Saturday, July 11, 2015

የኢትዮጽያና የአሜሪካ ሰው





አንድ ድረ ገጽ ውስጥ ገብተን ስለ ኢትዮጽያ መረጃ ብንጠይቅ ቢያንስ የህዝብ ብዛት ፣ መልከዓምድር ፣ ቋንቋ ፣ ባህል ፣ ሃይማኖት ፣ የመንግስት ስሪትና ገጽታውን የተመለከቱ ምላሾች ልናገኝ እንችላለን  ፡፡ አንድ ኢትዮጽያዊ ምን ይመስላል ? ተክለቁመናው… እምነቱ… ፍልስፍናው… ሀገራዊ ስሜቱ … እውቀቱ … የሚጠላውና የሚደሰትበት ?  እነዚህን ለመሳሰሉት ጥያቄዎች ግን የተዘረዘረ መልስ የሚሰጠን ድረ ገጽም ሆነ ተቋም አናገኝም ፡፡

በአስር ዓመት ቆጠራ የሚያካሄደው የማዕከላዊ ስታቲክስ ኤጀንሲም ዝርዝር ኪስ ይቀዳል በሚል እሳቤ ነው መሰለኝ መረጃውን እስከታች ተንትኖ ማስቀመጥ አለመደበትም

ይህ ጥያቄ ባደጉትም ሆነ እያደጉ በሚገኙት ሀገሮች በቂ ምላሽ እያገኘ መጥቷል ፡፡ ለአብነት ‹ አሜሪካኖች  ምን ይመስላሉ ?  › ብሎ የሚጠይቅ ግለሰብም ሆነ ሀገር የተጃመለ ሳይሆን የተዘረዘረ መረጃ በቀላሉ ያገኛል   ‹‹ የአሜሪካ ወንድ ቁመቱ በአማካኝ አምስት ጫማ ከዘጠኝ ኢንች ሲሆን 180 ፓውንድ ይመዝናል ፡፡ ደረቱ 41 ኢንች ፣ ወገቡ 35 ዳሌው 40.5 ኢንች ይደርሳል ፡፡ 90 ከመቶው ያህል ያጨሳል ፡፡ አብዛኛው መልበስ የሚወደው ጂንስ ሱሪና ቲሸርት ነው ፡፡ ብልቱ ሲቆም ስድስት ኢንች ይደርሳል ፡፡ ወጪ የማይጠየቅ ከሆነና ተግባሩ የማይጎዳው ከሆነ ከአምስቱ ሶስት ያህሉ ብልታቸውንን ማስረዘም ይፈልጋሉ ፡፡ 78 ከመቶ ያህሉ ብልቱን የተገረዘ ሲሆን ዕድሜው 78 ይጠጋል ፡፡ በአናቱ ላይ መቶ ሺህ የሚደርሱ ጸጉሮች ሲኖሩት ከዚህ ውስጥ በቀን ከሃያ እስከ መቶ ያህሉን ያጣል ›› ወዘተ እያለ ይተነትናል መረጃው ፡፡

ለመሆኑ የጋብቻና ፍቺው ቀመር ጤነኛ ነው ? ሳቅና ለቅሶው ? ሀገራዊ ስሜቱ የተለየ ነው ? መጠጥ ላይ እዛው ያነጋል ? ከፈጣሪ ጋር ይገናኝ ይሆን ? እነዚህና መሰል ስብዕና ተኮር ጥያቄዎች ብትወረውሩ አታፍሩም ፡፡ በጉዳዩ ላይ ድረ ገጾቹ የሚሉት እንደተጠበቀ ሆኖ ለማጣቀሻ የሚበቁ መጻህፍትም ይገኛሉ ፡፡ በዚህ ረገድ የደራሲ በርኒስ ካነር ‹‹ When it comes to guys what is normal ? ›› የሚለው መጽሀፍ አንጀት ያርሳል ፡፡

የእውነት አሜሪካዊያን ምን ይመስላሉ ? ለየት ያሉ ገጽታቸውን ከመረጃው እየቆነጠርኩ ‹ እነዚሁ ›  እላለሁ ፤ የኛ ማንነት በዚህ ረገድ የማይታወቅ ቢሆንም ለተሳትፎ ያህል ሸራፋ መረጃንና ያማረ ግምትን በማደባለቅ ‹ እንዲህ ነን › እያልኩ እገልጻለሁ ፡፡ ፎርፌ ጥሩ ስላልሆነ ።

ሳቅና ለቅሶ

/ አሜሪካ የአሜሪካ ሰው በቀን 15 ግዜ ሲስቅ  በወር የሚያለቅሰው ለአንድ ወይም ሁለት ግዜ ነው ፡፡       
/ኢትዮጽያ/  ኢትዮጽያዊው ሰው በቀን አንድ ግዜ እንደምንም ሲስቅ አስር ግዜ ፊቱ ይለዋወጣል ፡፡ ከዚህ ውስጥ ሁለት ግዜ በተለያዩ አናዳጅ ነገሮች ደምስሮቹ ይቆማሉ ፡፡ ሁለት ግዜ በማያውቀው ምክንያት ለንቦጩ ተዘርግፎ ከአንዳንድ ሰብዓዊነት ከሚሰማቸው ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች  ‹ እባክህ ሰብስበው ! › የሚል ቀና ምክር ይለገሰዋል ፡፡ ሁለት ግዜ መጣሁ ቀረሁ በሚል የእንባ ዝናብ ፊቱ ይዳምናል ፡፡ ሁለት ግዜ በጣም የሚወደውን ‹ እንኳን እናቴ ሞታ እንደውም አልቅስ አልቅስ ይለኛል › የተባለውን ጥቅስ እየተደገፈ  እዬዬውን ያስነካዋል ፤ ሰበበ ምክንያቱ ሲፈተሸ ለቅሶ ሲሰማ … ሰው በግፍ ሲታሰር … የእህል ዋጋና የቤት ኪራይ ሲጨምር … አለኝ የሚለው ወዳጅና ዘመድ ሲከዳው … ሆኖ ይገኛል ፡፡ ቀሪዋን ሁለት በቁጠባ የሚይዛት ይመስላል ፡፡ ጠላትን ለምን ደስ ይበለው እያለ እንደምንም ጨክኖ እንባውን አደባባይ ሳያወጣ ወደ ውስጥ ያለቅሳል ፡፡

ወሲብ ፤

/አሜሪካ /  14.3 የሚደርሰው የወሲብ ተጋሪ አያጣም ፡፡ ድንግልናቸውን የሚያስረክቡት በ16 ዓመታቸው ነው ፡፡ ከሌላ ሰው ጋር ያላቸውን ውጫዊ ግንኙነት በፍጹም አያምኑም ፡፡ በዓመት ለ135 ግዜ ወሲብ የሚፈጽም ሲሆን ከ 120 እስከ 600 ሚሊዮን የሚደርሱ ስፐርሞች ይረጫሉ ፡፡ ከነዚህ ውስጥ 400 ያህሉ ብቻ ናቸው እንቁላሉን የሚያገኙት ፡፡ 54 ከመቶ ያህሉ በቀን አንድ ግዜ ስለ ወሲብ ያስባሉ ፡፡ ቢጠቀሙም ባይጠቀሙም ከሶስቱ ሰዋች ሁለቱ ኮንዶሞችን አልጋቸው ስር ማስቀመጥ አይረሱም ፡፡
·        
/ኢትዮጽያ/  40 ከመቶ የሚደርሰው የወሲብ ተጣማሪ አለው ፡፡ 20 ከመቶው ጥሮ ግሮ የገነባው ሲሆን ቀሪው 20 ከመቶ የወንዱን እግር መራቅ ተከትሎ የሚያንጎዳጉድ ነው ፡፡ ሴቶቹ ድንግላቸውን በ 10 ዓመት ሲነጠቁ ፤ ወንዶቹ በ 15 ዓመታቸው ድንግልና ፍለጋ ይራወጣሉ ፡፡ በዓመት ለ 265 ግዜ ወሲብ የሚፈጽም ሲሆን ድርጊቱ ሲከፋፈል 35 ከመቶ በሃሳብና ወጪ ወራጁን በማየት ፣ 35 ከመቶ እጆቹ ብልቱ ላይ እንዲያንኮራፉ በማድረግ 35 በመቶ ደግሞ በተግባር ነው ፡፡ ከ 10 እስከ 20 ሚሊዮን የሚደርሱ ስፐርሞች ይረጫሉ ፡፡ ተግባሩ በዝቶ ፈሳሹ ያነሰው ከምግብ እጥረትና ከድርቀት መከሰት ነው ፡፡ እንደዛም ሆኖ 90 ከመቶ ያህሉ እንቁላሉን አግኝተው ልጅ መፍጠር ይችላሉ ፡፡ ልጆቹ ግን ሶስት ወር ሳይሞላቸው ተጨናግፈው በየገንዳው ይጣላሉ ፡፡ 70 ከመቶ ያህሉ በቀን ሶስት ግዜ ስለ ወሲብ ያስባሉ ፡፡ ከቁርስ ፣ ምሳና ራት በኃላ ማለት ነው ፡፡ 5 ከመቶው አራት ግዜ ያደርሱታል ፡፡ ይህ የሆነውም መክሰስ ስለሚጠቀሙ ነው ፡፡

ሞትና መንስኤው ፤

/አሜሪካ /   ከ45 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዋች ከዘጠኝ አንዱ በሳምባ ካንሰር ይሞታል ፡፡ 5.6 ከመቶ ያህሉ በስትሮክ ፣ 3.7 ያህሉ በኒሞኒያ ፣ 2 .8 ያህሉ በዲያቤት ይጠቃል ፡፡ ወንዶቹ ብዙውን ግዜ የሚሞቱት ራስን በማጥፋት ፣ በጉበት ፣ በአደጋ ፣ በወንጀል ድርጊቶች ነው ፡፡
·         
/ኢትዮጽያ/  አብዛኛው ህዝብ የሚያልቀው ንዳድ እያለ በሚጠራው ወባ ነው ፡፡ አሳምሮ መዳን ይቻላል በሚባልለት ቲቢም አስጠሊታ ሆኖ ማለፍ ተለምዷል ፡፡ የውሃ ሃብታም ቢሆንም ውሃ ጠላት እንጂ ወዳጅ ሆኖት አያውቅም ፡፡ በአጠቃቀም ጉድለት በውሃ ወለድ በሽታ ይወድቃል … በአጠቃቀም ፍርሃት በሃይጂን ጦስ ይቀሰፋል … በአስጠቃሚ ማጣት በረሃብ ይረግፋል … ሲንቀዠቀዥ መኪና ይበላዋል ፤ ባይንቀዠቀዥም መኪና ቤቱ ድረስ መጥቶ ይገድለዋል ፡፡

ሀገራዊ ስሜት ፤

/አሜሪካ /  አብዛኛዋቹ በአርበኝነት ስሜታቸው ይኮራሉ ፡፡ 90 ከመቶ ያህሉ ሀገሩ ትክክል ሰራችም አልሰራችም በክፉ ግዜ ከመደገፍ ወደ ኃላ አይልም ፡፡ 72 ከመቶው የአሜሪካ ባንዲራ መኪናቸው ላይ እንዲውለበለብ ይፈልጋሉ ፡፡ ከመከላከያ ሰራዊት ይልቅ ለአየር ኃይልና ባህር ኃይል የተለየ ግምት አላቸው ፡፡
·          

/ኢትዮጽያ/  አብዛኛዋቹ በአሁኑ ሳይሆን ባለፈው የሀገሪቱ ታሪክ የበለጠ ይኮራሉ ፡፡ 80 ከመቶ ያህሉ ሀገራቸውን በክፉ ቀን ለመርዳት የሚፈልጉት ዘመቻው ወደ ሰሜን ከሆነ ብቻ ነው ፡፡ 40 ከመቶ የሚደርሰው የሀገሪቱ ባንዲራ እንዲውለበለብ የሚፈልገው ያለምንም ቅጥያ ነው ፡፡ 40 ከመቶው መሃሉ ውስጥ ኮኮብ እንዲኖር ሲፈልግ 20 ከመቶው ከአንበሳው ጋር ቢያየው ይፈልጋል ፡፡ ከቤተ መንግስት መኪናዎች ውጪ ባለመኪናውም ሆነ ሹፌሩ ባንዲራውን መኪናው ላይ ማውለብለብ የሚፈልገው በዓመት አንድ ግዜ በባንዲራ ቀን ብቻ ነው  ፤ በአራት አመት አንድ ግዜ ደግሞ የኦሎምፒክ ጀግኖችን ለመቀበል ፡፡ አብዛኛው ሰው ጦሩ ሲታስብ ለጠፋው ባህር ኃይል ከፍተኛ ግምት አለው ፡፡ አንዳንዶች እንደውም 
‹‹ የባህር ኃይላችን መልህቅ የጣለበት
የጠቅል አሽከሮች በፓሪስ በኒውዮርክ የተሟገቱለት
የአሉላ ፈረሶች ውሃ የጠጡበት
የት አለ ባህሩ የተማማንልበት ›› በማለት ያስቡታል - ታዲያ በሆዳቸው ነው ፡፡

ችግር በመጣ ቁጥር ያለምንም ርህራሄ በሚደበድበው ፣ ያለ ጥያቄ በሚያፍሰውና በሚያስረው ፌዴራል ምክንያት ብዙዎቹ ለፓሊስ ያላቸው እምነት የጎመዘዘ ነው ፡፡ በምርጫ ማግስት በተፈጠረ ብጥብጥ የአንዳንዶችን ግንባር የኢላማ ተኩስ ሰሌዳ ባደረገው የአጋዚ ጦር ሰበብ ለምድር ኃይሉ ያለው አመለካከትም የጠራ አይደለም ፡፡ በንጽጽር በርካታ ሰዋች ለአየር ኃይሉ የተሻለ ድጋፍ ያላቸው ይመስላል ፡፡

በስራ ላይ ፤

/አሜሪካ /  ከአምስት ሰዋች አንዱ ስራ እየሰራ ያፏጫል ፣ ይዘፍናል ፣ ያንጎራጉራል ፡፡

·          

/ኢትዮጽያ/  ከ30 ሰዋች አንዱ ስራ እየሰራ ያፏጫል ፡፡ ከአስር ሰዋች አራቱ ከመዝፈን ይልቅ ያንጎራጉራሉ ፡፡ የእንጉርጉሮው አውድ ግን እንደቦታውና ሁኔታው የተለያየ ነው ፡፡ የፍቅር ቁስል ወይም እንከን ያለበት የትዝታ ዘሮችን በመሳብ ለምሳሌ የጸጋዬ እሸቱን
‹ የትዝታን ዜማ እንዴት ላንጎራጉረው
 እምባ እየቀደመኝ ገና ስጀምረው
ወይ አንጎራጉሬው ዘፍኜ አይወጣልኝ
ስምሽ ነው አፌ ላይ ቀድሞ የሚመጣልኝ › ማለት ይመርጣል ፡፡
ጸጸት ሸንቆጥ ያደረገው የመንግስት ሰራተኛ ደግሞ
‹ እደግ እደግ ብለን ያሳደግነው ቀጋ
ይላል ጎንበስ ቀና እኛኑ ሊወጋ ! › በማለት ትዝብቱን ለኮስ ያደርጋል ፡፡ የሙስናው ፣ የወንጀሉ ፣ ጤና ያጣው የፓለቲካ ሹክቻ ያስፈራው ቀና ሰው ደግሞ
‹ እባክህ አምላኬ ንፋሱን መልሰው
ወንድሙን ወንድሙ ሸጦ ሳይጨርሰው › እያለ ነው ፡፡
መጠጥ ፤

/አሜሪካ /  2.3 ከመቶ የሚደርሰው ህዝብ በየቀኑ ቢራ ይጠጣል ፡፡ 18 ከመቶው በየቀኑ የሚጠጣው አልኮል ሲሆን 45 ከመቶው ምርጫው ወይን ነው ፡፡ 14 ከመቶው መጠጥ ሲቀማምስ ከአቅሙ በላይ እንደሆነ ያምናል ፡፡ 31 ከመቶው ህዝብ መጠጥ ለቤተሰብ ብጥብጥና መፍረስ ትልቅ ምክንያት እንደሆነ ያምናል ፡፡
·          

/ኢትዮጽያ/  40 ከመቶ የሚደርሰው በየቀኑ ጠላ ፣ ጠጅና ካቲካላ ይጠጣል ፡፡ ከዚህ ውስጥ 30 ከመቶው ያህል መጠጡ አንድም የኑሮን ሸክም እንደሚያረሳሳ በሌላ በኩል ወይ ፈንካች አሊያም ተፈንካች እንደሚያደርጋቸው ያውቃሉ ፡፡ 10 ከመቶው ድራፍትና ቢራ በጣም አልፎ አልፎ ከጥሬ ስጋ የሚቀማምስ ሲሆን 4 ከመቶ የሚደርሱት ሀብታሞችና የሀገር ሌቦች ካለ ውስኪ አንነካም የሚሉ ናቸው ፡፡

ብቸኝነት ፤

/አሜሪካ / 13 ከመቶ ያህሉ ብቻውን የሚኖረው የኑሮ ተጋሪውን ሞት ነጥቆበት ሲሆን 38 ከመቶ የሚደርሰው ብቸኛ ግን ምክንያቱ ፍቺ ነው ፡፡ ብቻቸውን ከሚኖሩት ውስጥ 46 ከመቶ ያህሉ በድጋሚ አላገቡም ፡፡
·
/ኢትዮጽያ/  40 ከመቶ የሚደርሰው ጎረምሳና ጎልማሳ ብቻውን የሚኖረው በስጋትና በፍርሃት ምክንያት ነው ፡፡ የድህነቱን ቋጥኝ መሸከም ስለማይችል የሚፈልገውን ትዳር መመስረት አይፈልግም ፡፡ ወልዶ መሳም የተፈጥሮ መፈክር ቢሆንም የልጅ ፍላጎቱን የሚወጣው የልጆች ፕሮግራምን ደጋግሞ በማየት ነው ፡፡ 20 ከመቶ ያህሉ ተበድሮ ካስጨፈረው ሰርግ ማግስት የኑሮ ውሉን የቀደደው በጭቅጭቅ ነው ፡፡

ጸሎት ፤

/አሜሪካ /  59 ከመቶ የሚደርሰው ወንድ በየግዜው ይጸልያል ፡፡ ከዚህ ውስጥ 62 ከመቶው የጸሎቱ ምክንያታቸው ድጋፍና ርዳታ ለማግኘት ነው ፡፡ 54 ከመቶው ፈጣሪን ለማመስገን ፣ 47 ከመቶው ይቅርታ ለመጠየቅ ይጠቀማሉ ፡፡ በጣም የሚገርመው ሃይማኖት የሌላቸው 14 ከመቶ የሚደርሱ ሰዋች በየቀኑ የመጸለያቸው ጉዳይ ነው ፡፡

·        
/ኢትዮጽያ/  60 ከመቶ የሚደርሰው ህዝብ እንደየሃይማኖቱ ይጸልያል ፡፡ ከዚህ ውስጥ አንድ ሶስተኛው በልቡ ትልቅ የማመልከቻ ዶሴ ይዞ ይጓዛል ፡፡ የተወሰነው የተቀናቃኙ እግር ቄጤማ ፣ አይኑ ደግሞ ጨለማ እንዲሆን ፈላጊ ነው ፡፡ ለዚህም ስራ ማሰፈጸሚያ ይሁን መደለያ የማይሳለውና ቃል የማይገባው ነገር የለም ፡፡ ሌላው የሰማውን ሂስና ግለሂስ እንዳለ ኮፒ በማድረግ ለመተግበር ወደ ኃላ የማይለው ነው  ‹‹ እስኪ እንጠያየቅ አሁን አታዳለም ?! ... እውነት ፍትህ ትሰጣለህ ?  አንዱ ቂጣ እያረረበት ሌላው በውስኪ እንዲታጠብ ታደርጋለህ … አንዱን ኗሪ ሌላውን አኗኗሪ የምታደርገው በምን ሂሳብ ይሆን ?  ቤት አጥቶ በየሜዳው የሚተኛው በፓሊስ እየተባረረ ቪላ አማራጩ ደግሞ በፓሊስ ይጠበቃል ? እውነት የአንተ ‹  ላለው ይጨመራል ›  ብሂል መነሻው ምንድነው ? ›› ይለዋል አምላኩን ፡፡ መቼም ፈጣሪ ወፈ ሰማይ ‹ ካድሬዋች › ቢኖሩት ኖሮ ደፍሮ ላይናገር ይችላል ፡፡ ቀሪው አንድ ሶስተኛ ስቅስቅ ብሎ የሚያለቅሰው ‹ ምነው የእለት እንጀራ ነፈከኝ … ምነው የሰው እጅ አሳየኀኝ … ምነው የውሃ አጣጭዮን እንደ ቶምቦላ እጣ ብርቅ አደረከው ? › እያለ ሳይሆን አይቀርም ፡፡

የእረፍት ግዜ ፤

/አሜሪካ /  የአብዛኛው ወንድ እረፍት ግዜ አምስት ሰዓት አካባቢ ሲሆን ከዚህ ወስጥ ግማሽ ያህሉን ቴሌቪዥን በማየት ፣ ሃያ ደቂቃ ራሱን ለማዝናናትና ለማሰብ ፣ 50 ደቂቃውን ከቤተሰቡ ጋር ለማሳለፍ ያውለዋል ፡፡ 19 ከመቶ የሚደርሱት ብቻ የቤት ውስጥ ልዩ ልዩ ስራዋች የሚሰሩ ሲሆን 34 ከመቶ ያህሉ ደግሞ ምግብ ለማብሰልና በጽዳት ላይ እንደሚሳተፉ ይናገራሉ ፡፡
·     
/ኢትዮጽያ/  የመንግስት ሰራተኛ እረፍት ዘጠኝ ሰዓታት ያህል ነው ፡፡ ቢሮ ከሚያሳልፈው ስምንት ሰዓታት ውስጥ አምስቱን የሚያሳልፈው ጓደኛውን ፣ አለቃውንና ስርዓቱን በመቦጨቅ… ቻት በማድረግና የስራ ማስታወቂያ በመፈለግ … እንደ ሀገር ውስጥ ቱሪስት የተለያዩ መምሪያ ውስጥ የሚገኙ ሰዎችን በመጎብኘትና በማድነቅ … በትልቅ በትንሹ የሚታደምባቸውን አራት ነጥብ ፈሪ ስብሰባዎች በአክዋ አዲስና ማኪያቶ እየተጉመጠመጠ በመዋጥ ነው ፡፡ ከስራ በኃላ ቅዳሜና እሁድ የሚገኙ እረፍቶች ነጻነት የበዛባቸው በመሆኑ ቄንጠኛ እረፍቶች ናቸው ማለት ይቻላል ፡፡ እጆቹ ለስላሳ የሴት ገላም ሆነ ሰፊ የወንድ ደረት ፣ የጫት እንጨትም ይሁን የድራፍት ብርጭቆዎችን ባማለለ መልኩ መጨበጥ ይችሉበታል ፡፡ እነዚህን የቀመሱ አፎች ደግሞ በተዓምር ለዝምታ እጅ አይሰጡም ፡፡ እግር ኳሱ … የአረብ አብዮቱ … የሴት ውበቱ … የወንድ ልጅ ሀሞቱ … የምርጫችን ትርዒቱና ትዕቢቱ … እንደየአመጣጡ ይሸነሸናል ፡፡ ከዚያ አየር ላይ ክብ እየሰሩ የሚታዩ ገጣጣ ፣ ጠፍጣፋና ወልጋዳ ሳቆች እኢዲሁም ቁጭቶች ይከተላሉ ፡፡

ትምህርት፤

/አሜሪካ /  84 ከመቶ የሚደርሰው ዜገኛ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የጨረሰ ሲሆን የኮሌጅ ዲግሪ ያለው 28 ከመቶው ነው ፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪ ያለው በዓመት የ66ሺህ 810 ዶላር ተከፋይ ሲሆን ባለዲፕሎማው 30 ሺህ 414 ዶላር ያገኛል ፡፡

·        
/ኢትዮጽያ/  43 ከመቶ የሚደርሰው ህዝብ የማንበብና መጻፍ ችግር የለበትም ፡፡ ከኮሌጅ በዲፕሎማ የተመረቀ ሰው ደመወዙ መጠነኛ ቤት ለመከራየት ትንሽ ይጎድለዋል ፡፡ በዲግሪ የተመረቀ ሰው ደመወዙ ለክፉ የማይሰጥ ቤት ሊያከራየው ይችላል ፡፡ በፈለገው ተዓምራዊ የሂሳብ ቀመር ከሽርፍራፊ እህል አልፎ ወደ ስራ ለሚመላለስበት መጓጓዣ ስለማይተርፈው ቆራጥ እግረኛ መሆን ይጠበቅበታል ፡፡ በሌሊት እየተነሳ ‹ ልወዝወዘው በእግሬ › የሚለውን ዜማ እንዲያቀነቅን ተፈርዶበታል ፡፡ በማስትሬት የተመረቀ ሰው ባለ ሰፊ ምኞት ቢሆንም የምኞቱን ለሃጭ ከማንጠባጠብ ማገድ አይችልም ፡፡ ለምሳሌ ከክብሩ አንጻር ቢያንስ ቢያንስ ጥሬ ስጋንና ቢራን መጎንጨት ይኖርበታል ፡፡ ግና ልቡ እንጂ ኪሱ ባዶ በመሆኑ በስጋ ቤት ደጃፍ የሚያልፈው ሶስቱን የ ‹‹ ማ ›› ህጎች በመዘመር ነው ፡፡ ማየት… ማድነቅ… ማለፍ…



Sunday, April 19, 2015

የረጋ ደም ፍትህ ይወጣዋል ?


 
ደቡብ አፍሪካው አሰቃቂ ፍጅትና ወንጀል ብዙ ጥያቄዎችን እንድናነሳ እያደረገን ነው ። የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ አንዳንድ ሀገሮች በተገቢው ፍጥነት ወንጀልን የመከላከል ተግባር ወስደዋል ። ወንጀልን መከላከል የሁሉም መንግስታት የጋራ ግዴታና ሃላፊነት ነውና ።
1 . ኢትዮጽያ ሀገራችን  ያው እንደልማዷ ጉዳዩን ግዜያዊ ክስተት በማድረግ የወንጀል መከላከል ተግባሩን በእርጋታ ለመፍታት እየሰራች መሆኗን በአስራ አንደኛው ሰዓት ገልጻለች ። በሀገራችን የእርጋታ ርምጃዎች ውስጥ የብሄራዊ ስሜት ቀለም መደብዘዝ ፣ የዲፕሎማሲ እውቀት እጥረት ፣ ስልጣንን በአግባቡ አለመወጣትና ህዝባዊ ሃላፊነትን አለመረዳት ፍንትው ብለው ታይተዋል ።
ለምሳሌ ያህል ከህዝብ ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ ቅርበት የፈጠሩት ዶክተር ቴዎድሮስ ችግሩን በእርጋታ ማየት እንደሚገባ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል - ይህን ሀሳብ የመንግስትም ሀሳብ ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል ። መንግስት ችግር አልደረሰም ብሎ ሁኔታውን ካልካደ በስተቀር እንደ አምቡላንስ ወይም እሳት አደጋ መኪና በፍጥነት መሮጥ ነበረበት ። ምክንያቱም ሰው እያለቀ ወይም ቤት እየተቃጠለ መጀመሪያ በጉዳዩ ዙሪያ አውደ ጥናት ይዘጋጅ ማለት አይቻልም ።
በነገራችን ላይ ልክ እንደ ዶክተር ቴዎድሮስ የዙምባብዌ የአካባቢና ማስታወቂያ ሚንስትሮች ትዊተራቸውን ይጠቀማሉ ። የአካባቢ ጥበቃ ሚኒስትሩ ሳቪየር ጥቃቱን የገለጹት << አሳፋሪና ከአፓርታይድም የከፋ >> በማለት ሲሆን የማስታወቂያ ሚኒስትሩ ጆናታን ደግሞ << የዛሬ የዉጭ ሀገር ሰዎች ጥላቻ ነገ ወደ ጅምላ ጭፍጨፋ የሚያድግ ነው >> በማለት ነበር ። የባለስልጣናቱ አስተያየት ውስጥ ሀገራዊ መቆርቆር ብቻ ሳይሆን አሻግሮ የማየትንም ብስለት እንመለከታለን ። የአፍሪካ የግጭት መንስኤዎችንና አሰከፊ መዳረሻዎቻቸውን የምንፈትሽ ከሆነ የተጠቀሰው ስጋት ትክክል የማይሆንበት መሰረት አይኖረውም ።
ስለዚህ አርቆ በመመልከት ህዝባዊ ሃላፊነትን በትኩሱ መወጣት በአንድ በኩል ፣ ዲፕሎማሲው የሚፈልገውን የኤሊ ርምጃ ለግዜው ገለል አድርጎ እንደ አቦሸማኔ መወርወር በዚህ ግዜ ትክክል ይሆናሉ ። የዲፕሎማሲውን እሹሩሩ ከጀርባ ላይ አውርዶ አካፋን አካፋ ማለትም በዚህን ግዜ አስፈላጊ ነው ። ምክንያቱም ወንጀልንና ኢስብዓዊ ድርጊትን ያላወገዘ ብሎም ያላጋለጠ መንግስት ለሰው ልጆችና ለአለማቀፉ ህግ መቆሙ በምን ይረጋገጣል ?
2 . እንደ እኛ መንግስት ሁሉ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ የሚገኙ ታላላቅ የሰላም አባቶችና ስመ ጥር ፖለቲከኞች ድምጻቸውን ማጥፋታቸውም አጠያያቂ ነው ።
የማንዴላን መቀመጫ የተረከቡት ታምቦ ምቤኪ ልክ እንደ ማርቲን ሉተር ኪንግ << ህልም አለኝ >> ፣ እሳቸውም የሚታወቁበት << እኔ አፍሪካዊ ነኝ - I AM AN AFRICAN >> የሚል የሞራል ፍልስፍና አላቸው ። በዚህ መሳጭ ንግግር ውስጥ << እኔ የተወለድኩት ከአፍሪካ አህጉር ህዝቦች ነው >> ይላሉ - እኚህ ሰው ደቡብ አፍሪካዊ ብቻ አይደሉም ማለት ነው ። የብዙ አፍሪካዊያን ደም በሀገራቸው ሲፈስ ግን ቃል መተንፈስ አልቻሉም ። << የሶማሊያ ፣ የላይቤሪያ ፣ የሱዳን ፣ የቡሩንዲ ፣ የአልጂሪያ ህዝቦች በግጭት የሚደርስባቸው ሀመም እኔም የተሸከምኩት ህመም ነው >> ይላል ፍልስፍናቸው ። ዛሬ የቆንጨራ ስለት በየአስፋልቱ ሲፋጭ << እረ ህመሜ ጀመረኝ >> ማለት አልቻሉም ። ስቃይን ፣ ግርፋትን ፣ እስርን ፣ ስደትን ፣ አድልዋን ወዘተ የሚቃወመው ሀሳባቸው ለሰው ልጅ ክብርንና ልእልናም ያዜማል ። ቃናቸው ፣ የዜማቸው አወራረድ ፣ የቃላታቸው ከፍታ ፣ የሃሳባቸው ርቀት ለደቡብ አፍሪካ ብቻ አይደለም ምናልባትም ለአንድ ቀንዋ ፓን አፍሪካ መሪነት ያሳጫቸዋል ። አፍሪካዊው ታምቦ በሚስብ መልኩ ከጻፉት ሞራላዊ ህግጋት ውስጥ ጥቂት ስንኞችን ማንበቢያ ግዜያቸው አሁን ነበር - ግና ጉዳዩን << በእርጋታና በትዕግስት >>  እያጠኑት ይመስላል 
የሰላም ዘብ ናቸው ብሎ አለም በ1984 የሰላም ሽልማት አክሊል የደፋላቸው ዴዝሞን ቱቱም እንደኛ መንግስት ተመቻችተው የተኙ መስለዋል ። እኚህ ሰው አይደለም በርካታ አፍሪካዊያን እየተጨፈጨፉና እየተዋከቡ ባሉበት ወቅት ለግብረሶዶማዊያን መብት እንኳ ከልክ በላይ የተሟገቱ ነበር ። << ግብረሶዶማዊያንን ማግለል አፓርታይድን እንደመደገፍ ነው >> በሚለው ጥብቅ ሀሳባቸውም ይታወቃሉ ። ዛሬ የሀገራቸው ዜኖፊያ በርካታዎችን ሲረግጥና ሲያስጨንቅ << እርጋታ >> እያሉ ይመስላል ። የፍትህና የይቅርታን ፕሮጄክቶችን በመመስረት ትልቅ ስራም መስራታቸው ይታወቃል ። እነዚህ ፕሮጄክቶች ነገ የሀገራቸውን አጥፊዎች እንዲጠየቁ የማያደርግ ከሆነ ግን በሽልማታቸው ጉዳይ መጠያያቃችን አይቀሬ ይሆናል ።
በርግጥ የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል
የረጋ ደም ፍትህ ይወጣው ይሆን ?

 

Friday, December 19, 2014

የሂትለርና ቸርችል ሌላኛው እጆች !


አዶልፍ ሂትለርና ዊንስተን ቸርችል በተቃራኒው መንገድም ቢሆን የሚመሳስል ነገር አላቸው ። ሁለቱም በውትድርና ሀገራቸውን አገልግለዋል ። ሁለቱም ሀገራቸውን መርተዋል ። ሁለቱም ሀገራቸውን < ለማስቀደም > የአባራሪና ተባራራሪን ሚና ወክለው ተፋልመዋል - ሂትለር ድመት ቸርችል አይጥ እንዲሉ ።
ሁለቱም ሃይለኛ ተናጋሪ ናቸው ። ሁለቱም ደራሲ ናቸው ። እንደውም ሁለቱም ታስረው በእስር ቤት ውስጥ መጽሀፍ መፍጠራቸው ገጠመኙን ጠንከር ያደርገዋል ። ቸርችል በቦየር ጦርነት ወቅት ወደ ደቡብ አፍሪካ ባመራበት ወቅት ተይዞ እስር ቤት ውስጥ ተወርውሮ ነበር ። እዛ ግን ስራ አልፈታም ። < London to lady smith via Pretoria  > የሚል ስራ ጨርሶ ለአንባቢያን አቅርቧል ። ሂትለር የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርገሃል ተብሎ ዘብጥያ በተላከ ግዜ  < Mein Kampf  > ወይም የኔ ትግል የሚል ጠንካራ ስራ ሰርቶ በኌላ ላይ አሳትሞታል ። ርግጥ ነው ሂትለር በስሙ አስር ስራዎች ቢታተሙለትም ሁሉም እንደ ቸርችል ጠብሰቅ ያሉና ሚዛን የሚደፉ አይደሉም ። ቸርችል 43 መጽሀፍት ለአለም አበርክቷል ። በዚህም ጥረቱ በ1953 የስነጽሁፍ ኖቤል ተሸላሚ መሆን ችሏል ። ምናልባትም በዘርፉ ትልቅ ክብር ያገኘ ብቸኛው የአለማችን መሪ ነው ።
በስልጣናቸው ዘመን ሁለቱም የራሳቸው መለያ የሆነ የሰላምታ አሰጣጥ ስርዓት ነበራቸው ። ቸርችል ሁለት ጣቱን በማውጣት ሰላም ይላል - እናሸንፋለን ለማለት ጭምር ። ሂትለር ቀኝ አጁን ወደፊት በመዘርጋት ሰላምታ ይሰጥ ነበር - <  Seig Heli > - እናሸንፋለን እንደማለት ። ሁለት ጣት ሲወጣ መሳቅም መጥቀስም ይቻላል ። ቀኝ እጅ ወደፊት እንደ ቀስት ሲወረወር ግን ምናልባት ሂትለር ! ከማለት ውጪ መፈገግ አይቻልም - ኮስተር ብሎ ሰኮንዶችን ማሳለፍ እንጂ ። የናዚ ሰላምታ በአሁኑ ወቅት በጀርመን ፣ ኦስትሪያ ፣ ስሎቫኪያ እና ቼክ የወንጅል ድርጊት በመሆኑ እስከ ሶስት ዓመት ያስቀጣል ። የቪ ምልክት የትም ሀገር ወንጀል ባይሆንም በአንድ ወቅት በኢትዮጽያ የብዙዎች መቀጣጫ ሆኗል ።
ሁለቱም መሪዎች ሰዓሊዎች ናቸው ። በቀውጢው ዘመን ብሩሽና እርሳስ ጨብጠው በቀለማት ዜማ ሃሳባቸውንና ፍልስፍናቸውን ሸራ ላይ ተንፍሰዋል ። ርግጥ ነው ሂትለር በ1905 ገና በ16 ዓመቱ ዳገት የሆነበትን ትምህርት ትቶ ነበር ፕሮፌሽናል ሰዓሊ የመሆን ህልሙን ፍለጋ የጀመረው ። የቸርችል ህልም ከሰዓሊነት ይልቅ የጦር ዘጋቢነትና ደራሲነት ነበር ማለት ወደ እውነታው መንደር ጠጋ ያደርገናል ። ለማሳያም በወቅቱ በትላልቅ ጋዜጦች ላይ ይጽፋቸው የነበሩትን መጣጥፎችና ብርሃን ያዩ የህትመት ስራዎቹን መመልከት በቂ ነው ። ተደብቆ የቆየው የሰዓሊነት ፍላጎት ብቅ ያለው እንደ ሂትለር በወጣትነት ዘመን አይደለም - በጉልምስና/ 40 /  እንጂ ።
ቸርችል በአንድ ወቅት የፖለቲካው ህይወት ሲያስጠላው ራሱን አግሎ ነበር ። ያኔ ራሱን ለማዝናናት ከጽሁፉ ጎን ለጎን መስመሮችን መገጣጠም ጀመረ ። አንዳንድ መረጃዎች እንደሚነግሩን ስእሉን መማር የጀመረው ከጓደኛው ፓወል ሜዞ ነበር ። አንዳንድ መረጃዎች ደግሞ የታዋቂዎቹ ሰዓሊዎች ማለትም የክላውድ ሞንት ፣ ቪንስንት ቫ ጎህ እና ዊሊያም ተርነር ስራዎች ትልቅ ተጽዕኖ ፈጥረውበት እንደነበር ያስረዳሉ ።
        
Churchill 'S works
ለሂትለር የስዕል መስመሮችን ለመጀመሪያ ማን እንዳሳየው የሚገልጽ መረጃ የለም ። ይሁን እንጂ የትምህርት ቤቱ ሰርተፍኬት እንደሚያሳየው በብዙ ትምህርቶች በቂና ከበቂ በታች ውጤት አሰመዝግቦ በስዕል ትምህርት ግን < እጅግ በጣም ጥሩ > የሚል የሞቀ መገለጫ ነው የሰፈረለት ። ይህም ገና በታዳጊነቱ ስዕል አፍቃሪ መሆኑን ያቃጥራል ። ያም ሆነ ይህ የሂትለር ተጽዕኖ ውስጣዊ ፍላጎትና የህይወት ችግር ነበር ። አባቱ አሎያስ ሂትለርን ለሶስተኛ ግዜ ካገባት ሚስቱ በ51 ዓመቱ ነበር የወለደው ። ሂትለር ስድስት ዓመት ሲሞላው ጡረታ በመውጣቱ የችግር ጥላ ቤቱን በወፍራም ግራጫ ቀለም ለቅልቆት ነበር ። ሂትለር 13 ዓመት ሲሞላው ግራጫው ቀለም ወደ ጥቁርነት ተቀየረ - አሎይስ አረፈ ። እናቱ ክላራም በ1908 በጡት ካንሰር ሞተች ። እናም ራሱን ለማሸነፍ እንደ ቀስት መወርወር ነበረበት ።
በ1907 በቬና የስነጥበብ አካዳሚ ለመማር አመልክቶ ያቀረብከው ስራ ብቁ አይደለም ተብሎ ነበር ። በ1908 ትም ወደዚሁ ማዕከል መወርወር ግድ ብሎት ነበር ። አሁንም ለመግቢያ ፈተና ያቀረበውን ስራ የገመገሙ መምህራን ብቃት እንደሌለው በግልጽ ነገሩት ። በብቃቱ ይተማመን የነበረው ሂትለር ጠማማውን ምላሽ አምኖ ለመቀበል አልቻለም ። ተቋሙ ሂትለር ከሰዓሊነት ይልቅ በአርክቴክቸር የበለጠ ተሰጥኦ እንዳለው ያምን ነበር ። ሂትለር በአይሁዳዊያኑ መምህራን ላይ ቂም ቋጠረ ።
እንደ ቸርችል ከሃብታም ቤተሰብ ባለመፈጠሩ ስዕሉን ችላ ብሎ ሌላ የህይወት ሰበዝ የመምዘዝ እድል አልነበረውም ። እናም መሳሉን ገፋበት ። በተለይም ከ1908 እስከ 1913 በቬና ህይወቱን ለማቆየት በመቶ የሚቆጠሩ ስዕሎችንና ፖስት ካርዶችን ሰርቶ ሸጧል ።
ቸርችል በአንደኛው ዓለም ጦርነት ወቅት በጦር ሰራዊትና ባህር ሃይል ከፍተኛ የሃላፊነት ቦታዎች ላይ አገልግሏል ። ሂትለር የአንደኛው ዓለም ጦርነት ሲጀመር በኦስትሪያ ዜግነት በቫሪያን ጦር በፍቃደኝነት ለማገልገል ተቀላቀለ ። የስዕል ስራዎቹን ጦር ሜዳ ይዞ በመሄዱ < አርቲስቱ > እየተባለ ነበር የሚጠራው ። ጦርነቱ ቸርችልን እስከ ሚኒስትር ደረጃ እንዳደረሰው ሁሉ ሂትለርም የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ የጀግና ሽልማቶችን ከሻምበልነት ማዕረግ ጋር አስገኝቶለታል ። በትርፍ ሰዓቱም ለጦር ሰራዊቱ ጋዜጣ የካርቱን ስዕሎችን በመመገብ የአዝናኝነትን ሚና ከፍ አድርጓል ።
                             






hitler 's  works
የሂትለርና ቸርችል የአብዛኛዎቹ ስራዎች ጭብጥ መልከዓምድር ፣ ተፈጥሮና የሰው ምስል መሆናቸውን ስንመለከት ብዙ ጥያቄዎች ሊፈጠሩብን ይችላሉ ። ምክንያቱም ወቅቱ የፖለቲካ ውጥረት የበዛበት ፣ ህይወት በጥይት የሚያልፍበት ፣ አንዱ ሌላውን ለማጥቃት እንቅልፍ የሚያጣበት በመሆኑ ነባራዊውን እውነታ ማንጸባረቅ ለምን እንዳልፈለጉ ግልጽ አይደለም ።  ስራዎቻቸው ከጭብጥ አንጻር ተቀራራቢ ቢመስልም የስዕሎቹ መኳኳያ መንገድ ግን ለየቅል ነው ። ቸርችል የዘይት ቅብን መሰረት ሲያደርግ ሂትለር የውሃ ቀለም ይመቸዋል ። የስዕልን ፍላጎት ለረጅም ግዜ ይዞ በመቆየትም ቸርችል ቅድሚያውን ይይዛል ። ለዚያም ነው አምስት መቶ የሚደርሱ ስራዎችን ያመረተው ። የእንግሊዙ ታዋቂ ሰዓሊ ሰር ኦስዋልድ በርሊ << ቸርችል ለፖለቲካው እንደሰጠው ሰፊ ግዜ ለስዕሉም ቢሰጥ ኖሮ ዓለማችን ታላቂ ሰዓሊ ታገኝ ነበር >> ሲል ተናግሯል ። በአሁኑ ወቅትም የቸርችል ስራዎች በጨረታ እየተጫረቱ በሚሊየን ዶላር እየተሸጡ ናቸው ። በሌላ በኩል < civil registry office and old town hall of munich > የሚል ርዕስ የያዘው የሂትለር ስራ በ 161 ሺህ ዶላር ተሸጧል ። አጫራቹ ድርጅት ለኒዊስክ እንደገለጸው ስራው በጥሩ ሁኔታ የሚገኝ ሲሆን የሰዓሊውንም ችሎታ ያሳየ ነው ። ምንም እንኳን ብዙዎች የዚህን ከይሲ ሰው ጥሩ ስራ መስማትም ማድነቅም ባይፈልጉም ።
ርግጥ ነው ሂትለር ለሁለተኛው ዓለም ጦርነትና ለ 11 ሚሊየን ዜጎች እልቂት ተጠያቂ ነው ። ሂትለር እጆቹ በደም ከመጨማለቃቸው በፊት በስዕል ህብረ ቀለማት የለመለሙ ነበሩ ። ስዕሎቹን ተራ በተራ የተመለከተ ሰው መገረሙና መመሰጡ አይቀሬ ነው ። ስሜታዊ ከሆነም የቬና የስነጥበብ አካዳሚ እውነት ምን ነክቶት ነው ሁለት ግዜ ጠልዞ ከግቢ ያባረረው ? ሊል ይችላል ። ምናልባት ሂትለር ሰዓሊ ሆኖ ቢቀጥል የሁለተኛው አለም ጦርነት ርዕሰ ጉዳይ ላይኖር ይችላል ። ይህ ጦርነት በመወለዱ ግን ሂትለር ጥበባዊ ልዕልናውን ሲያጣ ቸርችል የሞገስ ካባና አክሊሉን አጠልቋል ። ምክንያቱም በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ላይ የሚያትቱ ስድስት መጽሀፍት ደርሷልና ። ሂትለር አይጥ ቸርችል ድመት እንዲሉ ።
የሂትለር ጺም ፣ የቸርችል ሲጋራ ድንገት በምናብ ብቅ እንደሚልብን ሁሉ ፤ የሂትለርን ተሸናፊነት የቸርችልን አሸናፊነት ምሳሌ እንደምናደርገው ሁሉ ፤ ሂትለርን በጨካኝነት ቸርችልን በደፋርነት እንደምንበይነው ሁሉ ፤ የሁለቱንም  ሌሎች ተመሳሳይ እጆች ማወቅ ይኖርብናል ። እናም እንደእኔ እምነት የስዕል ስራዎቻቸውን አሰባስቦ በአንድ ሙዚየም ውስጥ ለማሳየት የሚተጋ ግለሰብ ወይም ተቋም ያስፈልጋል ባይ ነኝ ።

Sunday, August 10, 2014

ታሪከኛው የኞኞ ልጅ !


 
የባለታሪኩ በኩር ስም አማረ ነው ። አማረ ህዳር 11 ቀን 1926 ዓም በድሬደዋ ተወለደ ። ወ/ሮ ትበልጫለሽ አማረን የወለዱት ለቁልቢ ገብርኤል ተስለው ነው ። ግሪካዊው አባቱ አማረ መወለዱን ይወቁ እንጂ እንደ አባት ተንከባክበው የማሳደግ ግዴታ እንዳለባቸው ያላወቁ መስለዋል - ወይም ባላወቀ ሸሽተዋል ።

ወ/ሮ ትበልጫለሽ ምን የመሰለውን የሚያምር ስም ከአማረ ወደ ጻውሎስ የቀየሩት በመጽሀፍ ቅዱስ አዘውታሪ አንባቢነታቸው ነው ። ከዚህ ይልቅ ሁለት ነገሮችን ማሳካት ቢችሉ እንዴት ጥሩ ነበር ? የባለቤታቸውን የሽሽት ሃሳብ ማስቆምና የባለቤታቸውን ስም እንደ ልጃቸው ማስቀየር ። በጣም ሳስበው አብረው ቢቆዩ   < ኞኞ > ለሚባል ገራሚ ስም ከዚህም ከዚያም ብለው  ኢትዮጽያዊ አቻ ማፈላለጋቸው አይቀርም ነበር ።

የአባቱን ናፍቆት በእናቱ ፍቅር ውስጥ ሲያገኝ የቆየው ጻውሎስ ገና በለጋ እድሜው ራሱን ብቁ ለማድረግ አባታዊ ሃላፊነትን ደርቦ እውን አድርጓል ። የአባትን ክፍተት በራሱ ጥረት የሚሞላ ልጅ ማግኘት የተለመደ አይደለም ። ዞሮ ዞሮ ጻውሎስን በዘልማድ እስከ አራተኛ ነው የተማረው እንላለን እንጂ በንባብ ምጥቀቱ እስከ ስንተኛ እንደደረሰ አፋችንን ሞልተን መንገር አንችልም ። ለማንኛውም የዚህ ድንቅ ሰው የህይወት ታሪክ በደረጄ ትዕዛዙ ተዘጋጅቶ ለንባብ ቀርቧል ። የገጹ ብዛት 308 ሲሆን ዋጋው 84 ብር ነው ።

አምባሰደር ዘውዴ ረታ

ጋዜጠኛ ንጉሴ አክሊሉ

ጋዜጠኛ ማዕረጉ በዛብህ

የቀድሞው ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ

አቶ ውብሸት ወርቃለማሁ

አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ

ሃያሲ አስፋው ዳምጤ

ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት የባለታሪኩን ታሪከኛነት ምስክር ከሚሰጡ ታዋቂ ሰዋች መካከል የተወሰኑት ናቸው ።

በጻውሎስ ኞኞ የህይወት ታሪክ ላይ የሚያጠነጠነው መጽሀፍ በዘጠኝ ምዕራፍ የተከፋፈለ ነው ። በምዕራፍ አንድ የልጅነትና ጉርምስና ፣ በምዕራፍ ሁለት የጋዜጠኝነቱ ህይወቱ ተዳሶበታል ። በምዕራፍ ሶስት ሰብዓዊ ተግባራቱ ፣ በምዕራፍ አራት የድርሰትና ታሪክ ጸሀፊነቱ ፣ በምዕራፍ አምስት የፖለቲካና ሃይማኖታዊ አመለካከቱ ይወሳበታል ። በምዕራፍ ስድስት ቤተሰባዊና ማህበራዊ ገጽታው ፣ በምእራፍ ሰባት ጻውሎስ ስለ ራሱ የተናገረውና ሌሎች ስለ እሱ የመሰከሩበት ሃሳቦች የተንሸራሸሩበት ነው ። በምእራፍ ስምንት እና ዘጠኝ ሽልማቶቹና የህይወት ፍጻሜው ተገልጾበታል ።

እነዚህ የምዕራፍ ሃዲዶች ትንሹን ጻውሎስ ከትልቁ ጻውሎስ ጋር እየተጠማዘዙ ያገናኙ በመሆናቸው የገጸ ባህሪውን አጠቃላይ ቁመና ለማሳየት በእጅጉ የረዱ ናቸው ። ደራሲው እያንዳንዱ ምዕራፍ አዳዲስና ልብ የሚሞላ መረጃ እንዲኖራቸው ብዙ የጣረ መሆኑን የሚያሳየው በርካታ የመረጃ ምንጮችን መጠቀሙ ብቻ ሳይሆን ከ25 በላይ የሚሆኑ ሰዎችን ቃለመጠይቅ ማድረጉም ጭምር ነው ።፡ይህም ስለ ጻውሎስ አውቃለሁ ብሎ የሚናገር ሰው ሁላ መጽሀፉን ሲያነብ << እንዴ እንዲህም አድርጎ ነበር እንዴ ? >> የሚል የኌላ ግርምታ እንዲፈጥር ማስገደዱ ነው ።

ለምሳሌ ብዙዎች ጻውሎስ እስከ አራተኛ ክፍል ብቻ መማሩን ፣ ጋዜጣ ፣ ፓስቲና እንቁላል ይሸጥ እንደነበር ያውቃሉ ። ይሁን እንጂ በእርሻ ሚኒስቴር ውስጥ በወር 8 ብር እየተከፈለው የከብት መርፌ ወጊ ሆኖ መስራቱ ቢነገራቸው ይገረማሉ ። ቆየት ብሎም በዳግማዊ ሚኒሊክ ሆስፒታል በ80 ብር ደመወዝ ድሬሰር ሆኖ አገልግሏል ቢባሉ እረ አትቀልድ ማለታቸው አይቀርም ። እንደው የጋዜጠኝነት ባቡር ሃዲዱን አሳተው እንጂ በዚህ አካሄዱ የነርስና ዶክተርነትን ጎራ አይቀላቀልም ለማለት አያስደፍርም - አስገራሚው ነገር ለከብት ወጊነትም ሆነ ለድሬሰርነት ያገኘው ሰርተፍኬት መኖሩን መጽሀፉ አለማተቱ ነው ።

በድምጽ ጋዜጣ በአራሚነት ጋዜጠኝነትን የተቀላቀለው ጻውሎስ በአራተኛ ክፍል ደረጃው እስከ ምክትል ዋና አዘጋጅነት ደረጃ ሰርቷል ። በስራዎቹ ህዝባዊ ፍቅርና ዝና እንዲሁም በርካታ ሽልማቶች ያገኘበትን ያህል በደፋር ትችቱ ብዙ መከራ ደርሶበታል ። በአንድ ወቅት ለኢትዮጽያ እድገት አለመሰፋፋት ተጠያቂዎች ባለስልጣናት ብቻ ሳይሆኑ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጭምር ናት የሚል ጽሁፍ በማሳተሙ ከፍተኛ አመጽ ተነሳ ። ጉዋደኞቹ አስተባብል ቢሉትም ያመንኩበትን ነው የጻፍኩት ብሎ አሻፈረኝ አለ ። ሊበቀሉት የሚፈልጉት ሰዎች በመበራከታቸው ጓደኛው ቤት ሶስት ቀናት መደበቅ ነበረበት - ኌላ በዓሉ ግርማና አጥናፍ ሰገድ ይልማ በእሱ ስም አስመስለው በጋዜጣ ላይ ይቅርታ በመጠየቃቸው ህይወቱ ተርፏል ። ከመንግስትም ብዙ ተጽዕኖ ፣ መገለልና ቅጣትን ተቀብሏል ። በዚህም ምክንያት ነበር ከአንዱ መ/ቤት ወደሌላው ሲወረወር የኖረው ። አዲስ ድምጽ ፣ አዲስ ዘመን ፣ ቴሌቪዥን ፣ ሬዲዮና ዜና አገልግሎት የመገኘቱም ምስጢር የዚህ ውጤት ነበር ።

ጻውሎስ ጥሩ ጋዜጠኛ ብቻ ሳይሆን ጮሌ የማስታወቂያና ህዝብ ግንኑነት ሰራተኛም ነበር ማለት ይቻላል ። ድምጽ ጋዜጣ በገቢ ራስዋን መቻል አለባት ሲባል እንደ ሌሎች ሰራተኞች በፍርሃት ከመደናገር ይልቅ ብልሃትን ነበር የፈጠረው ። በቀጣዩ ቀን የምትወጣውን ጋዜጣ ለማስተዋወቅ ጥሩንባ እየነፋ ያልሰማህ ስማ ማለት ጀመረ ።

<< ኢትዮጽያ የመጀመሪያውን ሮኬት ተኮሰች ! ዝርዝሩን በነገው ጋዜጣ ተመልከቱ ! >> ሲል ብዙዎች ሌሊቱ በግድ ነበር የነጋላቸው ። አርባ ሺህ ኮፒ ጋዜጣ የተሸጠው ግን ተማሪዎች ኩራዝ ቢጤ ለኩሰው የተኮሱትን ቀላል ነገር ነበር ።

<< የገንዘብ ሚንስትሩ ታሰሩ ! >> አለ በሌላ ቀን ደግሞ ድምጹን ጎላ አድርጎ ። ጋዜጣዋ ስትነበብ ግን የታሰሩት የጋናው ሚንስትር ናቸው ። ጻውሎስ በማስታወቂያው ሽወዳ በማብዛቱ ከተቀናቃኞቹ አዲስ ዘመን ተቃውሞ ቢፈጠርበትም ህዝቡ በሌላው ጹሁፉ እየተካሰ ጋዜጣዋን ይበልጥ ወደዳት ። ለአብነት ያህል የካቲት 25/1951 ይድረስ ለእግዚአብሄር በሚል ርዕስ ስር ያወጣው ጽሁፍ በአይነቱና ይዘቱ ለየት ያለ በመሆኑ ህዝባዊ ገረሜታና ፍርሃትን ጎን ለጎን አስተናግዷል ።

<< እንደምን ከርመሃል እንዳልልህ የምታሳምም እንጂ የምትታመም አይደለህም >> ሲል በአግቦ ይጀምራል << እኔ ደህና ነኝ እንዳልልህ ደህንነቴን ታውቃለህና አልደክምም ። አንተ አናደህኛል ፤ መቼም ሁሉን ነገር ተቆጣጣሪ ነህና በመናደዴ ተቆጥተህ እንዳታስጨረግደኝ አደራህን ። እንዲያወም አቦን የመብረቅ ክፍል ሹም አድርገህ ሾመሃል አሉ ... >> እያለ ይቀጥላል ስነጹሃዊው ሽሙጥ ። ስነጽሁፋዊው ውበት ያስደስታል - ሽሙጡ ደግሞ አንባቢ ላይ ፍርሃት እንዲጋባ መንገድ ይከፍታል ።

ጻውሎስ ወደ አዲስ ዘመን ሲዛወር ዝም ለማሰኘት ነበርና የሴቶችና የልጆች ዓምድ እንዲሰራ ተደርጓል ። በኌላ ግን አንድ ጥያቄ አለኝ የሚል የጥያቄና መልስ አምድ በመክፈቱ በዚሁ ጋዜጣም ዳግማዊ የዝና አክሊልን ደፋ ። ወደ ኢትዮጽያ ቴሌቪዥንም ሲዛወር የበሰለ ስራ መስራት ችሏል ። በተለይም የአባይና አዋሽ ወንዝን ከመነሻው እስከ መድረሻው ያለውን ሁኔታ በማጥናት ዘጋቢ ፊልም አቅርቧል ። ይህ የውጭ ጋዜጠኞች አቀራረብ በኛ ሀገር መሞከሩ የጋዜጠኛውን ሰፊ ምናብ ያመላክታል ። ኢትዮጽያ ሬዲዮ ሲዛወር አብዛኛውን ግዜውን ለራሱ መጽሀፍት ስራ ቢያውለውም  አልፎ አልፎ ጣፋጭ ታሪኮችን ያቀርብ ነበር ። ራሱን ጨምሮ ብዙ አድማጮችን ያስለቀሰውን የአለማየሁ ቴዎድሮስን ታሪክ እንደጥሩ አብነት ማንሳት ይቻላል ።

የጻውሎስ ሌላው ግዙፍ ሰውነት ሰብዓዊነቱ ነው ። ረሃብ የጠናበት የወሎ ህዝብ ወደ አ/አ የፈለሰ ግዜ ህዝቡን አስተባብሮ በርካታ ተግባራትን አከናውኗል ። አርባ ሺህ እንጀራ ፣ አራት ሰንጋ ፣ 800 ሊትር ወተት ተሰባስቦ ረሃብተኛው ፋሲካን መፈሰክ ችሏል ። ከአንድ ሺህ በላይ ልብሶች የታደሉ ሲሆን 159 ሺህ ብርም ተሰብስቧል ። ርዳታውን ለማጠናከርም በስሙ የሙዚቃ ባንድ ተቋቁሞ ከጓደኞቹ ጋር ሙዚቀኛ ለመምሰል ጥረት አድርጓል ። ሙሉጌታ ሉሌ በማራካሽ ፣ ጌታቸው ደስታ በፒያኖ ፣ ሳሙኤል ፈረንጅ በድምጽ ፣ ታደሰ ሙሉነህ በቶምቶም ፣ ራሱ ጻውሎስ ከበሮ በመምታት ታዳሚውን አዝናንተው የሚፈለገውን ገንዘብ ሰብስበዋል ።

ጻውሎስ በድርሰት አለም ውስጥም አይነተኛ ሚና መጨወት ችሏል ። ከ 20 በላይ የታተሙና ያልታተሙ ስራዎች አሉት ። በዘርፉም ሲመደቡም ልቦለድ ፣ አስደናቂ ታሪኮች ፣ ታሪክና ኢ- ልቦለዶች ናቸው ። አንዳንዶቹማ ስማቸው ራሱ ፈገግታ ይፈጥራል ። የኔዎቹ ገረዶች ፣ ያራዳው ታደሰና የጌታቸው ሚስቶችን ለአብነት ማንሳት ይቻላል ። የሰካራሞች ሸንጎ የተሰኘው ድርሰቱ ተቆራርጦም ቢሆን ለመድረክ በቅቶለታል ። የጻውሎስን የጽሁፍ ሚዛን ይበልጥ ከፍ ያደረጉት ግን ታሪክ ቀመስ ስራዎቹ ናቸው ። አጤ ሚኒሊክና አጤ ቴዎድሮስን እንደ ማሳያ መጠቆም ይቻላል ። ርግጥ ነው የልቦለዱ ስራዎቹ ብዙ ይቀራቸዋል ። በርግጥ ጻውሎስ ራሱ በአንድ ወቅት << ባለቺኝ ጠንባራ እውቀት እያጠናበርኩ ጠንባራ ድርሰት ቢጤ ካቀረብኩ አይበቃኝም >> በማለት ሙከራዎች መሆናቸውን የመሰከረ < ጠንባራ > ንግግር አድርጓል ።

የመጽሀፍ ነገር ሲነሳ << አጤ ሚኒሊክ ከሀገር ውስጥና ከወጭ የተጻጻፏቸው ደብዳቤዎች >> የሚል መጽሀፍ ለማሳተም በተዘጋጀበት ወቅት ከመንግስት የደረሰበት የሳንሱር አፈናና የርሱን የድፍረት ግብግብ ሳይጠቀስ የሚታለፍ አይሆንም ። መጽሀፉን ሰርቶ እንደጨረሰ ለኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ለግምገማ ይልካል ። ይሁን እንጂ ገና መጽሀፉን እንዳስመዘገበ መጽሀፉ < ከበላይ ይፈለጋል > ተብሎ ተወሰደበት ። ይህንን ወሬ እንደሰማም አሳታሚ ድርጅቶቹን መጽሀፌን መልሱ ብሎ ያፋጥጣቸዋል ፤ ተወስዷል ይሉታል ።

<< ማነው የወሰደው ? >>

<< የበላይ አካል >>

<< ንገሩኝና ሄጄ ልጠይቅ >> ቢልም < ታስበላናላህ > በማለት ምለሽ ይነፈገዋል ። ይሄኔ ግን የፈለገ ይምጣ በሚል ለመንግስቱ ሃይለማርያም የሚከተለውን ደብዳቤ ጻፈ

<< መጽሀፉን ካለችኝ ደመወዜ ፣ ለቤቴ እንኳን ከማይበቃው ደመወዜ ለፍቼ  ያዘጋጀሁት ነው ። ለሳንሱር ሰጥቼ ብጠይቅ የበላይ አካል ወስዶታል ታስበላናለህ አሉኝ ። የሚበሉት የመጨረሻ አካል እርስዋ ስለሆኑ መጽሀፌን ይመልሱልኝ >> ዳሩ ምን ያደርጋል ምላሽ ሳያገኝ የኢህአዴግ መራሹ ቡድን ወንበሩን ወረሰ ። ጻውሎስ የመጽሀፉን የመጨረሻ እጣ ፈንታ ሳያይም ነው ሞት የወሰደው ።

መጽሀፉ የጻውሎስን ገጠመኝና ትዝታዎች በአስደማሚ መልኩ በስፋት ይዳስሳል ። ቀልድና ፌዞቹ ብብትን ኮርኩረው የሳቅ ፈንዲሻን ይበትናሉ ። ቁምነገሩ ፣ ሀገራዊ ስሜቱ ፣ ድፍረቱ ፣ ለማወቅ የሚያደርገው ጥረትና ተቆርቋረነቱ በእጅጉ ይመስጣል ። በርግጥም ደራሲው ስለ ጻውሎስ መባል ያለበትን ሁሉ በማለቱ ምስጋና ይገባዋል ። ከአንባቢው የሚጠበቀው የተባለውን ነገር ዛሬ ነገ ሳይል ማጣጣም ብቻ ።

 

 

 

Thursday, May 29, 2014

ማቋረጥ

                                      

                   . ልቦለድ ቢጤ

መምህር ተሻለ አዲስ አበባ ውስጥ አለ በሚባለው ትምህርት ቤት ውስጥ የአማርኛ መምህር ነው ። ለሁለት ሰዓታት የነበረውን እረፍት ከጓደኞቹ ጋር ቼዝ ሲጫወት ቆይቶ ፔሬዱ ሲደርስ ወደሚያስተምርበት ክፍል እየተጣደፈ ሲጓዝ ነበር ድንገት ከኌላው በዳይሬክተሩ አቶ ዘሩ የተጠራው
<< የት ክፍል እየገባህ ነው ? >>
<< ስድስተኛ ቢ ነኝ - ምነው ፈለጉኝ እንዴ ? >>
<< እንግዶቹ ቤተመጻህፍቱንና ላቦራቶሪ ክፍሉን ጎብኝተው ጨርሰዋል >>
<< እንዴ እስካሁን ከዚህ ግቢ አልወጡም ? >> አለ ተሻለ በግርምት
<< አዎ አኔ ቢሮ ብዙ ስለቆዩ ነው ። ሪፖርቴን ጣፋጭ በሆነ መልኩ አቅርቤያለሁ ። ምቀኞች ደካማ ነው እያሉ የሚያሰወሩትን የትምህርት ጥራት መገምገም ስለፈለጉ ተግባራዊውን ነገርም ማየት ፈልገዋል ። ዛሬ ርዕሰ ጉዳይህ ምንድነው ? >> ዳይሬክተሩ እየተጣደፉ ነው የሚያወሩት ።
<< ቃላት ፣ የቃላት እርባታና የቃላት አረዳድ የሚል ነው ። በተጨማሪም ... >>
<< ኡ ? ... ምነው ተሻለ ? ምንድነው ዲሪቶ አደረከው እኮ ? >>
<< ተማሪዎች አንድን ተመሳሳይ ቃል እንዴት እንደሚተረጉሙትና በምሳሌም እንዴት እንደሚያስደግፉት የሚታይበት በመሆኑ የአረዳድ ማዕዘናቸውን የሚያሰፉበት ነው >>
<< ጥሩ ... ጥሩ ... ዘዴው ምንድነው ? ማለቴ የምታስተምርበት ? >> አሉ ግራና ቀኝ እየተገላመጡ
<< ተማሪዎች ቃሉን ከሶስት ቀናት በፊት ስለወሰዱ ያዩበትን መንገድ ሰምተን ወደ አጠቃላዩ ትምህርት ነው የምንደረደረው >>
<< አደራ እንግዲህ ? ... >> ዳይሬክተሩ ሀሳባቸውን ሳይቋጩ እንግዶቹን ወዳዩበት አቅጣጫ በሩጫ ተፈተለኩ ።
ሃላፊ ሆኖ የመርበትበትና ሃላፊ ሆኖ የመኮፈስ መንታ ገጽታዎች ሽንት ቤት ገብቶ አሜባን ማማጥና ከግልግል በኌላ ፈገግ ብሎ ቀበቶን ከማሰር ጋር እንዴት እንደተመሳሰለበት አላወቀም - ግን ያለቦታው ይህን ምሳሌ ነበር ሲያነጻጽር የነበረው ። ወደመሬት ወድቄ እምቦጭ እላለሁ የሚል የሚመስለውን ቦርጭ በአንድ እጅ ፣ ወዲህና ወዲያ የሚወራጨውን ካራቫት በሌላ እጃቸው ይዘው በዚህን ያህል ፍጥነት መሮጣቸውም በአስገራሚ መልኩ ፈገግታ ጭሮበታል ።
ለመምህር ተሻለ የማስተማር ስልት መሰረት የሆነው ቢቢሲ የተባለው መገናኛ ብዙሃን ነው ። ይህ ጣቢያ በቀጣዩ ሳምንታት የሚያቀርባቸውን አንኳር ጉዳዮች አስቀድሞ ነው የሚያስተዋውቀው ። ተማሪዎችም ቀጣዩን ምዕራፍ አስቀድመው ካወቁ መደናገርን አስወግደው ተሳታፊና እንደ ካራ ስል ይሆናሉ የሚል እምነት አለው ። ይህ ስልት ከፍተኛ ባለስልጣን ፣ ሀብታሞችና ታዋቂ ሰዎች ልጆቻቸውን በሚያስተምሩበት በዚህ ትምህርት ቤት በሁሉም መምህራን እንደ ቋሚ አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን በተለያዩ ግዜያት በተካሄዱ ስብሰባዎች ላይ እስከመናገር ደርሷል ። የማስተማሪያ መንገድንና የፈተና አወጣጥ ዘዴን ደብቅ እያደረግን የትምህርት ጥራትን ከፍ ለማድረግ መሞከር ከንቱ ምኞት ነው የሚል ሀሳብም አለው ።
የስድስተኛ ቢ በር ድንገት ተበርግዶ በርካታ የሀገሪቱ ባለስልጣናት ተግተልትለው ወደ ውስጥ ሲገቡ ተማሪዎቹ እንግዶቹን ቆመው ተቀበሏቸው ። እንግዶቹ ክፍት በተደረገው አንደኛው ጠርዝ ከተቀመጡ በኌላ መምህር ተሻለ ሞቅ ያለ ሰላምታ አቅርቦ ማስተማሩን ቀጠለ ።
<< እሺ ተማሪዎች ሁላችሁም እንደምታውቁት የዛሬው ክፍለ ግዜ የቃላት አረዳድ ላይ የተመሰረተ ነው ። እስኪ ዋነኛ ቃሉን የሚያስታውሰኝ ማነው ? >>
<< አቋረጠ >> አለ በላይ የተባለው የክፍሉ አለቃ ተሽቀዳድሞ ፤ እንደስሙ ሁሌም የበላይ መሆን አለብኝ ብሎ ስለሚያስብ ለብዙ ነገሮች ደንታ የለውም ።
<< ልክ ነው አቋረጠ ሲረባ ማቋረጥ ፣ ያቋርጣል ፣ አቋራጭ ፣ ያቆራርጣል ወዘተ እያለ ይቀጥላል ። ለመሆኑ አቋረጠ ምንድነው ? እንዴት ተረዳችሁት የሚል ነበር የቤት ስራው ? >>
<< እሺ መስፍን >> አለ መምህር ተሻለ እጅ ካወጡት ውስጥ ለአንደኛው እድል እየሰጠ
<< አቋረጠ ማለት የቀለበት መንገድ አጥርን ዘለለ ማለት ነው ። ሰዎች ብረቱን የሚያቋርጡት በቅርበት መሸጋገሪያ ድልድይ ስለማይሰራላቸው ነው ። ሆኖም ብዙ ሰዎች ቶሎ እንደርሳለን ብለው ሲዘሉ በመኪና አደጋ እስከመቼውም ሳይደርሱ ቀርተዋል ። የመኪና አደጋ አሰከፊ ነው >> አለ ተማሪው የሀዘን ገጽታ እያሳየ ።
<< የማን ልጅ ነህ መስፍን ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር በፈገግታ
<< የኢንጂነር ፈቃዱ >> ባለስልጣናቱ በአግርሞት ሳቅ አውካኩ
<< በመንፈስ ደግሞ የሳጅን አሰፋ ... >> አሉ ጥግ ላይ የተቀመጡት የፖሊስ ኮሚሽነሩ ፤ ቤቱ እንደገና በሳቅ ተንጫጫ ።
<< እሺ አያሌው ? >> ሳቁ እየሰከነ ሲመጣ መምህር ተሻለ ሁለተኛውን ተጠያቂ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የቀበሮ ማቋረጥ ነው ። ሰዎች ለውጊያ ሲሄዱ ቀበሮ መንገዱን ካቋረጠቻቸው ይሸነፋሉ ። አጼ ቴዎድሮስም ሆኑ አጼ ሚኒሊክ በዚህ እንደሚያምኑ አያቴ አጫውተውኛል >> አለና ቁጭ አለ ። መምህር ተሻለ ፊት ላይ መደናገጥ ቢታይም ባለስልጣናቱ ከመሳቅ የገደባቸው ነገር አልነበረም ።
<< አያሌው አያትህ ማናቸው ? >> አሉ አሁንም አንደኛው ሚኒስትር እንደዘበት
<< ቀኛዝማች ነቅአጥበብ ....  >>
ወደ መሃል ቁጭ ያለ አንድ ባለስልጣን የተማሪውን ሀሳብ አቋርጦ << እነ ፊታውራሪና ቀኛዝማች አሁንም ሄደው ሄደው አላለቁም እንዴ ? >> ከማለቱ ቤቱ በእንባ ቀረሽ ሳቅ ተበጠበጠ ። መምህር ተሻለ የውሸት ፈገግታ እየታየበት ቀጣዩን ተማሪ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የማራቶን ሩጫን ማቆም ማለት ነው ። ሩጫውን የሚያቆሙት ወንዶች ናቸው ። ወንዶች ሩጫውን የሚያቋርጡት በሴት ሰዓት ላለመግባት ነው ። የአባቴ ስም አሰልጣኝ ቶሎሳ ይባላል >>
የስድስተኛ ቢ ክፍል ኮርኒስ በሳቅ ወላፈን የእሳት ጢስ የፈጠረ መሰለ ። ሳቁን ያባባሰው ተማሪው አይቀርልኝም ብሎ ከወዲሁ  የአባቱን ስም ማስተዋወቁ ነበር ።
<< ማነህ ስምህ ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ወደተናጋሪው ተማሪ እየተመለከቱ
<< ዘላለም >>
<< ዘላለም  እኔ እንኳን የአባትህ ስም ቱርቦ ቱሞ ይሆናል ብዬ ጠብቄ ነበር >> አሉ ቀድመው እየሳቁ
<< እንዴ አያውቁም እንዴ ? እሱ እኮ ሞቷል - በጣም ጎበዝ አትሌት ነበር ። የሞተውም ተማሪ መስፍን እንዳለው በመኪና አደጋ ነው ። በመኪና አደጋ ላይ ብዙ መሰራት አለበት >> አለ ተማሪው ፈርጠም ብሎ
<< በእውነት የተማሪዎችህ የአመላለስ ስርዓት ጥሩ ነው ። በተለይ ጥሩ ነው ያልኩት በጣም ግልጽ ከመሆናቸው አንጻር ነው ። ይህ ባህሪ ነው እያደገ መውጣት ያለበት ። አንድን ጉዳይ የሚያዩበት መንገድም እንደሀገራችን ብሄር ብሄረሰቦች የሰፋና የሚያምር ነው ። የመሰላቸውን የመናገር ነጻነትም እንዳላቸው መረዳት ይቻላል ... >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ስሜታቸውን መቆጣጠር እያቃታቸው ።
ተማሪዎች እንደ ማዕበል በሚንጠው የሳቅ ጎርፍ ሳይናጡ እጃቸውን ለተሳትፎ በጉጉት ከማውጣት አልተቆጠቡም ። በምስጋናው የተነቃቃው መምህር ተሻለ ለመጀመሪያ ግዜ የሴት እጅ በማየቱ ተሳትፎውን ለማሰባጠር የመናገር እድሉን ትእግስት ለተባለች ተማሪ ሰጣት
<< አቋረጠ ማለት ንግግር አቋረጠ ማለት ነው ። ንግግር የሚያቋርጠው ደግሞ አበበ ገላው የተባለ ሰው ነው ። አበበ ገላው የጠላውንም ሆነ የወደደውን ሰው ንግግር ያቋርጣል ። አበበ ያቋረጠው ሰው የሀገር ውስጥ ስሪት ከሆነ ሰውየው ይሞታል ። ለምሳሌ ያህል ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ። አበበ ያቋረጠው ሰው የውጭ ሀገር ስሪት ከሆነ ሰውየው አይሞትም ። ለምሳሌ ያህል ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ >>
በሳቅ ሲታመስ የነበረው ክፍል በሚያስደነግጥ ጸጥታ ተወጣጠረ ። የባለስልጣናቱ ግንባር እንደ በረሃ መሬት እየተሰነጣጠቀ አስፈሪ የቦይ ምስል ሲፈጥር በግልጽ ይታያል  ። በግልባጭ በመምህር ተሻለና ዳይሬክተሩ ጆሮ ግንድ ስር መነሻውን አናት ያደረገ የላብ ጎርፍ ወደታችኛው የሰውነት ክፍሎች ደለል እየጠራረገ በፍጥነት ያሽቆለቁል ነበር ።
<< ምን እየተካሄደ ነው አቶ ዘሩ ?! ትምህርታዊ ኩዴታ እያደረጋችሁ ነው ! >> ተቀዳሚው ሚኒስትር ከወንበራቸው ተነስተው  ጸጥታውን በረጋገዱት
<< በእውነት አይን ያወጣና የተቀነባበረ የሽብር ተግባር ይመስላል ! >> ቃለ አቀባዩ እንደ ነብር ገሰሉ
<< በጣም ይቅርታ እጠይቃለሁ ። ምሳሌዎቹ በዚህ መልኩ ይቀርባሉ ብዬ አልጠበኩም ። የትምህርት ማቋረጥ ፣ የጽንስ ማቋረጥ ፣ የመንገድ መቋረጥ ፣ የወንዝ ማቋረጥ የሚኖራቸውን ተጽዕኖ አጉልቶ በማውጣት ... >>
<< ዝም በል አንተ ! ራስህ አቋርጥ ! ... ንግግርህን አቋርጥ ! ... >> የፖሊስ ኮሚሽነሩ ሌባ ጣታቸውን ቀስረው እየተንቀጠቀጡ የመምህር ተሻለን ቀልብ ገፈፉት ። ተክዘው የቆዩት አንደኛው ሚኒስትር ጣልቃ ገብተው <<  ያሳዝናል ! በተለይ ከዚህ ትምህርት ቤት ይህን የመሰለ ተራ አሉባልታ መስማት ያሳፍራል ... ትዕግስት ለመሆኑ የማን ልጅ ነሽ ? >> ሲሉ ለስለስ ባለ ድምጽ ጠየቋት
<< የአበበ >> አለች ልጅቱ ፈራ ተባ እያለች
<< የአበበ ? >> አንደኛው ሚኒስትር አንዴ ልጅቱን ሌላ ግዜ ባለስልጣናቱን እያፈራረቁ ተመለከቱ
<< የቱ አበበ ?! >> አሉ በመገረምም በመኮሳተርም
<< የአበበ ገላው እኮ አይደለም ! የጄኔራል አበበ ... >> የክፍሉ አለቃ በላይ ነበር ጣልቃ ገብቶ የመለሰላት ፤ ትዕግስት ጭንቅላቷን  አወዛወዘች
አንደኛው ሚኒስትር ተጨማሪ አስተያየት ሳይሰጡ ከክፍሉ ሲወጡ ባለስልጣናቱም እየተጣደፉ አጀቧቸው ። ፖሊስ ኮሚሽነሩና አንድ የደህንነት ባለስልጣን የአቶ ዘሩንና የመምህር ተሻለን ክንድ እንደ ምርኩዝ ተጠቅመው ተከተሉ ። የክፍሉ አለቃ በላይ እየሮጠ በሩን ከፍቶ የእንግዶቹን መራቅ ካረጋገጠ በኌላ ጥቁር ሰሌዳው ላይ << ማቋረጥ >> ሲል በትልቁ ጻፈ ። የክፍሉን ግራና ቀኝ ካሰተዋለ በኌላ
<< ቃሉ ማቋረጥ ቢሆንም እኛ እንቀጥላለን - ተጨማሪ ሃሳብ ያለው አለ  ? >> ሲል እጁን ኪሱ ከቶ ጠየቀ ። ዘላለም እጁን አወጣ
<< እሺ ዘላለም >>
<< ማቋረጥ ማለት የመምህር ተሻለን ትምህርት ማቋረጥ ነው >>
<< ትስማማላችሁ ? >>
<< በጣም ! በጣም ! ሰሌዳው ላይ ጻፈው ! ጻፈው ! >> ሲሉ ተንጫጫቡት ። በላይ የተነገረውን ጹሁፍ በትልቁ ጻፈው ። ቀጥሎ እጅ ያወጣችው ትዕግስት ነበረች
<< እሺ ትዕግስት ተጨማሪ ነው ? >>
<< ዋናው ጥያቄ የስድስተኛ ቢ የእውቀት ጉዞ ለምን በድንገት ተቋረጠ የሚለው ይመስለኛል ? >> ስትል ጥያቄ አዘል አስተያየት ወረወረች ። አለቃው የትዕግስትን ጥያቄ አሁንም ሰሌዳው ላይ አሰፈረው ።
<< እውነት የስድስተኛ ቢ የእውቀት ግጥሚያ ለምን ተቋረጠ ? >> ሲል የክፍሉ አለቃ እየንተጎራደደ ጠየቀ ። አያሌው እጅ በማውጣቱ እንዲናገር ተፈቀደለት ።
<< የእውቀቱ ጉዞ የተቋረጠው  ብዙ ቀበሮዎች ክፍላችንን ስላቋረጡት ነው ! ይህን አያቴ የነገሩኝ ሳይሆን አይኔ የተመለከተው ነው >> ሲል የክፍሉ ተማሪዎች በመልስ አሰጣጡ በሳቅ መንፈራፈር ጀመሩ ። አሳሳቃቸው የባለስልጣናቱን የሳቅ ከፍታ በልጦ መገኘትን ያለመ ይመስል ነበር ።
<< ምንድነው እንዲህ የሚያደርጋችሁ ... ?! >> የሚለው ደንገተኛ ድምጽ ከወደ በሩ ብቅ ብሎ የሳቁን ወላፈን በአንድ ግዜ ጤዛ አለበሰው ።
የነገር ሽታን የሚያነፈንፈው የደህንነቱ ሰው ኮሚሽነሩን አስከትሎ ወደ ክፍል ገባ ። ከዚያም የስድስተኛ ቢን ተማሪዎች ትምህርት ከጥቁር ሰሌዳው ላይ በቅደም ተከተል በጥንቃቄ ማንበብ ጀመረ ።
< ቀበሮዎች > የሚለው ቃል ጋ ሲደርስ ግን ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም ። የስድስተኛ ቢ ክፍል ተማሪዎች በባለስልጣኑ ድራማዊ ተግባር  ተገርመው ሳቁን ሊያጅቡት ቢገባም በፍጹም አልሳቁም ። በሚከብድ ጸጥታ የአሳሳቁን አይነት እየመረመሩና ቃሉን በነገር እያራቡ ነበር ። ከልቡ ሳቀ ... ከአንገት በላይ ሳቀ... እንደ ማሽላ ሳቀ...
ሳቀ ...
ይሳቅ ...
ስቆ...
አሳሳቆ ...

Monday, May 12, 2014

የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ?




ፖሊስ ረብሻንና ብጥብጥን ለማረጋጋት መጀመሪያ መጠቀም ያለበት ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርሱ በማይችሉ ነገሮች ነው ። ምክንያቱም ሰው የመኖር ፣ ከግርፋትና ሰብዓዊነት ከጎደለው አያያዝ የመጠበቅ መብት አለውና ። ለዚያም ነው ቆመጥ ፣ ውሃ ፣ አስለቃሽ ጋዝ ፣ የፕላስቲክ ጥይትና የመሳሰሉት በመጀመሪያ ረድፍ የግድ መታየት የሚኖርባቸው ።
በርግጥ እነዚህ ድርጊቶች በራሳቸው ጉዳት ሊያመጡ ስለሚችሉ ተግባራዊ ሲደረጉም ጥንቃቄና ሰብዓዊነት የተላበሰ መርህን ይፈልጋሉ ። ለምሳሌ ያህል ፖሊስ ዱላ ሲጠቀም በፍጹም ጭንቅላት ፣ አንገት ፣ አከርካሪ አጥንት ፣ ልብና ኩላሊት ላይ ማነጣጠር የለበትም ። የፕላስቲክ ጥይትም ቢሆን ከደረት በታች ባሉ የሰውነት ክፍሎች ላይ ነው ተግባራዊ መሆን ያለበት ። አስለቃሽ ጋዝም መጠኑና ደረጃው ከፍ እንዳይል ጥንቃቄ ይፈልጋል ።
የሀገራችን እውነታዎች ግን ለዚህ መርህ ጀርባቸውን የሰጡ መሆኑ ይታያል ። ፌዴራል ፖሊስ በአንድ ምት ጭጭ የሚያደርገውን ዱላውን በቀጥታ የሚሰነዝረው ለጭንቅላት ነው ። አጋጣሚ ሆኖ በሁለት ምክንያቶች ኢላማዎች ግባቸውን ይስታሉ ። አንዱ እንደ አይን ሁሉ የጭንቅላት አምላክ አትርፎህ ዱላው ጀርባህን እንደ ሙሴ ዘመን ባህር ይሰነጥቀዋል ። ሁለተኛው ራስህን ለመከላከል ወደላይ የሰነዘርከው እጅህ ተሰብሮም ቢሆን አንጎልህን ከመፈጥፈጥ ይታደገዋል ። በጣም የሚያሳቅቀው ግን አንዱ ፖሊስ መምታት ሲጀምር ሌላውም ሰልፍ ጠብቆ የጭካኔውን ደርሻ ማዋጣቱ ነው ። በሰብዓዊ ስሜት ተገፋፍቶ < እረ ይበቃዋል ? > ብሎ የሚከላከል አለመገኘቱ ሌላኛው አሳዛኝ ክስተት ነው ። ሰው ሬሳ እስኪሆን ድረስ እንደ እባብ መቀጥቀጥ ምን የሚባል ትምህርት እንደሆነ ግልጽ አይደለም ። ሰብዓዊው ህግ ብዙ ደም ለፈሰሰው የመጀመሪያ እርዳታ እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፈጠር እንዳለበት ሁሉ ያዛል ። በመሰረቱ እንደዚህ አይነት ክስተቶች የመሰረታዊ መብት ጥያቄዎች ግብግብ እንጂ ድንበር የመቁረስ ወይም ሀገር የማስገበር ጦርነት አይደለም ። በለየለት የሁለት ሀገር ጦርነት ላይ እንኳን የተማረከ ወታደር በቁጥጥር ስር ይውላል እንጂ ሰብዓዊና ሞራላዊ ህግን በመተላለፍ አይጨፈጨፍም ። ጀግኖች የሚቀጡህም ሆነ ጠማማ ካለብህ የሚያስተካክሉህ በማስተማር ነው ።
ለህይወት አስጊ የሆነው ተኩስ በአስገዳጅ ሁኔታ ተፈጻሚ ሊሆን የሚችለው በተለያዩ አጥጋቢ ምክንያቶች ነው ። ፖሊሱ ሁሉንም ስልቶች ውጤት አጥቶበት በተለይም ሁከቱ በህይወቱ ላይ አደጋ የሚያስከትልበት ከሆነ ራሱን ለመከላከል ፣ ሁከቱ የሌሎች ሰዎችን ህይወት ሊያጠፋ የሚችል ከሆነ ተመጣጣኝ ርምጃ ሊወስድ ይችላል ። ከረብሻና ተቃውሞ ዉጪም አንድ ወንጀለኛ ካመለጠ ሌሎችን ይጎዳል ተብሎ የሚታሰብ ከሆነ መሳሪያ ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል ።
ይህ ማለት ግን ከላይ የተቀመጡትን ምክንያቶች ሰበብ በማድረግ ፖሊስ ወይም የተደራጀው ሃይል ፍጹም ሊተካ የማይችለውን የሰው ልጅ ህይወት ይቀጥፋል ማለት አይደለም ። በተመድ ለፖሊስ የተዘጋጁ ደረጃቸውን የጠበቁ የስልጠና ማንዋሎች እንደሚያስረዱት እያንዳንዱ ፖሊስ ወደ ስራ ከመግባቱ በፊት በስልጠና ወቅት ራስን ስለመከላከል ፣ ስለ ሰብዓዊ አያያዝ ፣ ስለመጀመሪያ ርዳታ ፣ ስለተሰበሰበ ህዝብ ባህሪ ፣ ስለግጭት አፈታት ፣ ስለውጥረት አስተዳደር ወዘተ በቂ ትምህርት የሚያገኝ ቢሆን በችግር ግዜ አንድና አንድ ወደሆነው ግድያ ወይም የፈሪ ዱላ በፍጥነት አያመራም ። በስልጠና የበለጸገ እንዲሁም የሃላፊነቱ ሚና ከህዝባዊነት የመነጨ መሆኑን የሚገነዘብ ፖሊስ ቢያንስ በመጨረሻው ሰዓት ሲተኩስ እንኳ ወንጀለኛን ለመቆጣጠር እንጂ ነፍስን ለማቋረጥ አያልምም ። ጭንቅላት መምታት ነጥብ የሚያሰጠው በስልጠና ወቅት የተኩስ ሰሌዳ ላይ እንጂ የራስህ ቤተሰብና ወገንህ ተቸግሮ ተቃውሞ በሚያሰማበት ወይም ሁከት በሚፈጥርበት አንድ ቀን አይደለም ። ዞሮ ዞሮ ህዝብ ጠላት ሆኖ ስለማያውቅና ሊሆንም ስለማይችል እግሩን መምታትም ሲበዛበት ነው ።
አዲስ አበባንና በዙሪያዋ የሚገኙ የኦሮሚያ ከተሞችን በማካተት የተዘጋጀውን የጋራ ማስተር ፕላን በመቃወም በየቦታው የተቀሰቀሰው ቁጣ የብዙ ሰላማዊ ዜጎችን ህይወት በልቷል ። መንግስት የሟቾቹን ቁጥር 11 ቢልም ተቃዋሚ ድርጅቶች እስከ 45 ያደርሱታል - የውጭ መገናኛ ብዙሃን ደግሞ አስከ ሰላሳ ። የቁጥር ዝቅታና ከፍታ የሚመነጨው ኌላ የሚቀርበውን ዓለማቀፍ ስሞታና ክስ ታሳቢ ከማድረግ አንጻር ነው ። አነስተኛ ሰው ከሞተ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድኩት በማለት ቁጣን ለማርገብ ይቻላል ። የኢትዮጽያ መንግስት በዛ ያሉ መብት ጠያቂዎችን በአደባባይ የመግደል ልምድ ከግዜ ወደ ግዜ እያደበረ የመጣ ይመስላል ።
በምርጫ 97 ማግስት በተቀሰቀሰ ቀውስ የሰው ልጅ ክብር ህይወት በጥይት ሲረግፍ አቶ መለስ ዜናዊ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድነው በማለት መጠነኛ አሃዝ በመጥቀስ መግለጫ ሰጥተው ነበር ። ሆኖም ጉዳዩን እንዲያጣራ የተሰየመውና በአቶ ፍሬህይወት ሳሙኤል የሚመራው ቡድን << መንግስት ያልተመጣጠነ/ ከመጠን ያለፈ /  ርምጃ ወስዷል >> የሚል ያልተጠበቀ ሪፖርት አቀረበ ። በሪፖርቱ መሰረት 193 ሰዎች በጥይት ሲሞቱ 763 ያህል ቆስለው ነበር ። ሪፖርቱ ጓዳ የነበረን ራቁት ገላ ድንገት ለአደባባይ ያጋለጠ አውሎ ንፋስ ነበር ።
ተቃውሞ የሚበርደው ሰዎች ሲሞቱ ነው የሚለው ፍልስፍና ያልተለወጠ መሆኑም የዛሬው እውነታ እያሳበቀ ነው ።  በ1997 ግርግር አንዳንድ የአዲስ አበባና ፌዴራል ፖሊስ አባላት አጋዚ የተባለው ልዩ ጦር እንጂ እኛ ሰላማዊ ህዝብን አልገደለንም እያሉ ራሳቸውን ነጻ ሲያወጡ ነበር ። መጸጸቱ በራሱ ጥሩ ይመስለኛል - ግን ይህ አይነቱ ደመ ንጹህነት መሰዎዕትነት ለሚከፈልለው ሲቪል ማህበረሰብ ትርጉም አልባ ነው ። መደበኛው ፖሊስ የመግደል አማራጭን በመርህ ደረጀ የማይቀበል ከሆነ የገዳዩንም ጣልቃ ገብነት ማለዘብ የሚከብደው አይሆንም ። ምናልባት መቋቋም የማይችለው የአስገዳዩን ቀጭን ትዕዛዝ ከሆነ አላውቅም ። ዞሮ ዞሮ በኛ ሀገር ፖሊሲያዊም እንበለው አጋዚያዊ ቀመር የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ? ስንት ሰው ሲሞትና ስንት ሰው ሲቆስል ? ይህ ወለል ካልታወቀ እንዴት ነው < የወሰድኩት ርምጃ ተመጣጣኝ ነው > ማለት የሚደፈረው ? ግድያን ለማስቀረት መጣሩ ነው የሚሻለው ወይስ እየገደሉ በቁጥር ጅዋጅዌ መጫወት ?
የዛሬ የገደላ ዜና በሁላችንም የባንክ ደብተር ውስጥ የሚቀመጥ የቁጠባ ቦንድ ነው ። ይህን ኖት ነገ እያወጣን ስንመዝረው ውስጣችንን የሚሞላው ፍርሃት አፋችንን የሚሞላው ደም ነው ።
 እናም ነገ ያስፈራል ።
ውሃ ጠማኝ ፣ ደመወዝ አነሰኝ ፣ መሬቴን በህገወጥ መንገድ ተቀማሁ ፣ አስተዳደሩ ገለማኝ ብሎ ለተቃውሞ አደባባይ የሚወጣ ሰው ባልጠበቀው መልኩ ስሙ አሸብር ፣ ነውጤ ፣ ነፍጤ ተብሎ ቢቀየር እስር ቤት ሊያደርሰው ይችላል ።
ያስፈራል ።
የተቃውሞ ሰልፍ ድንገት ተደናቅፎ ግርግር ከፈጠረ ወይም ነፍሰጡሩ ተቃውሞ ድንገት ሜዳ ላይ ብሶታዊ ልጅ ቢገላገል ሊያስገድል ይችላል ።
በ2001 በወጣው የጸረ ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀጽ 21 << ናሙናዎችን የመስጠት ግዴታ >> ላይ ተጠርጣሪው ለምርመራ ፍቃደኛ ካልሆነ ፖሊስ አስፈላጊ የሆነ ተመጣጣኝ ሃይል ተጠቅሞ ከተጠርጣሪው ናሙና ሊወስድ ይችላል ይላል ። ተመጣጣኝ ሃይል  እዚህም ጋ አለች ።  እንግዲህ ሰውየው መረጃ አልሰጥም ብሎ ግግም ካለ ፖሊስ ገድሎትም ቢሆን ናሙና ይወስዳል ማለት ነው ? -  አያስቅም - ያስፈራል ።

           

Tuesday, May 6, 2014

እናትነት






ፍቅር - ቋንቋ - ቀንዲል ውበት

የልብ - የአንጀት - ጠሊቅ እውነት

እናትነት...                                                                                               

የደም ውህድ - ክፋይ ስጋ

የምጥ ስርፀት - የአጥንት ዋጋ ።


/ ለእናቴ የብርጓል ዘውዴ /                                                                                                                                       

 

Sunday, April 27, 2014

የደነበረው


የደነበረ በሬን የሚያረጋጋው ሁለተኛ አካል የለም ። በሬው መረጋጋት የሚችለው የራሱ የድንጋጤና የፍርሃት ድልቂያ በራሱ ግዜ እየሳሳ ሄዶ ጸጥ ማለት ሲጀምር ነው ።
እንደእኔ እምነት ኢህአዴግ ከደነበረው መንፈስ ገና አልተላቀቀም ። ድርጅቱ ገመድ በጥሶ መሮጥ የጀመረው በ1997 « እንከን የለሽ » ምርጫ ወቅት ነበር ። ዘጠኝ የእፎይታ አመታት በማለፉ ረጅም ቢሆንም እስካሁን እንከን የለሽ መረጋጋት አልፈጠረለትም ። ምክንያቱም ጉዳቱ ከስሜታዊ ቁስል ወደ ስነልቦና ጉዳት ሳይታወቅ ያደገ / Trauma / በመሆኑ ተመሳሳይ ግዜያትን ጠብቆ ሊገነፍል ስለሚችል ።
ያኔ በስንት ደምና አጥንት ያመጣነው ድል ድንገት ከከተማ በበቀለ እንጉዳይ / ድርጅት / እንዴት ይነጠቃል ? በሚል የአጥቢያ ድል አለቆቻችን ሳይቀሩ ቢሮ ዘግተው እዬዬ ብለዋል ። የቅንጅት ጉዳይ ያው በሚታወቀው መልኩ ከተዘጋ በኃላ በሬው እየፎገረ ማባረር የጀመረው « ሀሳብ » ን ነበር - ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብትን ። በዚህም በርካታ የህትመት ውጤቶች ከገበያው ድራሻቸው ጠፋ ። በሬው ይህን ርምጃ የወሰደው በግራና ቀኝ ጆሮው ላይ መርፌ እየወጉ ከሚያስፈረጥጡት አካላት አንደኛው መሆናቸውን በመረዳቱ ነው ።
ከዚያ ወዲህም ከዴሞክራሲ መብቶች አንዱ የሆነው ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብት ከአደገኛ ቀጠና ውስጥ መውጣት አልቻለም ። አንዴ ፈንጂ ወረዳ ስለሆንክ ግራና ቀኝህን ተመልከት ሲባል ሌላ ግዜ ቀይ መስመሩን አትጠጋ ወይም አትርገጥ ሲባል እየተሳቀቀ ቆይቷል ። በርግጥ የሀገራችን ህገ መንግስት ለዚህ መብት መበልጸግና መፋፋት በጽሁፍ ደረጃ ድጋፍ ይሰጣል ። ጋዜጠኛው አንዳንዴ ይህን እያሰበ የተወሰነ ርቀት ሲጔዝ ቢታይም ድንገት ከሩቅ የሚተኮስ ድሽቃ ከአፈር ይቀላቅለዋል ። ብእረኞቹ በሚደርስባቸው ተጽዕኖ ሲያማርሩና ሲያቃስቱ ፣ ከታፈረውና ከተከበረው ውክቢያ ጋር ፖሊስ ጣቢያና ፍርድ ቤት ሲመላለሱ ፣ መፈክር ይሁን ቁጣ ባለየ መልኩ ሲገሰልባቸው ፣ አንዳንዴም ሲታሰሩ ማየት ብርቅ አልሆነም ።
በመሰረቱ ኦትዮጽያ የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌን የህጔ አካል አድርጋ ተቀብላለች ። ይህም ግዙፍ ክሬዲት ሆኖ በየስብሰባው ምስጋና መወድስ ተዘርፎለታል ። አንዳንድ ነጭ ጥናት አቅራቢዎች < ኢትዬጽያን ተመልከቱ የህገ መንግስቷ አብዛኛው ገላ በሰብዓዊ መብት መልካም መዓዛ የታወደ ነው ፣ የኢትዬጽያን መንገድ ተከተሉ በስብዕና ፍቅር ትሰክራላችሁና > በማለት ምስክርነት ሲያቀርቡ ... እሰይ አበጀሽ የኛ ሎጋ አበጀሽ የኛ ልጅ .... እያልን ማስታወሻችን ላይ አንጎራጉረናል ። በየአለማቀፉ ሰብዓዊ መብት ድንጋጌ ታዋቂው አንቀጽ / 19 / ሁሉም ሰው ሀሳቡንና አስተያየቱን ያለማንም ጣልቃ ገብነት በማንኛውም ሚዲያ መግለጽ እንደሚችል ይደነግጋል ። ህገ መንግስታችን አባባሉን እንዳለ ወስዶ የአንቀጹን ቁጥር ብቻ ነው 29 ያደረገው ። ውበት ነበረው ። መልክ ብቻ ምን ያደርጋል ሆነ እንጂ ። በነገራችን ላይ ይህ መብት የተሰጠው  ለጋዜጠኛው ብቻም አልነበረም ።  በመሆኑም ሀሳብ መግለጫው ድልድይ በታሸገ ወይም በተሰበረ ቁጥር የመብት ግፊያና ነጠቃ እየደረሰበት የሚገኘው ብዙሃኑ ጭምር ሆነ ማለት ነው ።
ለማደግ በመፍጨርጨር ላይ በምትገኝ ሀገር ውስጥ ደፋር ፣ ነቃሽ ፣ እውነት አመላካችና ባለሶስት አይን ጋዜጠኛ አስፈላጊ ነው ። ምክንያቱም ማደግ የሚቻለው የልማት አጀንዳን እያግበሰበሱ ዴሞክራሲንና ነጻነትን በማስራብ አይደለም ። ማደግ የሚቻለው በልዩ ተዓምር ሳይሆን ጥሩና መጥፎውን ፣ ሜዳና ገደሉን ለይቶ ሚዛናዊ መስመር ማስመር ሲቻል ነው ። በተቃራኒው ለምን የድርጅቴ ሀሳብ ተብጠለጠለ ? ለምን የድርጅቴ አመራር ተተቸ ? በተቌሜ ክፍተት ሳይሆን በተክለቁመናው ለምን የገነፈለ የብእር ቀለም ተደፋበት ? ወዘተ በሚሉ እፍኝ ሰበቦች ጋዜጠኛውን ማስፈራራት ፣ ማሸማቀቅ ብሎም ወደ ወህኒ ቤት መወርወር በእውነት አሳፋሪ ተግባር ነው - መሰበር ያለበት ጭምር ።
ድርጅቱ በዚህ ረገድ ያለው ስዕል የደበዘዘ ነው ። ሲፒጄ ታህሳስ 2013 ባወጣው መግለጫ ከአፍሪካ ብዙ ጋዜጠኞችን በማሰር ኤርትራ ፣ ኢትዬጽያና ግብጽን የሚያህል የለም ። መንግስት በጸረ ሽብር ተግባር አንጂ በጋዜጠኝነት ያሰርኩት ሰው የለም ቢልም ማስተባበያው ለብዙዎች የተዋጠ አልሆነም ። ይህን መረጃ እውነት ነው ብለን ብንቀበል እንኴ በተከታታይ የተፈጸሙ ሌሎች ተግባራት ጥርጣሬ ውስጥ እንድንገባ አድርገውናል ። ለምሳሌ ፍሪደም ሃውስ የተባለው ድርጅት መንግስት 65 የዜናና አስተያየት ፣ 14 የፖለቲካ ድርጅቶች እና 27 ብሎጎች መዘጋታቸውን ግልጽ ማድረጉ ይታወቃል ። መንግስት ከድርጅቶች ጋር በርዕዬተ አለም ልዩነት ብቻ ሳይሆን ወንበርዋን ለዘለዓለም በማስጠበቅ ሹኽቻ ሊኖቆር ቢችልም ከግለሰቦች ጋር ታች ወርዶ የሚፈጥረው ግርግር ግን አሳማኝ አይደለም ። በሌላ አነጋገር የግለሰቦችን ብሎግ መዝጋት የግለሰቦችን እምነት ፣ አስተሳሰብና ፍልስፍና መርገጥ ነው ። የግለሰቦችን ብሎግ መዝጋት በሃሳብ ነጻነት አጀንዳ ዙሪያ ብዙ አለማወቅን ወይም ደንታ ቢስነትን ያመላክታል ። እንደናንተ ሳይሆን እንደእኔ አስቡ ብሎ ፈላጭ ቆራጭ መንገድን ማሳየትን ያስገነዝባል ።
ጸሀፊዎች አቌማቸው ግራም ሆነ ቀኝ ፣ ሊበራልም ሆነ ዴሞክራት ወይም እምነት የለሽ መከበር አለበት ። መንግስት በተሰደበና በተተቸ ቁጥር ብዕረኛን የሚያስር ከሆነ በነጻ ሃሳብን የመግለጽ ትርጔሜ አረዳድ ላይ ችግር አለ ማለት ነው ። እንግዲህ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ከዚህም በላይ ነው የሚሉት ። ይህን ማድረግ ካልተቻለ ግን መብቱን ከህገ መንግስቱ በድፍረት ልጦ ማንሳትን ይጠይቃል ።
መንግስት በሪፖርቶቹና ለውጭ እንግዶች ፍጆታ የፕሬስ ነጻነት ከግዜ ወደ ግዜ እያደገ መምጣቱን ከመናገር ተቆጥቦ አያውቅም ። አዳማጮቹም ዲፕሎማሲያዊ ወጉን ለመከተል ያህል እንጂ ኢትዬጽያ በፕሬስ ነጻነት 137ኛ / ከ 179/ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ሳያነቡ ቀርተው አይደለም - የአለማቀፉ ፕሬስ ነጻነት ሪፖርትን ። ምን ይሄ ብቻ በሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን ተከታታይ ስኮር ካርድ ከ D በታች ውጤት ያላት መሆኑንም ያውቃሉ ። ይህ ሪፖርት የሚዘጋጀው በዴሞክራሲ ፣ ፕሬስ ነጻነትና ሰብዓዊ ልማት ውጤቶች ላይ በመንተራስ ነው ። ቀጣዬቹ አለማቀፍ ሪፖርቶች ደግሞ የከፋ ስዕል ይዘው ለመውጣት የተዘጋጁ ይመስላሉ ። ሰሞኑን ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች ባልታወቀ ምክንያት እስር ቤት ተወርውረዋልና ።
ዜጎች በታሰሩ በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት እንዳላቸው ሁሉ የተያዙበትና የተጠረጠሩበት ምክንያት ወዲያው በግልጽ ሊነገራቸው ይገባል ። ሃሳብን የመግለጽ ፣ የማስተላለፍና የማሳወቅ መብት ተገዢነቱም ለብዙሃኑ ነው ። በመሆኑም ቁጥሩ የበረከተ ብሎገርና ጋዜጠኞች ሲታሰሩ ምክንያቱ በግልጽ መነገር ይኖርበታል ። አርብን እየጠበቁ ማሰር ግዜ ለመግዛት የተለመደ ፖሊሳዊ አሰራር እየሆነ መጥቷል ። ህዝብንና ህጋዊነትን ማዕከላዊ አድርጌያለሁ የሚል መንግስት ግን ይህም አንደኛው ተጠየቃዊ መርህ መሆኑን በመቀበል መረጃውን ማስተላለፍ ግድ ይለዋል ።
ያም ሆነ ይህ የዚህ ሁሉ ጠለፋ መሰረታዊ ምክንያት ምንድነው ? እንዲህ ለማለት የምገደደው በመንግስት በኩል መረጃው ለህዝብ ይፋ ስላልሆነ ነው ። የዚህ ክፍተት ተጠያቂ ደግሞ መንግስት ነው ። የማወቅ መብታችንን አፍኗልና ። ስለዚህ ምክንያቱ ምን ይሆን ብሎ መጠየቅ ብቻ ሳይሆን ምላሹን መገመትም ስህተት አይሆንም ።
ከፊታችን ያለው ምርጫ ?
የሰማያዊ ፓርቲ ትከሻ መስፋት ?
የዘጠኝ አመቱ ቁስል ማገርሸት ? ታዲያ የዘጠኝ አመቱን ቁስል በዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ማከም ይቻላል ወይም ማጣፋት ? ምንስ ያገናኘዋል ? ይህ ይህ ጠንካራ የጸሀፊዎች ቡድን መርፌ ሲወጉ እንደነበሩ የቀድሞ ፕሬሶች አይነተኛ ሚና ይጫወታል ተብሎ ተሰግቶ ይሆን ? ይሄኛው ግምት ሚዛን የሚደፋ ይመስላል ። ምክንያቱም እስካሁን ለንባብ ባበቋቸው ስራዎች ውስጥ የድርጅቱን ደካማ ጎን በአግባቡ ነቅሰው አውጥተዋልና ። 
ወይ የሀገራችን ፖለቲካ ... የአይኑ ቀለም ያላማረውን ሁሉ ማባረር ... የጠረጠረውን ወይም ያስደነበረውን በተገኘው ስለት
 መውጋት ወይም በሂሳብ ስሌት ማጣፋት ...
 
በዘጠኝ - አንድ ፣ በዘጠኝ - አንድ እንዲሉ ።

ያሳዝናል ።

Tuesday, April 1, 2014

ግብረሶዶማዊነት በሁለቱ ታዋቂ ጻጻሳት ልቦና


የተመሳሳይ  ታ ጋብቻ ህጋዊ የሆነበትን ቀን ተንተርሶ እንግሊዝ ሰሞኑን በግብረሰዶማዊያን ሰርግ ፈንጠዚያ ላይ ነበረች ። በስነስርዓቱ ላይ የተገኙት ዴቪድ ካሜሮን ጥምረቱን « ታሪካዊ » ሲሉ አወድሰውታል ። በምድረ እንግሊዝ ይህን መሰሉ ጥምረት በ2004 የተጀመረ ቢሆንም ወደ ህጋዊ ጋብቻነት የተቀየረው አሁን ነው ።
ይህ ጋብቻ እውን የሆነው የካቶሊኩ ሊቀጻጻስ ፍራንሲስ ታዋቂ አምስት ቃላቶች « ውዳሴ » ገና ባልከሰመበት ወቅት ነው « WHO AM I TO JUDGE » ይላሉ ጆርጅ ማሪዮ በርጎሊዬ - ለመፍረድ እኔ ማነኝ ? እንደማለት ።
ከዛሬ 24 ዓመታት በፊት ናዚር ጋይድ ሩፋኤል በበኩላቸው በእንግሊዝ ተገኝተው የግብረሶዶማዊነትን ኀጢያታዊ ተግባርና የወደፊት አደገኛነት ለታዋቂ ሰዎችና ምዕመናን ትምህርት እየሰጡ ነበር « HOMOSEXUALITY IS AGAINST NATURE » በማለት - ግብረሶዶማዊነት ተፈጥሮን ይቃረናል እንደማለት ። ይህን አባባል ግን ጋዜጠኞች ታዋቂው ባለአራት ቃላቶች በማለት አላወደሱትም ። ደግነቱ ሊቀጻጻስ ሺኖዳ ዛሬ በህይወት ስለሌሉ በዚህ ዜና አያዝኑም ።
እነዚህ ሁለት ጻጻሳት በትህትናቸውና አንቱ በሚያሰኝ ስራዎቻቸው ይመሳሰላሉ ።
ጻጻስ ፍራንሲስ የአርጀንቲና ሊቀ ጻጻስ በነበሩት ግዜ የተለየ ጥቅማጥቅም አያስፈልገኝም በማለት ተራ አፓርታማ ላይ ክፍሎች ተከራይተው ምግባቸውን ራሳቸው እያበሰሉ ፣ ህዝብን መስለው በአውቶብስ እየተጋፉ ነበር የሚጔጔዙት ። የካቶሊክ ሊቀጻጻስ ሆነው ሲሾሙም ቤተመንግስት ከመግባት ይልቅ የቫቲካን ሰራተኞች በሚኖሩበት ህንጻ ላይ መኖርን መርጠዋል ። ለሳቸው ይወጣ የነበረውን የትየለሌ ገንዘብ ለሰብዓዊ ርዳታ እያዋሉ ይገኛሉ ።
ጻጻስ ሽኖዳ የግብጽን በረሃ በመምረጥ የምንኩስና ህይወትን ለብዙ አመታት አጣጥመዋል ። ከግብጽ ውጭ ገዳማትንና መንፈሳዊ ኮሌጆችን በማሰፋፋት መንፈሳዊ እውቀት እንዲጎለበትና ቁጥሩ እንዲጨምር ልዩ ሚና ተጫውተዋል ። ኢል ከራዛ የተባለ ሃይማኖታዊ መጽሄት በማዘጋጀት ብቻ ሳይሆን ከሰፊው ዕውቀታቸው በመጨለፍ 101 የሚደርሱ መጽሃፍትን ለንባብ አብቅተዋል ። ስራዎቹም በልዩ ልዩ ቌንቌዎች ተተርጉመዋል ።
እነዚህ ሁለት ጻጻሳት ከክርስትና ባህር የተቀዱ ቢሆንም ዛሬ አለምን በስፋት እያነጋገረ በሚገኘው ግብረሶዶማዊነት ዙሪያ ያላቸው አመለካከት በፍጹም አይገናኝም ።
ለምን ?
አይታወቅም ።
አንድ መሆን ይጠበቅበት ነበር ?
ቢያንስ በጣም መራራቃቸው እንዴት ? የሚል ጥያቄ እንዲወለድ ምክንያት ይሆናል ።
የአሌክሳንደሪያው ጻጻስ ሽኖዳ ግብረሶዶማዊነት ከተፈጥሮና ከመጽሀፍ ቅዱስ ቃል የሚቃረን በመሆኑ ሃጢያት መሆኑንና አባላቱ መንግስተ ሰማያት እንደማይገቡ ያስረዳሉ ። የካቶሊኩ ጻጻስ ፍራንሲስ የቤተክርስቲያኒቱን መመሪያ በመንተራስ ግብረሶዶማዊነትን በሁለት ከፍለው ነው ሀሳብ የሚሰጡት ። የግብረሶዶማዊነት ዝንባሌ ያለው እንደሃጢያተኛ አይቆጠርም ። ግብረሶዶማዊ ተግባርን የሚፈጽም ግን ሃጢያተኛ ነው ። < ዝንባሌ > የሚለው ቃል እንዴት ሊፈጠር ቻለ ? በግርድፉም ደጋፊነትንና አድናቂነትን ይገልጻል ። የድጋፉ መነሻስ ከምንም ተነስቶ ነው ማለት ይቻላል ? ምናልባት ይህ ደጋፊ ነገ ተጨዋች ለመሆን በእጅጉ የቀረበ ይመስላል ። መገመት የማይቻለው አሰላለፉን ነው - ተመላላሽ አጥቂ ነው ወይስ ቌሚ ተከላካይ ? ወይም እንደ ሚስት ነው የሚተውን እንደ ባል እንደማለት ።
ቅጣቱን በተመለከተም የጻጻሳቱ አመለካከት እንደሰሜንና ደቡብ ዋልታ ጫፎች የተራራቀ ነው ። ሺኖዳ በብሉይ ኪዳንም ሆነ በአዲስ ኪዳን የተወገዘና ክፉ ውጤት የሚያስከትል መሆኑን ያስረዳሉ ። በኦሪት ዘሌላዊያን ምዕራፍ 20 ፡ 13 « አንድ ወንድ ከሌላው ወንድ ጋር የግብረ ስጋ ግንኙነት ቢፈጽም ሁለቱም አስከፊ ነገር ስላደረጉ በሞት ይቀጡ ። ስለመሞታቸውም ኃላፊነታቸው የራሳቸው ይሆናል » የሚለውን ለአብነት ጠቅሰዋል ።
የአዲስ ኪዳኖቹ
ወደ ሮም ሰዎች 1 ፡ 27
ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6 ፡ 9
የይሁዳ መልዕክት 7 የግብረሶዶማዊነትን ቅጣትና የእግዚአብሄርን መንግስት አለመውረስ የሚያስረዱ ናቸው ።
ፍራንሲስ እነዚህን ጥቅሶች በመተው የተለየ ምላሽ መስጠትን መርጠዋል ። ታዋቂ የተባለውን who am i to judge ? በርግጥ እነዚህ ተሳቢ ቃላቶች ነገር ለማሳመር ተከርክመው ቀረቡ እንጂ ሪሞርኬው ከፊት አለ - እንዲህ ነው ያሉት « አንድ ግብረሶዶማዊ ፈጣሪን ከተቀበለና መልካም ስነምግባር ካለው እኔ ማነኝ እና ነው የምዳኘው ? » አንዳንዶች ይህን አባባል የተጠቀሙት ትህትናን ለማሳየት ነው ሲሉ ሌሎች ደግሞ ህገ መጽሀፉን ለመሸሽ ነው ብለዋቸዋል ።
እዚህ ጋ ፍጥነታችንን አቀዝቅዘን ከሀሳቦቹ  ጀርባ ሊሆን ስለሚችለው ጉዳይ የሆነ ነገር እንበል ። ሽኖዳ መጽሀፍ ቅዱስን ቃል በቃል ጠቅሰው ሞት ይገባል ነው ያሉት ። ኃላፊነቱም የሟቹ ነው ። ህግ ከውሃ የቀጠነ መሆኑ ቢታወቅም እንደዚህ አይነት ውሳኔዎች ወዳልተፈለገና የከፋ ጫፍ እንደሚያደርሱም ይታወቃል ። ምክንያቱም ስሜታዊነትን አቅፈዋልና ። ለአብነት ያህል ኡጋንዳ የጸረ ግብረሶዶማዊነት ህግን ባጸደቀች ማግስት በተነሳ አመጽ አንድ ግብረሶዶማዊ ተቃጥሎ እንዲሞት ተደርጔል ። መቼም የሶዶምና ገሞራ ሰዎችም በዚህ መልኩ ነው የተፈጁት ብለን የምንከራከር ከሆነ የጻጻስ ፍራንሲስ አምስት ቃላቶች ትክክል ናቸው ማለት ነው ። እኛ ማነንና ነው ህግን የተላለፈ ሰው በጣም በተጋነነና ለቀሪው ትምህርት ሳይሆን በሽታ ሊፈጥር በሚችል መልኩ በእሳት የምናቃጥለው ? ህግ በቀለኛ መሆኑ ይታወቃል ። የበቀሉን ጉማሬ ከኃላ ኪሱ የሚያወጣው ግን መጀመሪያ ገስጾና አስተምሮ ነው ። ሰው ሲሞት እንኴን አስከሬኑን የማቃጠል ባህል መቅረት አለበት በሚባልበት ዘመን ህይወት ያለውን ሰው እንደዳመራ በመለኮስ ሰብሰብ ብሎ ወደ ሰሜን ይወድቃል ወይስ ወደ ምዕራብ እያሉ መወራረድ እንዴት ያስደስታል ? ያሰቅቃል እንጂ ።

በሌላ በኩል ጻጻስ ፍራንሲስ እንደቀድሞው ጻጻስ ተጽዕኖው በዝቶባቸዋል አሊያም የሳይንሱን እውነታ እየሸራረፉም ቢሆን መቀበል ጀምረዋል ። እንደሚታወቀው ግብረሶዶማዊነት የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን ሆኖ የመፈጠር ነው የሚሉ አንዳንድ ሳይንቲስቶች ጣጣውን የጄኔቲክና ሆርሞን ውጤት አድርገውታል ። ለዚህም ማሳያ ይሆን ዘንድ በክሮሞዞምስ ፣ አእምሮና ሆርሞኖች ላይ ጥናቶች አከናውነዋል ። ለአብነት ያህል 400 የሚደርሱ መንታ ልጆች ላይ የተደረገ ጥናት Xq28 የተባለውን ክሮሞዞም እንደሚጋሩት ያሳያል ። ይህን ክሮሞዞምስ ጥንድ ያልሆኑ ወንድሞች አይጋሩትም ወይም በጥቂቱ ነው የታየው ። በዚህም መሰረት አንዱ ልጅ ግብረሶዶማዊ ከሆነ ሌላኛው ጥንድ የመሆን እድሉ 50 ከመቶ ይደርሳል ። እነዚህና የመሳሰሉት ጥናቶች እውነት ይኖራቸው እንዴ የሚያሰኝ ጥያቄ እየፈጠረባቸው ይመስላል ።
ዛሬ አለምን ጉድ እያሰኘ የሚገኘው ግብረሶዶማዊነት ሳይሆን የግብረሶዶማዊያን የጋብቻ ጥያቄ ነው ። ምክንያቱም ጋብቻ የተባለውን አንጋፋና ህጋዊ ተቌም እየተጋፋ በመሆኑ ። አለም ተቀብሎት የኖረው የጋብቻ ብይን እድሜያቸው ለአቅመ አዳም / ሄዋን በደረሰና በፍቅር በተግባቡ አንድ ወንድና ሴት መካከል የሚደረገው ማህበራዊ ጥምረት ነው ። እነዚህ ጥምሮች ውለዱ ክበዱ የሚለውን የሰርግ ላይ ምርቃት ከአመት በኃላ ተግባራዊ ያደርጋሉ ። ፍሬና ፍቅር ማየት የሰው ልጆች ሁሉ ጸጋ ነውና ።
ዛሬ አንድ ተማሪ « ጋብቻ የሁለት ጺማም ሰዎች ቁርኝት ነው ፣ በፍቅር ለመደንገጥና ለመሳሳብም አጔጊ ዳሌ ፣ እንቡጥ ከንፈር ፣ የተቀሰሩ ጡቶች ፣ ገዳይ አይን ፣ አመለሸጋነትም ሆነ የጎን አካልነት ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም ። በግብረስጋ ለመርካት የግድ ወርቃማ ምንተሃፍረቶች አያስፈልጉንም - ማንኛውም ቀዳዳ እንጂ » የሚል መመረቂያ ጽሁፍ ቢሰራ ማነው ትክክል አይደለም የሚለው ? ጋብቻ በትርጉም ብቻ ሳይሆን ቀጥሎ በሚመጣው ቤተሰባዊ ተቌምነቱም እየተኮማተረ ነው ። ህንጻው ውስጥ ከወጉ ፣ ከእምነትና ስርዓቱ ፣ ከባህሉና ከአኗኗር ዘይቤው ጋር የማይመሳሰል ምናልባትም የሚቃረን ደባል ሰተት ብሎ ገብቷል ። ትግሉ ከቀዝቃዛው ጦርነት በላይ የጦዘውም ለዚህ ነው ።
ውጣልኝ !  - አልወጣም !
በህግ አምላክ  ?! - በህግማ ነው የመጣሁት !
እረ የሀገር ያለህ ? የመንግስት ያለህ ? - ነባሩ ትዳር በስቃይ ተተብትቦ ነጋ ጠባ ሊጮህ ነው ። ቆይቶ የሚያገኘው ፖለቲካዊ ምላሽ « ተቻችላችሁ ኑሩ  - ተከባበሩ » የሚል መሆኑ አያጠራጥርም ።
እዚህ ላይ ጻጻስ ፍራንሲስ ጋብቻን በተመለከተ አስገራሚ ለውጥ ማድረጋቸውን ማስታወስ ያስፈልጋል ። የአርጀንቲና ጻጻስ በነበሩበት ግዜ « ይህ የፈጣሪን እቅድ የማጥፋት ዘመቻ ነው » በማለት ነው ተቃውሟቸውን በግልጽ አሰምተዋል ። የካቶሊክ ሊቀ ጻጻስ ሆነው ከኢጣሊያኑ ኮሬ ዴላ ሴራ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ « ጋብቻ በአንድ ወንድና ሴት የተወሰነ ነው ፣ ነገር ግን ቤተክርስቲያናችን የተመሳሳይ ጾታን ጥምረት በተለይም ከህክምና አገልግሎትና ከንብረት ባለቤትነት አንጻር መደገፍ አለባት » በማለት ልዩ ጉዳዮች በልዩነት የሚመዘኑበት ሁኔታ መኖሩን ተናግረዋል ።
ሺኖዳ ፍቅር መንፈሳዊና ንጽህ ከመሆኑ አንጻር በሁለት ተመሳሳይ ጾታ መካከል የሚደረግ ጥምረትን የሚበይኑት ዝሙት በማለት ነው < ግብረሰዶማዊነት ተፈጥሯዊ እኮ ነው ? > የሚል ጥያቄም ቀርቦላቸው ነበር ። አንድ ሰው በዚያ መልኩ ከተፈጠረ መጸለይ ፣ መፈወስ በህክናም ማስተካከል ይቻላል ባይ ናቸው ። ይሁን እንጂ ቤተክርስቲያን ሰዎች በዚህ መልክ ይፈጠራሉ ብላ እንደማታምን ይልቁንም ዝሙት መሆኑን በምሳሌ ማስረዳት መርጠዋል ። ቅዱስ አውግስቶ እና ቅዱስ ፓለጊያ ዝሙት ፈጻሚዎች ነበሩ ። ኃላ ቅዱስ እስከመባል የደረሱት በመጥፎ ተግባራቸው ተጸጸተው ራሳቸውን በማስተካከላቸው ነው ።
የግብረሶዶማዊያን ነገር « ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡ ? ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡ ? » አይነት ደረጃ የደረሰ ይመስላል ። ምክንያቱም የተቀጣጠለውን እሳት በማጥፋት ረገድ የእሳት አደጋ ተከላካይ ባልደረባ በመሆን ትልቅ ሚና ይጫወታሉ ተብለው የሚገመቱት ቄሶች ራሳቸው የእሳት ራት በመሆናቸው ።
ልክ እንደ ሺኖዳ ሁሉ የቀድሞው ጻጻስ ቤንዲክት XVI የግብረሶዶማዊነት ጥልቅ ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች ቄሶች ሊሆኑ አይችሉም ብለው ፈርመው ነበር ። ጻጻስ ፍራንሴስ ግን ግብረሶዶማዊያን ቄሶች ይቅርታ ያገኛሉ የሚል አስተያየት ሰጥተዋል ። ጻጻሱ እንዲህ የተናገሩት ተቸግረው ይመስላል ። ምክንያቱም በሮማን ካቶሊክ የግብረሶዶማዊያን ቄሶችን ቁጥር በትክክል ማወቅ አስቸጋሪ ቢሆንም በርካታ መሆናቸው ብዙዎችን ያስማማልና ። ሌላው ቀርቶ በአሜሪካ ከ1970 እስከ 80ዎቹ በነበሩት ግዜያት በሎስ አንጀለስ ታይምስ በተደረገ ጥናት 1854 ቄሶች ራሳቸውን ግልጽ አድርገዋል ። ይህም በአሜሪካ ብቻ 33 ከመቶ የሚደርሱ ቄሶች ግብረሶዶማዊያን መሆናቸውን ያመለክታል ። ይህን አሃዝ 1 ነጥብ 2 ቢሊየን ተከታዮችን በምትመራው ካቶሊክ መካከል መመዘን የአደጋውን ስፋት በግልጽ ሊያመላክት ይችላል ።
በርግጥ የሁለቱ ጻጻሳት የተለያየ ምስጢር ምንድነው ?
አንዱ ለዘብተኛ ሌላው አክራሪ ስለሆነ ?
አንዱ የምዕራቡ ዓለም የስልጣኔ ውጤት ሌላው የአፍሪካ ኃላቀር ባንዲራ አራጋቢ ስለሆነ ?
አንዱ የተጽዕኖ ውጤት ሌላኛው በራሱ የቆመ ስለሆነ ?
ከእነሱ እምነትና አስተሳሰብ በመነሳት የነገዋን አፍሪካ መገመት ይቻላል ?
አይታወቅም ።