳንቲሞች ፣ ፍላሾች ፣ መቅረጸ ድምጽ ፣ ሞባይል ፣ የቢሮ ቁልፎች አንድ በአንድ ሳህኑ ላይ ዘረገፍኳቸው ፡፡ የኪሶቼን ሆድ እቃ ገልብጬ ሳጣራ መፋቂያ ብቻ ነው የቀረው ‹ የተከበርክ መፋቂያ ! › አልኩት በአቅራቢያው አጠራር  ‹  ፓርላማ ውስጥ እንጨት ለመሆንህ ምንም ማረጋገጫ መስጠት አይቻልም ! › በማለት በዘር ከሚርቁት ጓደኞቹ ጋ ቀላቀልኩት ፡፡ አንድ ዚፕ ያለውን የቆዳ ጃኬቴ ደግሞ ‹ እባብን ያየ በልጥ በረየ ! › የሚል ስነቃል ቢጤ ወርወር አደረግኩለትና አውልቄ ወረወርኩት ፡፡

እሳት የሚተፋው ማሽን እንደሚኒስትሩ ሊያንገላታኝ አልፈለገም ፡፡ በአንደኛ ሙከራዬ የይለፍ ካርድ ቆረጠልኝ፡፡ ‹ ተመስገን ! መጋረጃ ውስጥ ከመግባት ያዳንከኝ … › እያልኩ በውስጤ ለመቀላለድ ስሞክር ሌላ ሲቪል ለባሽ ጠጋ ብሎ በህገወጥ ጥያቄዎች ያጣድፈኝ ጀመር

‹ ምንድነው ስራህ ?! › ጤና ይስጥልኝን እንኳ ማስቀደም ያልፈለገ ትዕቢተኛ ቢጤ ነው ፡፡
‹ ጋዜጠኛ ! ›
‹ ከየት ? ›
‹ ከእገሌ ድርጅት ›
‹ እስኪ ባጅህ ? › ጥበቃ ክፍሉ ስሜን አጣርቶ የሰጠኝን መግቢያ እንኳ ለማመን የተቸገረ ዱልዱም ቢጤ ነው ፡፡
አሳየሁ
‹ ይሄ ምንድነው ? ›
‹ መቅረጸ ድምጽ ›
‹ ውስጡ ምን አለ ? ›
‹ ካሴት ›
‹ እስኪ ክፈተው ?! ›
ካሴቱን አሳየው
‹ ምነው አነሰች ? ›
‹ ስራው ነው ›
‹ የኃላውን ክፈተው ! ›
ከፈትኩት
‹ ባትሪዎቹን አውጣቸው ! ›
አውጥቼ ሰጠሁት ፡፡ አያቸው ምናልባትም አነበባቸው ወይም ደግሞ የድማሚትነት ባህሪ እንደሌላቸው ተገነዘበ መሰል መልሶ ሰጠኝ
‹ ዝጋውና አጫውተው  ! ›
የማጫወቻውን ቁልፍ ተጫንኩት
‹ ድምጹ የታል ታዲያ ? ›
‹  ባዶካሴት እኮ ነው ?! ›
‹ ድምጽ ያለው ካሴት ይዘሃል ? ›
‹ አልያዝኩም ›
ቅር ያለው ስለመሰለኝ ‹ ሮጥ ብዬ የቴዲ አፍሮን ጃ ያስተሰርያል ካሴት ገዝቼ ልምጣ ? › ብለው በኔም ሃሳብ በእሱም ምላሽ የምዝናና መስሎኝ ነበር ፡፡ ግና በሪፖርት ቀን ከእኔ የሚጠበቀው መስማት ብሎም በሚሰማው መሳቅ እንጂ ሳቅ መፍጠር አይደለምና ሃሳቤን ዋጥኩት
‹ እነዚህስ ምንድናቸው ? ›
‹ ፍላሽ ›
‹ ምንድነው እሱ ? ›
‹ መረጃ መያዣ ናቸው ›
‹ የምን መረጃ ? ›
‹ የጽሁፍ ፣ የድምጽ ፣ የተለያዩ … ›
ፍላሾቹን ለብቻ ያዛቸው ፡፡ አላመነኝም ወይም አላወቀውም ማለት ነው  ፡፡ ምናልባትም ‹ ባዶ ካሴት የያዘው ለድምጽ ፣ ፍላሽም የያዘውም ለድምጽ - እንዴት ያለ አራዳ ነው ? › በማለት በውስጡ ተሳልቆብኝ ይሆናል ፡፡
‹ ሞባይልህን አጥፋው ! ›
‹ ለምን ? ›
‹ ወደ ውስጥ ስለማይገባ ዝጋው ! ›
‹ ሌላ ግዜ ይገባል እኮ ?! ›
‹ ስለእሱ አያገባኝም ! ›

አሁን የጠ/ሚ/ር ጽ/ቤት ትዝ አለኝ ፡፡ ለጋዜጣዊ መግለጫ ስንሄድ የመጀመሪያው በር ላይ በፍተሻ ታሽተን እንገባለን ፡፡ እግረ መንገዱንም ሞባይላችንን አስረክበን ፡፡ የመጀመሪያ ቀን ለምን ይሆናል ?  አግባብ አይደለም ! ምናምን  ! እያልን ስናለቃቅስ አንድ ሰራተኛ  ‹‹ ሁለትና ሶስት ሰአት አይደል እንዴ የምትቆዩት ? እኛ ቋሚ ሰራተኞቹ መቼ ስልካችንን ይዘን ገብተን እናውቃለን ›› ብሎ ገላገለን
‹ ነው እንዴ ?! › ብለናል በድምጽ ሳይሆን ወደ ዉጭ ባልወጣ አግራሞት ፡፡

ከዚያ ደግሞ ዋናውን በር አልፈን ወደ አዳራሽ ልንቃረብ ስንል በጣም ያማረበት ማሽን እኛን በጉጉት ሲጠባበቅ ተመለከትን ፡፡ አሁን ምንድነው ይሄ  ? አግባብ ነው እንዴ ? ምናምን አላልንም - የቅድሙ የማጣሪያ ጨዋታ ሆኖ የአሁኑ ወደ ሩብ ግማሽ ፍጻሜ መዝለቂያ መሆኑ ነው ? ለማለትም አልቃጣንም … ይሄ ግቢ ቀልድ አያውቅም ማለት ነው አላልንም - ይሄ ግቢ ኤምኤውን የሰራው በፍተሻ ይሆን እንዴ ? አላልንም - አንዳንዶቻችን በውስጣችን ያልነው  ‹ ይህን ምርጥ የፍተሻ ተሞክሮ እንዴት ቀምሮ ማስፋፋት ይቻላል ! › የሚል ነበር ፡፡ ለምዶብን ፡፡
ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ትዝታ ወጥተን ወደ ፓርላማ እንመለስ ፡፡
ሞባይሌን ለሚስድ ኮል የሚሆን ቀጭን ክፍተት እንኳ ሳላስተርፍ ዘግቼ ለነጭ ለባሹ አስረከብኩ ፡፡ ከፍላሾቹ ጋ አንድ ትንሽ ኪስ ውስጥ ወረወራቸው ፡፡ ካርድ ቢጤ ተቀብዬ ወደ ውስጥ ዘለቅኩ ፡፡ ሶስት ጥያቄዎች ተከታትለው ብቅ አሉብኝ ፡፡

1 . ይሄን ደህንነት ተሸክሜው ነበር እንዴ ? ምክንያቱም በጣም ነው የደከመኝ
2 . ይሄ ሁሉ ነገር ጥንቃቄ ነው የሚባለው ወይስ ስጋት ? ምክንያቱም ነጭ ለባሹ ከሲአይኤ መረጃ የደረሰው ይመስላልና
3 . ሚኒስትሩን ያንገላታው ዱዳ ማሽን ይሻላል ወይስ እኔን የጨቀጨቀው ሰው ? ምክንያቱም  ምክንያት ስለማያስፈልገኝ !!!


ማስታወሻ፡ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ላይ የወጣ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡

Sunday, August 25, 2013

የእምብርት ዘመን ሲሄድ የቂጥ ዘመን መጣ








‹‹ ምን ዓይነት ዘመን ነው  ዘመነ ዲሪቶ
አባቱን ያዘዋል  ልጁ ተጎልቶ ››

እያለ አቀንቅኗል ድምጻዊ ተሾመ ደምሴ ፡፡ ተሾመ ልማዳዊው ህግ ወይም ስርዓት ተጣርሷል የሚል ጭብጥ ለማስተላለፍ የሞከረ ይመስላል ፡፡ ዜማውን በምሳሌያዊ አነጋገር ለውጡ ብንባል

‹‹ዘመነ ግልንቢጥ
ውሻ ወደ ሰርዶ
አህያ ወደ ሊጥ ›› የሚባለውን ብሂል መጥቀሳችን አይቀሬ ነው ፡፡

በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ምን ዓይነት ዘመን መጣ ያሰኘው የሴቶቻችን አፈንጋጭ አለባበስ ነበር ፡፡ ዘንድሮ ዘመነ ግልንቢጥ የተባለው ደግሞ በወንዶች ጉዳይ ሆኗል ፡፡ ለመሆኑ እንዴት ነው አህያ ወደ ሊጥ የሄደው ? የሚለውን ጥያቄ ከመፈተሻችን በፊት ትንሽ ስለቀደመው እናውራ ፡፡

ስለሴቶቹ ...
መቼም ዘመኑን ሆን ብሎ የሚያጠና ሰው ቢኖር ስለ እያንዳንዱ ግዜና መጠሪያ ስለሚሆነው ጉዳይ ስያሜ አያጣለትም ፡፡ ለአብነት ያህል በ1997 አካባቢ ሴቶቻችን በታይት ተወረው ነበር ፡፡ ይህን ግዜ ‹‹ የታይት ዘመን ›› ብሎ መጥራት ይቻላል ፡፡ የዛኔ የዘፈን ውድድር አለመፈጠሩ እንጂ ለታይት ለባሾቻችን ‹‹ ቀይ ›› ፣ ‹‹ ቢጫ በቀይ ›› ‹‹ ሙሉ አረንጓዴ ›› እያልን ጥሩ ማነጻጸሪያ መስጠት በተቻለ ነበር ፡፡ ታይት የሰውነት ቅርጽንና ውበትን አጋልጦ የማሳየት ኃይሉ ከፍተኛ ስለነበር ራሳቸውን ‹‹ ለቁምነገር የሸጡ ›› ወጣቶችም ጥቂቶች አልነበሩም ፡፡

አንዳንድ ሴቶች ደግሞ ታይትን ያለ ግልገል ሱሪ በማጥለቅ በየጎዳናው የሚያለከልኩ ወንዶች እንዲበዙ አድርገዋል ፡፡ የነዚህኞቹ ግብ በወንዶች ላይ ‹ ሙድ › ይዞ መዝናናት ይሁን ወይም የግብዣ ማስታወቂያ መስራት በውል የሚታወቅ አልነበረም ፡፡ ለሚነሳባቸው የተጃመለ ትችትም ‹‹ መብታችን ነው ! ›› በማለት የተንዥረገገ ነገር ግን የማይበላ የወይን ፍሬ ነው የሚባልለትን ህገመንግስት ተደግፈው የሚያወሩ ሴቶች ጥቂቶች እንዳልነበሩ እናስታውሳለን ፡፡ ህገመንግስቱ እንኳን የማስልበስን ራሱ የመገንጠልን ካባ በመከናነቡ አያስገርመንም የሚሉ አሽሟጣጮች በበኩላቸው የትራክተር ጎማ የሚያህል መቀመጫ ያላት ሴት በታይት ተወጣጥራ ስትንከባለል እያየን ላለማሳፈር መጣር ከጨዋነት አያስቆጥርም ይሉ ነበር ፡፡ ድርጊቱ የሳቅ ቧንቧን ቷ ! አድርጎ በመክፈቱ በየቦታው አይንና አፍን በመሸፈን የሚንፈቀፈቁ ሰዎች እንዲበራከቱ መንገድ ከፍቷልና ፡፡

ከዚህ ዘመን በኃላ ደግሞ አጭር ቀሚስ የፋሽን መገለጫ ሆኖ መጣ ፡፡ በርግጥ አጭር ቀሚስ ከማለት ይልቅ መሃሉ የተከፈተ ቁምጣ ማለት እውነቱን ቀረብ ያደርገዋል ፡፡ ሴቶቹ ቁጭ ሲሉ ገላቸውን ላለማሳየት ያቺን ምላስ የምታህል ጨርቅ በግድ ሊያረዝሟት ሲታገሉ ማየት ያስቃል ፡፡ ‹ ለምን ለበሱት - ለምን ይጨነቃሉ ? › የሚል ገረሜታ አእምሮን ይወራል ፡፡ የሴቶችን ፍላጎት ጠንቅቀን እናውቃለን የሚሉ ሴት አውሎች ግን በለበሱት ለመጨናነቅ ፣ ለማፈር ፣ የይቅርታ ፊት ለማሳየት መሞከር ሁሉ ድምር ውጤቱ ‹ ሆን ተብሎ የሚተወን የትኩረት መሳቢያ ድራማ  › ነው ባይ ናቸው ፡፡ በርግጥ አጭር ቀሚስ ወዲህ ወዲያ ሲሄዱበት የሚያምር ከሆነ በመቀመጥ ግዜ ገላን ላለማጋለጥ ነጠላ ወይም ሻርብ ነገር እግር ላይ ጣል ማድረግ በተቻለ ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ግን ከስንት አንድ ናቸው ፡፡ ስለዚህ የአጭር ቀሚስ አላማ ከፋሽንነትም በላይ የሚሻገር ነው የሚሉ አስተያየት ሰጪዎችን ሀሳብ መናቅ የትም አያደርስም ፡፡  ዘንድሮ ይህ ድርጊት ተገልብጦ በመምጣቱ የጭን መጋለጥ ሴቶችን ‹ አያሰጋም › ፡፡ ሱሪያቸው ግን ከኃላ ሆን ተብሎ ያጠረ በመሆኑ ለምሳሌ ያህል ከታክሲ የሚወርዱ ሴቶች መቀመጫቸውን ላለማሳየት ከላይ የለበሱትን ልብስ እስኪቀደድ ድረስ ወደታች ይጎትቱታል ፡፡ እኛም ልብስ መቀየሪያ ክፍል የገባን ያህል ላለማሳፈር ይሁን ላለመሳቀቅ ፊታችንን እናዞራለን - በጨዋ ደንብ ፡፡ ከወረዱ በኃላ ደግሞ  ‹ ምን ያለበሰቸውን ሱሪ ለመልበስ ትታገላለች ! ›  በማለት እናብጠለጥላታለን - በሀሜት ደንብ ፡፡

ታይትንና አጭር ቀሚስን ተሻግሮ በአደባባይ ብቅ ያለው ሱሪም ቀሚስም አይደለም - እምብርት እንጂ ፡፡ እንኳን ከዘመነ ጭን ወደ ዘመነ እምብርት አሸጋገራችሁ - አልናቸው እህቶቻችንን ፡፡  እምብርትን አጋልጦ ለማሳየት መደበኛ ሱሪም ሆነ ታይት መጠቀም ይቻላል ፤ ከላይ ደግሞ አጭር አላባሽ ፡፡ እድሜያቸው 14 እና 15 ያልሞላቸው ህጻናት ፣ የደረሱ ወጣቶች ፣ ብዙ ልጆች ያፈሩ እናቶች ሳይቀሩ እምብርታቸውን በየአደባባዩ አሰጡት ፡፡ ለብዙ ወንዶች ትርጉሙ ግልጽ አልነበረም ፡፡

ሴቶቹ በደፈናው ‹‹ ፋራ አትሁኑ ! ፋሽን ነው ›› አሉ ፡፡ መነሻው ህንድ ይሁን ሱርማ ፤ ጥቅሙ ሀሴት ያምጣ ግርማ ልብ ያለ ግን አልነበረም ፡፡ ወንዶቹ ‹‹ ከፋሽኑ ጀርባ ምን አለ ? ›› በማለት ጠየቁ ፡፡ ይህ ጥያቄያቸው በተለይ ከውበት ጋ የተያያዘ ነበር ፡፡ ምክንያቱም ወንዶች ጸጉር ፣ አይን ፣ አንገት ፣ ጡት ፣ ዳሌ ፣ ሽንጥና ባት እያሉ ሊያዜሙ ፣ ሃሳባቸውን ሊገልጹ ወይም ሊጽፉ ይችላሉ ፡፡ እስካሁን ግን ‹‹ እምብርትሽ ›› ብሎ ያቀነቀነ ዘፋኝ ወይም የጻፈ ደራሲ ወይም ያደነቀ አፍቃሪ አልተሰማም ፡፡ ታዲያ የእምብርት ፋይዳ ምን ይሆን ? መባሉ ግድ ነው ፡፡ አንዳንድ ሴቶች እምብርታቸው ላይ ጉትቻ እስከማንጠልጠል በመድረሳቸው ወንዶቹ እንደሚከተለው አሾፉ ‹‹ እምብርት ምድር ቤት የሚገኝ ጆሮ ነው  እንዴ ? ›› ወይም ‹‹ ከላይኛው የጆሮ ገጽ የዞረ መሆኑ ነው ? ››
ስለ ወንዶቹ …

እነሆ ዘመኑ ተገልብጦ ሴቶች በወንዶች ድርጊት እያዘኑ አልፎ አልፎም እያስካኩም ይመስላል ፡፡ የሴቶቹ እምብርት ተረት ሆኖ የወንዶቹ ቂጥ ወቅታዊ ማፍጠጫ ጉዳይ ስለሆነ ፡፡ ምናለፋችሁ በከተማችን ‹‹ የሚዝረከረኩ ወንዶች ›› ተበትነዋል ፡፡  ‹ እረ ወንድ ልጅ ሴታ ሴት ሲሆን ያስጠላል ! › የሚሉ ቆነጃጅትና እማወራዎች በዝተዋል ፡፡ ‹ ልጆቻችን ምን እስኪሆኑ ነው የምንጠብቀው ? › በማለት በሴት እድሮችና ማህበሮች ላይ ጉዳዩ የመወያያ አጀንዳ እንዲሆን የጣሩ ሴቶች ሞልተዋል ፡፡ ‹ ግብረ ሶዶማዊያን በዛ እያሉ እግዚኦ የሚሉ የሃይማኖት ተቋማትና ጋዜጠኞች የወንዶችን ልብስ መጣል እንዴት ዝም ብለው ያያሉ ? › የሚሉ ተቆርቋሪ እህቶች ሰሚ ያጡ ይመስላሉ ፡፡

የሀገራችን ሴቶች ወንዶች ቀበቷቸውን እንዲያላሉ በህጋዊ መንገድ የሚጠይቁት በአንድ መንገድ ብቻ ነው  ፤ በምጥ ወቅት ፡፡ በርግጥ  በፍቅር ጨዋታ ወቅት የሚኖረውን ውልቂያ የትኛው ክፍል እንደምንመድብ ሳያስቸግርን አይቀርም ፡፡ ታዲያ ዛሬ በህገወጥ መንገድ ቀበቶ አላልቶ ፤ ሱሪውን ከወገቡ ቁልቁል አርቆ ፤ የውስጥ ሱሪውንና የቂጡን ቀዳዳዎች እያስጎበኘ ላይ ታች በሀገራዊ ኩራት የሚጓዘው ‹ ትንሽ - ትልቅ › አበዛዙ ቀላል አልሆነም ፡፡

ወደው አይስቁ አሁን ይመጣል ፡፡ አንዳንድ የውስጥ ሱሪዎች የተቀደዱና ውሃ ካያቸው ዘመናት ያስቆጠሩ ሊሆኑ ይችላሉ  ፡፡ አንዳንድ የውስጥ ሱሪዎች ደግሞ ገመዳቸው ላልቶ ነው መሰለኝ ወደ ውስጥ የሰመጡ ናቸው ፡፡ በተለያየ ምክንያት የሚጎነበሱ ፋሽነኞች ታዲያ የሚያስጎበኙት የተራቆተ መቀመጫ በንጽህ ወንድ / አፍቃሪ ግብረሶዶም እና እንስት ባልሆነ / ከታየ ለአይን የሚቆረቁር ፣ የመንፈስ ልዕልናና ክብርን ዝቅ የሚያደርግ ነው ፡፡ ምክንያቱም  የአንዳንድ ሰው ቂጥ በጎርፍ የተቆረሰ ደለል ይመስላል … የአንዳንድ ሰው ቂጥ በላብና እድፍ ተቦክቶ ልስን የሚጠብቅ ግድግዳ ይመስላል … የአንዳንድ ሰው ቂጥ ወፍጮ ቤት ከዋለ ፊት ጋር  አንድ ነው ፡፡

አሁን ደግሞ የማይገባዎትን ጥያቄ ይወረውራሉ ፡፡ ፋሽኑ ሱሪው ነው ? የላላው ቀበቶ ነው ? ፓንቱ ነው ? የፓንቱና ሱሪው ደረጃ ሰርቶ መታየቱ ነው ? ወይስ የሰውየው ቂጥ ? ከግርምት ፣ ትዝብትና ሳቅ በኃላ ለመሆኑ ምንድነው ዓላማው ? ወይም ፋሽን ተከታዮቹን ምን ያህል ያስደስታል ? ለማለት ይገደዳሉ ፡፡ አብዛኛው ፋሽን ተከታይ በጆሮ ፣ ጸጉር ፣ ጃኬት ፣ ቲሸርት ፣ ጫማ ወዘተ ላይ ሲታይ እንደቆየው የዘመናዊነት መገለጫ ሳያካብዱ መመልከት እንደሚገባ የሚያስገነዝቡ ናቸው ፡፡ ፋሽን ይመጣል ፋሽን ይሄዳል እንዲሉ … ለምን ይቅርብኝ  ወይም ከማን አንሳለሁ በሚል ድሃ መነሻ የማያምርባቸውን ብቻ ሳይሆን የማያውቁትን ነገር የሚከውኑ ወንዶችም ሴቶችም የሚታዘንላቸው ናቸው ፡፡ እነዚህ ምስኪኖች ከሚሆኑትና ከሚለብሱት ዉጪ ስለ ጉዳዩ  አነሳስና ከጀርባው ስለሚጠረጠረው ጉዳይ ለማሰብ ግዜ የሚወስዱ አይደሉም ፡፡ 
 አነሳሱ  ...
ሱሪን ከቂጥ በታች አውርዶ መልበስ የተጀመረው በአሜሪካ እስር ቤቶች ውስጥ ነው ፡፡ Sagging Pants ይሉታል ፡፡ እስረኞች ቀበቷቸውን ራሳቸውን ለመግደልና በሌሎች ላይ ወንጀል መስሪያ መሳሪያ ማድረጋቸው ስለተደረሰበት እንዳይጠቀሙ ታገደ ፡፡ በዚህም ምክንያት ሰፊ ቱታቸውን መቆጣጠር ባለመቻላቸው ሱሪያቸው ታች መውረዱ ግድ ሆነ ፡፡

የጀርባው ንባብ  ...

ይህ ‹‹ ፋሽን ›› በጥርጣሬ ጨጎጊቶች የተከበበ ነው ፡፡ አንዳንዶች በእስር ቤት ልብስን ዝቅ አድርጎ መልበስን የሚያገናኙት ከግብረ ሶዶማዊነት ተግባር ጋ ነው ፡፡ የወሲብ ግንኑነታቸው መጠቆሚያ ስልት ነው በማለት ፡፡ አንዳንዶች የእስር ቤት አስተሳሰብ መሆኑን በመግለጽ በተለይ ጥቁሮች ‹ አሁንም እስር ላይ ነን › የሚል መልዕክት ያስተላልፉበታል ይላሉ ፡፡ አንዳንድ ጉዳዩን ያጠኑ ምሁራን ደግሞ ‹‹ በአሜሪካ የባርነት ዘመን ነጭ አለቆች የአፍሪካን ጥቁር ወንዶች አስገድደው ይደፍሯቸዋል ፡፡ ተግባሩ ከተፈጸመ በኃላ ተጠቂው ሱሪውን ዝቅ አድርጎ እንዲለብስ ይደረጋል ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ አለቃው በቀጣይነትም ግንኙነት መፈጸም ሲፈልግ በቀላሉ እንዲለየው ነው ›› በማለት ቃላችን ርግጠኛ ነው ሲሉ ይደመጣሉ ፡፡ ግራም ነፈሰ ቀኝ በ 1990ዎቹ አካባቢ የሂፕ ሆፕ አርቲስቶች ሱሪን አውርዶ መልበስን በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ሚና መጫወታቸው ብዙዎችን ያስማማል ፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ባህልና ፋሽንን ከመግለጽ በተጨማሪ የነጻነት ማሳያም እንደሆነ ይጠቆማል ፡፡

በዚህ እሳቤ የኛዎቹ ፋሽን ተከታዮች ምን መልዕክት እያስተላለፉ መሆኑ ግራ ያጋባል ፡፡ በርግጥ በሀገራችን ግብረሰዶማዊነት እየተስፋፋ መሆኑ ይታወቃል ፡፡ የሱሪው መውረድ ሰምና ወርቅ ፋሽንና ያልተለመደ ወሲባዊ ግንኙነትን እያመላከተ ይሆን ?  ግብረ ሰዶማዊያን ለመግባቢያነት ይረዳቸው ዘንድ ጆሮአቸው ላይ ጌጥ ያደርጋሉ ፤ ሱሪ አውርደው ከሚፏልሉት ወገኖቻችን ገሚሶቹም ጆሮአቸውን ማስዋብ ይወዳሉ ፡፡ ግብረ ሰዶማዊያን  አንድ ጆሮ ላይ ጌጥ ካደረጉ ‹ አልተያዝኩም › ማለት ፈልገው ነው ፤ ሱሪ አውራጆቻችንስ ‹ አልተያዝኩም › ነው ወይስ  ‹ የማውቀው ነገር የለም ›  እያሉ  ነው የሚገኙት ፡፡ ሀገራችን እንደ ሌሎች አፍሪካዊያን ቅኝ ያልተገዛችና የባርነት ቀንበር ያልቀፈደዳት ቢሆንም ከሀገራዊ ባርነት መቼ ተላቀን እያሉበት ይሆን ? ነው አለማቀፉን ምልከታ ያልተረዳ ተራ የፋሽን ጉዳይ ?

ያን ግሩም ሙዚቀኛ ‹ ተቀበል ! › ማለት አሁን ነበር ፡፡
አቦ ተቀበል ! አፈሩ ይቅለልህና
‹ እሺ ልቀበል ! › …
‹‹ ምን ዓይነት ዘመን ነው በል ! ››
‹ ምን አይነት ዘመን ነው › …
‹‹ ምን አይነት ዘመን ነው - ዘመነ ዥንጉርጉር
 በምናገባኝ ቅኝት በኬሬዳሽ መዝሙር
 እንደሰጡት ሆኖ እንዳጣው የሚያድር
 አይገደውም ከቶ
 ‹ አይገደውም ከቶ › …
ለማያውቀው አንቀጽ ውል አጥብቆ ሲያስር
 በእውር ፈረስ ጀርባ ሽምጥ ሲኮረኩር ››
በልልኝ አቦ !!
 በእውር ፈረስ ጀርባ ሽምጥ ሲኮረኩር › …


ማስታወሻ፡- ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ቅፅ 12 ቁጥር 159 ላይ የወጣ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡



Tuesday, August 13, 2013

የአቅጣጫ ለውጥ --- በማህበራዊ ሚዲያዎች ?




ታይም መጽሄት ፡፡

የፌስ ቡክ መስራች የሆነውን ማርክ ዙከርበርግን የ2010 የአመቱ ምርጥ ሰው በማለት ሰየመ ፡፡
የመጽሄቱ ውዳሴ ፡፡

ለፌስ ቡክ  --

‹‹ በአሁኑ ወቅት ከምድራችን ሶስተኛው ትልቅ ሀገር ነው ፡፡ በርግጠኝነትም ለዜጎቹ ከሌላው መንግስት በተሻለ መረችን ይሰጣል ››

ለማርክ ዙከርበርግ  --  


‹‹ ከሃርቫርድ ትምህርቱን ያቋረጠው ይህ ወጣት ቲሸርት የሚለብስ የሀገሪቱ ርዕሰ ብሄር ነው ››

››››                               ››››                                    ›››››                                  ››››

አንጋፋውና ታዋቂው መጽሄት ታይም ብዙዎችን ያስደመመውን ፈጠራና ፈጣሪ በዚህ መልኩ ቢያደንቀውም አትዮጽያን ጨምሮ በርካታ ሀገሮች ፌስ ቡክንና ማህበራዊ ሚዲያን የሚመለከቱት በታላቅ ጥርጣሬና ስጋት ነው ፡፡

በርግጥ ስጋቱ ከዘርፈ ብዙ አስተሳሰቦች የሚመነጭ ነው ፡፡ በዋናነት ግን የፖለቲካ አለመረጋጋት እንዲፈጠር ፣ ብሄርና ጎሳ ተኮር ግጭቶች እንዲጫሩ ፣ አክራሪ ሃይማኖታዊ አጀንዳዎች ስር እንዲሰዱ መንገድ ይከፍታል የሚሉት ሊጠቀሱ ይችላሉ ፡፡ ወረድ ሲባልም የግለሰቦች መብት ሊጣስ ፣ የስራ ባህል ሊዳከም ፣ ምርታማነት ሊያሽቆለቁል ይችላል የሚሉ መከራከሪያዎች ይቀርቡበታል ፡፡

በቴክኖሎጂው ዙሪያ የወፈረ ቅሬታ ያላቸው ሀገሮች በአብዛኛው ራሳቸውን ከሂደቱ ውስጥ ለማውጣት ግን የሚደፍሩ አይደሉም ፡፡ አካሄዳቸው አገም ጠቀም አይነት ነው ፡፡ ከቴክኖሎጂው መሸሽ እንደማይቻል ሁሉ ለዓለም ስል ትችትም ራስን አጋልጦ ላለመስጠት ሂደቱን በስሱ ወይም ለራሳቸው በሚመቻቸው መልኩ ያከናውኑታል ፡፡

እገዳ
 
‹‹ Nigeria Good People Great Nation ›› በሚል ርዕስ የሚጽፈው ብሎገር አማኑኤል አጁቡሉ የማህበራዊ ሚዲያ ቀበኛ ሀገሮችን ዘርዝሮ ጽፏል ፡፡ ፌስ ቡክ ፣ ዩቲዩብ ፣ ትዊተር እና ዊኪፒዲያን በመዝጋት ቻይናን የሚያህል የለም ሲል ያደረገቸውን ሚዛናዊነትንም ለመግለጽ በመሞከር ነው ፡፡ ቻይና ሚዲያዎቹን የዘጋችው የምዕራቡን ዓለም ተጽዕኖ ለመቋቋም ሲሆን በተነጻጻሪ የራሷን ሳይበር ኢንዱስትሪ በመፍጠር ተደራሽነቷን አረጋግጣለች ፡፡ ለአብነት ያህል Ozone የተባለው ማህበራዊ ገጽ 600 ሚሊየን አባላት አሉት ፡፡ Weibo የተባለው ሌላኛው ድረ ገጽ የቻይናን መልክ መላበሱ እንጂ ልክ እንደ ትዊተር ነው የሚሰራው ፡፡

እንደ ናይጄሪያዊው አማኑኤል ሁሉ ፍሪደም ሀውስ የተባለው ድርጅት በ 2012 ያጠናው መረጃ ኢትዮጽያን የብሎገር ፎቢያ እንዳለባት ጠቋሚ ነው ፡፡ 65 የዜናና አስተያየት፣ 14 የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ 7 የድምጽና ምስል ዌብሳይቶች፣ 37 ብሎጎችና 37 የፌስ ቡክ ገጾች ተዘግተዋልና ፡፡

ኢትዮጽያና አለምን ሲያጨቃጭቅ የነበረ ሌላ ክስተትም መጨመር ይቻላል ፡፡ የተወካዮች ምክር ቤት ባጸደቀው አንድ ህግ በሀገሪቱ ውስጥ ስካይፒና ጎግል ቮይስን መጠቀም እስከ 15 ዓመታት እንደሚያሳስር ተገልጾ ነበር ፡፡ በሌላ በኩል መንግስት ስካይፒ መጠቀም ህገወጥ ድርጊት አለመሆኑን ፣ ህገወጥ የሚሆነው ህገወጥ ጥሪዎችን ማከናወን መሆኑን አስተባብሏል ፡፡ በተለይ ከዚህ አጨቃጫቂ ዜና በኃላ ሀገሪቱ ፌስ ቡክ ፣ ትዊተርና የመሳሰሉ ማህበራዊ ገጾችን ልትዘጋ እንደምትችል በስፋት ሲወራ ቆይቷል ፡፡ የኢህአዴግ አባላትም ከስብሰባ በኃላ ፌስ ቡክ ላይ የተጣዱ ሰራተኞችን በመታዘብ ‹‹ ግድየም ለጥቂት ግዜ ተመልከቱ ?! ›› በማለት ጉዳዩ እያበቃለት መሆኑን ያረዱ ነበር ፡፡

ፌስ ቡክ በተለይም ከአቶ መለስ ዜናዊ ሞት በኃላ ብዙ የድርጅቱ ደጋፊዎችን አቁስሏል ፡፡ በአቶ መለስ ሞት ህልፈት ኢትዮጽያዊ ብቻ ሳይሆን ዓለም ማዘን ይገባዋል ብለው ራሳቸውን በማሳመናቸው በሳቸው ላይ ይሰጥ የነበረውን ትችት ባለመቀበል ይህን የአሉባልታ ማናፈሻ ማሽን ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ መከርቸም እንደሚገባ በትንሹም ሆነ በትልቅ ስብሰባ ላይ አጠንክረው አስተያየት ሰጥተዋል ፡፡ በፌስቡክ ላይ የተማረሩ አንዳንድ መ/ቤቶች ሚዲያው እንዲዘጋ ያደረጉ ሲሆን በምሳ ሰዓት ብቻ መጠቀም የሚቻልበትን መንገድ ያመቻቹም ድርጅቶቸች አሉ ፡፡ የወረደ አፈጻጸም አሳይተዋል የተባሉ አንዳንድ ሰራተኞችም    ‹‹ ፌስ ቡክን በማባረር ቢሆን አንደኛ ነህ ! ›› የሚል ግምገማዊ ፌዝ ተቀብለዋል ፡፡ የኢንተርኔት መስመር ለመዘርጋት ያቀዱ አንዳንዶች ደግሞ በፌስ ቡክ ተጠቃሚዎች እንዳንወረር በሚል ስጋት እቅዳቸውን አዘግይተውታል ፡፡ በተለይም እንደ ሀገራችን በምግብ እህል ራሳቸውን ያልቻሉ ታዳጊ ሀገሮች ልማትን እንጂ ፌስ ቡክንና ግብረ አበሮቹን በፍጹም ማስቀደም እንደሌለባቸው  የሚያስረዱ ምሁራዊ ጥናቶችም እዚህና እዚያ ቀርበዋል ፡፡ በዚህና በመሳሰሉ ምክንያቶች መንግስት ፌስ ቡክን ከርችሞ ስሙን ከነፓኪስታን ፣ ኢራን ፣ ሶርያ ፣ ቱርክ ፣ ታይላንድና የመሳሰሉት ተርታ እንደሚያሰልፍ ብዙዎች እየጠበቁ ነበር ፡፡

ያልተጠበቀ ለውጥ
 
ታዲያ ምን ተፈጠረ ?
ታይም መጽሄት በ2010 ያደነቀውን ፌስ ቡክ ዛሬ የኢትዮጽያ መንግስት እንዴትና ለምን ሊቀበለው ቻለ ? ማለት እንዴት ሊሰራበት ፈለገ ?

በቅርቡ የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጸ/ቤት በፌደራል ደረጃ ለሚገኙ ኮሙኒኬተሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና ሰጥቶ ነበር ፡፡ በስልጠናው በርካታ ጥናታዊ ወረቀቶች የቀረቡ ቢሆንም በውይይት ጎልቶ የወጣው ‹‹ አዲሱና ማህበራዊ ሚዲያ እንደ ተግባቦት ዘዴ ›› የሚለው ምዕራፍ ነበር ፡፡ ይህ ወረቀት በአጭሩና በጥቅሉ ሚዲያው ችግር ቢኖርበትም ጥቅሙን አጠናክሮ ለገጽታ ግንባታ መስራት የማይሸሽና የግዜው አማራጭ መሆኑን አስረድቷል ፡፡ የኮሙኒኬተር ባለሙያዎች የመ/ቤታቸውን ተግባር ብቻ ሳይሆን አጨቃጫቂውን የአባይ ግድብ የተመለከቱ መረጃዎችን ማሰራጨት እንደሚገባቸውም ተመልክቶ ነበር ፡፡
የፌስ ቡክና ማህበራዊ ሚዲያ ጉዳይም ተወካዮች ም/ቤት ደርሶ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ግንዛቤ እንዲያገኙበት ተደርጓል ፡፡ ዲፕሎማትና የአለም አቀፍ ባለሙያ የሆኑት አምባሳደር ቶፊክ አብዱላሂም በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ‹‹ የግብጽ ወጣቶች ፌስ ቡክና ትዊተር በጣም ይጠቀማሉ ፡፡ ኢትዮጽያዊያን ከግብጻዊያን ጋር እነዚህን ሚዲያዎች በመጠቀም በአባይ ወንዝ ፍትሀዊ አጠቃቀም ላይ መወያየት አለብን ፡፡ ወጣቱና የተማረው ትውልድ የግብጽ ህዝብን ለማሳመን መነሳት አለበት ›› በማለት አቅጣጫ ጠቋሚ አስተያየት ሰጥተዋል ፡፡
ግራም ነፈሰ ቀኝ የመንግስት አቋም እየተቀየረ መጥቷል ፡፡ የአቅጣጫውን ለውጥ ያመነጨው አባይ ወይስ ነባራዊው እውነት የሚል መከራከሪያ ማንሳት ግን አሁንም ይፈቀዳል ፡፡ መንግስት ከማህበራዊ ሚዲያዎች ጋር ሙሉ ለሙሉ መጋባት ባይፈልግ እንኳ ከተጨባጩ እውነት ጋ አዛምዶ ፍላጎቱን ለማሳካት እንደ አጋር ሊጠቀምበት ግድ ይለዋል ብሎ ማስቀመጥ ይቻላል ፡፡

የማይሸሸው እውነት
 
በአሁኑ ወቅት ተለምዷዊ በሚባሉት ሚዲያዎች / ጋዜጣ ፣ ሬዲዮ፣ ቴሌቭዥን / ብቻ በመታገዝ ማንነትን ለዓለም ማስተዋወቅ አይቻልም ፡፡ ማህበራዊ ሚዲያን ለመጠቀም የሚያስገድዱ በርካታ እውነቶችን ቴክኖሎጂው እያቀበለን ይገኛል ፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት 751 ሚሊየን ህዝብ ሞባይል ይጠቀማል ፡፡ በ20 ደቂቃዎች አንድ ሚሊየን መረጃዎች ሼር ይደረጋሉ ፡፡ በ20 ደቂቃዎች ሁለት ሚሊየን 176 ሺህ መልዕክት ይላካል ፡፡ በ20 ደቂቃዎች 10 . 2 ሚሊየን እስተያየቶች ይጻፋሉ ፡፡ በ20 ደቂቃዎች አንድ ሚሊየን 484 ሺህ የሁነት ማስታወቂያዎች ይለጠፋሉ ፡፡

ይህን አሐዝ ወደ አህጉራችን ጠጋ አድርገን መመልከትም ይገባል ፡፡ እንደ ‹‹ The internet coaching library ›› መረጃ መሰረት በአፍሪካ ከኢንተርኔት አልፎ የፌስ ቡክ ተጠቃሚው ቁጥር በሚያስገርም ሁኔታ እየጨመረ መጥቷል ፡፡ በዚህ መሰረት ፣

ግብጽ - 12 ሚሊየን 173 ሺ 540
ናይጄሪያ - 6 ሚሊየን 630 ሺ 200
ደቡብ አፍሪካ - 6 ሚሊየን 269 ሺ 600 ፌስ ቡክ ተጠቃሚዋችን በማስመዝገብ ትልቁን ደረጃ ይዘዋል ፡፡ ሞሮኮ ፣ አልጄሪያና ቱኒዚያ በቀጣዩ ቅደም ተከተል ውስጥ የሚገኙ ሀገሮች ሲሆኑ ኢትዮጽያ በ 10 ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች ፡፡ 902 ሺ 440 በማስመዝገብ ፡፡

በአጠቃላይ ከሁለት መቶ በላይ ድረ ገጾችን ከምታስተናግደው ዓለም ርቆ ፖለቲካንም ሆነ መረጃን በሚፈለገው ልክ ማሰፋት አይሞከርም ፡፡ በተለይም 1 . 11 ቢሊየን ተጠቃሚ ካለው ፌስ ቡክ ፣ 500 ሚሊየን ተመልካች ካለው ትዊተር ፣ 225 ሚሊየን ከሚጎበኘው ሊንክደን ፣ 345 ሚሊየን ተመልካች ካለው ጎግል ፕላስ ቁርኝት አለመፍጠር የነገን መንገድ ካለማወቅ ጋር የሚገናኝ ነው ፡፡ እንግዲህ መንግስት እየቆየም ቢሆን በግድ መቆርጠም እንዳለበት የተረዳው እውነት ይህን ያህል ከድንጋይ የጠጠረ እንደሆነ መረዳት አይከብድም ፡፡

የመንግስት የቤት ስራ
 
‹ ወንድ ወደሽ ጺም ጠልተሸ አይሆንም › እንዲሉ ትግሬዎች ማህበራዊ ሚዲያዎችን ለገጽታ ግንባታ የመጠቀም ፍላጎት ካየለ ግራና ቀኙን ለመቀበል ዝግጁ መሆንን ይጠይቃል ፡፡ ቀኙ ከአዎንታዊ ውጤት ጋር የተያያዘ በመሆኑ የአደናቃፊነት ሚና ላይታይበት ይችላል ፡፡ ምናልባት የኮብል ስቶኑ መንገድ ካልተመቸ አስፋልት የማድረግ ስራ ይጠበቅ ይሆናል ፡፡ በርግጥ ማህበራዊ ሚዲያ ገጽታን ለመገንባት ፣ የገቢ ምንጭ ለማስፋት ፣ የሚዲያዎቻችንን ክፍተት ለመሙላት ፣ የዴሞክራሲና ስርዓቱን ለማጠናከር ፣ የገለሙ አሰራሮችን ለማጋለጥና ለመለወጥ ፣ የጦር ወንጀለኞችን ለማደን / ጆሴፍ ኮኒን ያስታውሷል / ፣ ምርጫን ፍትሃዊ ለማድረግም ሆነ ለማሸነፍ ፣ አምባገነኖችን ለመፈንገልና ለመሳሰሉ ጉዳዮች የላቀ ጥቅም ይሰጣል ፡፡

 ከላይ ለመጠቃቀስ እንደተሞከረው ጥቃቅኑ ችግር ገለል ሲደረግ ከስር አድፍጦ የሚገኘው ትልቁና ፖለቲካዊ ስጋቱ ወይም የግራ / ግራጋቢው / ክፍል ነው ፡፡ ማህበራዊ ሚዲያ በከፍተኛ ደረጃ የትግል መሳሪያ መሆን የጀመረው የ 26 ዓመቱ ቱኒዚያዊው ሞሀመድ ቦዋዚዝ መልካም አስተዳደር ማስፈን ያልቻለውን መንግስት ለመቃወም ራሱን በአደባባይ ካቃጠለ በኃላ ነበር ፡፡ እነዚህ ሚዲያዎች በአረብ አገራት ጭቆናና ኢ-ፍትሃዊ አሰራርን ለመዋጋት ትልቅ አስተዋጽኦ የፈጠሩ ናቸው ፡፡ በግብጽ፣ ቱኒዝያና የመን በመሳሰሉ ሀገሮች በርካታ የተቃውሞና የአመጽ ጥሪዎች ተቀናብረው የተሰራጩት በፌስ ቡክና ትዊተር ነው ፡፡ አንድ የግብጽ አክቲቪስት ‹‹ ፌስ ቡክን ለተቃውሞ ፣ ትዊተርን ለማስተባበር ዩትዩብን ደግሞ ለዓለም ለመንገርና ለማሳየት እንጠቀምበታለን ›› ማለቱን ማስታወስ ይጠቅማል ፡፡ 

በግብጽ የሚታየውን ተደጋጋሚ ትግል መነሻ በማድረግም ብዙ ዘጋቢዎች ‹‹ የፌስ ቡክ አብዮት ›› እስከማለት ደርሰዋል ፡፡ በማህበራዊ ድረ ገጾች ጥናት ያደረገቸው ማርቲን ማህበራዊ ሚዲያ የትግል መነሳሳቱ እንዲጠናከርና የግዜ ማዕቀፍ እንዲያበጅ እገዛ አድርጓል ባይ ናት ፡፡ ዜጎች የጭካኔ ተግባራት ፣ የፍትህ መጣስና መዛባት፣ የሰቆቃ ህይወት በስፋት መኖሩን እንዲገነዘቡ ብሎም የፍርሃት ስነ ልቦናቸው እንዲወገድ ትልቅ ሚና ተጫውቷል ፡፡ ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው በርካታ አክቲቪስቶችም ‹‹ እነዚህ መሳሪያዎች ባይኖሩ የሙባረክ መንግስትን የመገልበጡ ሂደት በርካታ አመታቶችን ይፈልግ ነበር ›› ብለዋል ፡፡

ስለሆነም መንግስት በሁለቱ ጥቅሞቹና ጉዳቶቹ መካከል መንገዱን አስተካክሎ መጓዝ ይኖርበታል ፡፡ ችግሩን ተቀብሎ ሊያስተካክል ፣ ብርታቱን ሊመረኮዝበት እንደሆነ ሊያጤን ግድ ይለዋል ፡፡ ‹ ወንድ ወደሽ ጺም ጠልተሸ አይሆንም › የሚባለው ተረትም ቅርጹና መልዕክቱ ይኀው ነው ፡፡

››››                               ››››                                    ›››››                                  ››››

አዲስ ራዕይ መጽሄት ፡፡

የፌስ ቡክ ተጠቃሚ የሆነውን ከተማ ቀመስ ህዝብ የ 2006 ምርጤና  ነውጤ በማለት ስያሜ ይሰጣል ፡፡ ምርጦቹ  ‹ ልማታዊ ተጠቃሚዎች › የሚል የክብር ማዕረግ የሚያገኙ ሲሆን ነውጤዎቹ  ‹ ጥገኛ ተጠቃሚዎች › የሚል  ባርኖስ ይከናነባሉ ፡፡

የመጽሄቱ ውዳሴ ፡፡

ልማታዊ ተጠቃሚዎች በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ የሚወጡ ጸረ ልማት ዜናዎችን ፣  ዘገባዎችን ፣ ፎቶዎችንና ፊልሞችን ከፍተኛ ትዕግስት በመጠቀም አይቶ እንዳላየ በመዝጋት … እነዚህን ተውሳክና ተዛማች ሀሳቦች ባሉበት ቀጭጨው እንዲቀሩ LIKE እና  SHARE ባለማድረግ እንዲሁም COMMENT ባለመስጠት ሀገራዊ ግዴታቸውን ተወጥተዋል ፡፡

ዘላለማዊ ክብር ለመስመርተኞች !!




Monday, August 12, 2013

ጠይሟ ልዕልት !!




ጠይሟ ልዕልት
የሩጫው ድማሚት
ሰዓት ጠብቃ ስትፈነዳ
አንድም ታምራለች እንደ ጽጌሬዳ
አንድም ታርዳለች እንደ ካባው ናዳ ፡፡
ጠይሟ ቀስተ ዳመና
ባለብዙ ልዕልና
የስንቱን አይን በረገደች ?
በወቸው ጉድ በለጠጠች ::
የስንቱን ልብ አሞቀች ?
በፍቅር መዳፍ ጣለች ::
እናትስ ትውለድ ያንቺን አይነቱን አቦሸማኔ
ህዝብ የሚወድ አስተኔ  ፡፡
ለሀገር የሚሞት ወያኔ ፡፡

Sunday, July 28, 2013

‎የኃይሌ ገብረስላሴ መንገድ የት ያደርሳል ?‎



የአትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የህይወት ቅደም ተከተል ባልተጠበቀ መልኩ መጓዝ በመጀመሩ ይመስላል ሰሞኑን በህዝቡ ውስጥ ትልቅ የመወያያ አጀንዳ ሊሆን የበቃው ፡፡ ለመሆኑ የሚጠበቀው ቅደም ተከተል ምን ነበር ? የሚል መሰረታዊ ጥያቄ እንደሚነሳ እንጠብቅ ፡፡

በአሰላ አንድ ተራራማ መንደር የተወለደው ኃይሌ ወደ ት/ቤት ለመጓዝ ረጅም ርቀት መጓዝ ይጠበቅበት ነበር ፡፡ የህይወት አርጩሜ ዘወትር እንዲሮጥ ብታስገድደውም እሱ ባያውቀውም በጥንካሬ ለሌላ ዕድል እያዘጋጀችው ቆይታለች፡፡ እናም ፤
. በ15 ዓመቱ ውድድር ጀመረ ፡፡
. ከአራት ዓመት ቆይታ በኃላ ደቡብ ኮሪያ በተካሄደው ጁኒየር ሻምፒዮን በ 5 ሺህ እና 10 ሺህ ሜትር ሩጫ አሸነፈ ፡፡
. ከዛማ ምኑ ቅጡ ? ሁለት ግዜ በኦሎምፒክ ፣ አራት ግዜ በአለም ሻምፒዮንሺፕ ፣ ለአራት ተከታታይ ግዜ በበርሊን ማራቶን ማሸነፍ ችሏል ፡፡ አያሌ የብሄራዊና ዓለማቀፍ ውድድሮችን የሩጫ ሪከርድ ሰባብሯል ፡፡
. በውድድር መፈተን ብቻ ሳይሆን በዕድሜ መግፋት ሲጀምር ደረጃውን ቀየረ ፡፡ በ2006 ግማሽ ማራቶን አሸነፈ ፡፡
. በ 2007 አዲስ የማራቶን ሪከርድ ማስመዝገብ ችሏል ፡፡

በ 43 ዓመቱ በሞስኮ ኦሎምፒክ በማራቶን ለመሳተፍ ይፈልጋል ፡፡ ከወጪ ቀሪ ስናወራርድ ኃይሌ በ 28 ዓመታት ውስጥ በስፖርት መድረክ በተለይም በረጅም ርቀት ውስጥ ነግሶ ቆይቷል ፡፡ ከዚህ በኃላ ይህን የሩጫ ንጉስ አብዛኛው ህዝብ ይጠብቅ የነበረው / የንግድና ኢንቨስትመት ስራው እንደጠበቀ ሆኖ / በዚሁ መደዳ እንደሚገኝ ነበር ፡፡ ማለትም ፤

. በሩጫ አስልጣኝነት
. በአትሌትክስ አማካሪነት
. በስፖርት ጥናትና ምርምር
. እንደ አቶ ይድነቃቸው ተሰማ በአፍሪካ የስፖርት ተወካይነት
የሩጫው ንጉስ ግን ለ cctv ቴሌቪዥን እንዲህ አለ ‹‹ የአጭር ግዜ እቅዴ ለፓርላማ አባልነት መወዳደር ነው ፡፡ አንድ ቀን ደግሞ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት መሆን እፈልጋለሁ ››

የንጉሱ መሰረታዊ ምክንያት ?
 
አጃንስ ፕሬስ እንደዘገበው ኃይሌ ወደ ፖለቲካው መቀላቀል የሚፈልገው በፖለቲካው አማካኝነት ወደ ህብረተሰቡ ለመቅረብና ህብተረሰቡን ለመርዳት ነው ፡፡ ለፓርላማ የሚወዳደረው በግል ውክልና ነው ፡፡ ባለቤቱና ቤተሰቦቹ በኢትዮጽያ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፉን ባይወዱለትም እሱ ግን ራስን ከፖለቲካ ማራቅ ‹‹ ትልቅ ስህተት ›› ነው ባይ ነው ፡፡ ‹‹ እዚህ እስካለንና እዚህ እስከኖርን ድረስ በርካታ ችግሮቻችንን በመለየት በመፍትሄው ዙሪያ የራሳችንን ድርሻ መወጣት አለብን ›› በማለት ጽኑ እምነቱን ለማጠናከር ሞክሯል ፡፡

ውሃ የሚቋጥረው ምክንያት የማነው ?
 
ኃይሌ እንደ ሩጫው ሁሉ በተሰማራባቸው የንግድ መስኮች ውጤታማ ነው ፡፡ በሆቴል ፣ በመኪና ንግድ ፣ በህንጻ ኪራይ ፣ በሲኒማ ቤትና በታላቁ ሩጫ ዝግጅት  እያደረጋቸው ያሉት ዘርፈ ብዙ እንቅስቃሴዎችን መጠቃቀስ ይቻላል ፡፡ በቅርቡ በ 70 ሚሊየን ብር ካፒታል ወደ ቡና አምራችነት ጎራ የተቀላቀለ ሲሆን ማርን የመላክ ስራ ውስጥም ለመሳተፍ ዕቅድ እንዳለው ተመልክቷል ፡፡

የእነዚህ የተሳኩ ድምር ውጤቶች ግን በፖለቲካው መስክም ይደገማሉ ማለት ይከብዳል ፡፡ በርግጥ በኛ ሀገር ፖለቲከኛ ለመሆን የፖለቲካ ዲግሪ የግድ አለመሆኑ ያለፉት መንገዶቻችን ይጠቁማሉ ፡፡ አቶ መለስ ዜናዊም በአንድ ወቅት ለሹመት ከትምህርት ይልቅ ታማኝነት ሚዛን እንደሚደፋ አስረግጠው ተናግረዋል ፡፡ በርግጥ በእጅጉ የሚታወቀው ጆርጅ ዊሃ በርግጠኝነት አሸንፋለሁ በሚል ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውስጥ ገብቶ ያልተማረ አይመራንም … ዊሃን ያደነቅነው እግሩን እንጂ ጭንቅላቱን አይደለም በሚል የላይቤሪያ ህዝብ ካርዱን በሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ለተከታተሉትና በዓለም ባንክ ላገለገሉት ኤለን ጆንሰን ሰጥቷል ፡፡ ዊሀም ከዛ በኃላ ሚያሚ በሚገኘው ዴሪ ዩኒቨርስቲ የቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ትምህርት መከታተል ጀምሯል ተብሏል - ዛሬ ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ባይታወቅም ፡፡ እናም ለኃይሌ ስጋት የሚሆነው የትምህርት ዲግሪና / የክብር ያልሆነ / ፖለቲካዊ ዕውቀት አይሆንም ማለት ነው ፡፡ የሚከብደው ፖለቲካዊ  ተደራሽነቱን ለማረጋገጥ የመረጠበት መንገድ በእጅጉ አጠያያቂ ከመሆኑ ላይ ነው ፡፡

ኃይሌ በርካታ የመልካም አስተዳደር ህጸጾች ፣ የተንጠለጠሉ የዴሞክራሲ ጥያቄዎች ፣ የሰብዓዊ መብት ጉደለቶች ፣ የድህነት ማነቆዎች ያሉበት ህብረተሰብ ጋ ደርሶ መፍትሄ ለማምጣት የመረጠበት መንገድ የግል እንደራሴ በመሆን ነው ፡፡ በሀገራችን የፖለቲካ ታሪክ በግለሰብ ከተወከሉት ውስጥ ሻለቃ አድማሴ ዘለቀ ፣ አቶ በድሩ አደም እና ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንዲሁም የተቃዋሚው ብቸኛ ተወካይ አቶ ግርማ ስይፉ ትላልቅ ሀሳቦችን ሲያሰሙ ቢቆዩም ‹ አንድ እንጨት አይነድም › የሚለውን ብሂል እውነተኛነት ከማረጋገጥ ውጪ የፈጠሩት ነገር በጉልህ የተጻፈ አይደለም ፡፡ በርግጥ በደማቅ ሙሉ ቀለም በተቀባው ፓርላማ ውስጥ ሌላ ቀጭን ሰረዝ እንዲታይ መፍጠራቸው ለተቃራኒው ወገን ሊጠቅም ይችላል ፡፡

ችግሮችን በመጠቆም ለህብረተሰቡ የድልድይነት ፣ ለመንግስት ደግሞ የመስታውነት ሚና ይጫወታሉ ቢባል እንኳ መንግስት በግል ተወካዮች የቀረቡትንና የተጠኑትን ትላልቅ ሀሳቦችና ውጥኖች ዕውቅና በመስጠት አይደለም ለተግባራዊነቱ የሚንቀሳቀሰው ፡፡ ጉዳዩ ለድርጅቱ አንድ የድጋፍ ካፖርት የሚደርብ ከሆነ በድርጅቱ ልዩ ታፔላ ዳር እንዲደርስ ይደረጋል ፡፡ እናም የትኛውም ድርጅት ቢሆን መነሻ ሀሳቡና ግጥሙ ‹‹ የተከበሩ የም/ቤት አባል የአቶ እገሌ ነው … ›› ብሎ እንደ ነጠላ ሙዚቃ እንደለቀቀ ድምጻዊ እውቅና ለመስጠት አይጨናነቅም ፡፡ ካልፈለገም ገና ከመጀመሪያው እንዳልሰማ ሆኖ የማለፍ መብቱ የተጠበቀ ነው ፡፡ በዚህ የአጣብቂኝ አካሄድ የግል ተመራጭ ህብረተሰቡን ከመስማትና ከንፈሩን ከመምጠጥ ውጪ ምን የሚያመጣው ተጽዕኖ አለ ለሚለው ጥያቄ ደፋር ምላሽ ለማምጣት ይቸግራል ፡፡ ለዚህም ነው ይህ አይነቱ የፓርላማ ውክልና እና ተፈላጊው ራዕይ ምን ያህል ውሃ የሚቋጥር ነው የሚያሰኘውም ?

የኃይሌ ሌላኛው ራዕይ ‹‹ ፕሬዝዳንት ›› መሆን ነው ፡፡ ፕሬዝዳንት በመሆንስ ህብረተሰቡን ቀርቦ ካለበት ህመም መፈወስ ይቻላል ? ፕሬዝዳንቱ ዘወትር ሩህሩህና አዛኝ ድምጾች ቢኖራቸው በገዢው ፓርቲ ፖሊሲ ፣ ስትራቴጂና ይሁንታ ላይ ተጽዕኖ የመፍጠር አቅም አላቸው ? የእነዚህ ጥያቄዎች ትክክለኛ ምላሽ የሀገሪቱን የፖለቲካ ስርዓት በአግባቡ ከማወቅና ካለማወቅ የሚመነጭ ነው የሚሆነው ፡፡

የፕሬዝዳንትነት በትረ መኮንን

የኢፌዴሪ ህገመንግስት የሀገሪቱን ፕሬዝዳንት ‹‹ ርዕሰ ብሄር ›› ብሎ ቢጠራም ትልቁን ስልጣን የሰጠው ለጠ/ሚ/ሩ ነው ፡፡ ጠ/ሚ/ሩን የሚሰይመው ደግሞ አብላጫ የፓርላማ ወንበር ያለው የፖለቲካ ድርጅት ነው ፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 71 መሰረት ፕሬዝዳንቱ የተሰጡት ስራዎች ሰባት ናቸው ፡፡ ከነዚህም መካከል የሁለቱ ምክር ቤቶች ዓመታዊ ስብሰባን መክፈት … ያለቀላቸውን ህጎችና ስምምነቶችን በነጋሪት ጋዜጣ እንዲወጡ ማወጅ … በጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚቀርብለትን አምባሰደሮችና ሌሎች መልዕክተኞች ሹመት ማጽደቅ … እንግዶችን ቢሮ ቁጭ ብሎ መቀበል … ሜዳሊያና ሽልማት መስጠት እና ይቅርታ ማድረግ ይገኙበታል ፡፡

እነዚህን ስራዎች ጣጣው እንዳለቀለት የአምባሳደር ሙሉ ልብስ ወይም ተፈትፍቶ ጉርሻን በጉጉት እንደሚጠብቅ የአድአ እንጀራ ልትቆጥሩት ትችላላችሁ ፡፡ የመጀመሪያው መሰረታዊ ጉዳይ ፕሬዝዳንቱ በወሳኝ ሁነቶች ውስጥ ራሱን ሊያሳትፍና እኔም ነጥብ ሊያዝለት የሚገባ ልዩ ድምጽ አለኝ ለማለት የሚያስችለው መፈናፈኛ የሌለው መሆኑ ሲሆን ሁለተኛውና ዋነኛው ግን እነዚህንም በህግ የተቀመጡ ስራዎች ለመስራት የመረጠው ፓርቲ ይሁንታ ማስፈለጉ ነው ፡፡ በህገመንግስቱ ድንጋጌ መሰረት አንድ ሰው ፕሬዝዳንት ሆኖ የሚሾመው በሁለቱ ፓርላማዎች የጋራ ስብሰባ ሁለት ሶስተኛ እጅ ካገኘ ብቻ ነው ፡፡

አንድ በምርጫም በቁንጥጫም ስልጣን የጨበጠ ፓርቲ ደግሞ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት እንዲሆንለት የሚፈልገውን ግለሰብ የሚመርጠው የአይኑ ቀለም ስላማረው ወይም ታዋቂ ስለሆነ ብቻ አይደለም ፡፡ ፖሊሲውን የሚያስፈጽም ፣ ፓርቲውን የሚያሞግስ ያለፈውን ስርዓት በጥፊ የሚያቀምስ … በክፉ ቀን ዎሽቶም ቢሆን የሚደግፈው እንዲሆን ይፈልጋል ፡፡ ከዚህ ውጪ ትላልቅ ህጸጾችን ቢመለከት እንኳ በየሄደበትና በአጋጣሚው ሁሉ ‹ ዘራፍ ! አጉራ ጠናኝ - አሁንስ መንግስቱን መሰልከኝ ! › ምናምን የሚሉ ጉርምርምታዎቹን በደረቅ ውስኪ ተጉመጥሙጦ መዋጥ ይጠበቅበታል ፡፡ ወይም ዝቅ ባለ ድምጽ የችግሩን አሳሳቢነት በትህትና መጠቆም ይኖርበታል ፡፡ ልክ እንደ ቢሮክራቱ የቢሮ ደብዳቤ - ከሰላምታ ጋር ! መባሉንም ሳይዘነጋ፡፡ለነገሩ ፕሬዝዳንቱ በተቃራነው እየተንጋደደ የሜሄድ ከሆነ ፓርቲው ለምንስ በዕጩነት ያቀርበዋል ? አጉል ባህሪው እያደር የተገለጠም ከሆነ ጸጥ እንዲል የሚያስችሉ መፍትሄዎች 1001 ያህል ስለሆኑ ብዙም አያስጨንቅም ፡፡ ስለዚህ ለፓርቲው ታማኝነቱ ወይም በውስጠ ታዋቂነት ደጋፊነቱ የግድ ይመስላል ፡፡

እንግዲህ ፕሬዝዳንትነት የገባ የወጣውን ስቆ ከመቀበል ፣ ዋንጫ ከመስጠትና የተሰፋ የመክፈቻ ንግግር ከማድረግ ፣ ውጭ ሀገር ከመጎብኘትና ከምግባረ ሰናይ ድርጅቶች የክብር ኒሻን ከመጠበቅ ዉጪ ምን የተረፈ ውጤት አለው ? በርግጥ ኃይሌ ፕሬዝዳንት ከሆነ ሊሻሻሉ ወይም ሊለወጡ የሚችሉ ጥቃቅን አሰራሮች ይጠፋሉ ማለት አይደለም ፡፡

የ First Lady ጉዳይ አንዱ ይመስለኛል ፡፡ First Lady መባል ያለበት የፕሬዝዳንቱ ወይስ የጠቅላይ ሚንስትሩ ባለቤት ? ስልጣኑን ሁሉ ጠቅልሎ የያዘው የሀገራችን ጠ/ሚ/ር ይህንን የክብር ስያሜ ቢያንስ ሚስት ላለው ፕሬዝዳንት መልቀቅ ይኖርበታል ፡፡ በዶ/ር ነጋሶ ዘመን ሚስታቸው የውጭ ዜጋ በመሆኗ ፣ ፕሬዝዳንት ግርማ ደግሞ ሚስት የሌላቸው መሆኑ እንጂ ቦታው ተቀምቶ አይደለም የሚል ያልተረጋገጠ ሀሳብም ስላለ ይህንን ዕቅድ የተሳካ ማድረግ የሚቻል ይመስላል ፡፡ እና ሚስትንና ልጆችን ይዞ በየሀገሩ መዝናናት ፣ በተከበረ የራት ግብዣ ላይ መናገርና ከአቻ ጋር መፎጋገር ፣ በማርሽ ባንድ መታጀብ ፣ በክብር ዘብ መሃል መንጎማለል ፣ የክብር መድፍ ማስተኮስ … ግዴላችሁም እቺኛው ክፍል የምታስመረቅን ሳትሆን አትቀርም ፡፡ በአጠቃላይ ግን ፕሬዝዳንት በመሆን ትርጉም ያለው ለውጥ ሊፈጠር የሚችለው ለህብረተሰቡ ነው ወይስ ለራሱ ለፕሬዝዳንቱ ክብርና ዝና ? የሚል ጥያቄ ያስከትላል ፡፡

ስውር ተጽዕኖዎች
   
                                                  
ከሁሉ አስቀድሞ እያንዳንዱ ሰው በፈለገው መስክ የመሰማራትና ህልሙን የመፈለግ መብት ያለው በመሆኑ የኃይሌን የፖለቲካ ተሳትፎ ማንም መቃወም የማይችል መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል ፡፡ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነው እውነታ የኃይሌ የፖለቲካ ተሳትፎ ሳይሆን ያስቀመጣቸው ሀሳቦች ናቸው ፡፡ እንደራሴ ወይም ፕሬዝዳንት በመሆን ህብረተሰቡን ይበልጥ እጠቀማለሁ የሚሉት ፡፡ የሙግቱ ባቡሩም እንዴት ይቻላል ? በሚለው ሃዲድ ላይ የሚያተኩር ይሆናል ማለት ነው ፡

አሁን ባለው የፖለቲካ መዋቅር እንደሌሎች ሀገሮች በግል ተወዳድሮ ፕሬዝዳንት መሆን አይቻልም ፡፡ በጣም የሚከበርና የሚደመጥ ሴናተር ለመሆንም መንገድ የለም ፡፡ ይህ ቢቻል በርግጥም ታዋቂ ግለሰቦች ለውጥ ለመፍጠር ቅርብ ይሆኑ ነበር ፡፡ ኃይሌ እኛ በምንከተለው የፖለቲካ ስርዓት ፍላጎቱን ዕውን ለማድረግ የማይቻለው ከሆነ ቢያንስ በአንደኛው ውጤት ለመጽናናት የፈለገ ይመስላል ፡፡ ፕሬዝዳንት በመሆን ክብርና ዝና ለመጎናጸፍ ፡፡

ይህ ክብር ለአንዳንድ ታዊቂዎች ካላቸው ሀብት በላይ ነው ፡፡ ለምሳሌ ያህል የሰውነት ቅርጽ ተወዳዳሪና የፊልም አክተር የሆነው አርኖልድ ሸዋዚንገር የካሊፎርንያ ገዢ ሆኖ በየዓመቱ የተፈቀደለትን 175 ሺህ ዶላር አይቀበልም ነበር ፡፡ በሀብት ጫፍ የደረሱ አንዳንድ አትሌቶችና ስፖርተኞች ከሙያቸው ወደ ፖለቲካ ሲዞሩ ከፍተኛ ክብርና ርካታ አግኝተዋል ፡፡ ጋዜጠኛ ሲያረጅ ጸሀፊ ይሆናል እንዲሉ አትሌቶች ሩጫ በማቆሚያቸው ወቅትም ዝናቸው የሚቀጥልበትን ሰንሰለት ቢጠግኑ አይገርምም ፡፡

ለሁለት አስር ዓመታት አለማቀፍ የክሪኬት ተጫዋች ሆኖ ያገለገለው ፓኪስታናዊው ኢምራን ካህን ወደ መጨረሻው Movement For Justice የተባለ ድርጅት እስከማቋቋም ደርሶ ነበር ፡፡ በግንቦት 2013 ፓርቲው 35 መቀመጫ ሲያገኝ አንዱ ተመራጭ ሆኗል ፡፡ PEW የተባለ የምርምር ማዕከል በሰራው የ 2012 ጥናት ከአስር ፓኪስታናዊ ሰባቱ ለካህን ጥሩ አስተያየት አላቸው ፡፡

የእንግሊዙ መካከለኛ ርቀት ሯጭ ስባስቲያን ኮ አራት የኦሎምፒክ ሜዳሊያዎችን አሸንፏል ፡፡ በ1979 ሶስት የዓለም ሪኮርዶችን በ 41 ቀናት ልዩነት ውስጥ ማሻሻል ችሏል ፡፡ ኮ ራሱን ከሩጫው ዓለም ሲያገል ወግ አጥባቂውን ፓርቲ በመወከል ከ 1992 እስከ 1997 ድረስ የፓርላማ አባል ሆኖ አገልግሏል ፡፡ እንግሊዞች ይህን ድንቅ ሯጭ የህይወት ዘመን የም/ቤት አባል አድርገው ሾመዋል ፡፡ እንግሊዝ በ 2012 ለማግኘት የቋመጠችውን የኦሎምፒክ አዘጋጅነት ፉክክር በብቃት የመራ ሲሆን የኦሎምፒክ ጨዋታ ኮሚቴን እንዲመራም ኃላፊነቱን አግኝቶ ነበር ፡፡ የቢቢሲ ስፖርት ዝግጅትም በታህሳስ 2012 የዓመቱ ምርጥ ሰው በማለት ሸልሞታል ፡፡

ታዋቂው የብራዚል ተጫዋች ዚኮ በ 1990ዎቹ የስፖርት ሚንስትር እስከመሆን ደርሷል ፡፡ የቶተንሃም ተጫዋች ሮማን ፓብሊቼንኮ የፑቲንን ‹‹ United Russia  ›› ን በመወከል በ 2007 ተወዳድሮ ለከተማ ም/ቤትነት ተመርጧል ፡፡ በ 1995 የዓለማችን ምርጥ ተጫዎች የሚል ክብር ያገኘው ጆርጅ ዊሃ ለፕሬዝዳንትነት ተወዳድሮ ህልሙ በኤለን ጆንሰን ጨንግፏል ፡፡ ስለ አሉሚናቲ ማህበረሰብ በርካታ ሚስጥራዊ መጻህፍትን የደረሰው ዴቪድ አይክ ተስፋ የተጣለበት የኮቨንተሪ ሲቲ በረኛ ነበር ፡፡ 38ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጌራርልድ ፎርድ የሁለት ግዜ የአሜሪካ እግር ኳስ ሻምፒዮን ነበሩ ፡፡
ወደ ፖለቲካው ጎራ የተቀላቀሉ ሌሎች ታዋቂ አትሌቶችን መጠቃቀስ ይቻላል ፡፡ ምሩጽን አይቼ ነው ወደ ሩጫው የተገፋፋሁት የሚለው ኃይሌ አውቆም ሆኖ ሳያውቀው እነ ስባስቲያን ኮ ተጽዕኖ ቢያደርጉበት አይገርምም ፡፡

የድርጅት ጥላ
 
ከፓርላማ መራቅ ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› ነው የሚለው ኃይሌ ከግል ተወዳዳሪነት ዉጪ የድርጅት አባልነትን የማይታሰብ መሆኑን ተናግሯል ፡፡ ምናልባት እዚህ ላይ ራሱ የተናገረው ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› ለራሱም የሚሰራ መስሏል ፡፡
በሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ በግል መወዳደር የግል ታዋቂነትንና ዝናን ከመጨመር ዉጪ ፖለቲካዊ ፋይዳ እንደሌለው ከላይ አይተናል ፡፡ ኃይሌ በግሉ ከሚወዳደር ይልቅ እንደ ፓኪስታናዊው ኢምራን ካህን የራሱን ድርጅት ማቋቋም አሊያም ከገዢው ወይም ከተቃዋሚ ድርጅቶች ሰፈር ጎራ ቢል ይመረጣል ፡፡ እንደዚያ ሲሆን ነው የእውነት ህብረተሰቡን ሊቀርብና ለውጥ ሊያመጣለት የሚችለው ፡፡

ለምሳሌ ያህል ኢህአዴግ ውስጥ ታቀፈ እንበል ፡፡ የድርጅት ጥላ ካገኘ በጣም ቢያንስ ባካባተው ሰፊ ልምድ መሰረት አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ወይም ስፖርት ኮሚሽን ውስጥ በኃላፊነት ለመሾም ምቹ ሁኔታ ይፈጠራል ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ያደፈውን አሰራር ለማጥራት እንዲሁም በህልሙ የያዛቸውን አዳዲስ አሰራሮች እውን ለማድረግ ይመቻል ፡፡ ይህም ለውጥ ስለሚያስገኝ የስንት ዓመት የውጤት ጥማት ያለበትን ህብረተሰብ ታደገ ማለት ይሆናል ፡፡ ስለዚህ እውነተኛ ፖለቲከኛ ለመሆን ከቆረጠ አካሄዱ ‹‹ ታላቅ ስህተት ›› እንዳይፈጥር መመርመር ይኖርበታል ፡፡

የትኛው መስመር ?

በርግጥ ኃይሌ የትኛውን መስመር ቢከተል ነው ህብረተሰቡን ይበልጥ መቅረብና መርዳት የሚችለው ?
. ኢንቨስትመንቱን በማስፋፋት
. የበጎ አድራጎት ስራን በማጠናከር
. ሙያዊ ልምዱን በመመንዘር
. የፕሬዝዳንትነት ካባን በመላበስ …  ????????


ማስታወሻ፡- ይህ ፅሑፍ በቁም ነገር መፅሔት ቅፅ 12 ቁጥር 157 ላይ የወጣ ፅሑፍ ነው፡፡ ፅሑፉን በሌላ ሚዲያ ላይ የምትጠቀሙ ከሆነ ምንጩን እንድትጠቅሱ ትለመናላችሁ፡፡